በእስር ላይ የሚገኙት እስራኤላዊው የትድሀር ኩባንያ ባለቤት የሱዳን ዜግነት ባለው እስረኛ ተደብድበው መጎዳታቸው ተጠቆመ
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በተመሠረተባቸው ክስ ምክንያት በእስር ላይ የሚገኙት የትድሀር ኤክስካቬሺን ኤንድ ኧርዝ ሙቪንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ዋና ሥራ አስኪያጅ እስራኤላዊው ሚናሼ ሌቭ ዮሴፍ፣ በሌላ የውጭ አገር እስረኛ ተደብድበው ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰባቸው ተጠቆመ፡፡
ሚስተር ዮሴፍ በእስር ላይ በሚገኙበት በአዲስ አበባ ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር እስር ቤት ውስጥ ታኅሳስ 13 ቀን 2008 ዓ.ም. ጉዳት የደረሰባቸው፣ የሱዳን ዜግነት ባለው ሌላ እስረኛ መሆኑን ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
የድብደባው ምክንያት እስካሁን አለመታወቁን የገለጹት የሪፖርተር ምንጮች እንደተናገሩት፣ ሚስተር ዮሴፍ ጭንቅላታቸውን በተደጋጋሚ ተመትተው ራሳቸውን በመሳታቸው ጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሪፈራል ሆስፒታል ገብተዋል፡፡
ተጐጂው በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል አንድ ቀን አድረው ታኅሳስ 14 ቀን 2008 ዓ.ም. ወደ ማረሚያ ቤት የተመለሱ ቢሆንም፣ በአንድ ጆሯቸውና በዓይናቸው ላይ የደረሰባቸው ጉዳት ስላለ በማረሚያ ቤቱ ክሊኒክ ውስጥ እየታከሙ መሆኑን ምንጮች ገልጸዋል፡፡
የተደብዳቢው ሚስተር ዮሴፍ ባለቤት ሚስ አናት ሌቪ ባለቤታቸው በጣም መጐዳታቸውን በመግለጽ፣ የባለቤታቸው ጉዳት መጠን ስለማይታወቅ መንግሥት ፈቅዶላቸው ወደ አገራቸው በመውሰድ እንዲያሳክሙ እየጠየቁ መሆኑንም ምንጮች አስረድተዋል፡፡ ማረሚያ ቤቱ ደብዳቢው ድርጊቱን ከፈጸመ ጊዜ ጀምሮ ለብቻው እንዳሰረውም ምንጮች ተናግረዋል፡፡
ሚስተር ዮሴፍ የተደበደቡበትን ምክንያትና ስለደብዳቢያቸው ለማወቅ፣ በኢትዮጵያ የእስራኤል የቀድሞ አምባሳደርና ሌላ እስራኤላዊ ታኅሳስ 15 ቀን 2008 ዓ.ም. ማረሚያ ቤት ሄደው የጠየቋቸው ቢሆንም፣ ከማረሚያ ቤቱ አስተዳደርና ከተጐጂው ስላገኙት መረጃ ከመናገር መቆጠባቸውን ምንጮች ተናግረዋል፡፡
በሚስተር ዮሴፍ ላይ ደርሷል ስለተባለው ድብደባና ጉዳት ማብራሪያ ለማግኘት፣ የአዲስ አበባ ማረሚያ ቤት ኃላፊዎችንና የሕዝብ ግንኙነት ባለሙያዎችን ለማግኘት የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡