እናት መሬት!
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
ከደምስ በለጠ
እናት መሬት ሆይ! በምድርሽ ላይ ደም እንደውኃ ፈሰሰ ። ጨቋኞች የሰው ስጋ መተሩብሽ ። ወጣቶችሽ እንደዱር አውሬ እየታደኑብሽ ነው ። አዳኞቹ ደግሞ ከሰው የተፈጠሩ አይመስሉም ። ወይ አንቺ እናት መሬት ! እስከመቼ ? እኮ እስከመቼ ? የደም አበላ ይከፈልሽ ! መቼ ይሆን የደም ግብርሽ የሚቆመው ? መቼ ይሆን ለዘንዶው ግብር የሚሰጡ የህጻናት መስዋትነት የሚገታው ? ሴቶችሽ ሃፍረታቸው ተገለበ ! ባልቴት እናቶች ቀሚሶቻቸው በልጆጃቸው ደም ጨቀዬ ። አዝውንቶችሽ የዘመን ክብር ሽበታቸው በወራዶች ተነጨ ፤ ሪዛቸው ተጎተተ ። የአብያተ ክርስቲያናቱ መጋረጃዎች ለጋጠ-ወጦች መከናነቢያ ተሰጡ ። የመስጊዶችን ቅዱስ ቦታዎችን በተበከለ ቆሻሻ እግሮቻቸው አጎደፏቸው ።
ታዲያ የዛሬው ዘመን ወጣት ምን እያለ ይሆን ?
ዘመን የሚያመጣቸው ወይም የሚወስዳቸው ሁነቶች በታሪክ ውስጥ ያጋጥማሉ ። የትላንቷ ኢትዮጵያ ወጣት ለሃገራችን ህዝብ መልካም ዘመን እናመጣለን ከሚል ህሳቤ ፤ በአንድ የፖለቲካ መርሕ ፤ ሆኖም ግን በተለያየ የፖለቲካ ድርጅት ውስጥ በመሰለፍ ፤ ጠመንጃ አንስቶ የአገሪቷን ማእከላዊ መንግስት ተፋልሟል ። የዚህ ትግል ውጤት ዛሬ አገሪቷ ለደረሰችበት ሁኔታ መሰረት ጥሏል ፤ ወይም መንስኤ ሆኦኗል ፤ የሚል ክርክር ውስጥ መግባት አልፈልግም ። ከዚያ አንድ ዘመን ቀደም ብሎ የነበረው ትውልድ ግን ፤ ጊዜው ጎትቶ ከቀየው ድረስ ያመጣበትን የፀረ- ቅኝ ገዢዎች ትግል በታላቅ አርበኝነት ተወጥቷል ። የሃገሪቷንም አንድነት ጠብቆ ለመጪው ትውልድ አስተላልፏል ።
የዛሬው የኢትዮጵያ ወጣት ትውልድ ደግሞ ፤ ራሱን ካልጠበቀው ሁኔታ ውስጥ ገብቶ አግኝቶታል ። ይህ ዘመን ፤ የዚህ የአዲሱ ዘመን ወጣት ዘመን ቢሆንም ፤ ራሱ ሳይፈልገው በግድ የተጫነበት ማህበራዊና ፖለቲካዊ ችግር ውስጥ ገብቷል ። ፈለገውም አልፈለገውም የዘመናችን ወጣት ፤ የአገሪቱን አንድነት የመጠበቅ ፤ ብሎም ማህበራዊና ፖለቲካዊ ፍትህ ይመጣ ዘንድ መታገሉ አይቀሬ ይሆናል ። ታዲያ ይህ የዛሬው የኢትዮጵያ ወጣት ለዚህ ይበቃ ይሆን ? ወይስ የቀደሙት የፈፀሙትን አይነት ስህተት ፈጽሞ የሱም ዘመን አገሪቱን ሌላ የችግር አዙሪት ውስጥ ከቷት ያልፍ ይሆን ?
ላለፉት ዘጠኝ ወራት በረዕሰ-ከተማችን በአዲስ አበባ ዙሪያ የተቀሰቀሰው ህዝባዊ አመፅ በተለያዩ የኦሮሚያ ከተሞችና ገጠሮች በመስፋፋት ፤ እስካሁንም እዚህም እዚያም እሳቱ እየነደደ ይገኛል ። ለዚህም የኦሮሞ ወጣቶች የደምና የህይወት መስዋእትነት ከፍለዋል ። አሁንም እየከፈሉ ናቸው ። ዛሬ በጎጃም ደብረ-ማርቆስና ባህር ዳርም የደም ዋጋ እየተከፈለ ነው ። ሌሎችም አካባቢዎች ፤ የመስዋእትነቱ ዋጋ ለመክፈል በዝግጅት ላይ ናቸው ። ይህ ሁኔታ ይፈጠር ዘንድ ፤ ትልቁን ሚና የተጫወተውና አሁንም በመጫወት ላይ ያለው ፤ ስርአቱ ራሱና የስርአቱ ባህርይ ነው ።
በጎንደር የተነሳው ሕዝባዊ እንቢተኝነትና አመፅ በጎንደር ወጣቶች የተመራ ነው ። ይህን አመጽ ለየት የሚያደርገው ደግሞ ያለውን ስርአት ከፍ ያለ ፈተና ውስጥ የከተተ መሆኑ ነው ። የጎንደር ሰው ከመሞት አልፎ ለመግደልም ብረት አንስቷል ። የስርአቱን ገዳይ አግአዚ የተባለውን ጦርም ፈትኖታል ። አግአዚ ጦር በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች እየተላከ ያልታጠቁ ሰዎችን ፤ ሴቶችንና ህጻናትን በመግደል ተወዳዳሪ አልተገኘለትም ። ሴት ገዳይ ነው ። ህፃናትን አራጅ ነው ። አግአዚ ፤ በዚህ ጦር ሜዳ ላይ ውሎ ፤ የሃገሪቷን ድንበር አስከበረ ሲባል ታይቶም ተሰምቶ አይታውቅም ። ታዲያ ይህን የአገዛዙን ማስፈራሪያ ዱላ ፤ የጎንደር ሰዎች ፈትነውታል ፤ ዘርጥጠውም ጥለውታልም ።
ከአገራችን ታሪክ ፤ የዛሬ አራት መቶ አመት ወደ ኋላ ተመልሼ አንድ ማጣቀሻ ዋቤ ላደርግ ወደድኩ ። ግራኝ አህመድ ወደ ሰሜን ኢትዮጵያ ያደረጋቸው መስፋፋቶች ላይ የተፈጠረ ታሪክ ነው ። “የግራኝ አባት ቄስ የነበረ ሰው መሆኑንና ከግራኝ እናት ጋር አድሮ በጠዋት ለቅዳሴ ሲወጣ ፤ በጥምጥሙ ፈንታ የእስላሟን የግራኝን እናት መቀነት ራሱ ላይ ጠምጥሞ ወደመቅደስ ሊገባ ሲል ፤ ከእስላሟ ጋር ማደሩን ያወቁት ቄሶች ፤ ተሰብስበው በመቋሚያቸው ቀጥቅጠው ገደሉት ። በዚህ ምክንያት አብያተ ክርስቲያናትን ያቃጥል ነበር ።” የሚል ተረት ተረት የኔ ዘመን ትውልድ በልጅነታችን ከካህናት ስንሰማ ቆይተናል ። ለዚህ ተረት ደግሞ አንድም የታሪክ ማጣቀሻ አልተገኘለትም ።
ልክ እንደዚሁ አይነት ሌላ ተረት ተረት ፤ በካህናት ስለግራኝ አህመድ ይነገሩ የነበሩ ፤ ጦር በታኝ የሆኑ ወሬዎች በንጉሱ በአፄ ልብነድንግል ጦር ውስጥ በሰፊው ይወራ ረበር ። ጎንደር ብትሄዱ በአንድ እጁ ግራኝ የተከለው እየተባለ የሚወራለት ቋጥኝ ይኖራል ። ወሎ ላይ ደግሞ የግራኝ ፈረስ በአንድ እግሩ ረግጦ የናደው የተራራ ክፋይ እስካሁን ድረስ ይወሳለታል ። ጎጃም ላይ ወይም ትግራይ ብሎም ሸዋ ላይ ተመሳሳይነት ያላቸው የግራኝ አፈ-ታሪኮች ከዚያ ዘመን ጀምረው እየተወሩ ዛሬ ላይ ደርሰው ሰምተናቸው ይሆናል ። ግራኝ ለአስራ አምስት አመታት ፤ በአንድ የጦር ሜዳ ላይ ሳይሸነፍ ጥቃቱን በንጉሱ ጦር ላይ አዝንቧል ። “ግራኝን እንዴት ማሸነፍ አቃተን ?” ተብሎ በንጉሱ ሰራዊት በኩል ፤ በጊዜው ይነሳ ለነበረው ጥያቄ ፤ የጊዜው ምሁራን የነበሩትና ሁሉን አዋቂ የሚባሉት ካህናት በንጉሱ ጦር ውስጥ የሚነዙት ወሬ ነበራቸው ። ግራኝ ከተራ የሰው ልጅ ውሱን አቅም በላይ ኃይል ያለው ፤ ተራራ የሚንድ ፤ የሚቀመጥበት ፈረስ ራሱ እንደግራኝ ሁሉ የታሰረበትን ዋርካ ነቅሎ የሚሄድ ፤ ልክ እንደ ዛሬው የአሜሪካን የፊልም ኢንዱስትሪ ፈጠራ “ሱፐር ማን” አይነት ባህርይ ይሰጡት ነበር ።
ስለዚህ የግራኝ ጦር መጥቶ ለውጊያ ከንጉሱ ጦር ፊት ሲቆም ፤ የሁሉም የንጉሱ ወታደር ጥያቄ ፤ ይህን የእስላሞቹን ጦር እየመራ ያለው ማነው የሚል ይሆናል ። የጦሩ አዝማች ግራኝ መሆኑን ያወቀ የንጉሱ ወታደር የአቅሙን ያህል ከመዋጋቱ በፊት ፤ ቀድሞ በሰማው መሰረት ፤ በምናቡ የፈጠረውን የግራኝ ሃያልነትን ሲያስብ ፤ አስቀድሞ ወኔው ከድቶታል ። ያን በምናቡ ካህናቱ የሳሉበትን ፤ በአካል የማያውቀውን ጎልያድ እንደማይችለው በማሰብ ለሽሽት ይዘጋጃል ። እንደዚያ ዘመን ሰው አስተሳሰብ ፤ ይህን አስፈሪ የሰይጣን ቁራጭ ጎልያድ ፤ አንድ የፖርቱጋል ወታደር በአንድ ጥይት በጌምድር ላይ ሲያጋድመው ፤ የአበሻ ወታደር ተመልክቶ “ግራኝ ማለት ይህ ነው እንዴ ?” ብሎ በእጅጉ ሳይገረም አልቀረም ።
እንደዚሁ ሁሉ ፤ ይህን ህፃናትና ሴቶች ገዳይ የሆነውን ጦር ጎንደሮች እንደ ግራኝ ሁሉ ሞክረው አጋድመውታል ። ጎንደር የተበላሸውን ሲያስተካክል የተጣመመውን ሲያቃና ይህ የመጀመሪያው አይደለም ። ሱስንዮስ የሻረውን ፋሲለ-ደስ አቅንቶታል አገሩንም አረጋግቶ ሰላምን መልሷል ። ይህ የሆነው ጎንደር ላይ ነው ።ስሁል ሚካኤል ንጉሱን በሻሽ አስንቆ ገድሎ ፤ ያፈረሰውን ማዕከላዊ መንግስት ፤ ጎንደር (ጎን እደር) ግንባሩን ለሃሩር እግሩን ለጠጠር ሰጥቶ ፤ የአዲሲቱን ኢትዮጵያ መሰረት እንደገና ከቴዎድሮስ ጋር ጥሏል ። ዛሬም እንደ ጥንቱ የአባቶቹን ሰንደቅ በክብር ወደቦታው መልሷል ። ታሳሪዎች ለጅብ እንዳይሰጡ ከጎናቸው ቆሟል ። በአድማ ምክንያት ድሆች እንዳይራቡ ያለውን አካፍሎ አብሮ በልቷል ። ይህን የመሰለ ማሕበራዊ ፍትህ ደግሞ የነገ ብሩህ ተስፋነት ጠቋሚ ምልክት ነው ። ለጎንደር ምን ይህ ብቻ ! ስንት የሚወሳ ታሪክ አለው መሰላችሁ ። የጨለማው ዘመን በሚባልበት ዘመን እንኳ ፤ በአገራችን ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በእውነተኛ ዲሞክራሲ በምርጫ ስልጣን የሰጠ ህዝብ ጎንደር ነው ። ይህን ታሪክ በሌላ ጊዜ እመለስበታለሁ ።
ዛሬ ታዲያ ፤ ኦሮሞዎችም አማራዎችም የደም ግብር እየከፈሉ ነው ። ወደ አንድነትም በመምጣት ፤ የነፃነታቸው መአዛ ፤ የት ላይ እንደሚገኝ ቀምሰው አውቀውታል ። ከእንግዲህ ይህ ትውልድ ጠመንጃ ያነሳ ዘንድ ተገዷል ። ጠመንጃ ካነሳ ደግሞ ፤ ለሴቶች ገዳዩ አጋዚ ፤ ህዝባዊ አጋዚ ይሆንበታል ፤ ያለርህራሄም እየጣለ ይወድቃል ። ህዝባዊ አመፁ በመላዋ ሃገሪቱ ተቀጣጥሎአል ። የተንበረከከ ፈሪ ነው ፤ የቆመ ደግሞ ለመተናነቅ ዝግጁ ነው ።ተንበርክኮ የነበረው ዛሬ ተነስቶ ቆሟል ።
እዚህ ላይ ለሚዲያዎች የማስተላልፈው አንድ መልእክት አለ ። ዜና ተገኘ ተብሎ ዝም ብሎ አይረጭም ። “ከትግራይ የተነሳ በሰላሳ ኡራል መኪና የተጫነ ወታደር ወደ ጎንደር እየተጓዘ ነው ። ወደ ባህርዳር የሚጓዝ ፤ ታንክና መትረየስ የጫኑ ወታደራዊ መኪናዎች በሸራ ተሸፍነው በጎሃ ፅዮን በኩል ታዩ ፤” ወዘተርፈ…… እየተባሉ የሚለቀቁ ዜናዎች ፤ የተነቃቃው ህዝባዊ እንቢተኝነት ላይ ቀዝቃዛ ሽብር መቸለስና ፤እንደግራኝ ዘመን ካህናት ትጥቅ አስፈቺና ጦር በታኝ ወሬ ስለሚሆን ፤ እየታሰበበት ቢለቀቅ መልካም ነው ። ሰዎች በዘመናት በራሳቸው ውስጥ ያዳበሩትንና ያሳደጉትን ፍርኃት አላቸው ። ዛሬ ከጨቋኞች መትረየስ ፊት ፤ ያለ ምንም ፍርኃት ፤ ለመብቱና ለነፃነቱ ሊተናነቅ ቀጥ ብሎ የቆመ ወጣት ተፈጥሯል ።
በዚህ ለነጻነቱና ለክብሩ በቆመ ነፃ ወጣት ስነልቡና ውስጥ ፤ በዜና ስም የራስን የፍርኃት ቆፈን እየሰነቀሩ ሊተናነቅ የቆመውን እንደገና እንዲምበረከክ ግፊት ማድረግ ፤ ተገቢ አይደለም ። ይህ አይነቱን የዜና አቀራረብ ወገን ነኝ በሚል ሚዲያ ማስተላለፍ ፤ ለጠላት ፕሮፓጋንዳ መሳሪያ መሆንን ያመጣል ። ጦርነቱ የጠመንጃ ብቻ ሳይሆን የፕሮፓጋንዳ ጭምር ነውና።
እየኖረ በየቀኑ ከመሞት ፤ ዛሬ ጥሎ መውደቅን የመረጠ ወጣት አለ ። ይህ ወጣት ደግሞ ፤ ጎረቤት አገሮችን አስጠልሉኝ ብሎ የሙጥኝ ተጠግቶ ሳይሆን ፤ በራሱ አገር በራሱ ምድር ላይ ፤ ቀጥ ብሎ ቆሟል ። በዚህ ቆራጥ በሆነ ፤ የዚህ ዘመን ትውልድ ላይ ፤ በልማድ የተገኘ ፍርኃት ቆፈን ማልበስ የማይሰረይ ሃጢያት ይሆናል ። በዚህ ለነፃነት ሲባል ፤ እየጣሉ የመውደቅ ዘመን ላይ ፤ ነጻነት ናፋቂ ሁሉ ፤ ስለ ነፃነት እንጂ ስለ ግል ግብና ስለድርጅት ፕሮፓጋንዳ ማሰብ ግምኛ ነው ።
ለዚህ ደግሞ ጎንደሮች የተከተሉት ፤ የትግል አቅጣጫ ፤ ጎንበስ ተብሎ እጅ ሊነሳው የሚገባ ታላቅ ተግባር ነው ። ትግሉ ገና “ሀ” ብሎ መሰረት ሲጥል ፤ አገዛዙ ሊለጥፍባቸው ከሚችለው ውንጀላዋች ፈውስ ይሆን ዘንድ ፤ ትግሉ ህዝባዊ ነው እዚሁ ተወልዶ እዚሁ ያደገ ነው ፤ ማንም ውጪ ያለ ድርጅት በኛ ስም መግለጫ እንዳያወጣ ፤ ሲሉ የባይረስ ማርከሻውን ፔኒሲለን ወግተው ነው ትግሉን የጀመሩት ። ቀጥለውም በአገሩ ምድር ላይ ቆሞ የሚሞተው ኦሮሞ ወጣት ደም የኛም ደም ነው አሉ ። ኦሮሞውም አፀፋውን በመመለስ ከአዳማ አስከ ነቀምቴ አልፎም እስከ ባሌ ሮቤ ድረስ የሚፈሰው የአማራ ደም የኔ ደም ነው አለ ። ዛሬ ሁሉም በተጠንቀቅ ዘብ ቆሟል ።
የጎንደር ወጣቶች ፤ ከእስረኞች ይፈቱ እስከ ስራ ማቆም አድማ የዘለቀ ትግላቸውን እየመሩ ያሉት ከነመፍትሄው ፤ ከነመድሃኒቱ እዚያው ጎንደር ውስጥ ነው ። ሁሉም ደግሞ ትግሉን እንደ ጎንደሮች ቢያቀናጅ የበለጠ ውጤት ሊገኝ ይችላል ። የጎንደር ወጣቶች ዛሬ ራሳቸውን በራሳቸው እያስተዳደሩ ነው ። ትግሉ የተናጠል እንዳይሆንም የኦሮሞና የአማራ ወጣቶች የግንኙነት መስመራቸውን ባስፈላጊው መንገድ ሁሉ ከትልቁ ፤ እስከትንሹ ዘዴ በመጠቀም አብሮ የመስራት ባህላቸውን ሊያዳብሩ ጊዜው የግድ ይላል ። ወጣቶች ይህ ቀረሽ የማይባል የፈጠራ ችሎታ እንዳላችሁ አሌ አይባልም ፤ ዘመኑ የናንተ ነውና ። ይህን ድንቅ የሆነ ዘመናችሁን በአንድነት በእጃችሁ አስገብታችሁ ራሳችሁ ተቆጣጠሩት ። አለበለዚያ የናንተ ወርቃማ ዘመን ለሌሎች ቁማር መጫወቻ ይሆናል ። ከፊታችሁ ታላቅ ሃላፊነት ተደግኗል ። ( በዚህ አጋጣሚ ፤የራሱን ዘመን በራሱ መንገድ ተቆጣጥሮ በትግራይ ተራሮች ታልቅ ገድል ስለፈፀመው ስለ አስራሰባት አመቱ ወጣት ስለአብቹ ታሪክ ደግሞ በሚቀጥለው ፅሁፌ አቀርብላችኋለሁ ። “አብቹ ነጋ ነጋ” ።)
መግቢያዬ ላይ ያስቀመጥኳቸው ጥያቄዎች አሉ ። ልድገማቸው ። ወጣቱ በራሱ ዘመን ፤ ሳይፈልገው በግድ የተጫነበት ማህበራዊና ፖለቲካዊ ችግር ውስጥ ገብቷል ። ፈለገውም አልፈለገውም የዘመናችን ወጣት ፤ የአገሪቱን አንድነት የመጠበቅ ፤ ብሎም ማህበራዊና ፖለቲካዊ ፍትህ ይመጣ ዘንድ መታገሉ አይቀሬ ይሆናል ። ታዲያ ይህ የዛሬው የኢትዮጵያ ወጣት ለዚህ ይበቃ ይሆን ? ወይስ የቀደሙት የዚያ ዘመን ወጣቶች የፈፀሙትን አይነት ስህተት ፈጽሞ ፤ የሱም ዘመን አገሪቱን ሌላ የችግር አዙሪት ውስጥ ከቷት ያልፍ ይሆን ?
የዛሬውን ወጣት ከትላንትናዎቹ ለየት የሚያደርገው የርእዮተ-አለም ቃልኪዳን እስረኛ አለመሆኑ ነው ። የዛሬው ወጣት ግብ አንድና አንድ ብቻ ነው ። ለራሱና ለህዝቡ ነጻነትና ፍትህን ማስፈን ብቻ ። እንዳያያዙ ፤ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ፍትህ ያሰፍናል የሚል ግምት አለኝ ። ትግሉ የነፃነት ነው ሲል ወጣቱ ፤ የነፃነት ብቻ ነው ። ነፃነት በራሱ ፍትህ ነው ። ነፃነት ሰላም ነው ። ነፃነት ፍቅር ነው ። ስለዚህም በአማራና በኦሮሞ ወጣቶች መካከል ፤ አገዛዙ አስፍኖት የነበረው የጥላቻ መጋረጃ ተቀዷል ። እንደገና የታደሰው የወጣቶቹ አንድነት በሃገራችን ላይ ፍትህ ሰላምና ፍቅር ያሰፍናል ። የሰው ልጆች ታሪክ እንደሚያሳየው ፤ ነጻነት ከምንም ነገር በላይ ጣፋጭ ናት ። ሆኖም ግን ዋጋ ታስከፍላለች ። የኦሮሞ ወጣት ላለፉት ዘጠኝ ወራት ለነጻነት ህይወቱን እየከፈለ ነው ። ጎንደር ከነብረቱ እምቢ ለነፃነቴ ብሎ ደሙን እየከፈለ ነው ። ጎጃም ከነድፍረቱ በባዶ እጁ ህይወቱን እየባጀ ነው ። ይህ የነጻነት ተጋድሎ በመላ አገሪቱ እየተቀጣተለ ነው ። እሳቱም ጨቋኞችን እየለበለበ ፤ እስከወዲያኛው ይዟቸው ይሄዳል ። እናት መሬትም ታብባለች ። ወጣቱ ለነጻነት የሚያደርገው ትግል ፤ ለወደፊቱ ትውልድ ፍንትው ብላ የምትታይ ከዘረኝነትና ከትምክህት የፀዳች ብሩህ ፤ መሪ ኮከብ ትሆንለታለች የሚል ተስፋ ሰንቄ ፤ የዛሬውን ፅሁፌን አበቃለሁ ።
በፅሁፉ ላይ አስተያየትም ሆነ ፤ ትችት ካላችሁ ፤ እነሆ የኢሜል አድራሻዬ [email protected] .
ላስ ቬጋስ ኒቫዳ
ኦገስት 20/2016 እ.ኤ. አ.