አማራን ከጥቃት ለማዳን መደራጀት ብቻ መፍትሔ መሆኑን ምሁራን እና ፖለቲከኞች አመለከቱ።

አማራን ከጥቃት ለማዳን መደራጀት ብቻ መፍትሔ መሆኑን ምሁራን እና ፖለቲከኞች አመለከቱ። የአማራ ወጣቶች ህብረት ዛሬ በባሀርዳር ክልላዊ ውይይት አካሂዷል፡፡

የአማራ ወጣቶች ህብረት የጠራው ህዝባዊ ውይይት በባህር ዳር ተካሂዷል። በውይይቱ ላይ ከአማራ ክልል 17 ከተሞች የተውጣጡ ከሶስት ሺህ በላይ ወጣቶች ተገኝተዋል። የውይይቱ ተሳታፊዎች “አማራ አብዛኛውን ጊዜ ኢትዮጵያዊነቱን በማስቀደሙ ተጎጂ እንጂ ተጠቃሚ አይደለም” የሚል እምነታቸውን አንጸባርቀዋል። ከአሁን በኋላ ግን “አማራ መጀመሪያ በአማራነቱ ተደራጅቶ በመቀጠል ለኢትዮጵያ መቆም አለበት” ብለዋል፡፡

በውይይቱ ላይ በእንግድነት የተገኙት የኢትዮጵያውያን ሃገር አቀፍ ንቅናቄ (ኢሃን) ሊቀመንበር ይልቃል ጌትነት ባሰሙት ንግግር “በአማራነት መደራጀት ኢትዮጵያን አያፈርሳትም” ብለዋል። የወልቃይት የአማራ ማንነት አስመላሽ ኮሚቴን ወክላ የተገኘችው ንግስት ይርጋ በበኩሏ “የአማራ ህዝብ የሚደራጀው የአቃፊነት ተፈጥሯዊ ስጦታውን የበለጠ ለማጠናከር እንጂ ሀገር ለማፍረስ ወይም ለመገንጠል አይደለም” ስትል ከመደራጀቱ ጀርባ ሌላ አጀንዳ እንደሌለ ገልጻለች።

የባህር ዳር ወጣቶች ማህበር ምክትል ሰብሳቢ ትህትና በላይ እንደምትለው አማራ ከአደጋ መዳን የሚችለው በራሱ ሲደራጅ ብቻ ነው፡፡ በባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስ መምህር ባንታየሁ ሺፈራው በተለይ ለዶይቼ ቬለ DW እንደተናገረው ደግሞ ባለፉት በርካታ አመታት አማራ ኢትዮጵያዊነቱን ማስቀደሙ ታሪካዊ ጠላቶችን አፍርቷል፡፡ በመሆኑም አማራ በብሔር መደራጀት እንዳለበት እምነታቸውን ተናግረዋል፡፡