ሕገ-ወጥ የወርቅ ንግድ ወደ ብሔራዊ ባንክ የሚገባውን የወርቅ መጠን እንዲያሽቆለቁል አድርጎታል ተባለ

ከፍተኛ የወርቅ ክምችት ከሚገኝባቸው ክልሎች አንዱ የሆነው ቤኒሻንጉል ጉሙዝ በክልሉ እየተመረተ ወደ ብሔራዊ ባንክ የሚገባው የወርቅ መጠን ከጊዜ ወደ ጊዜ በከፍተና ደረጃ እየቀነሰ መሆኑን የክልሉ የማዕድን ሀብት ልማት ኤጀንሲ አስታውቋል። በዘንድሮ ዓመት እስካሁን ወደ ብሔራዊ ባንክ የገባው 40ኪ.ግ ብቻ መሆኑን ኤጀንሲው አመልክቷል።

ካለፉት 3 እና 4 ዓመታት  ወደ ብሔራዊ ባንክ ከገባው የወርቅ ምርት ጋር ሲነጻጸር 1000 ኪሎ ግራም  ያህል ያነሰ ነው ተባለ።  ይህን አስመልክቶ ዶቼ ቬለ «DW»  ያነጋገራቸው የቤ/ጉ/ክ የማዕድን ሀብት ልማት ኤጀንሲ የጂሶ ሳይንስና ባህላዊ ማዕድን ምርት ማሳደጊያ ባለሙያ አቶ ጌታቸው አለነ በክልሉ የሚገኙ የወርቅ አምራቾች ዘመናዊ የወርቅ መፈለጊያ ማሽን መጠቀም ከጀመሩ ወዲህ የወርቅ ምርት እየጨመረ ቢሆንም በአካባቢው በተበራከተው ሕገ-ወጥ የወርቅ ንግድ ምክንያት በኩሙሩክና አልማሀል በተባሉ አካባቢዎች ወደ ሱዳን እየተሸጠ እንደሆነ ተናግረዋል።

በባንክ ያለው የዶላር ምንዛሪና በድምበር አካባቢ በጥቁር ገበያ የምንዛሪ ልዩነት እየሰፋ በመጣ ቁጥር ወደ ሌላ ሀገር በሕገ ወጥ መንገድ የሚዘዋወረው የወርቅ መጠን ሊጨምር ይችላል ያሉት አቶ ጌታቸው ብሔራዊ ባንክ ከዚህ ቀደም ከ 150 ግራም በላይ ሲቀርብለት ብቻ ግዥ ሲፈጽም እንደነበር በመግለጽ ይህ ደግሞ የወርቅ ኮንትሮባንድ እንዲስፋፋ ምክንያት በመሆኑ ከ1 ዓመት በፊት መንግስት አምራቾችን ተጠቃሚ ለማድረግና ወርቅ ኮንትሮባንድ ንግድን ለማስቀረት ባንኩ ከ50 ግራም ጀምሮ ግዥ እንዲፈጽም መወሰኑንም ገልጸዋል። ከኮንትሮባድ ንግዱ በተጨማሪም የወርቅ ምርት በስፋት የሚገኝባቸው አሶሳ፣ኩሙርክ፣ ሸረቆሌ እና ሌሎችም አካባቢዎች በወርቅ ምርት ስራ የተሰማሩ 180 የሚሆኑ ማህበራት ተቀናጅተው አለመስራት፣አልፎ አልፎ የውኃ እጥረት መኖርና አንድ አንድ አምራች ማህበራት ደግሞ ሙሉ በሙሉ ወደስራ አለመግባት ለላው ለምርቱ ማሽቆልቆል እንደምክንያት የሚጠቀሱ ናቸው። በክልል ደረጃ ይህንን ለማስቀረት የክልሉ መንግስት ለተፈጥሮ ሀብቱ ትኩረት በመስጸት በህገ ወጥ የወርቅ ግብይት ላይ የተሰማሩ ግለሰቦች ላይ ተገቢ እርምጃ የሚወሰድበት አሰራር ተግባራዊ እየጠደረገ ነው ያለው ኤጀንሲው የሀገር ውስ የወርቅ አምራቾች ያመረቱትን ወርቅ ለብሔራዊ ባንክ በመሸጥ ሀገራዊ ሀላፊነታቸውን መወጣት አለባቸው ብለዋል።