ኃይሌ ምን አገባው ! ( ሄኖክ የሺጥላ )
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
ኃይሌ ምን አገባው ! ( ሄኖክ የሺጥላ )
ኃይሌ ወንድማችን ፣ ቆጣቢው ኃይሌ ፣አባ ሃናው ኃይሌ ፣ ባለፎቁ ኃይሌ ፣ ባለ ሲኒማ ቤቱ ኃይሌ ፣ የኦሎምፒክን ሜዳይ ደግሞ ደጋግሞ ያጠለቀው ትልቁ ሰው ኃይሌ ተሳሳተ ይላሉ ። አሁን ኃይሌ ምኑ ጋ ነው የተሳሳተው ? እኔ እስከሚገባኝ ኃይሌ የሚያውቀውን ነው ያወራው ፣ የገባውን ነው የተናገረው ! እኛ እኮ ኃይሌን ያወቅነው ኢትዮጵያውን ወክሎ ስለ ዲሞክራሲ ሲያወራ አይደለም ። እኛ ኃይልዬን የምናውቀው ሲሮጥ ነው ። አዎ ተዘጋጅ -ቷ ! ከዛ በቃ ሀይልዬ ፍልቅልቅ እያለ ሲሮጥ !
ኃይሌ ለኢትጵያ ሕዝብ ዲሞክራሲ እንደ ቅንጦት ነው ፣ መልካም አስተዳደር እንጂ ዲሞክራሲ አያስፈልጋትም ሲል ስህተቱ ምኑ ላይ ነው ? ተሳሳተ እንዴ ?እንደውም ኃይሌ ከተሳሳተ የተሳሳተው የኢትዮጵያ ሕዝብ መልካም አስተዳደር ችግር ሊኖርበት ስለሚችል ፣ የመልካም አስተዳደር ያስፈልገዋል ማለቱ ነው ። እኔን እስከሚገባኝ በአሁኑ ሰዓት የኢትዮጵያ ሕዝብ ምንም አያስፈልገውም ! ምንም !
ቆይ መልካም አስተዳደር ለኢትዮጵያ ሕዝብ ምን ይሰራለታል ? ምን ሊያደርገው ? የት ሊያስቀምጠው ? አሁን ማን ይሙት ለአንድ ገበሬ ዲሞክራሲ ብትሰጠው ምን ያደርግበታል ? አያርስበት !? አይጎለጉልበት !? አይዘራበት !? ምን በወጣው ። እዛው ዲሞክራሲውንም እንደ መሬቱ እርስ በእርሳቸው ይከፋፈሉት ! ኃይሌ ልክ ነው ባካችሁ !
አሁን የኢትዮጵያ ሕዝብ የነጻነት ጥያቄ መጠየቁ አግባብ ነው ነው የምትሉት ? ነጻነት ምን ይሰራለታል ? ግዛ ብትሉት ዋጋውንስ ይችለዋል ወይ ? ነጻነት እኮ ብዙ ያስከፍላል ? ዲሞክራሲ እኮ ” እንደ ሾላ ፍሬ በድንጋይ ተመቶ የሚለቀም ነገር አይደለም !” ። እንደውም ሳስበው የኛ ሕዝብ ችግር ስለማያውቀው ነጻነት ማውራቱ ላይ ይመስለኛል ። ይሄ ሕዝብ ነጻ ሆኖ ያውቃል እንዴ ? ታዲያ ያለመደበትን ነጻነት ማንን ለመመስል ነው ” ነጻነት -ናጽነት – ፕሊሱማ –” እና ወዘተ እያልን የምንደሰኩረው ። «ከየት አባቱ ያመጣውን ነጻነት !» እንደውም የዚህ ሕዝብ ችግር ቂጥኝ ነው ! የዚህ ሕዝብ ችግር የዲሞክራሲ እጦት ሳይሆን ፣ ያልተመጣጠነ «ወሲብ» ችግር ነው !
ይሄ ሕዝብ እኮ ዓመት ሙሉ እህል ሳይበላ ፣ ለአምት-በዓል በግ የሚያርድ ሕዝብ ነው ። ታዲያ የዚህ ሕዝብ ችግር ከዲሞክራሲ እጦት ጋ ምን አገናኘው ? የዚህ ህዝብ ችግር የመስ’እዋት ችግር ነው። ለምሳሌ የቴዲ አፍሮ የሙዚቃ ኮንሰርት በያ ሰሞን ሲሰረዝ ፣ የአስቴርን የሙዚቃ ኮንሰርት ተቀላቅሎ ይህ ብርቅ ሕዝብ ሲጨፍር እንዳደረ ሰምቻለሁ። ምን ማለት እንደሆነ ይተርጎም ? እሺ ይህንን ስንተረጉመው ምን ማለት ነው የ- አንድነት ፓርቲ በምንወደው መንግስታችን በጉልበት ሲፈርስ ፣ ሄዶ ሰማያውን መቀላቀል ማለት ነው ። ታዲያ ለዚህ ሕዝብ ዲሞክራሲ ያስፈልገዋል ? በምድር ላይ ከዚህ ሕዝብ በላይ ያለ ዲሞክራሲ– ዲሞክራሲን የተረዳ ይኖራል ?
ሀይሌ እውነቱን ነው ፣ ለዚህ ሕዝብ ዲሞክራሲ ሳይሆን ካልሲ ነው የሚያስፈልገው ! ለዚህ ሕዝብ ነጻነት ሳይሆን ፣ ፓንት ነው የሚያስፈልገው ። የዚህ ሕዝብ ችግር የመልካም አስተዳደር ችግር ሳይሆን ፣ የመልካም ምድራዊ አቀማመጥን በትክክል ያለመረዳት ችግር ነው ። ምን ማለት ነው ? ይሄ ሕዝብ ሃገሩ ራሷ የቱ ጋ እንዳለች እንኳ በቅጡ አያውቅም! ለዚህም ነው በአራቱም አቅጣጫ ሃገሩን ለመፈለግ ካገሩ የሚወጣው ! የዚህ ሕዝብ ችግር የመንግስት ባለ ስልጣናት የሚያደርሱበት በደል አይደለም ! የዚህ ሕዝብ ችግር ያንን በደል ችሎ ( ዋጥ -ሥልቅት አድርጎ ) መኖር መቻሉ ላይ ነው ። ታዲያ ህዝቡ ረሃቡ ከተመቸው ፣ ድንቁርናው ከደላው ፣ ስደቱ ከከየፈው ፣ ኃይሌ ምን አገባው ! ደሞ ኃይሌን እናውቀዋለን እንጂ እሱ አያውቀንም ! ቢያውቀን ኖሮ እንዲህ አይለንም ! እመኑኝ ኃይሌ አያውቀንም !
