አንዳርጋቸው ፅጌ ዘፈን ጋብዞን ሄደ !
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
ከአንበሳው ይብራ
መስከርም 22 ቀን 2013 እ.ኤ.አ ቀመር በእለተ ሰንበት ግንቦት ሰባት በአርሊንግቶን ቨርጂኒያ ፤ ህዝባዊ ስብሰባ ጠራ ። በስብሰባው መክፈቻ ላይ የዋሽንግተኑ ቻፕተር ተወካይ አንድ ቃል ገባ ። እንዲህም አለ ። “በመካከላችን የግንቦት 7 መሪዎቻችን ተገኝተዋል ። ግንቦት ሰባትን በተመለከተና ወቅታዊ የሃገራችንን ጉዳዮች አስመልክተው ከናንተ ጋራ ውይይት ያደርጋሉ ። ከዚህ ውይይት ጠቃሚ መረጃ እንደምታገኙ ተስፋዪ ከፍ ያለ ነው ፡ በተጨማሪም ለሚኖሯችሁ ጥያቄዎች አጥጋቢ ምላሽ እንደምታገኙ ባለ ሙሉ ተስፋ ነኝ” ። በጣም ጥሩ ነው አልን ።
ጥያቄዎቻችንን ከማቅረባችን በፊት ግን ፤ ንግግራቸውን እንስማ ብለን ፤ በተለይ አንዳርጋቸው በኢሳት ቴሌቪዥን የሰጣቸውን መግለጫዎች ያብራራል ብለን ጠበቅን ። አንዳርጋቸው ያደረጋትን አጨር ማብራሪያ ሲጀምር ፡ “የእውነቶች ሁሉ እውነት ከወያኔ በላይ የኢትዮጵያ የሃገሯ የደህንነቷና ጥቅሟ ጠላት ከወያኔ በላይ የለም ብየ ነው የምነሳው” ካለ በኋላ አንዲት ነገር ሳይቀንስ ያንኑ የሻእቢያ ጥብቅናውን ነግሮን ነው የሄደው ፤ እንዲያውም አለ አንዳርጋቸው ስለዚያች ሃገር (ኤርትራ) ብዙ ያልነገርኳችሁ ነገር አለ አለን ። ከወደ አስመራ የተሰማውም ዜና የሚያመላክተው ግን አንዳርጋቸው የሰጠው ማብራሪያ እንዳልተወደደለት ነው ። በሻእቢያዎቹ ሞገስ አገኛለሁ ብሎ ያሰበው አንዳርጋቸው አስመራ ሲገባ ፤ በሻእቢያ ስልታዊ ትምህርት ይጠብቀዋል ። የሱ ያልሆኑ ነገሮችን ሁሉ ነካክቷልና ።
ውድ አንባቢዎቼ ታስታውሱ እንደሆን ሃይለማርያም ደሳለኝ ለአልጀዚራዋ ጋዜጠኛ በዲሴምበር 2012 በሰጡት ቃለ-ምልልስ ላይ እንዲህ ብለው ነበር ። “If you ask me, ‘Do you want to go to Asmara and sit down and negotiate with Isaias Afwerki?’ Then, I will say yes’. አስመራ ሄደህ ከኢሳኢያስ አፈወርቂ ጋር ተቀምጠህ ትደራደራለህ ወይ ብለሽ ብትጠይቂኝ አዎን ነው የምልሽ ፤ ብለው ነበር ። እና ኃይለማርያም ደሳለኝ ይህን ጥያቄ ራሳቸው ጠይቀው ራሳቸው ሲመልሱ በአሳዳሪዎቻቸው ወያኔዎች ሞገስ አገኛለሁ ብለው አስበው ነበር ። እሳቸው የፈለጉት የወያኔን ሰላም ፈላጊነት በተሻለ መንገድ ለማሳየትም ነበር ። ሃሳባቸው ግን የፈለጉትን ግብ ሳይመታ ቀርቶ እንዲያውም ፤ የተሰጣቸውን መስመር በማለፋቸው “ማን ይህን በል አለህ” በሚል በወያኔ ከፍተኛ ተግሳፅ እንደደረሰባቸው ሁላችንም የሰማነው ነው ። ምን ጭራህን ትቆላለህ ይለዋል ይህን አይነቱን ሰው ያገሬ ሰው ። ሃይለማርያም ወያኔ ፊት ጭራ እንደቆሉ ሁሉ አንዳርጋቸውም ሻእቢያ ፊት ጭራውን ቆልቷል ። እንደሰማነው አስመራዎቹ አንዳርጋቸው የማይመለከተውን ሁሉ ዘባርቋል ብለው አስበዋል ።
ሻእቢያዎች እንዲህ አይነት ነገር ሲያጋጥማቸው ለምን እንዲህ አልክ ለምን እንዲህ አደረክ ብለው አይጠይቁም ፤ ለተናጋሪው ግን የአሰራር ገደብ ያደርጉለታል ። ከዚህ በፊት ይሰጡት የነበረውን ፊት ቀስ በቀስ ይነፍጉታል ። በሚሄድበት ቦታ ሁሉ የሚያገኛቸውን አገልግሎቶች ሁሉ ይቀንሱበታል ። ክፍት የነበሩት በሮች ሁሉ ገርበብ ይደረጋሉ ፤ በኋላም ላይ ከናካቴው ይዘጋሉ ። ዛሬ አስመራ አንዳርጋቸው የሚጠብቀው ይህ ነው ።
የአርሊንግቶኑ ስብሰባ ላይ ብርሃኑ ነጋም ሆነ አንዳርጋቸው መሬት ላይ ጠብ የማይል ወሬ ነው የነገሩን ። “ወሬ በዝቷል ፤ ሁሉም እኮ እኩል የሆነው ለዚህ ነው” ሲሉ ተናገረ ብርሃኑ ። ምን ማለት ይሆን ይህ አባባል ? እኔ አልገባኝም ። እኩል አይደለንም እንዴ ? በምን ይሆን የምንበላለጠው ? “በስራ የሚታየውን እናሳይና then we will talk” ትክክል ብለሃል ብርሃኑ ግን እኮ በዚህ አምስት አመት ውስጥ እኛ አልነበርንም በነጋ በጠባ ኢሳት ወይ ፓልቶክ ላይ እየወጣን ወሬ ያበዛነው ። እናንተ ናችሁ ። ከወሬ ውጪ ምን አሳያችሁን ። ወያኔ እንኳ የአባይን ግድብ 20% የሚሆነውን ሰርቻለሁ ብሎናል ። እናንተ ከያዛችሁት ፕላን ምን ያህሉን ሰራችሁ ። ፕላንስ ነበራችሁ ወይ ? ወይስ ዝም ብሎ በደመ-ነፍስ ነው ስራችሁ ሁሉ ። አንዳርጋቸውስ ምንድነው ያለው በዚህ ስብሰባ “እዛ አካባቢ ያለውን ሰራዊት ለማንም ፓርቲ አሽከር እንዳይሆን ፤ ትምህርቱ ይሄ ነው ስልጠናው ይሄ ነው” ። “ፅድቁ ቀርቶብኝ በቅጡ በኮነነኝ” እንደሚባለው ፤ መጀመሪያ ሰራዊት ይኑራችሁና አሽከር ስለመሆንና አለመሆን በኋላ እንነጋገራለን ። ዛሬ ህዝባችን ውጤት ይጠብቃል ። ከእንግዲህ ውጤት ካላየ አምስት ሳንቲም ጠብ እንደማይለው በአርሊንግቶኑ ስብሰባ ላይ ህዝቡ አስይቷችኋል ። እና የምንመክረው ዘፈናችሁን ቀይሩ ነው ። “በፋሲካ ይተገዛች ባሪያ ሁሌ ፋሲካ ይመስላታል” እንዲሉ ፡ ሁሌ በኢሳት ወይም በፓልቶክ ብቅ እያላችሁ ፤ ወይም አዳራሽ ውስጥ እየሰበሰባችሁን ስለምታወሩ የምትሉትን ሁሉ የምናምን መስሏችኋል ። አሁንም እየነገራችሁን ያለው ትምህርት እየሰጣችሁ እንደሆነ ነው ። አንድ ጠብታ ተግባር ማየት እንፈልጋለን ።
አርሊግቶን የተጠራው ስብሰባ አቢይ አላማ አንዳርጋቸው በኢሳት ለሰጠው ቃለ-መጠይቅ ማብራሪያ በማስፈለጉ ነበር ፤ የሆነው ግን ይህ አይደለም ። ክህዝብ ሊነሳ የሚችለው ጥያቄ ስላስፈራችሁ በእቅድ አንዳርጋቸው ወደአስመራ በሚበርበት እለት ስብሰባ አዘጋጃችሁ ፤ ወይም በረራ አለበት ብላችሁ ከአዳራሹ የእጅ ሻንጣ ይዞ እንዲወጣ አደረጋችሁ ። ስብሰባው ቅዳሜ ሊዘጋጅ አይችልም ነበር ?
ጥያቄ ለማቅረብ እድል ከተሰጣቸው ሰዎች አንዱ ስለማያገባችሁ ስለነኢሳኢያስ አታውሩ ብሎ ማሳሰቢያ ሰጠ ። ሌላው ጠያቂ እያሾፈና እየሳቀ “አቶ አንዳርጋቸው የጦር ሰው ስለሆኑ እንግዲህ ” ብሎ ሲናገር ከአዳራሹ የተሰማው ሳቅ የሚያመላክተው ነገር ነበረው ለሚገባው ሰው ፤ እስቲ እናሹፍ ( አሁን አየር ሃይል አላችሁ አይደል?) ።
አንዳርጋቸው በኢሳት ላቀረበው የሻእቢያና የኢሳኢያስ ፍቅር ማብራሪያ በመስጠጥና የተናገርኩት ትክክል አልነበረም ብሎ ለህዝብ በማስረዳት ፈንታ ፤ በአዳራሹ የተሰበሰበውን ሰው በነበረከት ስምኦን ውስኪና በአላሙዲን ኬክ አቅርቦት ማዝናናት ነው የመረጥከው ። አላሙዲን ለነበረከት ከእንግሊዝ አገር ኬክ አሰርቶ ቢያመጣላቸው እንኳ እኛ ምን አገባን ።
አቶ አንዳርጋቸው ፤ ስለተገረፉት ሰዎች ማለትም ስለሰብአዊ መብት መረገጥ ፤ ስለወያኔ ፍርድ ቤቶች ፍትህ መጓደል ፤ ስለወያኔ ሚዲያዎች ነፃ አለመሆን ፤ ስለዲሞክራሲ እና ስለመሳሰሉት ጉዳዮች አንዳንድ ቦታ እስከ10ሺህ አንዳንዴም 4ሺህ ሰዎችን አስትምር ነበር ወያኔዎቹ ጋር እያለሁ ብለኽናል ። ጥሩ የማስተማር ችሎታ የለህም እንዴ ? ወያኔዎቹ ትምህርትህ ካልገባቸው ፤ የተቀዱበት ወንዛቸው አንድ ነውና ፤ ድምህቶችም አይገባቸውም ብትተወው ይሻልሃል ።
ስለዚህ ስብሰባ ኢሳት ያቀረበው ልዩ ዝግጅት 57ኛዋ ደቂቃ ላይ መመልከት ይቻላል ፤ በቅርቡ ኢሳኢያስ ስለተናገርው ያልካትና ብዙው ሰው ያስተዋለው አንድ ነገር ነበር ፤ አሁንም ለዚህ ስብሰባ ተብሎ የተለቀቀ ነገር የማቀው ነገር የለኝም ብሎት እንደሆነ አላለውም አላውቀም ስለ ኢሳኢያስ የተነሳ ጉዳይ አለ ፤ ብለኽናል ። ቦታና ጊዜ ተጠቅሶ የቀረበንና ኢትዮጵያ ከሁለተኛ የአለም ጦርነት በኋላ የተፈጠረች አገር ናት ሲል ለኤርትራ ጋዜጠኞች የሰጠውን ቃለ ምልልስ አላምንም እያልከን እኮ ነው ። ሄደህ ከኢሳኢያስ እስክትጣራ እንጠብቅሃለን ። ለነገሩ ኢሳትም እኮ ኢሳኢያስ ስለተናገረው አንድ ነገር ትንፍሽ አላለም ።
ለዚሁ ስብሰባ ሲባል በግንቦት7 ምንጭነትና በኢሳት አጋፋሪነት የቀረበውን 4 ፓይለቶች የግንቦት 7ን ህዝባዊ ሃይል ተቀላቀሉ ዜናስ እንዴት ልታስረዳን ትችላለህ ? ለዚህ ስብሰባ የተለቀቀ ዜና አይደለምን? ! ፓይለቶቹ መቼ ወደኤርትራ እንደገቡና ከየት አገርስ እንደመጡ ቀኑና ጊዜው አልተገለፅም ። 2ቱን ከቻይና የመጡ መሆናቸውን ስትገልፅ ሌሎቹ 2ቱ ከይት እንደመጡ አልነገርከንም በቀጥታ ከኢትዮጵያ ወይስ ከኬንያ ና ከደቡብ አፍሪቃ ስደተኛ ካምፖች ።
አንዳርጋቸው ስለ ኢትዮጵያ ታሪክና እናትህም አንተም ስለተወለዳችሁባት ስለመዲናችን አዲስ አበባ ያለህን ፍቅር ፤ ብሎም ስለነበርክበት የተማሪ ትግል ስህተቶች በድፍረት በመናገርህ ሳላደንቅ ያለፍኩ እንዳይመስልህ። ይህን ንግግርህን ብርሃኑ ነጋ ለታክቲክ የምንጠቀምባቸው ነገሮች አሉን ከሚላቸው ውስጥ ነው ብየ ለማመን አልፈልግም ከልብ የተናገርከው ነው ብየ እገምታለሁ ። ስለብርሃኑ ከተነሳ ደግሞ አንድ ነገር ልበል በዚሁ ስብሰባ ላይ ከተናገረው።
ብርሃኑ የግንቦት 7 መሰረታዊ እምነቶች ብለህ 3 አበይት ጉዳዮችን እንዲህ ስትል አቀረብክ ። ኢትዮጵያ ውስጥ መሰራታዊ የሆኑ የዲሞክራሲና ሰብአዊ መብቶች የተከበሩባት ሃገር እንድትሆን ፤ ዲሞክራሲያዊ የፖለቲካ ስርአት ኢትዮጵያ ውስጥ እንዲገነባ ፤ ኢትዮጵያ አንድ የፖለቲካ ማህበረሰብ መሆኗና አንድ አገር መሆኗን መቀበል ነው ፤ አልከን ። ብርሃኑ ዛሬ በምትኖርባት አሜሪካ የዲሞክራሲ ስርአቱ ጀማሪዎች “The founding fathers” በተግባር ዲሞክራሲን ስለተጠቀሙበት ነው ዛሬ አሜሪካ እዚህ የደረሰችው ። ብርሃኑ በአምስተርዳም የኢሳት ቢሮ የፈፀምከው ተግባርና ትጠቀምባቸው የነበሩ ስድቦች እንዲሁም ተፈጥሮ በነበረው ጉዳይ የአውሮፓው አጣሪ ኮሚቴ ያቀረበውን ሪፖርት እንዴት እንደገለበጥከው ልናቀርብ እንችላለን ፤ ይህ ታዲያ ዲሞክራሲያዊ ነበር ? በሾለከው የድምፅህ ቅጂ ላይ ድርጅቶች አንዴ ይከስማሉ ሌላ ጊዜ ይፈነዳሉ ስትል የተናገርከው፤ በራሱ ዲሞክራሲያዊነት አይደለምና ታዳሚው ሊሰማ የሚፈልገውን ብቻ ሳይሆን ፤ ዲሞክራሲን ልምድህ ብታደርገው ለራስህም ይጠቅምሃል ። ከሌሎች ኢትዮጵያዊ ዲሞክራሲያዊ ሃይሎች ጋር መስራትም ተገቢ ነው ብለን እናምናለንም ብለኻል ፤ ያው የድምፅህ ቅጂ እንዳስተማረን የአብሮ መስራት ባህርይም የለህም ።
ብርሃኑ በተጨማሪ ከዚህ ቀደሞቹ የፓለቲካ ድርጅቶች በተለየ ሁኔታ ግንቦት7 ለሂደት ትኩረት ይሰጣል ብለኻል ። ከዚህ ቀደም እኮ የኤርትራን አካሄድ ወይም ሂደት ገብተው ሞክረውት እንደማያዋጣ መዝነውና ተመልክተው ትተው የወጡና አሁንም እዚያው ተዘፍቀው የቀሩ ድርጅቶች አሉ ። የናንተ ሂደት ምን አዲስ ነገር ቢኖረው ነው? በአንድ ሰው እድሜ 5 አመታት ቀላል አይደለም ። ሂደታችሁ እኮ የትም ፈቅ አላለም።
በአጠቃላይ በዚህ ስብሰባ መድረክ ላይ የነገራችሁንን ነገር እኮ ሸራተን ድረስ ሳታለፉን $20 ዶላርም መግቢያ ሳታስከፍሉን ፤ በተለመደው አይንና ጆሮችሁ በኢሳት ለትነግሩን ትችሉ ነበር ።
አንዳርጋቸው ስለትግራይ ድምህት ወጣቶች የሙዚቃ ባንድ የኢትዮጵያን ባንዲራ መልበስ ነገርከን ። ሽእቢያ ልበሱ ካላቸው ነገ ደግሞ የኤርትራን ባንዲራ ይለብሳሉ ። አንድ የሙዚቃ ባንድ የመድረክ ልብሴ ነው ያለውን ዩኒፎርም በፈለገው አይነት ይለብሳል ፤ ያን ለበሰ ማለት ደሞ ሆነ ማለት አይደለም ። የመለስ ዜናዊ አስከሬን የኢትዮጵያን ባንዲራ ለብሶ አልነበረም እንዴ ። በእግዚአብሄር እምነት የሌለው እቴይስቱ መለስ ፀሎተ-ፍትሃት ተደርጎለት የለም እንዴ አስከሬኑ ሲሸኝስ በኦርቶዶክስ ካህናት ታጅቦ አልነበረም እንዴ ? ምን ይደንቃል ! አገራችን እንደሆነ በዚህም በለው በዛ ትያትር ቤት ሆናለች ። ይልቅ ስለ ድምህቶች መልእክት እንነጋገር ።
እኛም ድ.ም.ህ.ቶች ይህ መልእክት ይድረሳችሁ እንላለን !
እንደሚታወቀው የትግራይ ህዝብ በደርግ ስርአት ይደርስበት ከነበረው ሰብአዊና ዲሞክራሲያዊ አፈና ለመላቀቅ የ17 አመታት የትጥቅ ትግል አድርጎ ፤ ብሎ ሲጀምር መልእክታችሁ ፤ ወያኔ ለመጀመሪያ ጊዜ አዲስ አበባ ሲገባ የተናገረውን አዋጆች አይነት ስሜት ይፈጥራል ። በደርግ ስርአት አፈና የደረሰው ደግሞ በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ ሁሉ እንጂ በትግራይ ህዝብ ላይ ብቻ አልነበረም ። በመቀጠልም ከ65 ሺህ በላይ ግጀግኖች ልጆቹ ሲሰው በአሰር ሺዎች የሚቆጠሩ ደግሞ አካለ ጎዶሎ ሆነዋል ፤ ይላል መልእክታችሁ ። መቼም በሞተና በተጎዳ ላይ ወቀሳ ማቅረብ በባህላችን ተገቢ ባይሆንም እናንተ ስላነሳችሁት ነው መልስ እንድንሰጥ የተገደድነው ። የአንድ ህዝብ መስዋእትነት የሚለካው በውጤቱ ነው ። በኛ በኩል እነዚህ ሰዎች ኤርትራን ከእናት ሃገሯ ለማስገንጠል ሲሉ የተዋደቁ ናቸው እንላለን ። የነዚህ ሰዎች ሞትና ጉዳት ለኢትዮጵያ ምን አተረፈላት ብሎ ራስን መጠየቅ የተገባ ነው ። በነዚህ ሰዎች ደምና አጥንት ኢትዮጵያ የባህር በሮቿን አጥታለች ፤ ህዝቧ በዘር ፤ በሃይማኖት ፤ በጎሳ ፤ በቋንቋ ተከፋፍሏል ፡ ሩቅ መሄድ ሳያስፈልግ እናንተ ራሳችሁ እንኳ የተደራጃችሁት በዘር መሆኑ በቂ ምስክር ነው ። የነዚህ ሰዎች ሞትና ጉዳት በሙዚቃችሁ ፊልም ላይ እንደሚታየው ህዝባችንን ለአረብ አገር ባርነት ዳርጓል ። የነዚህ ሰዎች ሞትና ጉዳት የስንቱን ኢትዮጵያዊ ቤትና ኑሮ ፈትቷል መሰላችሁ ፤ ለኢትቶጵያ አንድነት የተዋደቀው ሰራዊት ከነቤተ-ስቡ ተበትኗል ። በአገራችን ኢትዮጵያ ሽርሙጥና ተስፋፍቷል ፡ ህዝባችን በቀሳፊ በሽታዎች እየማቀቀ ይገኛል ፤ የትግራይ ህዝብ ከፈለው የሚባለው መስዋእትነት ውጤት ይህ ነው ። አንድ እንሁን የሚለውን ጥሪያችሁን በመላው አለም ላለነው ኢትዮጵያውያን አስተላልፋችሁልናል ። አንድ እንዳንሆን ሌት ተቀን የሚደክመው ሻእቢያ ጉያ ተቀምጣችሁ አንድነት ይመጣል የሚል እምነት የለንም ። እግዚአብሄር ካላችሁበት እስር ቤት ያወጣችሁ ዘንድ ፀሎታችን ነው።
ይህን መልእክት አድርሱልን ብለዋል ብሎ አንዳርጋቸው ስለነገረን ፤ ለመልእክታችሁ መልስ ለመጠት ብለን ነው ።
ወድ አንባቢዪ ሆይ ! በአጠቃላይ በዚህ በሴፕቴምበር 22/2013 በአርሊንግቶን ቨርጂኒያ ሸራተን ሆቴል የተደረገው ስብሰባ በአብዛኛው የኢሳት የአንዳርጋቸውን ቃለ-መጠይቅ እንደገና ፎርሙን ቀየር አድርጎ ነው የቀረበው ። አንዳርጋቸውም ሆነ ብርሃኑ በስብሰባው ንግግራቸው ላይ ባጠቃላይ በወያኔ የወደፊት ውድቀት ላይ እየፎከሩ የማይጨበጥ ተስፋ ብቻ ነው የሰጡን ። ሁሌ ካፋቸው የማይለየው የህዝባችን ብሶትንም ሲያኝኩት ውለዋል ። እኛ የምንጠብቀው ተግባር እናንተ የምታወሩልን ቀቢፀ-ተስፋንና ብሶት ብቻ ። ይህ ስብሰባ ትንሽ ትያትር ቢጤ የተሰራበትም ነበር ። አንዳርጋቸው እዚህ ስብሰባ ላይ ሰራዊታችን ሻንጣውን ይዞ ገባ ? መኪና ውስጥ መተው አለዚያም የሆቴሉ receptionist ቶችጋ ማስቀመጥ ይችል ነበር ። ከስብሰባው አዳራሽ ሲወጣ ሻንጣውን ይዞ ነበር የወጣው ። መልእክቱ ምን ይሆን ? በአጠቃላይ በዚህ ስብሰባ አንዳርጋቸው በግንቦት 7 ስም ይህን ሰርቻለሁ ፤ ይህን አድርጌያለሁ ፤ ሰራዊታችን በዚህ አውደ-ውጊያ ይህን ግዳይ ጣለ ብሎ ለመናገር የሚለው ቢያጣ ሁለት የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ምንቅስቃስ ህዝቢ ትግራይን ሙዚቃዎች ጋብዞን በመሄዱ አመስግኛለሁ ። እንዴት ነበር ስብሰባው ብለው ለጠየቁኝ ሁሉ አንዳርጋቸው ፅጌ ዘፈን ጋብዞን ሄደ ብያቼዋለሁ።
ቸር ይግጠመን!
እንኳን ለመስቀል በዓል በሰላም አደረሳችሁ ! ከአንበሳው ይብራ
[email protected]