የወልቃይት አማሮች ወደ ሚታረዱበት ቄራ «ሂዱ» ሲባሉ ዝም ብለን ልናይ ነው?


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


የወልቃይት አማሮች ወደ ሚታረዱበት ቄራ «ሂዱ» ሲባሉ ዝም ብለን ልናይ ነው?

በአለም ታሪክ ውስጥ የማንነት ጥያቄ በህዝበ ውሳኔ የተፈታበት አገር ያለ አይመስለኝም። የእኔን ማንነት የሚነግረኝ ወያኔ የሚያስቆጥረው የልግጫ ህዝበ ውሳኔ ውጤት ሊሆን አይችልም። እስቲ አስቡት! በህዝበ ውሳኔ እንዲፈታ የተፈረደበት የወልቃይት አማሮች የማንነት ጥያቄ የኦሮምያ ክልልና የሶማሌ ክልል የተጣሉበት አይነት የግጦሽ መሬት የይገባኛል ጥያቄ ሆኖ ነው ማለት ነው? ወልቃይትኮ የማንነት ጥያቄ ያነሱ አማሮች የሚኖሩበት ምድር እንጅ እንደ አፋምቦ ሰው የማይኖርበት ምድረ በዳ የግጦሽ መሬት አይደለም።

የይገባኛል ጥያቄ የተነሳው በአማራና በትግራይ ክልል መስተዳድሮች መካከል ይመስል «የፌድሬሽን ምክር ቤት» የሚባለው የወያኔ ተቋም ወልቃይቶች ያነሱትን የማንነት ጥያቄ የትግራይና የአማራ ክልሎች ያነሱት የግጦሽ መሬት ይገባኛል ጥያቄ አድርጎ ተርጉሞታል። በርግጥ እንደዚህ ተደርጎ የተተረጎመበት አላማ ግልጽ ነው! አላማው ፈረንጆች እንደሚሉት «Referendum under the barrel of the gun» አካሂዶ የወልቃይቶችን ጥያቄ በህግ አግባብ ተፈታ በማስባል እንደ መቶ ፐርሰንቱ የቅርጫ ውጤት ወያኔ የሚፈልገውን በምስለኔዎቹ አስፈጽሞ የወልቃይቶችን ጥያቄ እስከመጨረሻው አዳፍኖ እነሱንም እስከወዲያኛው ለማጥፋት ነው።

የሚገርመው ደግሞ «አማራ» የሆነ አፈ ጉባኤ ያለው «የፌድሬሽን ምክር ቤት» የሚባለው ተቋም የወልቃይት አማሮችን ጉዳይ እንዲፈታ የመረጠው አካል አማራን በመጥላት ክብረ ወሰን የተቀዳጀውን የትግራይ ክልል አስተዳደር መሆኑ ነው። ወልቃይቶች ግን ጥያቄያቸው አማራ ነን የሚል ነው።

«በህገ አራዊቱ» መሰረት የወልቃይቶች ጥያቄ ወደ ትግራይ ክልል መላክ የነበረበት ጥያቄው ክልሉን ዘልሎ ወደ ፌድሬሽን ምክር ቤት የቀረበ ቢሆን ኖሮ ነበር። ሁላችንም እንደምናውቀው የወልቃይት የማንነት ጥያቄ ለትግራይ ክልል ከአገር በፊት ቀርቦለት ነበር። ነገር ግን የክልሉ መስተዳደር ከህግ በላይ የሆኑ ባለጊዜዎች ባድማ ስለሆነ የአማራ ማንነት ጥያቄያቸውን እንዲፈታላቸው ያቀረቡትን ወልቃይቶች «አይናችሁን እንዳላየው» ብሎ በውሻ አባሯቸዋል። ይህንን የሚያውቀው «የፌድሬሽን ምክር ቤት» ተብዮው የወያኔ የፖለቲካ ጉዳዮች ማስፈጸሚያ ተቋም የአማሮችን የማንነት ጥያቄ እንዲፈታ የባለጊዜዎችን ክልል በድጋሜ ጠይቆታል። ይህ ጆርጅ ኦርዌል «ሁሉም እንስሳ እኩል ነበሩ አሁን ግን ሁሉም እንስሳ እኩል ቢኾኑም ጥቂት እንስሶች ግን ከሌሎቹ ይልቅ የበለጠ እኩል ናቸው» ያለው አይነት መሆኑ ነው።

እስቲ የፌድሬሽን ምክር ቤቱ የወልቃይቶችን ጉዳይ እንዲፈታ ደብዳቤ የጻፈለት የትግራይ ክልል አስተዳደር የማንነት ጥያቄ ስላነሱ የወልቃይት አማሮች ምን ሲል ነው የከረመው? «ትግስታችን አልቋል፤ ከእንግዲህ በኋላ የማያዳግም እርምጃ እንወስዳለን» ሲል አይደለም የሰነበተው? በተግባርስ በመቶዎች የሚቆጠሩ የወልቃይት አማሮችን ሲያስርና ሲያሳድድ እንዲሁም ደብዛቸውን ሲያጠፋ አይደለም የባጀው? ይሄው ዛሬ የማንነት ጥያቄ አነሳህ ተብሎ ሊላይ ብርሀኔ ፍርድ ቤት እየተጎተተ በእስር እየተሰቃዬ አይደለምን? እና የማንነት ጥያቄውን ወንጀል አድርጎ የማንነት ጥያቄ ያነሱ ሰዎችን ሲገድልና ሲያስር የሰነበተው ክልል እንዴት አድርጎ የማንነት ጥያቄያቸውን ሊፈታ ይችላል? የፌድሬሽን ምክር ቤት ወልቃይቶች የማንነት ጥያቄያቸውን ለትግራይ ክልል አቅርበው «አይናችሁን እንዳላይ» ብሎ በውሻ እንዳባረራቸው አልሰማም ይሆን? ወልቃይቶች ለምክር ቤቱ ባስገቡት ማመልካቻ ላይስ ስለዚህ የጻፉትን ምክር ቤቱ አላነበበውም? ህግ እንዳለ ለማስመሰል ለትግራይ ክልል የለበጣ ደብዳቤ ሲጽፍ «አይናችሁን እንዳላይ» ብሎ ወልቃይቶችን ያባረረውን ክልል በድጋሜ የማንነት ጥያቄውን ፍታ ብሎ መጠየቁ ግን የህግ ጥሰት መሆኑን የተገነዘበ አይመስልም።

ለኔ እንደሚታየኝ የአማራ ማንነት ጥያቄ ያነሱ ሰዎችን ሲገድል፣ ሲያሳድድና ሲያስር የከረመው የትግራይ ክልል አስተዳደር የአማራ ማንነት ጥያቄን የሚመልሰው የአማራ ማንነት ጥያቄ ያነሱ አማሮችን ገድሎ በመጨረስ ጠያቂዎቹን በማጥፋት ብቻ ነው። የአማራ ማንነት ጥያቄ ያነሱ ሰዎችን ሲገድል፣ ሲያሳድድና ሲያስር የከረመ ክልል የወልቃይት አማሮችን የማንነት ጥያቄ ፍታ ብሎ የፌድሬሽን ምክር ቤት የለበጣ ደብዳዴ ስለጻፈለት የወልቃይት አማሮች የማንነት ጥያቄ በህጋዊ መንገድ ሊፈታ ይችላል ብሎ የሚያስብ ጅል የለም። የትግራይ ክልል የአማራን ጉዳይ በህጋዊ መንገድ የሚፈታ ቢሆን ኖሮ ቀድሞውኑ ጥያቄው ቀርቦለት «እንዳላያችሁ ከፊቴ ጥፉ» አይላቸውም ነበር። ከሁሉ አስቀድሞም ተከዜን ተሻግሮ ጎንደርን በወረራ አይዝም ነበር።

«ትግስታችን አልቋል፤ ከእንግዲህ የማያዳግም እርምጃ እንወስዳለን» እያለ ሲዝትባቸው ለነበሩ የወይቃይት አማሮች የፌድሬሽን ምክር ቤት ተብዮው «የማንነት ጥያቄያችሁን ሒዱና የትግራይ ክልል ይፍታላችሁ» ሲል መወሰኑ የወልቃይት አማሮችን ወደ አራጃቸሁ ቤት ሂዱ ብሎ ማዘዙ አልታየው ብሎ ይሆን? በአደባባይ ትዕግስቱ እንዳለቀ ሲናገር የከረመው ክልል ዛሬ ምን ትዕግስት አግኝቶ ነው የወልቃይቶችን የማንነት ጥያቄ በጥሞና እንዲፈታ የተጠየቀው?

በርግጥ የፌድሬሽን ምክር ቤቱን ውሳኔ የትግራይ ክልል ይፈልገዋል። ለምን ቢባል ያለህግ ሊያርዳቸው ሲፈልጋቸው የነበሩትን አማሮችን በህግ ሽፋን እንዲያርዳቸው ወደ ቄራው ሰተት ብለው እንዲሄዱለት ምክር ቤቱ የጻፈው ደብዳቤ ያዝዛልና። ካሁን በኋላ የትግራይ ክልል እንደ ፋሲካ በግ ወደሚታረዱበት ቄራ ሂዱ ተብለው የሚሄዱለትን አማሮች ጭካኔው እስኪያረካለት፤ ጥላቻው እስኪሽርለትና ከምድረ ገጽ እንኪጠፉ ድረስ «ኣሻ አምሀራይ» እያለ ስጋቸውን በመዘልፈል ይረፈርፋቸዋል። የፌድሬሽን ምክር ቤቱ ደብዳቤ ህጋዊ ያደረገው ነገር ቢኖር የወልቃይቶቹን የማንነት ጥያቄ ተገቢነት ማንበር ሳይሆን በህግ እንዲታረዱ ተላልፈው መሰጠታቸውን ነው።

የፌድሬሽን ምክር ቤቱ የማንነት ጥያቄን የማንነት ጥያቄ ካነሱ ሰዎች እጅ አውጥቶ የማንነት ጥያቄውን የባለቤትነት ጥያቄ ያላነሱ የሁለት ክልሎች የአስተዳደር ይገባኛል ጥያቄ አድርጎ የመለወጥ ስልጣን ማነው የሰጠው? የፌድሬሽን ምክር ቤቱ የወልቃይት አማሮችን የማንነት ጥያቄ ከተቀበለ ለምን የማንነት ጥያቄያቸውን ጥያቄ ያላነሱ የሁለት ክልሎች የአስተዳደር ይገባኛል ጥያቄ አድርጎ ሊተረጉመው ፈለገ? «ትግስቴ አልቋል፤ ከእንግዲህ የማያዳግም እርምጃ እወስዳለሁ» እያለ ሲዝት የነበረው የትግራይ ክልል ከሁሉ አስቀድሞ የማንነት ጥያቄው ቀርቦለት ያልፈታውን አሁን የፌድሬሽን ምክር ቤቱ የወልቃይቶችን የማንነት ጥያቄ እንዲፈታ የለበጣ ደብዳቤ ስለጻፈለት የወልቃይቶችን የማንነት ጥያቄ ሊፈታ ይችላልን? ቀርቦለት የገፋውን ጥያቄስ እንደገና እንዲመለከተው መጠየቁ ፌድሬሽን ምክር ቤቱ እተዳደርበታለሁ የሚለውን ህግ ጥርስ የሚያፈግፍና ፍርደ ገምድል ውሳኔ አይደለምን?

ሌላው ሁሉ ይቅርና «አማራ ነን» ያሉ የወልቃይቶች ጥያቄስ የሚፈታው የትግራይ ክልል ብቻ ነው? አማራ ክልል የሚባለው አስተዳደር የወልቃይት አማሮች የማንነት ጥያቄ ጉዳይ አይመለከተውም ማለት ነው? የፌድሬሽን ምክር ቤት የማንነት ጥያቄውን የባለቤትነት ጥያቄ ያላነሱ የሁለት ክልሎች የአስተዳደር ይገባኛል ጥያቄ አድርጎ ከተረጎመው በኋላስ መፍትሔ መስጠት ያለበት አንዱ ክልል ብቻስ ነውን? ይሄ በእውነቱ አለም ሁሉ እያየ በአንድ ህዝብ ላይ እየተፈጸመ ያለ ጥቃትና በደል አይደለምን? ህግ ቢኖር ኖሮ የወልቃይት ጥያቄ የማንነት ጥያቄ እንጂ የሁለት ክልሎች የአስተዳደር ይገባኛል ጥያቄ አይደለም። በህጉ መሰረትን ይህንን መመለስ ያለበት ቀድሞ ጥያቄው ቀርቦለት አሻፈረኝ ያለው የትግራይ ክልል መስተዳደር ሳይሆን አቤቱታ የቀረበለት የፌድሬሽን ምክር ቤት ብቻ ነው።

በመጨረሻ ከወልቃይት ውጭ ያለው አማራ ዝም ያለው አማራ መሆኑን የሚነግረው የትግራይ ክልል መስተዳደር መሆኑን ሲሰማ አሜን ብሎ ተቀብሎ ለመኖር ተዘጋጅቷል ማለት ነው? የወልቃይቶች በአማራነት መገደላቸው የሁሉም የአማራ ሞት አይደለም? ያገባናል የምንል ሰዎችስ እስከመቼ ዝም ብለን እናያለን? ትግሬዎቹስ ቢሆኑ ወልቃይቶች አማራ ሆነው ወያኔ ትግሬ ናችሁ ስላላቸው ትግሬ ይሆናሉ ብለው ማሰባቸው ወደኋላ በልጆቻቸው ላይ ችግር እንደሚያመጣ አልታያቸውም ይሆን? በተለይ በተለይ እናንተ የተማራችሁ አማሮች የሆናችሁ፤ ወገኖቻችሁ ግዳያቸውን ሊጥል ሲመኝና ሲፈልግ ወደ ነበረው አራጃቸው እንዲሄዱ ሲታዘዙ፤ አይናችሁ እያየ የናንተው ወንድሞች እንደፋሲካ በግ ወደሚታረዱበት ቄራ ሂዱ ሲባሉ ዝም ብላችሁ እስከመቼ ታያላችሁ? የት ነው ያላችሁት? አገር ሲጠብቁ የኖሩት የወልቃይት አማሮች አንደ ፋሲካ ሰንጋ ወደ እርድ ቦታ ሊጓዙ መሆናቸውን አልሰማችሁም ይሆን?

Achamyeleh Tamiru's photo.