“በኦሮሚያ ክልል እየሞቱ ያሉት አማሮች ገዳይ ወያኔ ነው ፤ አማራው ከኦሮሞው ጋር መተባበር አለበት” – ከቤተ አማራ ንቅናቄ የተሰጠ መግለጫ


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


ቁ፡ 1 12/14/2015

በወቅታዊ የኢትዮጵያ ጉዳዮች ላይ ከቤተ አማራ ንቅናቄ የተሰጠ መግለጫ

የአማራ ህዝብ ጀግኖች አባቶቹና እናቶቹ ከሌሎች አገር ወዳድ ወገኖች ጋር በመሆን ከመሰረቷት ብሎም በተከታታይ የደም እና የአጥንት ዋጋ ከፍለው ጠብቀው ካቆዩአት የገዛ አገሩ ለዘመናት በተሸረበ ሴራ ወደ ጎን በሃይል ተግፍትሮ የዜግነት መብቱን ከተገፈፈና በተከታታይ የዘር ማጥፋት ዘመቻ ሰለባ ከሆነ እነሆ 25 አመት ሊሞላው ነው። እስካሁን የተደረገው ግፍ አልበቃ ብሎ የዘር ማጥፋቱ እርምጃ በተፋጠነ ሁኔታ ሌት እና ቀን እየተሰራበት ይገኛል። የዚህ እኩይ አላማ ጠንሳሽ እና አስፈጻሚ በዋነኝነት አሁን አገሪቱን በመምራት ላይ ያለው ህወሀት ሲሆን በሂደት የሴራው ተካፋይ የሆኑ ብዙ ጥቅመኛ ቡድኖች ከጎኑ እንደተሰለፉ የሚታወቅ ነው። በዚህም ምክንያት ንጹሃን የአማራ ልጆች በጅምላ ተጨፍጭፈዋል፤ ተፈናቅለዋል፤ አገር ጥለው ተሰደዋል፤ ሀብት ንብረታቸውን ተዘርፈዋል፡፡ ይህ አልበቃ ብሎ መሬታቸው በየጊዜው እየተቆረሰ ላጎራባች ክልሎች እና ለሱዳን እየታደለ ይገኛል፡፡ በአጠቃላይ አማራ በአሁኑ ሰአት እንደህዝብ ከፍተኛ የሆነ እና አሳሳቢ የህልውና አደጋ ተጋርጦበት ይገኛል፡፡ የቤተ አማራ ንቅናቄ (ቤአን) የአማራውን ሰፊ ህዝብ ከዚህ ለአመታት እየተፈጸመበት ካለው ግፍ እና ከተደገሰለት ዘር ማጥፋት ዘመቻ ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ መላው የአማራን ህዝብ በማንቀሳቀስ የሚገላገልበትን መንገድ በመሻት አበክሮ በመስራት ላይ ይገኛል። ስለሆነም የቤተ አማራ ንቅናቄ ማእከላዊ ኮሚቴ የአገሪቱን ወቅታዊ ሁኔታ በጥልቀት ከገመገመ በኋላ ይህንን ባለ አራት ነጥብ የአቋም መግለጫ አውጥቷል፡፡

የአማራን ህዝብ እና መሬትን በተመለከተ

ወያኔ ገና የስልጣን በትሩን በጨበጠ ማግስት የወልቃይት እና የራያን አማሮች አጥፍቶ በተረፉት ላይም በግድ እንግዳ ባህል ጭኖ ለም መሬቶችን ሲወር ተው ባይ አካል በማጣቱ ተሟሙቆ ቋራን እና አርማጭሆን ብሎም ሰፊውን እና ታሪካዊዉን ጎንደርን አንድ መቶ ሃምሳ ሺህ በማይሞሉ ቅማንት ወገኖቻችን ስም አካሎ ቀስ ብሎም ወደ “ታላቋ ትግራይ”ለመጠቅለል ታላቅ ሴራ በመሸርብ ወንድማማች የሆነውን ህዝብ እያጫረሰ ይገኛል። በመቀጠልም አማራን አሳንሶ እና አደህይቶ ከጥቅም ውጭ ለማድረግ ታሪካዊና ለም የጎንደር መሬቱን ለሱዳን ለማስረከብ ጫፍ ላይ ደርሷል። በዚህ ጉዳይ ላይ የሰፊው አማራ አይኖች ጎንደር ላይ እንዲያተኩሩ ግድ የሚልበት ወቅት ላይ ነን፡፡ በጎጃም፤ በወሎ፤ በሸዋ፤ እንዲሁም በመላ ኢትዮጵያ እና በአለም ዙሪያ ያሉ አማሮች ጉዳዩን በአንክሮ እና በእልህ ሊመለከቱት ይገባል፡፡ ዝርፊያውን ለማክሸፍም የተቀናጀ ህዝባዊ እርምጃ ያስፈልጋል፡፡ ቤአን ይህን ትግል ለማስተባበር እና ግቡን እንዲመታ ለማድረግ ታከተኝ ሰለቸኝ ሳይል በሙሉ አቅሙ እንቅስቃሴ ላይ መሆኑን እየገለፀ በአገር ውስጥም ሆነ በውጭ ያለ ማንኛውም አማራ ሁሉ የአያት ቅድመ አያቶቹን ወሰን ላለማስደፈር እንዲታገል ጥሪውን ያቀርባል፡፡
በጎንደር እየተፈጸመ ስላለው የህዝብ እልቂት በተመለከተ

ግፈኛው የወያኔ አገዛዝ በተለያዩ የኢትዮጵያ ቦታዎች ዜጎች ላይ አማራ በመሆናቸው ብቻ ተደጋጋሚ ጥቃትና የዘር ማጥፋት ሲያካሂድ መቆየቱ አለም ያወቀው ጸሃይ የሞቀው ሃቅ ነው፡፡ ለዚህም በመተከል አካባቢ የተፈጸመው ግፍ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ሲሆን በአሁኑ ስዓት ደግሞ በጎንደር ልዩ ልዩ ቦታዎች የአማራን ደም እያፈሰሰ ዘሩን በማጥፋት ላይ ይገኛል ። በተያያዘ መልኩ አማራና ቅማንት በሚል አንዱን ህዝብ ለሁለት ሰንጥቆ እርስ በእርስ እያጫረሰው መሆኑ የአማራን ህዝብ ሰቆቃ እጥፍ ድርብ አድርጎታል ፡፡ ከዛም አልፎ ከቀናት በፊት ወደር በሌለው ጭካኔ እስረኞችን በጎንደር በአታ ወህኒ ቤት እና አንገረብ ላይ በሰራው አዲስ ተጨማሪ ማጎሪያ በእሳት አቃጥሏል፡፡ እነዚህን እስረኞች ከውስጥ በእሳት ከውጭ በጥይት አረር ቆልቷቸዋል፡፡ ይህም በናዚ ዘመን ከተፈጸመው የሰው ዘር እልቂት የከፋ ዘግናኝ ክስተት ሆኖ ተመዝግቧል፡፡

የኦሮሞ ህዝብ እንቅስቃሴን በተመለከተ

የቤተ አማራ ንቅናቄ (ቤአን) አሁን በኦሮሞ ህዝብ ላይ የተፈጠረው ችግር ምንጭ የወያኔው መንግስት ገና በጫካ ውስጥ እያለ የተጠናወተው የመሬት ዝርፊያ እና ወረራ አባዜው ነው ብሎ ያምናል። የመሬት ዝረፊያና “ፖቴንሻል ትሬት” ቅነሳ ዋና ዓላማው የሆነበትም ምክንያት ካለበት የአናሳነት ስሜት በመነሳት ተቀናቃኞቹን በሃይል እና በኢኮኖሚ ለማዳከም ነው፡፡ እጁን የፈታውም የአማራውን መሬቶች በመውረር እንደሆነ ይታወቃል። ወልቃይትን፤ ራያን እና መተከልን ከአማራ ወስዶ በጎሳ ቡድንተኝነት ለተሰባሰቡ የግፍ አገዛዙ አባላት ማከፋፈሉ የሚታወስ ነው፡፡ ይህንን የመሬት ወረራ ጥሙን ለማርካት ሲል የአዲስ አበባ ከተማ ማስፋፊያ ማስተር ፕላን እያለ በዙርያው ያሉ የኦሮሞ አርሶ አደሮችን ሊያፈናቅል ሲንቀሳቀስ የተቃወመውን ህዝብ በህጋዊ መንገድ ማስተናገድ ሲገባው ከፍተኛ የህወሓት ወታደራዊ ሃይል በመጠቀሙ ሽብር ፈጥሮ የብዙ ሰዎችን ህይወት እያጠፋና ንብረት እያወደመ ይገኛል፡፡ በዚህ ሁኔታ ከልብ እያዘን ከዚሁ የአገዛዙ ሽብር ጋር ተያይዞ በኦሮሞ አካባቢ የሚኖሩት የአማሮች ደህንነት ጉዳይ እጅግ በጣም አሳስቦናል። የአማራ ደም ሲፈስ ካላየ የማይረካው ወያኔ አጋጣሚውን በመጠቀም እንደለመደው አማራን ራሱ እዬገደለ “ኦሮሞ ገደለ” በማለት ላይ ነው። በጥብቅ መታወቅ እና መሰመር ያለበት ትልቅ ጉዳይ ግን ደማቸው የሚፈሰው ወገኖቻችን የሚገደሉት በወያኔ ብቻ መሆኑ ነው። ወያኔ ራሱ ባይገድላቸው እንዲሁ በግርግር መሃል ቢሞቱ እንኳ ተገቢውን ጥበቃ ስላላደረገ ዜጎቻችንን ሊጠብቅ ባለመቻሉ ለሚችል ሌላ አካል በቶሎ ስልጣን ማስረከብ አለበት ብለን አስረግጠን እንናገራለን። መልካም አስተዳደር ቢቀር የንጹሃን ዜጎችን ደህንነት መጠበቅ ያልቻለ አገዛዝ አንድም ቀን ስልጣን ላይ ማደር የለበትም። መንግስት ነኝ ብሎ የተቀመጠው ወያኔ እንጅ የኦሮሞ ተማሪዎች እና ገበሬወች ስላልሆኑ ለእያንዳንዷ የአማራ ህይዎት መጥፋት ተጠያቂው ራሱ ወያኔ መሆኑ በሁሉም ዘንድ ግንዛቤ ሊወሰድበት ይገባል፡፡ ማንኛውም የአማራ ተወላጅም በኦሮሞ ምድር ደም የሚያፈሰው ራሱ ወያኔ መሆኑን አውቆ ባመቸው መንገድ እንዲታገል እና ገዳዮችን ጊዜው ሲደርስ ለፍርድ ለማቅረብ ያመች ዘንድ ማስረጃ የመሰብሰብ ስራ መስራት አለበት፡፡ አሁን ወያኔ “የአማራ ክልል” ብሎ ባጠረው ምድር የሚኖረው አማራም በኦሮሞ አካባቢ ግፍ እየተፈጸመባቸው ለሚገኙ ወገኖቹ የወንድማዊነት አለኝታነቱን ማሳዬት ይጠበቅበታል፡፡ የኦሮሞን ህዝብ ትግል የሚመሩ አካላትም የገዳይ ወያኔዎችን ማስረጃ በመሰብሰብ ለአማራ ወንድሞቻቸው በማስተላለፍ እንዲተባበሩ ያስፈልጋል፡፡ በዚህ አጋጣሚም ቤአን በመላ አገሪቱ የሚኖር አማራ ሁሉ ደህንነቱን የሚጠብቅለት መንግስት እንደሌለው አውቆ ራሱን እያሰባሰበና እያደራጀ ራሱ በሚመርጠው የጎበዝ አለቃ እየተመራ የራሱን ጠባቂ ጊዜያዊ የራስ አድን ኃይል እንዲያቋቁም ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

ድርቅ እና ርሃቡን በተመለከተ

የወያኔው ገዥ ቡድን የጭካኔው መገለጫ ብዙ ነው። አሁን እጃችን ላይ ያለው ማስረጃ እንደሚያረጋግጠው ደግሞ ሕዝባችን እጂግ የከፋ የርሃብ አደጋ ውስጥ ነው። ከ 15 ሚሊዮን በላይ ኢትዮጵያውያን በረሃብ አለንጋ እየተገረፉ እና ከነዚህም ውስጥ ብዙዎች በሞት እያሸለቡ ፣ ባእዳን መንግስታት ሳይቀሩ እርዳታ ለማቅረብ እየተሯሯጡ ባለበት ሰአት የማስተር ፕላን ፖለቲካ፤ የሱዳን ድንበር ማካለልና፣ የቅማንት ማንነት እያለ ህዝቡን እርዳታ አልባ ሆኖ እንዲያልቅ እያደረገው ይገኛል ። በመሰረቱ እነዚህ ነገሮች ረሃብ እና ቸነፈር በሌለበት ብሎም ሰላም በሰፈነበት ሁኔታ ውስጥ ዜጎች ከላይ እስከታች መክረው እና ዘክረው የሚወስኗቸው ሁኔታዎች ሆነው እያሉ ግፈኛው አገዛዝ ግን በማናለብኝነቱ ቀጠለበት፡፡ ቤአን የወያኔው ገዥ ቡድ ከሽብር ተግባሩ ባስቸኳይ ታቅቦ በረሃብ ሰበብ በሞት አፋፍ ላይ ላሉ አማሮች እና ሌሎች ህዝቦች ተገቢውን የምግብ እርዳታ በጊዜ ማድረስ ግዴታው መሆኑን ያሳስባል።

ድል ለአማራ ህዝብ!
ቤተ አማራ ወደፊት!

የቤተ አማራ ንቅናቄ (ቤአን)