የውስኪ ቤት ወሬ:- ጌታቸው ረዳ እና የሲዳማው እስረኛ – ስዩም ተሾመ

ህወሓቶችን በቀዳዳ አጮልቀን ማየታችንን ቀጥለናል። ከወትሮው በተለየ መልኩ የህወሓቶች ቅጥር ግቢ በጣም ተረብሿል። ከሁሉም በላይ ደግሞ አንድ የቤተሰቡ አባል ክፉኛ ተሸብሯል። ዝም ብሎ ይቆዝምና በድንገት ብስጭት ያላል። እንደ እብድ ብቻውን ማውራት ጀምሯል። ዝም ብሎ ይቆዝማል። በቆዘመበት ለብቻው ያጉተመትማል። ከዚያ በድንገት እጁን ካወራጨ በኋላ በአቅራቢያው እብደቱን የሚታዘብ ሰው አለመኖሩን ለማረጋገጥ ዙሪያ ገባውን ይቃኛል። ከዚያ ተመልሶ መቆዘም ይጀምራል። ለዚህ የዳረጉትን ሰዎች በስም እየጠራ ይሳደባል። ወዲያው ደግሞ ሃፍረት ይሰማዋል። መሃል አደባባይ ላይ እርቃኑን የቆመ ይመሰልል፤ በአንድ እጁ ሃፍረተ-ስጋውን በሌላኛው ደግሞ ዓይኑን ለመሸፈን ይጥራል። በዙሪያው ቆመው ከሚሳለቁ ሰዎች ሃፍረተ-ስጋውን ለመሸፈን የሚያደርገው ጥረት ሰማይን በነጠላ እንደ መሸፈን ይሆንበታል።

ሰውዬው ሁለት ዓይኑን በእጁ ሲሸፍን ማየት የማይፈልገው ነገር ቀድሞ የባሰ እየጨመረና እየሰፋ፣ ይበልጥ እየጎላና እየገዘፈ ይመጣል። ዓይኖቹን ሰሸፍን ከሚሸሸው ስሜት ጋር ፊት ለፊት ይጋፈጣል። ለካስ የፊት ዓይን ሲጨፈን የኋላ ዓይን ይከፈታል። የኋላ ዓይን በውስጣችን ያለውን ጥሩና መጥፎ ስሜት የምናይበት ዓይነ-ህሊና ነው። ስለዚህ ሰውዬው የፊት ዓይኑን ሲጨፍን ቅሌትና ውርደቱን በዓይነ-ህሊናው ማየት ይጀምራል። ከምንግዜውም በላይ የፀፀትና ሽንፈት ስሜት አጥንቱ ድረስ ዘልቆ ይሰማዋል። እንደ ቁርጥማት የሚያደርገውን ያሳጣዋል፤ እንደ ጎን ውጋት ቀስፎ ይይዘዋል። ከዚያ የቀኝ እጁን አይበሉባ በኃይል በማወናጨፍ ሰቅዞ የያዘውን ውጋትና ቁርጥማት ለማስወገድ ይሞክራል። ከዚያ የሚታዘበው ሰው መኖር አለመኖሩን ለማረጋገጥ ዙሪያ ገባውን ይቃኛል። ወዲያው ደግሞ ተመልሶ መቆዘም ይጀምራል። ለብቻው ያልጎመጉማል። ይሄ ሁሉ ሲሆን እኛ አጮልቀን እያየን ነው። አጮልቀን ካየነው በመጠኑ ጨለፍን እንሆ እንላለን።

አቶ ጌታቸው ረዳ ኢሜይሉ ከተጠለፈ በኋላ በሃፍረትና ውርደት ስሜት ውስጥ ተዘፍቋል። ከዚህ ዱካክ ለመውጣት ዘወትር ይቆዝማል፣ ብቻውን ያጉረመርማል፣ ስም እየጠራ ይሳደባል፣ በራሱ ጥፋት ሌሎችን ይራገማል፣ ራሱን ያመናጭቃል… ጌታቸው ረዳ ተጨንቋል። ሃፍረትና ፀፀት ከፀጉሩ እስከ ጥፍሩ ወርሮታል። ከእንዲህ ያለ ሲቃ ለመውጣት በጠዋት መጠጥ ይጀምራል። ዙሪያውን በሰዎች ይከብባል። በጨዋታና ሳቅ መሃል ሃፍረቱን ለመርሳት ይሞክራል። ሆኖም ግን በዙሪያው ካሉት አንዱ “ጌቾ! እንዴት ግን አንተ የቫይበር ሚሴጅን ማጥፋት ትረሳለህ? ለወደፊቱም ቢሆን እንዲህ ያሉ ሴንሴቲቭ ሚሴጆችን ማጥፋት መልመድ አለብህ!” በማለት ምክር አዘል ተግሳፅ ይለግሰዋል። ጌታቸው በውስጡ “ወይ መሬት ያለ ሰው” ብሎ ዝም ይላል። የፈት ገፅታው ላይ የነበረው ሳቅና ፈገግታ እንደ ጉም እየበነነ ሲሄድ የሚሸሸው የሃፍረትና ውርደት ስሜት በውስጡ መትነን ይጀምራል።

ጌታቸው የሚሸሸው ነገር ከኋላ እየተከተለ ያሳድደዋል። ሳቅና ፈገግታው ጠፍቶ ዳግም ቁዘማ ይጀምራል፣ ድምፁ ሳይሰማ ያጉረመርማል። ዓይኖቹን መጨፈን ይፈልጋል፣ ነገር ግን ጓደኞቹ ዙሪያውን ከብበው ዓይን ዓይኑን ያዩታል። አዛኝ-ቅቤ አንጋች ሁላ! አዳሜ የራሱን ቅሌትና ውርደት ተሸክሞ አጉል መካሪ መሆን ይቃጣዋል። ሁሉም አዛኝ-አስተሳዛኝ መስሎ ዓይን -ዓይኑን ያዩታል። የሚያፅናኑት መስለው ሽንፈቱን ለማየት ቋምጠዋል። ይህን ሲያስብ ጌታቸው ብልጭ ይልበታል። በድንገቴ ቁጣና እልህ ውስጡ ይቃጠላል። ደፋር፥ ዥግና መምሰል አለበት፤ ጠላት፥ እሱን የሚበልጠው ጠላት መፍጠር አለበት። በእሱ ላይ የደረሰው በእነሱም ላይ እንደሚደርስ ማሳየት አለበት። ነገሩን ከግላዊ ቅሌት ወደ ፖለቲካዊ ስሌት መቀየር ይኖርበታል። ስለዚህ ጮክ ብሎ “አብይ ነው!” ይላል። “እሱ ነው ራሺያ ሆኖ ኢሜይሌን ሃክ ያስደረገው! ለስዩም የሰጠው እሱ ነው! ይሄ ደደብ ደግሞ ፌስቡክ ላይ አውጥቶ ለጠፈው! ደደብ! ደደብ ነው!” እያለ ጮክ ብሎ መሳደብና መወራጨት ይጀምራል። ጩኸትና መወራጨቱ የሚጠጣውን ውስኪ እንደ እንፋሎት እያተነነ ወደ ጭንቅላቱ ይልከዋል። በቁጣና ብስጭት ገና ሞቅ ሳይለው ይሰክራል። በስካሩ ልክ ድምፁ ጣሪያ ሰብሮ መውጣት ይጀምራል።

መሃል አቶ ጌታቸው ስልክ ይደወልለታል። ከደወለው ሰውዬ ጋር የረጅም ግዜ ትውውቅ ያላቸው ይመስላል። ከንግግራቸው መረዳት እንደሚቻለው ደዋዩ ለረጅም ግዜ ችግር ውስጥ ያለ ይመስላል። ችግሩ ሰሞኑን አቶ ጌታቸው ከእሱ የባሰ ውጥንቅጥ ውስጥ ያለ መሆኑ ነው። የራሱ ችግር አስጨንቆታል። ከዘቢብ ሸኩር ጋር ያደረገው ጨዋታ አደባባይ ወጥቷል። የለየለት አውደልዳይ ሴሰኛ መሆኑ ታውቆበታል። ያኔ አጠራሯ ስሜቱን ሽቅብ ያንረው የነበረ አጠራር ዛሬ በየቡና ቤቱ መጠሪያ ስሙ ሆኗል። እንደ ቀልድ የፃፋቸው የብልግና ቃላት እሱ የፈጠራቸው ይመስል ከስሙ እኩል መጠሪያው ሆነዋል። ስለዚህ አቶ ጌታቸው ረዳ በራሱ ችግር ተወጥሯል። በአንድ ተራ ጦማሪ አማካኝነት ስምና ዝናው አፈር በልቷል። በዚህ ምክንያት የሚደርስበትን ሃፍረትና ፀፀት መሸከም ተስኖታል፣ ደዋዩ ደግሞ እስር ቤት ውስጥ ስላለው ችግር ያወራል።

በእርግጥ ደዋዩ ሰውዬው በወንጀል ተጠርጥሮ የታሰረ ነው። የደወለውም ከእስር ቤቱ ጥበቃዎች ስልክ በመዋስ ነው። ይሁን እንጂ ጌታቸው ለእስረኛው ከተስፋ በስተቀር ሊያደርግለት የሚችለው ነገር የለም። ምክንያቱም እንኳን ለሌላ ለራሱም አቅም አንሶታል። በሌላ በኩል ደዋዩ ያለው መቀሌ ወይም አላማጣ አይደለም። ትግራይ ቀርቶ አፋር አሳይታ፣ ወሎ አሊያም ወሊሶ አይደለም። ታሳሪው ያለው በሐዋሳ ከተማ እስር ቤት ነው። ብዙዎቻችሁ ደዋዩ ሐዋሳ አከባቢ በተፈፀመ ወንጀል ተጠርጥሮ የታሰረ የትግራይ ተወላጅ ሊመስላችሁ ይችላል። ነገር ግን አይደለም። ለአቶ ጌታቸው ረዳ ስልክ ደውሎ የሚያናግረው ሰዉዬ የሲዳማ ብሔር ተወላጅ ነው። የታሰረውም በሌላ ምክንያት ሳይሆን ባለፈው አመት ሐምሌ ወር ላይ ከሲዳማ ዞን የክልልነት ጥያቄ ጋር ተያይዞ በዞኑ ሁከትና ብጥብጥ እንዲነሳ በማድረግና በዜጎች ሕይወትና ንብረት ላይ ጉዳት አድርሰዋል በሚል ወንጀል ተጠርጥረው ከታሰሩት ውስጥ አንዱ ነው።

አቶ ጌታቸው የሚጠጣው ውስኪ በውስጡ ከነበረው ቅሌትና ብስጭት ጋር ተቀላቅሎ በስካር ናላውን አዙሮታል። በዚህ ምክንያት ከሐዋሳው እስረኛ ጋር የሚያደርገው የስልክ ውይይት ካሉበት ቤት አልፎ ለአልፎ ሂያጅ መንገደኛ ጭምር ይሰማል። ሾካካው ውስጥ አዋቂ ደግሞ ከአንድ ጥግ ላይ ተቀምጦ በሞባይሉ ፌስቡክ የሚጠቀም ይመስላል። ሆኖም ግን ጆሮዎቹ እና ሙሉ ቀልቡ ያለው አቶ ጌታቸው ጋር ነው። በእርግጥ ፊት ለፊቱ እየሆነ ያለው ነገር ለማመን የሚከብድ ነው። የህወሓት/ኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ አባል የሆነ ግለሰብ በሲዳማ ዞን ሁከትና ብጥብጥ በማስነሳት በሰዎች ሕይወትና ንብረት ላይ ጉዳት አድርሷል ተብሎ የተጠረጠረን ግለሰብ በስልክ ያናግራል። የእስር ቤቱ ጠባቂዎች ለተጠርጣሪ እስረኞች የሞባል ስልክ መስጠታቸው ራሱን ያቻለ አንድ ነገር ነው። እስረኛው ስልኩን የደወለው ሐዋሳ ወይም ይርጋለም የሚገኙ ዘመዶቹ ጋር ቢሆን እሱም አንድ ነገር ነው።

መታሰር ይጨንቃል፣ ነፃነትን ይገድባል። ስለዚህ የታሰረ ሰው ብዙ ነገር ሊያስብ፣ ያልተጠበቀ ነገር ሊያደርግ ይችላል። ለምሳሌ እስረኛው በፌደራል መንግስት ውስጥ ላለ ባለስልጣን ዘመዱ ወይም ወዳጁ ደውሎ የፍርድ ሂደቱን እንዲያፋጥንለት፣ ቅጣቱን እንዲያቀልለት፣ ጥፋት እንደሌለበት ወይም ከእስር ቤት ስለሚወጣበት ሁኔታ ሊያነጋግር ይችላል። “የጨነቀው እርጉዝ ያገባል” እንደሚባለው አንድ ታሳሪ ለወዳጅ ዘመዶቹ ወይም ለሚያቃቸው ባለስልጣናት ስልክ ደውሎ ብዙ ነገር ሊል ይችላል። ነገር ግን የብሔር ግጭትና ሁከት በማስነሳት ወንጀል ተጠርጥሮ ሐዋሳ ላይ የታሰረ ግለሰብ ክልልና ከተማ አቆራርጦ መቀሌ ሲደውል “ጠርጥር! ከገንፎ ውስጥም አይጠፋም ስንጥር!” ያስብላል። “የሲዳማ ዞን የክልልነት ጥያቄ በአስቸኳይ መፍትሄ ሊሰጠው ይገባል” ህወሓት በአፈቀላጤው ጌታቸው ረዳ በኩል ሐዋሳ እስር ቤት ከሚገኝ የኢጄቶ መሪ አሊያም አስተባባሪ ጋር በተደጋጋሚ በስልክ እየተገናኘ የሚወያይ ከሆነ በሐዋሳና ሲዳማ ዞን በሚኖሩ የሌላ ብሔር ተወላጆች ላይ ሌላ አስከፊ ዕልቂትና መከራ እየተደገሰ እንደሆነ መገመት ይቻላል። በተለይ ደግሞ በቅርቡ በሲዳማ ዞን የክልልነት ጥያቄ ላይ ህዝበ ውሳኔ እንደሚካሄድ ሲታሰብ ህወሓት በሲዳማ ዞን ፈንጂ እየቀበረ እንደሆነ መገንዘብ ይቻላል።

አቶ ጌታቸው የሲዳማ ተወላጅ ከሆነ ተጠርጣሪ እስረኛ ጋር አውሮቶ አንደጨረሰ በዙሪያው ካሉት ሰዎች ጋር ጮክ ብሎ ማውራቱን ቀጠለ። በጨዋታ መሃል አንዱ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝን ስም አነሳ። ይህን ግዜ አቶ ጌታቸው ረዳ ስሜቱ ቅይርይር አለ። እንኳን ለቤቱ ለአልፎ ሂያጅ በሚሰማ ድምፅ አቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝን እጅግ ፀያፍ የሆነ ዘረኛ ስድብ መሳደብ ጀመረ። ጥግ ላይ የተቀመጠው ሾካካ ሰውዬ ቀስ ብሎ በዓይኑ ቂጥ የአቶ ጌታቸው ረዳን የፊት ገፅታ ተመለከተ። ለቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ያለው ጥላቻና ንቀት ከመጠን ያለፈ እንደሆነ ተገነዘበ። ለዚህ ደግሞ ምክንያቱ አቶ ኃይለማሪያም ከመንግስት ኮሚኒኬሽን ፅ/ቤት ሃላፊነት አሽቀንጥሮ ስላወረደው ሊሆን እንደሚችል ገመተ። ይሆን እንጂ ለአቶ ኃይለማሪያም ደሳለኝ ከልክ ያለፈ ጥላቻና ንቀት ያለው ሰው በወላይታ የአዲስ አመት ክብረ በዓል ላይ በክብር እንግድነት በተገኘበት ወቅት ደማቅ አቀባበል የተደረገለት መሆኑ ነው። በእርግጥ እንደ እነ አስራት አሳለ ያሉ የስልጣን ጥማት ያለባቸው ሰዎች በአቶ ጌታቸው ረዳ መገኘት ደስ ሊሰኙ ይችላሉ። የወላይታ ህዝብ ግን ለእነ ጌታቸው ከመጠቀሚያነት የዘለለ ፋይዳ የለውም። ከአቶ መለስ ዜናዊ እስከ ጌታቸው ረዳ ድረስ ለወላይታ ህዝብ ያላቸው ንቀት ለከት የለውም። ስለ አንድ ህዝብ ያለህ አቋምና አመለካከት የሚገለፀው ለአዲስ አመት ክብረ በዓል ላይ በምታደርገው በአስመሳይ ቃላት የታጨቀ ንግግር ሳይሆን እንዲህ እንደ ጌታቸው ረዳ ውስኪ ቤት ውስጥ በምትዘላብዳቸው ጥቂት ቃላት ነው!!!