በዚህ ዓመት ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው ጠቅላላ ምርጫ ከሌሎች አገሮች ጣልቃ ገብነት የፀዳ እንዲሆን ጥንቃቄ መደረግ እንዳለበት የቻይና አምባሳደር አሳሰቡ፡፡

በዚህ ዓመት ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው ቀጣዩ ጠቅላላ ምርጫ ከሌሎች አገሮች ጣልቃ ገብነት የፀዳ እንዲሆን ጥንቃቄ መደረግ እንዳለበት፣ በኢትዮጵያ የቻይና አምባሳደር ታን ጂያን አሳሰቡ፡፡

አምባሳደሩ በኢትዮጵያ በኩል የተለየ ለውጭ ጣልቃ ገብነት የሚዳርግ ሥጋት ባይኖርም፣ ያደጉ አገሮች በአንድ አገር የውስጥ ፖለቲካ መግቢያ ምክንያታቸው ብዙ ስለሆነ ነቅቶ መጠበቁ የተሻለ ነው ብለዋል፡፡

ጣልቃ ገብነቱ በአብዛኞቹ ታዳጊ አገሮች ላይ የሚሞከርና የተለመደ መሆኑን የገለጹት አምባሳደር ታን፣ ያደጉት አገሮች የሰብዓዊ መብት ጥበቃን ሰበብ አድርገው የራሳቸውን አጀንዳ እንዲያራምዱ ታዳጊ አገሮች መፍቀድ የለባቸውም ብለዋል፡፡

የሰብዓዊ መብት ጥበቃ ጉዳዮችን ሰበብ አድርገው በታዳጊ አገሮች የውስጥ ጉዳይ እጃቸውን የሚያስገቡ አገሮች የሚመፃደቁትን ያህል የሰብዓዊነት መብት ጥበቃ ታሪክ የላቸውም ብለዋል፡፡ በታሪክ የማይዘነጉ አሰቃቂ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ያደርሱ የነበሩ ናቸው ሲሉም አክለዋል፡፡

እንደ ኢትዮጵያና ቻይና ያሉ ታዳጊ አገሮች የራሳቸው የሰብዓዊ መብት አረዳድ ያላቸው፣ ጽንሰ ሐሳቡን ለመረዳት የሌሎችን መሪነት የማይሹ ሉዓላዊ አገሮች እንደሆኑ የተናገሩት፣ የሁለቱን አገሮች ትብብርና ቻይና በመጪው ዓመት በኢትዮጵያ ልትሠራ ያቀደቻቸውን ፕሮግራሞች በተመለከተ፣ ዓርብ ታኅሳስ 17 ቀን 2012 በቻይና ኤምባሲ ጋዜጣዊ መግለጫ በሰጡበት ወቅት ነው፡፡

የሁለቱ አገሮች ትብብር በተለይም በኢኮኖሚው ዘርፍ ጠንክሮ እንደሚቀጥል፣ በኢትዮጵያ ኢንቨስት በማድረግም ረገድ የቻይና ኢንቨስተሮች ቀዳሚ መሆናቸውን፣ ባለፉት አሥር ወራት ብቻ 147 የቻይና የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች ኢትዮጵያ መቀበሏን ገልጸዋል፡፡

በውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት የቻይና ኢንቨስተሮች ተሳትፎም በየዓመቱ በ12.2 በመቶ እያደገ መምጣቱ ተናግረዋል፡፡ በዚህ ዓመት ኢትዮጵያ ከተቀበለቻቸው የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ፕሮጀክቶች መካከል 60 በመቶ ከቻይና መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡ የቻይና – አፍሪካ ቀርከሃ ማዕከል በኢትዮጵያ ለመክፈት እንቅስቃሴ እንደሚጀመር፣ ቴክኒሺያኖች የሚሠለጥኑበት ወርክሾፕ ለማቋቋምም ዕቅድ መያዙን ገልጸዋል፡፡

ከቀናት በፊት ወደ ህዋ ለመጠቀችው ሳተላይት የቻይና መንግሥት ድጋፍ ወሳኝ እንደነበር ያስታወሱት አምባሳደር ታን፣ ግዙፉ የኢኮሜርስ ኩባንያ አሊባባ በኢትዮጵያ ሥራ ለመጀመር መስማማቱን ትልቅ ስኬት ነው ብለዋል፡፡ በቻይና መንግሥት ድጋፍ እየተከናወነ የሚገኘው የአዲስ አበባ የወንዝ ዳርቻ ልማት ፕሮጀክት በዚህ ዓመት ግንቦት ወር ላይ የሚጠናቀቅ ሲሆን፣ የመለስ ዜናዊ አመራር አካዳሚ ግንባታም በመጪው ዓመት ጥቅምት ወር እንደሚጠናቀቅ ተናግረዋል፡፡

እ.ኤ.አ. በ2019 ብቻ 1,590 ኢትዮጵያውያን ለተለያዩ ሥልጠናዎች ወደ ቻይና መሄዳቸውን በማስታወስ፣ የሁለቱ አገሮች ትብብር ጠንካራ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

ቻይና ለኢትዮጵያ ብድር ከሰጡ አገሮችና የገንዘብ ምንጮች መካከል አንዷ ስትሆን፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) በቻይና ባለፈው ዓመት ጉብኝት ሲያደርጉ ኢትዮጵያ ብድር የመክፈያዋ ጊዜ እንዲራዘምላት የቻይናን መንግሥት ይሁንታ ማግኘታቸው አይዘነጋም፡፡