ማለቴ ለማኝነት ( ሄኖክ የሺጥላ )
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
ማለቴ ለማኝነት ( ሄኖክ የሺጥላ )
ቋር ላይ የተነጣጠረ ምስማር ቢጣመም ጥፋቱ የምስማሩ ፣ ወይም የቋሩ ወይም የመዶሻው አይደለም ። ጥፋቱ ያናጢው ነው ።
በግብርና መር ኢኮኖሚ የሚመራ ስርዓት፣ ህዝቡ በድርቅ ምክንያት ለረሃብ ወይም ረሃቡ ገፍቶ ለቸነፈር ‘ና ለጠኔ ቢዳረግ ፣ ችግሩ የገበሬው ፣ ወይም የመሬቱ ወይም የአየሩ አይደለም ፣ ችግሩ የስርዓቱ ነው ። ድርቅ ተፈጥሯዊ ክስተት ነው ። ረሃብን ግን ተፈጥሯዊ የሚያደርገው የአስተዳደር ችግር ነው ። እንድንናገር ከተፈቀደልን የሃገረችን ነገር “ለማ” ብለን ሳንጨርስ “ገለማ” የሆነውም በዚሁ በአስተዳደር ዙሪያ ባለው ችግር ነው( ይመስለናል ይላሉ ሙሁሮቹ!) ። አስተዳደር ስል ፣ እያስተዳደርን ነው ለሚሉት ቦታ መስጠቴ አይደለም ፥ ግን አለ አይደል ፎርማል ለመሆን እንጂ ። ፎርማል ስል <ፎርማሊን> ትዝ አለኝ ። አዎ ፎርማሊን በአስተሳስቡ ለሞተ ሰው የሚወጋ የ ድንቁርና ማድረቂያ መድሃኒት ቢሆን ኖሮ ፣ ወያኔን ምን ትጠብቃለህ ” ተጠቀም እንጂ !” ብዬ የማይነጥፍ ምክሬን በለገስኩ !
እሱንም በልመና ኣስገብተው በልማታችን ባይሉን ምን ኣለ በሉ !
ባደጉ ሀገሮች ድርቅ ከአንድ ተፍጥሯዊ ክስተትነቱ ባሻገር ፣ የምርምር እና የጥናት አጋጣሚን የሚፈጥር አንድ ትልቅ ቤተ ሙከራም ነው ። መሬት መንቀጥቀጥም ይሁን ፣ የመሬት መንሸራተት ፣ ከክስተትነት ባለፈ ለተሻለ መረዳት እና የወደፊት ጥንቃቄ ትተውት የሚሄዱት ለጥናት እና ምርምር ናሙና የሚሆን ሳይንሳዊ አሻራ አላቸው ። በኛ ሀገር ግን ሰውነቱን ጉበት ቀብቶ እንደሚንዘፈዘፍ አጭበርባሪ ለማኝ ፣ መንግስት ድርቁን እንደጉበት ሰውነቱን ተቀብቶ ፣ ሀገሪቷን እያንዘፈዘፈ ስንዴ መለመኛ ከማድረግ ባሻገር ፥ ከዛሬ ተምሮ ነገን ምን ማድረግ እንዳለበት ወደሚወስድ ሰዋዊ ባህሪ ለመመለስ ሲሞክር ኣላየነውም ። ይህ የመንግስት ባህሪ አንገት የሚያስቀረቅር ከሆነ ደሞ ሰንበት በት ብሏል ።
እንደውም ሳስበው ፣ የሀገራችን ኢኮኖሚ መሰረቱ ወረቀት ላይ ” ግብርና መር ” በተግባር ግን ” ልመና መር ” መሆኑ ነው ። ይህ ደሞ ስልጣንን ያለ እውቀት መቆናጠጥ ከሚያጎናጽፈው ንቀት እና ትቢት ባሻገር ፣የስልጣን ባለቤት ነኝ ለሚለው አካል፥ አብሮ በተጨማሪነት የሚደጉመው ውል አልባነት ፣ ሃሳብ አልባነት ፣ ጥበብ አልባነት ከፖለቲካ ኪሳራነት በተጨማሪ የክሽፈቱ ምንዳና ማሳያም በመሆኑ ነው ! ማለቴ ለማኝነቱ እና እግር ስር እንደ ህጣን ኣለሁ የሚለው ፈጣጣ (ፈንጣጣ) ልማቱም የግራ መጋባት እና የእውቀት ማነስ ውጤት ነው። ወጠጤ ጎልማሶች ኣልረዳ ኣሉን እንጂ!
በክላሽ እና በ ትራሽ ፖለቲካቸው ኣደከሙን እንጂ ! ስለ ሰ’ብኣዊ መብት ስትጠይቅ ስለ ኮብል ስቶን እያወሩ የመረዳት እና የማስረዳት ኣቅማችንን ለነሱ ስንል ” እታች” ኣወረዱት እንጂ ። ሀገር ስንል ጎሳ እያሉ ፥ መሬት ስንል ኣፈር እያሉ ፥ ህዝብ ስንል ፥ ዝንብ እያሉ ፥ ቆሻሻ ሌጋሲያቸውን ታሪክ ብለው ኣሰፈሩት ! “ያስፈራሉም ” ያሳፍራሉም !