ሚኒስትሩ የሚመሩትን መ/ቤት የመንግስት ሕንጻ ከነበረበት አስለቅቀው የራሳቸው የግል ሕንጻ እንዲከራይ አደረጉት::

[ሙስና እና ሽሙጥ = ክቡር ሚኒስትሩ አማካሪያቸውን አስጠሩት]
–    እየተከታተልክ ነው ለመሆኑ?
–    ምኑን ክቡር ሚኒስትር?
–    ቴሌቪዥን ነዋ፡፡
–    በሚገባ ክቡር ሚኒስትር፡፡
–    ምን አሰብክ ታዲያ?
–    በጣም አስፈሪ ነገር ነው፡፡
–    ምኑ ነው የሚያስፈራው?
–    ትራምፕ ነዋ፡፡
–    ትራኩ ነው ያልከኝ?
–    የአሜሪካኑ ትራምፕ ነው ያስጨነቀኝ ስልዎት፡፡
–    እኔ ደግሞ የዩሮ ትራኩ ጉዳይ ነው የሚያስጨንቀኝ፡፡
–    እኔ እኮ ወሬ ብቻ ይመስለኝ ነበር፡፡
–    ምኑ?
–    ክቡር ሚኒስትሩ ዩሮ ትራከር አላቸው ሲባል፡፡
–    ቢኖረኝ ምን ችግር አለው?
–    ያው ከየት ያመጡታል ብዬ ነው?
–    ከብዙ ቦታ ላመጣው እችላለሁ፡፡
–    ለነገሩ እርስዎ ብዙ ቦታ እንዳለዎት አውቃለሁ፡፡
–    ምን አልክ አንተ?
–    ማለቴ ሊያመጡበት የሚችሉበት ብዙ አቅም አለዎት ብዬ ነው፡፡
–    ዛሬ የፈለኩህ እንዴት አየኸው ልልህ ነው?
–    ምኑን ክቡር ሚኒስትር?
–    የሰሞኑን የጠቅላይ ሚኒስትሩን ንግግር፡፡
–    በቴሌቪዥን ነዋ፡፡
–    ቀልዱን ተውና ቁምነገሩን አስቀድም፡፡
–    ሰው በጣም ተገርሟል ክቡር ሚኒስትር፡፡
–    በምኑ ነው የተገረመው?
–    ኢሕአዴግ ለመጀመሪያ ጊዜ ጥፋቱን በማመኑ ነዋ፡፡
–    ይኼ ምኑ ነው የሚያስገርመው?
–    ለመጀመሪያ ጊዜ ጥፋቱን ማመኑ ነዋ፡፡
–    እስከዛሬ አምኖ አያውቅም?
–    አዎና ክቡር ሚኒስትር፡፡
–    ለምን አምኖ እንደማያውቅ ታውቃለህ?
–    አላውቅም፡፡
–    አጥፍቶ ስለማያውቅ ነዋ፡፡
–    ምን አሉኝ?
–    አጥፍቶ አያውቅም፡፡
–    ለነገሩ አጥፍቶ የሚያውቀው ሌላ ነገር ነው፡፡
–    ምን?
–    መብራት፡፡
–    እ…
–    ውኃ፡፡
–    እ…
–    ኔትወርክ፡፡
–    ሌላስ?
–    አንዳንዴም የሰው ሕይወት፡፡
–    በል በል ሌላ ፖለቲካ ውስጥ አትግባ፡፡
–    ይቅርታ ክቡር ሚኒስትር፡፡
–    ለማንኛውም አሠራራችንን መለወጥ አለብን፡፡
–    እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
–    ሁሉን ነገር በአዲስ መልኩ መጀመር አለብን፡፡
–    በአዲስ ሲሉ?
–    ሕዝቡ በጣም ተማሮብናል፡፡
–    እርሱማ ግልጽ ነው፡፡
–    ስለዚህ ሕዝቡን ማስደሰት አለብን፡፡
–    እኮ በምን እናስደስተው?
–    አዲስ ሕንፃ ውስጥ መግባት አለብን፡፡
–    ለምን ሲባል?
–    ሕዝቡ በደል በደል በሚሸት ሕንፃ ውስጥ ከዚህ በኋላ መገልገል የለበትም፡፡
–    እና ምን ይደረግ?
–    አዲስ ሕንፃ ውስጥ መግባት አለብን ስልህ፡፡
–    የትኛው ሕንፃ ውስጥ ነው የምንገባው?
–    የምንገባበትን ሕንፃ እኔ እጨርሰዋለሁ፡፡
–    የመንግሥት ሕንፃ ነው?
–    የግል ነው እንጂ፡፡
–    በኪራይ ክቡር ሚኒስትር?
–    አዎና የግል ሴክተሩን እኮ ማበረታታት አለብን፡፡
–    እና ከመንግሥት ሕንፃ ወጥተን ወደ ኪራይ እንግባ እያሉ ነው?
–    ለሕዝቡ ሲባል የማይደረግ ምንም ነገር የለም፡፡
–    ለማን አሉኝ?
–    ለሕዝቡ፡፡
–    ለእርስዎ ማለትዎ ነው?
[ክቡር ሚኒስትሩ ለምሳ ቤታቸው ሲሄዱ ሚስታቸውን አገኟቸው]
–    ምነው ደስ ያለህ ትመስላለህ?
–    እንዴት አልደሰት?
–    እኮ ምን ተገኘ?
–    ያው አፉን ከፍቶ የነበረው ሕንፃችን ተከራይ ተገኘለት፡፡
–    ማን ሊከራየው ነው?
–    እኛ ነና፡፡
–    እናንተ ማን ናችሁ?
–    የእኛ መሥሪያ ቤት፡፡
–    ምን?
–    አዎን ሁሉን ነገር ጨርሼዋለሁ፡፡
–    ለምንድን ነው ቢሮ የምትቀይሩት?
–    በአዲስ መንፈስ ሥራ መጀመር አለብና፡፡
–    ያላችሁበት የመንግሥት ሕንፃ አይደል እንዴ?
–    ቢሆንስ?
–    ታዲያ ከዛ ወጥታችሁ ወደ ግለሰብ ሕንፃ ልትገቡ?
–    ምን አለበት?
–    ለነገሩ ከመንግሥት ሕንፃ ወደ መንግሥት ባለሥልጣን ሕንፃ ነው የገባችሁት፡፡
–    አመጣሽው ጨዋታውን፡፡
–    ያን ያህል ልዩነት ያለው አይመስለኝም፡፡
–    ያው ነው ስልሽ፡፡
–    የእኔ ሥራ ብቻ ተቀዛቅዟል፡፡
–    የትኛው ሥራሽ?
–    የፈርኒቸሩ ሥራ ነዋ፡፡
–    ለእሱም ቢዝነስ ሥራ አግቼልሻለሁ፡፡
–    ምን ተገኘ?
–    አዲሱ ሕንፃ ውስጥ ስንገባ አዲስ ፈርኒቸር ያስፈልገናል፡፡
–    የድሮዎቹ ምን ሆኑ?
–    ወንበሮቹ ራሳቸው ግፍ ግፍ ይሸታሉ፡፡
–    ታዲያ ወንበሮቹ ሳይሆኑ ወንበሮቹ ላይ የተቀመጡት እኮ ናቸው ግፈኞቹ፡፡
–    ቢሆንም ሕዝቡ በእነዚህ ግፈኛ ወንበሮች ከዚህ በኋላ መገልገል የለበትም፡፡
–    እኔማ ደስ ነው የሚለኝ፤ ቢዝነስ አገኘሁ፡፡
–    ስለዚህ ተዘጋጂ፡፡
–    ስለእሱ አታስብ፡፡
[ክቡር ሚኒስትሩ ቢሮ ሲገቡ አማካሪያቸውን አስጠሩት]
–    አቤት ክቡር ሚኒስትት፡፡
–    አንድ ሐሳብ መጥቶልኝ ነው፡፡
–    የምን ሐሳብ?
–    አዲሱ ቢሮ ስንገባ አዲስ ፈርኒቸር መግዛት አለብን፡፡
–    ምን?
–    ሁሉን ነገር በአዲስ መንፈስ መጀመር አለብን ስልህ፡፡
–    ፈርኒቸሮቹ ከተገዙ እኮ ስድስት ወራቸው ነው፡፡
–    ስማ ቢሆኑም ሕዝቡ በእነዚህ ግፈኛ ወንበሮች መገልገል የለበትም፤ መቀየር አለባቸው፡፡
–    መቀየርማ ያለባቸው ሰዎቹ ናቸው፡፡
–    ሰዎቹን መቀየር ከባድ ስለሆነ ወንበሮቹን ብንቀይራቸው ይሻላል፡፡
–    ሕዝቡ እኮ የተማረረው በወንበሮቹ ሳይሆን በሰዎቹ ነው፡፡
–    አየህ በወንበሮቹ ጀምረን በሰዎቹ እንቀጥላለን፡፡
–    ለማንኛውም የሰዎቹን ቅያሬ ስንጠብቅ ቀኑ እንዳይደርስብን፡፡
–    የምኑ ቀን?
–    የምፅዓት ቀን!
[የክቡር ሚኒስትሩ ጸሐፊ ቢሯቸው ገባች]
–    ጠዋት የት ሄደሽ ነው?
–    አንድ ጉዳይ ገጥሞኝ ነው ክቡር ሚኒስትር፡፡
–    ታዲያ አታስፈቅጂም እንዴ?
–    ስልክዎትን ብለው ብለው አልሠራ አለኝ፡፡
–    ሞክረሽልኝ ነበር?
–    በጣም ብዙ ጊዜ ነው የሞከርኩት ክቡር ሚኒስትር፡፡
–    አየሽ ሌላም ሰው ቢፈልገኝ አልገኝም ማለት ነው፡፡
–    ለእኔ አልሠራልኝም ነበር፡፡
–    ሕዝቡ የሚማረረው እኮ እንደዚህ እየሆነ ነው፡፡
–    እንዴት ክቡር ሚኒስትር?
–    ስልኬ በአዲስ መቀየር እንዳለበት ገብቶኛል፡፡
–    እ…
–    አዲስ አይፎን ያስፈልገኛል፡፡
[ክቡር ሚኒስትሩ የአይቲ ክፍል ኃላፊውን አስጠሩት]
–    አቤት ክቡር ሚኒስትር፡፡
–    ሕዝቡ ምን ያህል እየተማረረ እንደሆነ ታውቃለህ አይደል?
–    በጣም ተማሯል፡፡
–    ሕዝቡን እኔን ሊያገኘኝ አልቻለም፡፡
–    ቢሮ መቼ ተቀምጠው ያውቃሉ?
–    ቢሮ ባልቀመጥም ቢያንስ በስልክ ሊያገኘኝ ይገባል፡፡
–    ስልክዎትን የሚያውቀውማ ይደውልልዎታል፡፡
–    የማያውቀውም ቢሆን ቢያንስ በኢሜይል ሊያገኘኝ ይገባል፡፡
–    ታዲያ ለምን አያገኝዎትም?
–    አየህ ኮምፒዩተሮቻችን አሮጌ ናቸው፡፡
–    እ…
–    አሁን አዲስ ሕንፃ ውስጥ ስለምንገባ ሁሉንም በአዲስ ኮምፒዩተር መተካት አለብን፡፡
–    ክቡር ሚኒስትር አሁን ያሉት ኮምፒውተሮች እኮ ከተገዙ ገና ስድስት ወራቸው ነው፡፡
–    ስማ ቴክኖሎጂው እኮ በየጊዜው ነው የሚቀያየረው፡፡
–    እ…
–    ስልኮቻችንም በአዲስ መቀየር አለባቸው፡፡
–    ጨረታ ይውጣ?
–    ቢሮክራሲ አያስፈልግም፡፡
–    ምን?
–    እኔ እጨርሰዋለሁ፡፡
[ክቡር ሚኒስትሩ የኮምፒዩተር ቢዝነስ የሚሠራው ወንድማቸው ጋ ደወሉ]
–    አቤት ጋሼ፡፡
–    የት ነው ያለኸው?
–    ካርታ እየተጫወትኩ ነው፡፡
–    አንተ ልጅ ይኼ ካርታ ሱስ ሆነብህ አይደል?
–    ያው በዘር እኮ ነው ሱስ የሆነብን ጋሼ፡፡
–    እኔ የት ነው ካርታ ስጫወት ያየኸው?
–    ያው አንተ በመሬት ካርታ ነዋ የምትጫወተው፡፡
–    ለማንኛውም አሁን ሥራ አግኝቼልሃለሁ፡፡
–    የምን ሥራ ጋሼ?
–    ለቢሯችን ሙሉ ኮምፒዩተር እንድታቀርብ፡፡
–    እየቀለድክ ነው ጋሼ?
–    የምን ቀልድ ነው? እውነቴን ነው፡፡
–    ከስድስት ወር በፊት ነው እኮ ለሙሉ ቢሮው ኮምፒዩተር ያቀረብኩት፡፡
–    እና ይኼኛውን አትፈልገውም?
–    ኧረ እንደሱ ማለቴ አይደለም፤ በጣም ደስ ብሎኝ ነው፡፡
–    ምኑ ነው ደስ ያለህ?
–    በቃ በዚህ ሥራ ሕንፃዬን እጨርሰዋለሁ ብዬ ነዋ፡፡
–    ሕንፃህንም ተጨማሪ ቦታ ስለሚያስፈልገን መከራየታችን አይቀርም፡፡
–    አንጀት አርስ ነህ ጋሼ፡፡
[ክቡር ሚኒስትሩ አንድ ስብሰባ ተጠርተው ሄዱ፤ ሳያስቡት መገምገም ጀመሩ]
–    ክቡር ሚኒስትር ከብልሹ አሠራርዎት ሊታቀቡ አልቻሉም፡፡
–    እናንተ ከእኔ ውጪ ሰው አይታያችሁም እንዴ?
–    ይኸው ባለፈው ተገምግመው አሁንም ያው ነዎት፡፡
–    ምን አደረግኩ?
–    ይኸው አዲስ ሕንፃ ውስጥ ካልገባን እያሉ ነው፡፡
–    በአዲስ መልክ ሥራ መጀመር ስላለብን ነዋ፡፡
–    ደግሞ ሕንፃው የእርስዎ ነው አሉ?
–    በተመጣጣኝ ዋጋ እስካከራየሁት ድረስ ምን ችግር አለው?
–    እ…
–    ፈርኒቸሮቹንም ቢሆን በአገር ዋጋ ነው የምናቀርበው፡፡
–    ሌላስ?
–    ኮምፒዩተሮቹም ቢሆኑ ሌተስት የሆኑት እኛ ጋ ስላሉ ነው፡፡
–    ወይ ቅሌት፡፡
–    ይህንንም ያደረግነው ሥራችንን በአዲስ መንፈስ ለመጀመር ነው፡፡
–    እርስዎም በአዲስ መልክ ጀምረውልኛላ፡፡
–    ምኑን?
–    ሌብነቱን!