• ክቡር ሚኒስትር ያው የተለመደው ጊዜ ደርሷል፡፡
  • የምን የተለመደ ጊዜ ነው?
  • እርስዎ የሚወዱት ጊዜ ነዋ፡፡
  • እኔ ደግሞ የምወደው ጊዜ የቱ ነው?
  • የበዓል ጊዜ ነዋ፡፡
  • እኔ እንደ በዓል የምጠላው ነገር የለም እኮ፡፡
  • ያው እንትኑን ይወዱታል ብዬ ነው፡፡
  • ምኑን?
  • ስጦታውን፡፡
  • ስጦታ መምጣት ጀመረ እንዴ?
  • ይኸው አሁን ያጨናነቀኝ ነገር እሱ ነው፡፡
  • በይ የተለመደው ሥራሽን እንዳትዘነጊ፡፡
  • የምን ሥራ?
  • የመለየቱን ነዋ፡፡
  • ምኑን ነው የምለየው?
  • ስጦታውን፡፡
  • እንዴት ነው የምለየው?
  • የኪራይ ሰብሳቢውን ከልማታዊው፡፡
  • እሱማ ተለይቷል፡፡
  • ስለዚህ የልማታዊውን ታስቀሪልኛለሽ፡፡
  • የኪራይ ሰብሳቢውንስ?
  • እሱን ትመልሺልኛለሽ፡፡
  • ስጦታውን ቢያዩት ግን ሐሳብዎትን የሚቀይሩ ይመስለኛል፡፡
  • ለምን ሲባል?
  • የልማታዊዎቹ ስጦታ እኮ ፖስት ካርድ ብቻ ነው፡፡
  • የኪራይ ሰብሳቢዎቹስ?
  • የእነሱማ ከዶሮ እስከ በሬ ይደርሳል፡፡
  • እና የልማታዊዎቹ ስጦታ ካርድ ብቻ ነው እያልሽኝ ነው?
  • እህሳ?
  • አየሽ ልማታዊዎቹ የሚጐድላቸው እኮ ይኼ ነው፡፡
  • ምንድን ነው የሚጐድላቸው?
  • ከኪራይ ሰብሳቢዎቹ መማር ያለባቸው ነገር አለ፡፡
  • ልማታዊው ከኪራይ ሰብሳቢ ምን ሊማር ይችላል?
  • ለምሳሌ ስጦታ አሰጣጥ፡፡
  • ልማታዊ ስጦታ የሚባል ነገር የለማ፡፡
  • ታዲያ ምንድን ነው የሚባለው?
  • ሙስና!

[ክቡር ሚኒስትሩ አማካሪያቸው አስጠሩት]

  • ፈለጉኝ ክቡር ሚኒስትር?
  • እዚህ ጋዜጣ ላይ የወጣውን ዜና አንብበኸዋል?
  • የትኛውን ዜና?
  • የውጭ ምንዛሪ እጥረት የኤምባሲዎቻችንን ሥራ እያወከ ነው የሚለውን ነዋ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር እሱ ችግር እኮ አንገብጋቢ ነው፡፡
  • እኔ ያልገባኝ እኮ አንድ ነገር ነው፡፡
  • ምንድን ነው ያልገባዎት?
  • ኤምባሲዎቻችን ንግድ ውስጥ ገብተዋል እንዴ?
  • እ…
  • ማለቴ የሚያስገቡት ዕቃ አለ?
  • አልገባኝም ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ንግድ ውስጥ ካልገቡ የውጭ ምንዛሪ ምን ያደርግላቸዋል?
  • የገባዎት አልመሰለኝም፡፡
  • ምኑ?
  • ኤምባሲዎች የሥራ ማስኬጃዎችን ጨምሮ ለሠራተኞቻቸው በውጭ ምንዛሪ ነው የሚከፍሉት፡፡
  • ለምን በብር አይጠቀሙም?
  • ያው ብር ውጭ አገር ስለማይሠራ ነዋ፡፡
  • አሁን እኛም መደራደር አለብና፡፡
  • ምን ብለን?
  • ብር ውጭ አገር ካልሠራ ዶላር እዚህም አገር አይሠራም ብለን ነዋ፡፡
  • እየቀለዱ ነው?
  • በአገር ቀልድ የለም፡፡
  • እኛ እኮ ኢኮኖሚያችን ገና ታዳጊ ነው፡፡
  • ይኸው ዓለም ላይ ኢኮኖሚው እንደ እኛ እያደገ ያለ አገር እኮ የለም፡፡
  • ቢሆንም ያደጉት አገሮች ላይ ለመድረስ ገና ብዙ ይቀረናል፡፡
  • ሌላው የገረመኝ የኤምባሲ ሠራተኞቹ የመንግሥት ሠራተኛ ሆነው እንዴት በውጭ ምንዛሪ ደመወዝ ይከፈላቸዋል?
  • ታዲያ በምን ይከፈላቸው?
  • ሌላው ሠራተኛ እንደሚከፈለው በብር ነዋ፡፡
  • ውጭ እየኖሩ?
  • እኔም እኮ በውጭ ምንዛሪ እንዲከፈለኝ እፈልጋለሁ፡፡
  • እዚህ እየኖሩ?
  • ምን አለበት?
  • አይቻልማ፡፡
  • ስለዚህ መፍትሔው አንድ ነው፡፡
  • ምንድን ነው?
  • ሥራዬን ውጭ አገር ሆኜ መሥራት፡፡

[የክቡር ሚኒስትሩ ወዳጅ ሚኒስትር ደወሉላቸውና ተገናኙ]

  • ክቡር ሚኒስትር ሥራ እንዴት ነው?
  • ይኸው ተያይዘነዋል፡፡
  • የዚህ የመልካም አስተዳደር ችግር ግን አንገብጋቢ እየሆነ ነው፡፡
  • አንገብጋቢ መሆኑንማ በየጊዜው እየገለጽን ነው፡፡
  • አሁን ሰው የሰለቸው አሱ ነው፡፡
  • ምንድን ነው የሰለቸው?
  • ወሬ ብቻ ሆነ፡፡
  • እና ምን ይደረግ?
  • ዕርምጃ መውሰድ ነዋ፡፡
  • እየወሰድን አይደል እንዴ?
  • ማን ላይ ነው ዕርምጃ የተወሰደው?
  • የፀረ ልማት ኃይሎች ላይ ነዋ፡፡
  • ክቡር ሚኒስትር ችግሩ እኮ የመልካም አስተዳደር ነው፡፡
  • እሱማ አውቃለሁ፡፡
  • ስለዚህ ማላከኩን ማቆም አለብን፡፡
  • የምን ማላከክ?
  • የችግሩን መንስዔ፡፡
  • ፀረ ልማቶችን ግን አንታገሳቸውም፡፡
  • ራሳችንን ግን እንመርምር፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • ካድሬዎቻችን ምን እያደረጉ እንደሆነ አያውቁም እንዴ?
  • ምን እያደረጉ ነው?
  • በአጭር መንገድ እየከበሩ ነው፡፡
  • እኔ የሚገርመኝ ሰው ሲያድግ ግን ሰው አይወድም ማለት ነው?
  • ማደጉ እኮ አይደለም ችግሩ፡፡
  • ታዲያ ምንድን ነው ችግሩ?
  • የሚያድጉበት መንገድና ፍጥነት ነዋ፡፡
  • አገራችንም በፈጣን ዕድገት ውስጥ መሆኗ ችግር አለው እያልከኝ ነው?
  • ክቡር ሚኒስትር ያ ሌላ ይኼ ሌላ፡፡
  • እሺ ምን ይደረግ?
  • መጠየቅ ያለበት ይጠየቅ፡፡
  • እ…
  • መቀጣት ያለበት ይቀጣ፡፡

[ክቡር ሚኒስትሩ ጋ አንድ ደላላ ባለሀብት ደወለ]

  • ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • ምን ልታዘዝ?
  • አንድ ሐሳብ አለኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
  • የምን ሐሳብ?
  • ሙሉ አዲስ አበባን ለምን አትሰጡኝም?
  • ምን ልታደርጋት?
  • ላለማት ነዋ፡፡
  • እየቀለድክ ነው?
  • ኧረ እውነቴን ነው፡፡
  • ሙሉ አዲስ አበባን ለአንድ ሰው ልንሰጥ?
  • ምን አለበት?
  • ለአንድ ሰው እንዴት ይኼ ሁሉ ቦታ ይሰጣል?
  • ስንተዋወቅ አንተናነቃ፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • ይኸው ለህንዱ ኩባንያ ሁለት አዲስ አበባን የሚያክል ቦታ አይደል እንዴ የሰጣችሁት?
  • የተሰጠው እኮ 100 ሺሕ ሔክታር ነው፡፡
  • ያ ማለት እኮ ሁለት አዲስ አበባን ለመሆን ስምንት ሺሕ ሔክታር የጐደለው ማለት ነው?
  • ታዲያ ፈረንጆቹ እውነታቸውን ነዋ፡፡
  • እንዴት ማለት?
  • ኢትዮጵያ ውስጥ የመሬት ወረራ አለ የሚሉት?
  • እሱን እርስዎ አሉ፡፡
  • እንዲህ አስቤው ስለማላውቅ ነው፡፡
  • ለእኔ ግን አንድ አዲስ አበባን ቢሰጡኝ አለማታለሁ፡፡
  • እሱስ ታለማለህ፡፡
  • ይህን ካደረጉ ሌላም አለማለሁ፡፡
  • ሌላ ምን ልታለማ?
  • እርስዎን!

[አንድ የክቡር ሚኒስትሩ ወዳጅ ከውጭ ደወለ]

  • ክቡር ሚኒስትር የህንዱ ባለሀብት ላይ የወሰዳችሁት ዕርምጃ አስደስቶኛል፡፡
  • ጊዜው የሥራ ነው፡፡
  • ለነገሩ ታግሳችሁታል፡፡
  • ስድስት ዓመት ታገስን፡፡
  • እና አሁን ትግስታችሁ አለቀ፡፡
  • ከስድስት ዓመት በላይ መታገስ አንችልም፡፡
  • ግን እኮ አሥራ ምናምን ዓመታት የታገሳችኋቸው አሉ፡፡
  • እ…
  • ወይስ ትግስታችሁም ይከፈላል?
  • ምን ተብሎ?
  • ልማታዊና ኪራይ ሰብሳቢ!

[ክቡር ሚኒስትሩ ቤት ሲገቡ ሚስታቸው አገኟቸው]

  • ግቢው እኮ እንዲሁ ሲበጠበጥ ዋለ፡፡
  • በምንድን ነው የተበጠበጠው?
  • በላካቸው ከብቶች ነዋ፡፡
  • እኮ ምን አበጣበጣቸው?
  • ቦታ ነዋ፡፡
  • እንዴት?
  • እንደምታየው በሬ ሰፊ ቦታ ይፈልጋል፡፡
  • እሺ፡፡
  • ፍየሎቹ ደግሞ ቦታ ጠበበን ብለው ከበሬው ጋር ሁከት ገጠሙ፡፡
  • በጐቹስ?
  • በጐቹማ በሬው ሰፊ ቦታ ይዟል በሚል ፍየሎቹ ከበሬው ጋ እንዲጋጩ የሚያነሳሱት እነሱ ነበሩ፡፡
  • ዶሮዎቹስ?
  • እነሱ ደግሞ ሌሎቹ ሲጋጩ እየተንጫጩ ግቢውን ሲያምሱት ነበር፡፡
  • የሚገርም ተንታኝ ሆነሽልኛል፡፡
  • ምን ላድርግ?
  • ለዚህ ሥራሽ የሚገባሽን አውቃለሁ፡፡
  • ምንድን ነው የሚገባኝ?
  • ሽልማት፡፡
  • ማን ይሸልመኛል?
  • የሽልማት ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት!