አለማየሁ እንደ አራፋት… (ከተስፋዬ ገ/አብ)


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


ይህን ከመፃፌ በፊት አልጀዚራ እያየሁ ነበር። ያሲር አረፋት የተገደለው (…he might have been poisoned with polonium, a rare radioactive isotope. ) ተመርዞ ሊሆን እንደሚችል የሚጠቁም ወሬ አወጁ። ልብሱና የጥርስ ብሩሹን ስዊዘርላንድ ላይ በመመርመር የተገኘውን ውጤት ዋቢ በማድረግ፣ አራፋት 2004 ላይ ተመርዞ ተገድሎ ሊሆን እንደሚችል ጠቁመዋል። ሞቶ ከተቀበረ ከስምንት አመታት በሁዋላ ይህ ምስጢር ተገኘ። በጎ ነው። እውነት ከተቀበረችበት ብቅ ማለቷ በርግጥም በጎ ነው። ጊዜው ሲደርስ ጆንጋራንግ እንዴት እንደተገደለም እንሰማ ይሆናል።

ቴሌቪዥኑን አጥፍቼ ወደ መኝታዬ ሳመራ ስለ አለማየሁ አቶምሳ አስታወስኩ። በተመሳሳይ ተመርዞ መታመሙና ከዛሬ ነገ ህይወቱ ታልፋለች እየተባለ ባንኮክ ህክምና ላይ እንደሚገኝ አውቃለሁ። ለመሆኑ አለማየሁን ማን መረዘው? ለምን አላማ?

የዚህን ምስጢር ከእለታት አንድ ቀን እንሰማዋለን ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። በዚህ ባለንበት ዘመን አስቸጋሪ ሰዎችን የማስወገጃው ቀዳሚ ዘዴ ምረዛ እየሆነ በመሄዱ፣ በጣም አሳሳቢ ሆኖአል። በተለይም እስርቤት ያሉ የነፃነት ታጋዮች፣ ራሳቸውን የሚከላከሉበት እድል በጣም ጠባብ በመሆኑ ጉዳዩን ይበልጥ አሳሳቢ ያደርገዋል።

አለማየሁን በቅርብ አውቀው ነበር። ከኦህዴድ አመራር አባላት የተለየ ነበር። ዋናው ተወዳጅ ባህርይው የአንጎሉን መናገር መቻሉ ነበር። ታዛዥ እና እጁ በደም የተጨማለቀ አለመሆኑም ይታወቃል። ወደ ኦሮሚያ ፕሬዚዳንትነት ከመሳቡ በፊት ከአመራር አነባላቱ ጋር እየተጋጨ፣ ገለል ተደርጎ ቆይቶአል። የግጭቱ ምክንያት ሙስናን መቃወሙና ማህበራዊ ፍትህ መጠየቁ ነበር። በዚህ ምክንያት በኦነግነት ተፈርጆ በአይነቁራኛ ሲጠበቅ ኖሮአል። በኦነግነት የሚጠረጠር የነበረን ግለሰብ ወደ ስልጣን እንዲመጣ ለምን እንዳደረጉ ገርሞን ሳንጨርስ፣ መመረዙ ተነገረን።

“ማን መረዘው? ለምን?” ለሚሉት ጥያቄዎች ያልተረጋገጠ ሹክሹክታ እንጂ ምንም መረጃ የለም። በምረዛው በሰፊው የሚታሙት ግለሰቦችም ተጠርተው አልተጠየቁም፣ ስራቸው ላይ ናቸው። አባዱላ እና ሙክታር የድርጊቱ ፈፃሚዎች ስለመሆናቸው ተብሎ ተብሎ ያለቀለት ነው። የወያኔ መንግስትም በጉዳዩ ላይ ትንፍሽ ብሎ አያውቅም። አባዱላ ስልጣኑን በመነጠቁ፣ ሙክታር ደግሞ የአለማየሁን ቦታ በመመኘቱ በርግጥ ይህን ሊፈፅሙ ይችላሉ? ወይስ በእነርሱ ሰም ድርጊቱን የፈፀመ ሌላ ጥልማሞት አለ? አለማየሁ ማገገም ከቻለ ፍንጭ ይሰጠን ይሆናል። እግዚሃር ይማረው!