- ክቡር ሚኒስትር ያው የተለመደው ጊዜ ደርሷል፡፡
- የምን የተለመደ ጊዜ ነው?
- እርስዎ የሚወዱት ጊዜ ነዋ፡፡
- እኔ ደግሞ የምወደው ጊዜ የቱ ነው?
- የበዓል ጊዜ ነዋ፡፡
- እኔ እንደ በዓል የምጠላው ነገር የለም እኮ፡፡
- ያው እንትኑን ይወዱታል ብዬ ነው፡፡
- ምኑን?
- ስጦታውን፡፡
- ስጦታ መምጣት ጀመረ እንዴ?
- ይኸው አሁን ያጨናነቀኝ ነገር እሱ ነው፡፡
- በይ የተለመደው ሥራሽን እንዳትዘነጊ፡፡
- የምን ሥራ?
- የመለየቱን ነዋ፡፡
- ምኑን ነው የምለየው?
- ስጦታውን፡፡
- እንዴት ነው የምለየው?
- የኪራይ ሰብሳቢውን ከልማታዊው፡፡
- እሱማ ተለይቷል፡፡
- ስለዚህ የልማታዊውን ታስቀሪልኛለሽ፡፡
- የኪራይ ሰብሳቢውንስ?
- እሱን ትመልሺልኛለሽ፡፡
- ስጦታውን ቢያዩት ግን ሐሳብዎትን የሚቀይሩ ይመስለኛል፡፡
- ለምን ሲባል?
- የልማታዊዎቹ ስጦታ እኮ ፖስት ካርድ ብቻ ነው፡፡
- የኪራይ ሰብሳቢዎቹስ?
- የእነሱማ ከዶሮ እስከ በሬ ይደርሳል፡፡
- እና የልማታዊዎቹ ስጦታ ካርድ ብቻ ነው እያልሽኝ ነው?
- እህሳ?
- አየሽ ልማታዊዎቹ የሚጐድላቸው እኮ ይኼ ነው፡፡
- ምንድን ነው የሚጐድላቸው?
- ከኪራይ ሰብሳቢዎቹ መማር ያለባቸው ነገር አለ፡፡
- ልማታዊው ከኪራይ ሰብሳቢ ምን ሊማር ይችላል?
- ለምሳሌ ስጦታ አሰጣጥ፡፡
- ልማታዊ ስጦታ የሚባል ነገር የለማ፡፡
- ታዲያ ምንድን ነው የሚባለው?
- ሙስና!
[ክቡር ሚኒስትሩ አማካሪያቸው አስጠሩት]
- ፈለጉኝ ክቡር ሚኒስትር?
- እዚህ ጋዜጣ ላይ የወጣውን ዜና አንብበኸዋል?
- የትኛውን ዜና?
- የውጭ ምንዛሪ እጥረት የኤምባሲዎቻችንን ሥራ እያወከ ነው የሚለውን ነዋ፡፡
- ክቡር ሚኒስትር እሱ ችግር እኮ አንገብጋቢ ነው፡፡
- እኔ ያልገባኝ እኮ አንድ ነገር ነው፡፡
- ምንድን ነው ያልገባዎት?
- ኤምባሲዎቻችን ንግድ ውስጥ ገብተዋል እንዴ?
- እ…
- ማለቴ የሚያስገቡት ዕቃ አለ?
- አልገባኝም ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ንግድ ውስጥ ካልገቡ የውጭ ምንዛሪ ምን ያደርግላቸዋል?
- የገባዎት አልመሰለኝም፡፡
- ምኑ?
- ኤምባሲዎች የሥራ ማስኬጃዎችን ጨምሮ ለሠራተኞቻቸው በውጭ ምንዛሪ ነው የሚከፍሉት፡፡
- ለምን በብር አይጠቀሙም?
- ያው ብር ውጭ አገር ስለማይሠራ ነዋ፡፡
- አሁን እኛም መደራደር አለብና፡፡
- ምን ብለን?
- ብር ውጭ አገር ካልሠራ ዶላር እዚህም አገር አይሠራም ብለን ነዋ፡፡
- እየቀለዱ ነው?
- በአገር ቀልድ የለም፡፡
- እኛ እኮ ኢኮኖሚያችን ገና ታዳጊ ነው፡፡
- ይኸው ዓለም ላይ ኢኮኖሚው እንደ እኛ እያደገ ያለ አገር እኮ የለም፡፡
- ቢሆንም ያደጉት አገሮች ላይ ለመድረስ ገና ብዙ ይቀረናል፡፡
- ሌላው የገረመኝ የኤምባሲ ሠራተኞቹ የመንግሥት ሠራተኛ ሆነው እንዴት በውጭ ምንዛሪ ደመወዝ ይከፈላቸዋል?
- ታዲያ በምን ይከፈላቸው?
- ሌላው ሠራተኛ እንደሚከፈለው በብር ነዋ፡፡
- ውጭ እየኖሩ?
- እኔም እኮ በውጭ ምንዛሪ እንዲከፈለኝ እፈልጋለሁ፡፡
- እዚህ እየኖሩ?
- ምን አለበት?
- አይቻልማ፡፡
- ስለዚህ መፍትሔው አንድ ነው፡፡
- ምንድን ነው?
- ሥራዬን ውጭ አገር ሆኜ መሥራት፡፡
[የክቡር ሚኒስትሩ ወዳጅ ሚኒስትር ደወሉላቸውና ተገናኙ]
- ክቡር ሚኒስትር ሥራ እንዴት ነው?
- ይኸው ተያይዘነዋል፡፡
- የዚህ የመልካም አስተዳደር ችግር ግን አንገብጋቢ እየሆነ ነው፡፡
- አንገብጋቢ መሆኑንማ በየጊዜው እየገለጽን ነው፡፡
- አሁን ሰው የሰለቸው አሱ ነው፡፡
- ምንድን ነው የሰለቸው?
- ወሬ ብቻ ሆነ፡፡
- እና ምን ይደረግ?
- ዕርምጃ መውሰድ ነዋ፡፡
- እየወሰድን አይደል እንዴ?
- ማን ላይ ነው ዕርምጃ የተወሰደው?
- የፀረ ልማት ኃይሎች ላይ ነዋ፡፡
- ክቡር ሚኒስትር ችግሩ እኮ የመልካም አስተዳደር ነው፡፡
- እሱማ አውቃለሁ፡፡
- ስለዚህ ማላከኩን ማቆም አለብን፡፡
- የምን ማላከክ?
- የችግሩን መንስዔ፡፡
- ፀረ ልማቶችን ግን አንታገሳቸውም፡፡
- ራሳችንን ግን እንመርምር፡፡
- እንዴት ማለት?
- ካድሬዎቻችን ምን እያደረጉ እንደሆነ አያውቁም እንዴ?
- ምን እያደረጉ ነው?
- በአጭር መንገድ እየከበሩ ነው፡፡
- እኔ የሚገርመኝ ሰው ሲያድግ ግን ሰው አይወድም ማለት ነው?
- ማደጉ እኮ አይደለም ችግሩ፡፡
- ታዲያ ምንድን ነው ችግሩ?
- የሚያድጉበት መንገድና ፍጥነት ነዋ፡፡
- አገራችንም በፈጣን ዕድገት ውስጥ መሆኗ ችግር አለው እያልከኝ ነው?
- ክቡር ሚኒስትር ያ ሌላ ይኼ ሌላ፡፡
- እሺ ምን ይደረግ?
- መጠየቅ ያለበት ይጠየቅ፡፡
- እ…
- መቀጣት ያለበት ይቀጣ፡፡
[ክቡር ሚኒስትሩ ጋ አንድ ደላላ ባለሀብት ደወለ]
- ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምን ልታዘዝ?
- አንድ ሐሳብ አለኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- የምን ሐሳብ?
- ሙሉ አዲስ አበባን ለምን አትሰጡኝም?
- ምን ልታደርጋት?
- ላለማት ነዋ፡፡
- እየቀለድክ ነው?
- ኧረ እውነቴን ነው፡፡
- ሙሉ አዲስ አበባን ለአንድ ሰው ልንሰጥ?
- ምን አለበት?
- ለአንድ ሰው እንዴት ይኼ ሁሉ ቦታ ይሰጣል?
- ስንተዋወቅ አንተናነቃ፡፡
- እንዴት ማለት?
- ይኸው ለህንዱ ኩባንያ ሁለት አዲስ አበባን የሚያክል ቦታ አይደል እንዴ የሰጣችሁት?
- የተሰጠው እኮ 100 ሺሕ ሔክታር ነው፡፡
- ያ ማለት እኮ ሁለት አዲስ አበባን ለመሆን ስምንት ሺሕ ሔክታር የጐደለው ማለት ነው?
- ታዲያ ፈረንጆቹ እውነታቸውን ነዋ፡፡
- እንዴት ማለት?
- ኢትዮጵያ ውስጥ የመሬት ወረራ አለ የሚሉት?
- እሱን እርስዎ አሉ፡፡
- እንዲህ አስቤው ስለማላውቅ ነው፡፡
- ለእኔ ግን አንድ አዲስ አበባን ቢሰጡኝ አለማታለሁ፡፡
- እሱስ ታለማለህ፡፡
- ይህን ካደረጉ ሌላም አለማለሁ፡፡
- ሌላ ምን ልታለማ?
- እርስዎን!
[አንድ የክቡር ሚኒስትሩ ወዳጅ ከውጭ ደወለ]
- ክቡር ሚኒስትር የህንዱ ባለሀብት ላይ የወሰዳችሁት ዕርምጃ አስደስቶኛል፡፡
- ጊዜው የሥራ ነው፡፡
- ለነገሩ ታግሳችሁታል፡፡
- ስድስት ዓመት ታገስን፡፡
- እና አሁን ትግስታችሁ አለቀ፡፡
- ከስድስት ዓመት በላይ መታገስ አንችልም፡፡
- ግን እኮ አሥራ ምናምን ዓመታት የታገሳችኋቸው አሉ፡፡
- እ…
- ወይስ ትግስታችሁም ይከፈላል?
- ምን ተብሎ?
- ልማታዊና ኪራይ ሰብሳቢ!
[ክቡር ሚኒስትሩ ቤት ሲገቡ ሚስታቸው አገኟቸው]
- ግቢው እኮ እንዲሁ ሲበጠበጥ ዋለ፡፡
- በምንድን ነው የተበጠበጠው?
- በላካቸው ከብቶች ነዋ፡፡
- እኮ ምን አበጣበጣቸው?
- ቦታ ነዋ፡፡
- እንዴት?
- እንደምታየው በሬ ሰፊ ቦታ ይፈልጋል፡፡
- እሺ፡፡
- ፍየሎቹ ደግሞ ቦታ ጠበበን ብለው ከበሬው ጋር ሁከት ገጠሙ፡፡
- በጐቹስ?
- በጐቹማ በሬው ሰፊ ቦታ ይዟል በሚል ፍየሎቹ ከበሬው ጋ እንዲጋጩ የሚያነሳሱት እነሱ ነበሩ፡፡
- ዶሮዎቹስ?
- እነሱ ደግሞ ሌሎቹ ሲጋጩ እየተንጫጩ ግቢውን ሲያምሱት ነበር፡፡
- የሚገርም ተንታኝ ሆነሽልኛል፡፡
- ምን ላድርግ?
- ለዚህ ሥራሽ የሚገባሽን አውቃለሁ፡፡
- ምንድን ነው የሚገባኝ?
- ሽልማት፡፡
- ማን ይሸልመኛል?
- የሽልማት ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት!