መሬት የተፈጠረችው ሁሉም በሰላም እንዲኖርባት እንጂ ይህ ያንተ ያ የኔ ተብሎ ለመገዳደል አይደለም – የአማራ ክልል የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ

መሬት የተፈጠረችው ሁሉም በሰላም እንዲኖርባት እንጂ ይህ ያንተ ያ የኔ ተብሎ ለመገዳደል አይደለም ሲል የአማራ ክልል የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ አስታወቀ። መንግስት የህዝብን ህይወት በዘፈቀደ በሚገድሉ ሰዎች ላይ እርምጃ እንዲወስድ ጉባዔው በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በሰጠው መግለጫ አመልክቷል፡፡

የአማራ ክልል የሃይማኖት ተቋማት ጉባዔ የቦርድ ሰብሳቢ መለአከ ሰላም ኤፍሬም ሙሉዓለም ትናንት ማምሻውን ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ እንደተናገሩት ህዝብ ህዝብን ይጠብቀናል እንጂ ሊጎዳው አይገባም፡፡አምላክ ሰውን ሲፈጥር በመሬት ላይ በሰላም ያለገደብ እንዲኖርም ነው ብለዋል፡፡የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ ሼህ ሰኢድ መሐመድ በበኩላቸው ዘረኝነት በፈጣሪ ዘንድ ተቀባይነት የለውም ሲሉ ነው ለጋዜጠኞች ያመለከቱት። የማህበራዊ ሚዲያ ተዋናዮች የሚያስተላልፉትን መልዕክት ይዘት በጥንቃቄ ማየት እንዳለባቸውም ሼህ ሰኢድ ተናግረዋል፡፡በዘርና በቋንቋ ናውዘው በሰው ልጆች ላይ ጉዳት በሚያደርሱ ወገኖች ላይ መንግስት አስተማሪ እርምጃ መውሰድ እንዳለበትም ተመልክቶአል።