ማሞ ሌላ መታወቂያው ሌላ!


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


ከጋዜጠኛ ደምስ በለጠ

በቅርቡ የግንቦት ሰባት የውጪ ጉዳይ ግንኙነት ዋና ሹም ነአምን ዘለቀ ፤ የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ፤ ከ1991 ዓ.ም እ.ኤ.አ ጀምሮ ፤ የኤርትራው ሻእቢያዊ መንግስት ፤ በኤርትራ ህዝብ ላይ የሚፈፀመውን ኢ ሰብአዊ የመብት ረገጣ አስመልክቶ ፤ በኤርትራ ባለስልጣናት ላይ አለማቀፋዊ እርምጃ ይወሰድ ዘንድ አቅርቦት የነበረውን መጠይቅ በተመለከተ ፤ የድርጅታቸው አባላት የሆኑትንና ያልሆኑትን ኢትዮጵያውያን ሁሉ ፤ የመቃወሚያ ፊርማቸውን እንዲያስቀምጡ ጠይቀው ነበር ። “አርበኛው” ነአምን ዘለቀ ፤ ለወዳጃችን የሻእቢያ መንግስትና ባለስልጣናት ስንል ፤ የማንሆነው የለም በሚል መርህ ይመስላል ፤ የጉዳዩን አሳሳቢነት ለማስረገጥ ውሃ ባይቋጥርም ፤ ያልፈነቀሉት ድንጋይ ፤ ያላቀረቡት ሰበብ አልነበረም ።

ሰሞኑን ደግሞ የኸው የተባበሩት መግስታት ድርጅት ፤ ኤርትራ በህዝቧ ላይ የምትፈፅመውን የመብት ረገጣ አስመልክቶ የአፍሪካ ህብረት ፤ አቋም ይይዝ ዘንድ ጠይቋል ። እንደተለመደው ነአምን ዘለቀ ፤ ለወዳጃቸው ሻእቢያ ሲሉ ፤ “ከገሙ አይቀር ጥንብት” እንደሚባለው፤ ለአፍሪካ ህብረትም ፐቲሽን የማስፈረም ዘመቻቸውን ይጀምራሉ ተብሎም ይጠበቃል ። ይህን ካላደረጉ ደግሞ ፤ ራሳቸው “በደብል ስታንዳርድ” መታማታቸው የማይቀር ይሆናል ። አለበለዚያ ደግሞ የፐትሽኑ ፊርማ ፤ አቧራ ከማስነሳት ሌላ ፋይዳ እንዳልነበረው ማሳያ ከመሆን አይዘልም ። ሁሉንም በመቆየት እናየዋለን ፤ እያየነውም ነው ።

ወደ ዋናው ነጥቤ ልግባ ። “ኢሳኢያስ ሌላ መታወቂያቸው ሌላ ብየ ልጀምረው” ። ፕሬዚደንት ኢሳኢያስ አፈወርቂ የሚታወቁት ፤ የአሜሪካውን አምባሳደርና አገራቸውን ዩናይትድ ስቴትስን በአደባባይ በመዝለፍ ፤ የጣሊያኑን ኤምባሲ አንደኛ ፀኃፊ ከምፅዋ አስሮ አምጥቶ አስመራም በካቴና አስሮ ሁለት ቀናት አሳድሮ ከአገር ማባረር ፤ ብሎም የቀድሞውን የተባበሩት መንግስታት ፤ የመጀመሪያው አፍሪካዊ ፤ ዋና ፀኃፊ የነበሩትን ኮፊ አናንን ፤ በማዋረድ መዝለፍና በመሳሰሉት ድርጊቶቻቸው ነው ። የአለማችን ዲፕሎማሲያዊ መድረክና ሌሎች አለም አቀፍ ድርጅቶች ፤ ለእያንዳንዳቸው የአገር መሪዎች ፤ ደረጃና መለኪያ አላቸው ። ስለዚህም ኢሳኢያስ አፈወርቂን የዲፕሎማሲው ማሕበረ-ሰብ የሚመለከቷቸው ፤ ለአለም ህግ የማይገዙ ፤ ጋጠወጥ ፤ ባለጌና ስርአት አልባ የሃገር መሪ አድርጎ ነው ።

እነ ነአምን ደግሞ ስለ ኢሳኢያስ ሊያሳዩን የሚከጅሉት ስእል ለየት ያለነው ። መከራከሪያ ነጥቦቻቸው “ኢሳኢያስ ፤ ሌባ መሪ አይደሉም” ፤ “ኢሳኢያስ ሃገራቸውን ይወዳሉ” ፤ በዚህ ላይ “ለኛ ለግንቦቶች ብቸኛ ወዳጃችን ናቸው” ፤ የሚል ነው ። እነዚህን ነጥቦች በዝርዝር እመለስባቸዋለሁ ።

አለም አቀፉ ድርጅት ደግሞ ኢሳኢያስንና ባለስልጣኖቻቸውን ፤ እየከሰሰ ያለው ከላይ በተጠቀሱት ነጥቦች ላይ እንዳልሆነ ሊታወቅ ይገባል ።

ክርክራችን ሁሉ የባዶ ቆርቆሮ ጩኸት እንዳይሆን ፤ የክሶቹን አቢይ ጭብጦች ፤ ዝርዝር ውስጥ ሳልገባ በአጭሩ ላስቀምጥ ። አንደኛ የኤርትራው መሪና ባለስልጣናቱ የአገሪቱን ህዝብ በባርነት ስርአት ውስጥ በማማቀቅ ፤ ሁለተኛ በቶርቸር በማሰቃያት ፤ ሶስተኛ የእምነት ነፃነትን በመግፈፍ ፤ አራተኛ በአስገድዶ መድፈር ፤ አምስተኛ ህዝቡን እንዳሻው በመግደል ፤ ስድስተኛ ተጠያቂነት በሌለው ሁኔታ ህዝብን በገፍ በማሰርና ፤ ሰባተኛ ሌሎች ኢ-ሰብአዊ ድርጊቶችን መፈፀም ናቸው ።

ነአምንና ካምፓኒያቸው ግን የክርክራቸው ማጠንጠኛ ነጥቦች ፤ ከላይ የተጠቀሱት ክሶች አይደሉም ። ኢሳኢያስ አፈወርቂ አገራቸውን ይወዳሉ ነው የሚሉን ። አለም አቀፉ ድርጅት እኮ በኤርትራው ፕሬዝደንት ላይ የአገር ፍቅር ክስ አልመሰረተም ። ኢሳኢያስ ኤርትራን ቢወዱ ባይወዱ የራሳቸው ጉዳይ ነው ። የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ደግሞ አንድ መሪና ግብረአበሮቹ አገራቸውን ወደዱ አልወደዱ የሚከስበት ህግም ሆነ መለኪያ የለውም ። ፈፅሞም አያገባውም ። “ማሞ ሌላ መታወቂያው ሌላ” ።

ለማንኛውም ግን በአጭሩ የነነአምንን የመጀመሪያ መከራከሪያ ነጥብ ፤ በሰው ልጅ መለኪያ እንመልከተው ። አንድ መሪ አገሩን መውደዱን የምናይበት የቀን ተቀን ተግባራት አሉት ። አገሩን የሚወድ መሪ ፤ ህዝቡን በኑሮው አስመርሮ ለባሕር አሳ ሲሳይ አይዳርግም ፤ አገሩን የሚወድ መሪ የአገሪቱን ወጣቶች ህይወት ፤ የምድር ሲኦል አያደርግም ፤ አገሩን የሚወድ መሪ ፤ የህዝቡን ባህላዊና ሃይማኖታዊ እሴቶች አይንድም ። በሱዳን “ሸገራብ” በኢትዮጵያ “ሽመልባ” ወይም ህፃናትና እስከ አስራ ስምንት አመት ታዳጊዎችን የሚቀበለውን የUNHCR መጠለያ ጣቢያ “እንዳባጉናን” አስመልክቶ UNHCR የሚያወጣቸውን ሪፖርቶች መመልከት ኤርትራዊ ሁሉ የሚቀበለውን መከራ ለማሳየት በቂ ማርጋገጫዎች ናቸው ። ከአስመራ ጉዞዎቼ ባንዱ ላይ ለዚህ ማሳያ የሚሆን ገጠመኝ ተመልክቻለሁ ።

ፕሬዚደንት ኢሳኢያስ ለህዝባቸው ያላቸውን ፍቅር እንዲህ ነበር የገለፁት ። ከአገር ውስጥ ጋዜጠኛ ጋር ቃለ መጠይቅ ያደርጋሉ ። ጠያቂው “የኤርትራ ወጣቶች በድንበር እየወጡ በብዛት እየተሰደዱ ነው” በዚህ ላይ ምን አስተያየት አለዎ ? ሲል ጥያቄውን ያቀርባል ። የኢሳኢያስ መልስ ፤ “ድሮስ ቢሆን “ድርብ ጥርስ ፡ አያምር ወይ አይነክስ” በራሱ ወልቆ ከሄደልህ እፎይ ነው”፤ ነበር ያሉት ። ይህ ነው እንግዲህ አገር መውደድ ? የራሱ ህዝብ ላይ እንዲህ የመረረ ንቀት ያለው ሰው ነው አገሩን የሚወድ ? ታዲያ እንግዲህ ፤ እነ ነአምን የኢሳኢያስን አገራቸውን መውደድ በምን ለክተውት ይሆን ?

ግንቦቶች ሁለተኛው መከራከሪያ ነጥባቸውን ሲያቀርቡ ፤ “ኢሳኢያስ ሌባ መሪ አይደሉም” ፤ ይሉናል ። የሰባዊ መብት ተሟጋቹ ኮሚሽን ኢሳኢያስን በስርቆት አልከሰሰም ። ያም ሆኖ ግን ፤ አንድ መሪ ሰረቀ ወይም አልሰረቀም የሚባለው ፤ በአገሪቱ ህግና ስርአት ውስጥ ሃላፊነትና ተጠያቂነት ሲኖር ነው ። ይህ በሌለበት ሁኔታ እንዴት ተደርጎ ነው ሰርቋል ወይም አልሰረቀም ሊባል የሚችለው ? ለኢሳኢያስና ባለስልጣኖቻቸው ፤ አገሪቷ ኤርትራም ሆነች ህዝቧ ፤ የግል ንብረቶቻቸው ናቸው ። በአገሪቱ ላይ ሰፍኖ ያለው ፤ የወታደር መሳፍንት አገዛዝ ሲሆን ፤ ኤርትራ በ5 ስሪቶች ተከፍላ በአምስት ጀነራሎች ትመራለች ። እንደዘመነ-መሳፍንት ዘመን ፤ አምስቱ ጀነራሎች በግዛቶቻቸው ላይ ምንም ተጠያቂነት የለባቸውም ። እንደልባቸው ያሻቸውን የማድራግ መብቶች አሏቸው ። ጀነራሎቹ የየራሳቸው እስር ቤቶች ፤ መመርመሪያ ጣቢያዎችና ፤ በጀት ሲኖራቸው ፤ ልባቸው በፈቀደ የኤርትራን ህዝብ እንዳሻቸው ይነዱታል ።

ሌላ ቦታ ሄደን ፤ እገሌ ሌባ ነው ወይም አይደለም ከማለታችን በፊት ፤ ትንሽም ይሁን ትልቅ ድርጅት ገንዘብን አስመልክቶ ፤ የሃላፊነትና የተጠያቂነት ባህል ሊኖረው ይገባል ። ግንቦት ሰባትና ኢሳት ከህዝብ የሰበሰቡትንና የሚሰብስቡትን ገንዘብ ፤ ከተቋቋሙ ጀምረው አስቆጥረው ያውቃሉን ? የዋሁን ህዝብ እንተወውና ሌላው ቢቀር ፤ ግንቦትና ኢሳት ስለገንዘብ አውጣጥና አያያዛቸው ለአባሎቻቸው ይፋ አድርገው አሳይተዋልን ? በምን የሞራል የበላይነት ነው ፤ አto ነአምን እገሌ ሌባ ነው ወይም አይደለም ፤ ይሰርቃል ወይም አይሰርቅም የሚል ጥያቄ ሊያነሱ የሚችሉት ?

እነ ኢሳኢያስም የሻእቢያን ሃብት አለማስቆጠር የጀመሩት ገና በጧቱ “ሀ” ብለው ትግላቸውን ሲጀምሩ ነው ፤ “ከአህያ የዋለች እንደሚባለው……” ይኽው ልክ ግንቦት ሰባትና ኢሳትም ፤ ዛሬ በሰለጠነው በሃያ አንደኛው ዘመን ላይ እየኖሩ ፤ የሻእቢያን ፈለግ በመከተል ፤ ወጪና ገቢያቸው በታቦት ጨርቅ ተሸፍኖ ቁጭ ብሏል ። ስለዚህ ኢሳኢያስ ሌባ ነው ወይም አይደለም ለማለት ግልፅነትና ተጠያቂነት ሊኖር ይገባል ።

ሌላውና ሶስተኛው መከራከሪያቸው ላይ ልምጣ ። ለአርበኞች ግንቦት ሰባት “ብቸኛ ወዳጆቻችን ኢሳኢያስና ባለስልጣኖቻቸው ናቸው” የሚል ነው ። ታዲያ ምን ይጠበስ ። ሻእቢያና መሪዎቹ የናንተ ወዳጆች ስለሆኑ አለም አቀፉ ድርጅት ፤ በሰዎች ላይ የሚደርሰውን መከራ አይቶ እንዳላየ መሆን ነበረበት ? ምንም እንኳ ዛሬ ፤ ወደ አሜሪካ ኑሯቸው የተመለሱ ቢሆኑም ፤ አምና ፊሽካው ሲነፋ ከአሜሪካ የሄዱትን አርበኞች ፤ ኢሳኢያስና ባለስልጣናቱ ስላስጠለሏቸው ፤ የኤርትራ ህዝብ ላይ የሚደርሰውን መከራ አለም አቀፉ ድርጅት አይቶ እንዳላየ ማለፍ ነበረበት ? ለናንተ ሲባል የኤርትራ ህዝብ በባርነት መገዛት አለበት?

አንዴ በአስመራ ነዋሪ ላይ የተጣለ ቅጣት ትዝ ይለኛል ። ጊዜው 2011 እ.አ.አ. ነው ። አስመራ ከተማ ላይ የሚላስ የሚቀመሰ እህል ጠፋ ። ከገጠር ወደ ከተማ የሚገባ ማንኛውም አይነት የእህልም ሆነ የጥራጥሬ ዘር በከተማ መውጫና መግቢያ ላይ ከህዝቡ ተወረሰ ። አላማው ባይታወቅና ፤ የአስመራ ነዋሪ እስካሁን መልስ ባያገኝለትም ፤ የከተማው ህዝብ በረሃብ እንዲቆላ ተደርጓል ። ይህ የሆነው ደግሞ በፕሬዚደንት ኢሳኢያስ ትአዛዝ ነበር ። የሰው ልጅ የመጀመሪያው ጥያቄ ደግሞ ምግብ ነው ። ህዝቡ ይህን በመሰለ ረሃብ እየተቀጣ የመኖር ዋስትናው ተገፎ ፤ ሰባዊ መብቱ ተደፍጥጧል ።

ይህን በተመለከተ ፤ ከምፅዋ በህዝብ ማመላለሻ አውቶቡስ ተሳፍሬ ወደ አስመራ ስመለስ ፤ ያጋጠመኝንና አንዲት ሴት ያደረጉትን ላውጋችሁ ። ነፋሲት ላይ ተሳፈሩ ። እንደገቡ ሴትዮዋ ሁሉንም ሰው በተለማማጭ አይኖቻቸው በንቃት ይመለከታሉ ። በኋላ ላይ እንደነገሩን ፤ የአስመራ ከተማ ነዋሪ ናቸው ፤ ነፋሲት አካባቢ ካለ ገጠር ዘመዶቻቸውን ጥየቃ ሄደው እየተመለሱ ነበር ። በግምት እያንዳንዳቸው ከሶስት ወይም ከአራት ኪሎ የማይበልጡ ሁለት ቋጠሮዎች በነጠላዎቻቸው ጫፎች ላይ አስረው በመቀመጫቸው ጀርባ ግራና ቀኝ ፤ ደብቀው አስቀመጡ ። የነፋሲትን ኬላ እንዴት እንዳለፉት ባላውቅም ፤ ቋጠሮዎቻቸው አስመራ ከተማ መግቢያ ላይ ተያዙባቸው ። የኬላው ፈታሽ ከሻእቢያ መንግስት የተሰጠውን ትእዛዝ ለማስፈፀም ቸኮለ ። የያዙትን የእህል ቋጠሯቸውን ፈትተው ለመንግስት ያስረክቡ ዘንድ ወተወተ ። ሴትዮዋ ልጄ “መአረይ” እባክህ ተውልኝ ። አራስ ልጅ እቤቴ ተኝታለች ከወለደች ገና ሳምንቷ ነው ። የሚላስ የሚቀመስ በቤቴ የለኝም እያሉ በገባኝም ባልገባኝም ትግርኛ ለመኑ ።

የኬላው ፈታሽ ፤ ወይ ፍንክች ያአባ ቢላዋ ልጅ ፤ ቋጠሮውን ያስረክቡ ብሎ ደረቀ ። ሴትዮዋ እህሉን ለማስረከብ ከአውቶቡሱ ወረዱ ። መሬት ላይ ቁጢጥ ብለው ተቀምጠው ሁለቱንም ቋጠሮዎቻቸውን ፈቷቸው ። በድንገት ብድግ አሉና ሁለቱንም የኩታቸውን ጫፎች ይዘው ፤ እህሉን ወደላይ በተኑት ። አብዛኛው እህል አንድ ቦታ መሬት ላይ ተዘረገፈ ። ላንተ ከማስረክብ ለወፎች ሰጥቼ ብፀድቅ ይሻለኛል አሉ ። መሬቱ ላይ የተዘረገፈውን እህል በእግራቸው በታተኑትና ወደ አውቶቡሱ ገቡ ። ሴትዮዋ ይህን ያደርጋሉ ብሎ የጠበቀ ባለመኖሩ ፤ አውቶቡሱ ውስጥ ያልነበረ ፀጥታ ሰፈነ ። የሁሉም ሰው አይኖች ሴትዮዋ ላይ አተኮሩ ። ሴትዮዋ ወደ አውቶቡሱ ሲገቡ ፊታቸው ላይ መረጋጋት ይታይ ነበር ። ፈታሾቹም ግራ ተጋብተው ተነጋገሩና ፤ አውቶቡሱ ቶሎ እንዲሄድ አደረጉ ። እኛም አስመራ ገባን ።

ይህ ከሆነ ከጥቂት ቀናት በኋላ ፤ የተለመደው ጋዜጠኛ ፕሬዚደንት ኢሳኢያስን የአገሪቱን ሁኔታ አስመልክቶ ጥያቄ ይጠይቃል ። ከጥያቄው መካከል አንዱ ፤ እህል ከገጠር እንዳይገባ የተደረገበት ጉዳይ ነበር ። ፕሬዚደንት ኢሳኢያስ ለክልከላው መልስ ከመስጠት ይልቅ እንዲህ በማለት ነበር የመለሱት ። ‘የአስመራ ሰዎች እንዴት አድርጋችሁ እህል ወደ አስመራ እንደምታስገቡ አውቃለሁ ። በጥሬ እህል ብንከለክላችሁ በወተት ላስቲክ እያደረጋችሁ በሊጥ መልክ እህል እንደምታስገቡ አውቃለሁ” ሲሉ ተናገሩ ። አሿፊው የአስመራ ሰው ሰውየው ኩሽና ገባ ብሎ አሾፈ ። ድኻው ደግሞ መፃኢው ኑሮና ተስፋው በምናቡ እየታየው ልቡን ሽብር ሞላው ። ምነው ይህ ህዝብ ከዚህ የማይሻል የለም ብሎ አይሰደድ ?

የኤርትራ ህዝብ እየተቀጣ ያለው በተለያየ መልኩ ነው ። ስለዚህ ሻእቢያ ፤ ለኔ ወዳጄ ነው ተብሎ ፤ የኤርትራ ህዝብ መከራ አይደፈጠጥም ። የኤርትራ ህዝብ ዛሬ መናገር ባይችልም ይታዘባል ።

ይህን የፐቲሽን ፊርማ አስመልክቶ የተለያዩ ሰዎች የተለያየ አስተያየቶቻቸውን ሰንዝረዋል ። ከነዚህ ውስጥ አንዱ መሳይ ከበደ ናቸው ። መሳይ ከበደ እነ ነአምን ዘለቀ ያቀረቡትን ፐቲሽን ለምን እንዳልፈረሙ ምክንያታቸውን በሞራል ጥያቄ አስታከው ፤ መደረግ የነበረበትን ሲመክሩ እንዲህ ይላሉ ።

አለም አቀፉ ድርጅት በኤርትራ ላይ ከማተኮር ይልቅ የኢትዮጵያ መንግስት ላይ ተመሳሳይ ክስ ማቅረብ ነበረበት ባይ ናቸው ። እንዴት ነው ነገሩ ዶ/ር መሳይ ? ዓለም አቀፉ ድርጅት ፤ ርስዎ ለኢትዮጵያውያን መልክትዎን ማስተላለፍ በሚወዱበት በእንግሊዝኛ ቋንቋ በነጭ ወረቀት ላይ በጥቁር ቀለም ያሰፈረው መጠይቅ የሚለው ፤ “የኤርትራ መንግስት ፤ ወደኤርትራ ገብተን ፤ ምርመራችንን እንድናካሂድ ባለመፍቀዱ በ20 አገራት ውስጥ በስደት የሚኖሩ 42ሺህ ኤርትራውያንን አነጋግረን ባገኘነው መረጃ ላይ ተመርኩዘን ያወጣነው ሪፖርት ነው” ሲል አስረግጦ አስቀምጧል ።

ታዲያ ኮሚሽኑ በኤርትራውያኑ ላይ ያደረገውን ቃለ መጠይቅና ምርመራ ፤ ተመርኩዞ እንዴት የኢትዮጵያን መንግስት መክሰስ ይችላል ? “ማሞ ሌላ መታወቂያው ሌላ” ። አማርኛዬ ካልገባዎት በእንግሊዝኛ አስተርጉመው ያንብቡት ። ይህን ስል ታዲያ የኢትዮጵያ መንግስት የሰባዊ መብት ችግር የለበትም እያልኩ እንዳልሆነ ይታወቅልኝ ።

ፅሁፍዎ እንደሚያስረዳው ፤ አንዱ መልእክትዎ እኔ ይህን ፐትሽን አልፈረምኩም የሚል ነው ። ጥሩ አደርገዋል ፤ በኢሳኢያስ ዳፋ ለምን የእርስዎ ስም ይቆሽሽ ። ያም ሆኖ ግን ፤ እርስዎ ፐቲሽኑን ፈረሙ አልፈረሙ የሚኖርዎ ድምፅ አንድ ብቻ ነው ። ስለዚህ ቋቱን አይሞላውም ወይ አይቀንሰውም ። ከዛሬ ሁለት ሺህ አመት በፊት ፤ ጲላጦስ ይሁዳውያኑ ፊት የተጠቀመበትን “አራድነት” ተጠቅመው የኢትዮጵያ መንግስት ለምን አልተከሰሰም በሚል ሰበብ ፤ ከታሪክ ተጠያቂነት ውልቅ ማለትዎን ደግሞ ፤ ታላቅ ጥበብ እንደሆነ ሳላደንቅልዎ ለማለፍ አልፈለኩም ።

የኤርትራ መንግስት ባለስልጣናት በሰብአዊ መብት ረገጣ መከሰሳቸውን አስመልክቶ ፍትህ ተዘናበለ ፤ ፍርድ ተገመደለ ሲሉ አስተያየታቸውን የሰጡት ሌላው ሰው ሻለቃ ዳዊት ወ/ጊዮርጊስ ናቸው ።

ኤርትራ ነፃነቷን ከማግኘቷ በፊት ጀምሮ ፤ በሻእቢያ ወዳጅነታቸው በሚታወቁት ሻለቃ ትንተና ፤ ግዙፏና ቱጃሯ ሳውዲት አረብ “በወሃቢ” ምንጭነት ሳትጠየቅ ፤ ብሎም በየመንና በአገሯ ውስጥ፤ በውጪ ዜጎች ላይ ለምታደርሰው ሰብአዊ መብት ጥሰት ሳትከሰስ ፤ ሚጢጢዋ ኤርትራ ተከሰሰች የሚል ጉዳይ ላይ ያጠነጠነ ነው ። ስለዚህም የተባበሩት መንግስታት ሰብአዊ መብት ኮሚሽን በኤርትራ ባለስልጣናት ላይ ያቀረበው ክስ ፍትህ የጎደለው ነው ይላሉ ። ከሻለቃው ፅሁፍ ያልገባኝ ጉዳይ ፤ የኤርትራ ባለስልጣናት በህዝባቸው ላይ ላደረሱት ሰብአዊ መብት ረገጣ ፤ ግድያ ፤ ቶርችርና ፤ አስገድዶ መድፈር ፤ ሳውዲት አረብ እስክትጠየቅ ድረስ በፍፁም አይነሳ ነው? ወይስ የኤርትራ ባለስልጣናት እንደ ሳውዲት አረብ ጉቦ እየከፈሉ ከሰባዊ መብት ረገጣ መዝገብ ላይ ስማቸውን ያስፍቁ ነው ነገሩ ። ስለ 400 ሽዎቹ በባርነት ደረጃ እየማቀቁ ስላሉት የኤርትራ ዜጎች ፤ ሴቶች ልጆቹ ያለፈቃዳቸው በኤርትራ ከፍተኛ የጦርና የሲቪል ባለስልጣናት ስለሚደፈሩበት ሰላማዊ ዜጎች ግን ትንፍሽ ያሉት ነገር የለም ።

ለእርስዎና ለወዳጆችዎ ለግንቦት ሰባት ድርጅት ፤ ሻእቢያ ምሽግ እስከሆነ ድረስ ፤ የኤርትራ ህዝብ የግፍና የመከራ ቀንበር እንደተሸከመ ይኑር ? የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ሪፖርቱን ያቀረበው በነዚህ ነጥቦች ላይ ሆኖ ሳለ ሻለቃ ዳዊት እየነገሩን ያለው ስለሳውዲት አረብ ነው ። ሻለቃ ፤ እዚህ ላይ ነው እንግዲህ “ማሞ ሌላ መታወቂያው ሌላ” የሚባለው ።

ይህን አጋጣሚ ተጠቅሜ ፤ አንድ ጥያቄ ሻለቃውን መጠየቅ እፈልጋለሁ ። ይህ ፤ ሁሌ ፅሁፍዎ ስር የሚያስቀምጡት “Institute for strategic and Security Studies” የሚባለው መስሪያ ቤት ፤ የኤርትራ ፤ የግብፅ ፤ የሳውዲ ወይስ የሴኔጋል ነው ? የዩናይትድ ስቴትስ ኦፍ አሜሪካ ከሆነ ደግሞ እንደዚያ መጠቀስ ነበረበት ብዬ ነው ። ይህቺን መስሪያ ቤት እንደርስዎ ሁሉ አንድ ሌላ የቀድሞው የደርግ መንግስት ባለስልጣን ሲጠቀምባት በማየቴ ፤ የቀድሞ የደርግ ባለስልጣናት ምሽግ መስላኝ ነውና አደራዎን ያብራሩልኝ ። የአሜሪካ ከሆነች ደግሞ የአሜሪካ ብለው ይግለጿት ። ካልሆነችም የማን መሆኗን ይንገሩን ።

የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ተሟጋች 47 አገሮች ያሉበት አካል በኮንሰንሱስ ያስተላለፈውን ውሳኔ ተመርኩዞ ፤ የአፍሪካ ህብረትም የራሱን ምርመራ አድርጎ በሰባዊ መብት ረገጣ ተጠያቂ የሆኑትን የኤርትራ ባለስልጣናት ለይቶ በማውጣት ለፍርድ ያቀርብ ዘንድ ፤ ጥያቄ ቀርቦለታል ።

ግንቦት ሰባትና ነአምን ዘለቀ ለተባበሩት መንግስታት እንዳዘጋጁት ሁሉ ፤ ለአፍሪካ ህብረትም ሌላ ፐትሽን እንደሚያዘጋጁ በመተማመን ፤ የዚያ ሰው ይበለን እያልኩ ፤ በዚያ ሁኔታ ላይ አስከምንገናኝ በዚሁ ልሰናበታችሁ ።

ጁላይ 4 ቀን 2016 እ.ኤ.አ
ላስ ቬጋስ ፤ ኒቫዳ