መንግስት የአዲስ አበባን ማስተር ፕላን ለህዝብ ይፋ የሚደርግበትን ፕሮግራም ሰረዘ፤
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
ሰሞኑን በኦሮሚያና ሌሎች ክልሎች ባሉ ዪኒቨርስትዎችና ት/ቤቶች የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ተግባራዊነት ጋር ተያይዞ የተነሳውን ተቃውሞ ተከትሎ መንግስት በተማሪዎች ላይ አሰቃቂ እርምጃ እየወሰደ ተቃውሞውን ለማፈን የሚቻለውን ሁሉ እያደረገ ቢሆንም ከዚህ በፊት ‹‹ማንም የማስተር ፕላኑን ተግባራዊነት አያስቀረውም›› ካለው አቋም እንዲያፈገፍግ የተገደደበት ሁኔታ መኖሩን የከተማ ልማትና ቤት ሚ/ር ውስጥ አዋቂ ምንጮች ገልጸዋል፡፡
ለዚህም ባለፈው ሳምንት የከተማ ልማትና ቤት ሚ/ር ከአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጽ/ቤት ጋር በመሆን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተገኙበት በአፍሪካ ኅብረት የስብሰባ አዳራሽ ለሚከናወነው ፕላኑን ለማስተዋወቅ የተዘጋጀው ፕሮግራም ለባለድርሻ አካላት ጥሪ ከተላለፈ፣ የአዳራሽና መስተንግዶ ቅድመ ክፍያ ከተከፈለና አስፈላጊው ዝግጅት ከተጠናቀቀ በኋላ ፕሮግራሙ እንዲሰረዝ መደረጉን በማስረጃነት አቅርበዋል፡፡
ምንጮቹ ህወኃት መራሹ መንግስት ይህንኑ የአዲስ አበባ ማስፋፊያ ማስተር ፕላን የሚያስፈጽም ጽ/ቤት አደራጅቶ ለሁለት ዓመታት ዝግጅት ሲያደርግና ተፈጻሚነቱ በምንም መንገድ አይደናቀፍም ሲል ከርሞ አሁን የተነሳውን ህዝባዊ እንቅስቃሴ ተከትሎ በአደባባይ በተደጋጋሚ የገለጸውን ይህን ሃሳብ ቀይሮ ቀድሞውኑ ፕሮግራሙ የአዲስ አበባና የኦሮሚያ ልዩ ዞን የተቀናጀ ልማት ማስተር ፕላን እንጂ የአዲስ አበባ ማስፋፊያ ማስተር ፕላን አልነበረም ለማለት መገደዱን በተጨማሪ ማስረጃነት ያቀርባሉ፡፡
እነዚሁ ምንጮች – ይህንኑ እንዲያስፈጽም የተቋቋመው የአዲስ አበባ ማስተር ፕላን ጽ/ቤት ኃላፊ የሆኑት አቶ ማቴዎስ በአሁኑ ጊዜ ውጪ አገር እንደሚገኙና ከሄዱበት መመለሰ/አለመመለሳቸው እንዳልታወቀ ጨምረው ገልጸዋል፡፡ ምንጮቹ ህዝባዊ እንቅስቃሴው ይህ የማስተዋወቂያ ፕሮግራም (ለጊዜውም ቢሆን?) እንዲሰረዝ ማድረግ ቢችልም ይህ በአገራችን ካለው የህወኃት ፍጹም የበላይነት አምባገነናዊ የጠቅላይነት አገዛዝ አንጻር ዘላቂ ውጤት ያለመሆኑንና እነዚህ የፊንፊኔ ልዩ ዞን ከተሞች ቀርተው ታላላቅ የኦሮሚያ ከተሞች( አዳማ፣ ጂማ፣ ሻሸመኔ፣ጭሮ፣ ነቀምት፣…) እና ኦሮሚያ ክልል በአጠቃላይ በህወኃት ቁጥጥር ሥር መሆናቸውን አስታውሰው ይህ አጠቃላይ የስርዓት ለውጥ ጥያቄውንና የአንድነትና የዲሞክራሲ ግንባታ ትግሉን እንዳያዘናጋ ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡
ምንጮቹ በቀጣይ ከዚህ ሂደት ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን እየተከታተሉ ለህዝብ እንደሚያደርሱ ቃል ገብተዋል፡፡