የኢህአዴግ መንግስት ገና ስልጣን ሲይዝ ጀምሮ ግንቦት 20 መከበር የለበትም ብዬ ስሞግት ነበር – አንዳርጋቸው ፅጌ

«የግንቦት 20 በዓል ከመንግስት ለውጥ ባሻገር በህዝብ ላይ የሚፈፀመውን ግፍና ጭቆና አላስቀረም”አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ
(ኢፕድ) – የግንቦት 20 የድል በዓል የደርግ ስርዓትን ከማስወገድ ባለፈ መንግስት በህዝብ ላይ የሚፈፀመውን ግፍና ጭቆና አለማስቀረቱን አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ አስታወቁ፡፡ በዓሉ በአደባባይ የምንደሰኩርበት ሳይሆን አንገታችንን ሊያስደፋን የሚገባ እንደሆነ አመለከቱ ።
አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ በተለይ ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንዳስታወቁት፤ ባለፉት 27 ዓመታት የደርግ ስርዓት መውደቅን ምክንያት በማድረግ ሲከበር የኖረው የግንቦት 20 በዓል ከመንግስት ለውጥ ባሻገር በህዝብ ላይ የሚፈፀመውን ግፍና ጭቆና አላስረቀም፡፡ በደርግ ስርዓት በጥይት ከሚገደለው በላይ ህዝብ በከፋ ድህነትና እርስበርስ እንዲጋጭ በማድረግ የሞተው ይልቃል፡፡
«እኔ የኢህአዴግ መንግስት ገና ስልጣን ሲይዝ ጀምሮ ይህ በዓል መከበር የለበትም ብዬ ስሞግት ነበር» ያሉት አቶ አንዳርጋቸው፤ በወቅቱም ሆነ እስካሁን ድረስ ካለፈው ስርዓት በተሻለ አገርን መለወጥም ሆነ ህዝብን ተጠቃሚ ማድረግ አለመቻሉን አስረድተዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት የኢህአዴግ መንግስት ከየትኛውም የአገሪቱ መንግስታት በላቀ ደረጃ የሰብአዊ መብጥ ጥሰት ሲፈጽም የቆየ ከመሆኑም ባሻገር በከፍተኛ ደረጃ የአገርና ህዝብን ሃብት በመመዝበር እድገቱ ቁልቁል እንዲጓዝ አድርጓል ሲሉ ወቅሰዋል፡፡
ባለፉት ዓመታት በአገሪቱ ተከናወነ የሚባለውም ልማት የኢህአዴግ መንግስት ስልጣን ላይ ከቆየበት ጊዜ አኳያ እዚህ ግባ የሚባል እንዳልሆነ አመልክተው ፤ ይልቁንም በከፍተኛ ደረጃ አገርና ህዝብ የተዘረፈበት፤ ህዝቡ እርስበርሱ እንዲጋጭ የተደረገበት፤ በስደት ያለው አገር ወዳዱ ህብረተሰብ በአገሩ ልማት የተገለለበት በመሆን ጥቁር ነጥብ የጣለ በዓል ነው ብለዋል ፡፡ ባለፉት አመታት መስራት ከሚቻለው በታች የተሰራ እንጂ ሊጠቀስ የሚችል እድገት ያየንበትም እንዳልሆነም ጠቁመዋል ፡፡
አንዳንድ የስርዓቱ አቀንቃኞች በከተሞች ላይ የተሰሩ ጥቂት ፎቆችን በማሳየት ልማት እንደመጣ አድርገው የሚያቀርቡበትን ሁኔታ ፈጽመው እንደማይቀበሉት የገለፁት አቶ አንዳርጋቸው፤ በተለይም በአዲስ አበባ ከተማ ለዘመናት የነበሩ የምስኪኑ ማህበረሰብ ደሳሳ ጎጆዎች ዛሬም በከፋ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኙ ጠቅሰዋል፡፡ እያንዳንዱ ዜጋ የንፁህ መጠጥ ውሃና የህክምና አገልግሎት የማያገኝበት እውነታ ከፊት ተቀምጦ እያለ ስለግንቦት 20 ድል ማውራት ከዲስኩርነት ባለፈ ለህዝብም ሆነ ለአገር የሚፈይደው ነገር አለመኖሩን አስረድተዋል፡፡