ብልሹ አስተዳደርን የዴሞክራሲ ምህዳር በማስፋትና በተቋማት ግንባታ (ሜ/ጄ አበበ ተ/ሃይማኖት “ጆቤ”)


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


የሜ/ጄ አበበ ተ/ሃይማኖት በጣም ረጅም ፅሁፍ በርካታ ሂሶችን ያነሳ ነው! የህወሕት ልሳን በክልልና የፌደራል ተቇማት ስፖንሰር እየተደረጉ ተቃዋሚዎችን እንደሚወነጅሉ መከላከያው በፖለቲካው እንደተዘፈቀ ይተቻል! ፍርድ እንደጠፋ ይሄሳል! መቶ ፐርሰንት አስቂኝ ብቻ ሳይሆን አደገኛ ነው ይላል! እውን ኢትዮጵያ ፓርላማ አላት? ብሎ ይጠይቃል! ለስርዓት ቅርብ እንደመሆናቸው የሚያሞግሱት ብዙ ቢሆንም ትችቱ ቀላል አይደለም!መልካም ንባብ ምንጩ ዳንኤል ብርሃኔ ብሎግፖስት ነው::

Highlights:-

* በዴሞክራታይዜሽን እና ኢ-ዴሞክራታይዜሽን ሂደቶች ሁሌም መሳሳብ እና ዉጥረት ይኖራል። መንግስት እንደ መንግስት ግን የዴሞክራታይዜሽን አጋዥ አልያም የኢ-ዴሞክራታይዜሽን አሳላጭ ነው መሆን እሚችለው፤ መሀል ላይ የሚንገዋለል መንግስታዊና ተቛማዊ አቛም ሊኖር አይችልም።

* ባጠቃላይ ሲታይ ብዙ ማንነቶች፤ በርካታ ፖለቲካዊ ፍላጎቶች፤መልስ እንሻለን የሚሉ የተለያዩ ጥያቄዎች ባሉበት አገር አንድ ግንባር (ኢህአዴግ) እና አጋሮቹ 100% መቀመጫውን መቆጣጠር እሚያሳየን ነገር፤አንድም ባጠቃላይ ፖለቲካዊ ስርዓቱ ላይ ችግር መኖሩን አልያም የምርጫ ስርዓቱ ችግር እንዳለበት ወይም ተግባራዊነት ላይ ችግር እንደነበረበት ነው፤ 100% እሚባል ውጤት አስቂኝ ግን ደግሞ አደገኛ ነው ፡፡ ይሄ ዉጤት አርቆ ለሚያስብ ሰው የአደጋ እንጂ የድል ምልክት ተደርጎ መቆጠር አይችልም። መሬት ላይ ያለዉን የተለያየ ፖለቲካዊ ፍላጎት እማያንፀባርቅ የምክር ቤት ሁኔታ የስጋት እንጂ የኩራት ምንጭ መሆን አይችልም።

* ዲሞክራሲያዊ ምህዳሩ በጠበበ ቁጥር የዜጎች ተስፋ እተሟጠጠ ስጋታቸው እና ፍርሃታቸው እየጨመረ ከቁጥጥር ውጪ የመሆኑ እድል ይሰፋል፡፡ ይህን መሰል ሁኔታም ከውስጥም ከውጪም ለነሱ ለሚችሉ ፅንፈኛ ሃይሎች ምቹ ሁኔታ ስለሚፈጥር አገሪትዋን ወደላስፈላጊ መንገድ ሊመራ ይችላል፡፡ ፍትህ ተራ ፍርድ የማግኘት ጉዳይ አይደለም፡፡ ፍትህ የማህበራዊ ተቛም የመጀመርያ ፀጋው ነው ይላል ጆን ራዉልስ፡፡ ሙስናና መልካም ያልሆነ አስተዳደርም ሃገርን ሊበትን የሚችል፤እየታየ ያለውን ኢኮኖሚያዊ እድገት ገደል የመክተት አቅም ያላቸው ስርዓታዊ በሽታዎች ናቸው፡፡የሶስቱም እናት ደግሞ የጠበበ ወይም የኮሰመነ የዲሞክራሲ ምህዳር ነው፡፡

* ከባዱ ስራ ግን ቀጥሎ መከሰት ያለበት እርምጃ ላይ ነው፤ከባድ እና ውስብስብ እሚሆነብት ምክኒያትም ትግሉ ከሞላ ጎደል ግልፅ ከሆነ ዉጫዊ ሃይል ወይም ተቛም ጋር ሳይሆን ከገዢው ፓርቲና መንግስታዊ መዋቅር ይዘው ከሚገኙ አመራር እና የነሱ ተባባሪዎች ጋር መሆኑ ነው።

* በተለይ ከ 10ኛው የኢህአዴግ ጉባኤ ማግስት በአንድ በኩል የመቀዛቀዝ በሌላ በኩል ደግሞ ችግሮች ቢኖሩም ብዙ እሚያስጨንቁ አይደሉም የማለት እና የማጣጣል አዝማምያዎች እየታዩ ነው። ጠቅላይ ሚንስቴር ሃይለማርያም ደሳለኝ ምክርቤቶችን አስመልክተው፤ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስቴር አቶ ደመቀም ሚድያን አስመልክተው የተናገሩት ነገር ገምቢ እና አበረታች ቢሆንም ሌሎች የመንግስት አካላት ግን ችግሩ ቀለል አድርገው ሲመለከቱ እያየን ነው።

* ያገሪትዋን ከፍተኛ ስልጣን በህገ መንግስት የተረጋገጠለት ተቋም አሁን ያሉት አማራጮች ሁለት ናቸው፡፡ አንደኛው አማራጭ ህገ መንግስታዊ ስልጣኑን ተጠቅሞ የዜጎችን ጥቅም ማስከበር ሁለተኛው አማራጭ ህገ መንግስታዊ ስልጣኑን መጠቀም እማይቻል እና የህዝባችን አደራ መሸከም ካልቻለ ያገሪትዋን ሃብት ያላግባብ ከሚባክን ህዝበ ውሳኔ አዘጋጅቶ አይረቤነቱን ህጋዊ ድጋፍ ሰጥቶ ተቋሙን ማፍረስ፡፡

* [ወይን መፅሄት በ ሃምሳኛ እትሙ] የትግራይ ህዝብ እየለበለበው ያለዉን የብልሹ አስተዳደር ችግር እያለ እንደ ድሮ መሳፍንት ‘ራስ እገሌ ከ እገሌ ይበልጣል’ ዓይነት ፅሁፍ ይዞ መዉጣቱ በጣም የሚያሳፍር ነው። መወየን ተራማጅነትን የሚገልፅ ቢሆንም እየተደረገ ያለው ግን የ አድሃርያን ተግባር ነው፤ ወያነነቱም የት ሄደ? ያስብላል። ለመሆኑ ወይን በስራ ላይ ካሉት ኢታማዦር ሹም ምን ቢፈልግ ነው የህዝቡን ድምፅ ማሰማት ሲገባው ወደ ወረደ መሳርያነት ራሱን ያሸጋገረው? ፖለቲካዊ ዘመቻም ከሆነ ጡረታ ሲወጡ ያደርግላቸዋል። ሁለቱም ኢታማዦር ሹሞች የየራሳቸው እና የጋራ የሚያኮራ ታሪክ እያላቸው የ ‘አንዱ ይበልጣል’ ንፅፅር ምን አመጣው?

* ወይን መፅሄት “አብ መከላኸሊ ሓይሊ እዉን ክግበር ዝኽእል ዘይሕጋዊ መማረፂታት እንተልዩ ምሕሳብን ምፍታንን ጀሚሮም” ይላል። ትርጉም “በመከላከያ ሃይል ዉስጥም ማድረግ እሚቻል ህጋዊ ያልሆነ አማራጭ ካለ ብለው ማሳብና መሞከር ጀመሩ” ይላል። ለሌተናል ጄኔራል ፃድቃን እና እኔ ባለፉት ወራት አንዳንድ ከትጥቅ ትግሉ ጋር የተያያዘ የምናውቀዉን ፅፈን ነበር፤ ሰው ሊስማማ ላይስማማ ይችላል። የሚገርመው ግን ወይን ወይም ስፖንሰሮቹ “ህገ ወጥ ድርጊት በማስብ እና በመሞከር” ብለው ለማስፈራራት የሞከሩት ነገር ነው። ከአስራ አምስት ዓመት በኃላ ይህ ማስፈራርያ ለምን መጣ? አርፋቹህ ተቀመጡ ለማለት ነው? ወይንና ‘እማይታወቀው’ መሐመድ በወቅቱ የነበሩት ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ (ነብሳቸው ይማርልን) እያወቁ “ምህረት” አድርገዋል፤ አሁን ግን የሚምራቹህ ሰው የለም እያሉን ይሆን እንዴ ?

* ጠንካራ የሃገር መከላከያ የዴሞክራሲያዊ ስርዓታችን ዘበኛ ቢሆንም፤ ከልክ በላይ ካበጠ ግን የ ኢ-ዴሞክራስያዊ ሃይሎች መሳርያ ስለሚሆን በዚህ ረገድ የተሰማሩ ሙሁራን ወታሃደራዊ ክፍሉ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ወይ ቅልበሳ (democratization and de-democratization) ላይ የሚኖረዉን ሚና እንዲያጠኑት መንግስት ሁኔታዎችን ማመቻቸት አለበት፤

* የህወሓት 40ኛ አመት በትግራይ ቴሌቪዥን የወራት ሙሉ ሽፋን እንዲሁም በኢቢሲ (EBC) ላቅ ያለ ሽፋን የተሰጠው የምርጫ ተፎካካሪ ፓርቲዎች ትንፋሽ ለመተንፈስ እንኳ የማትበቃ ጥቂት ደቂቃ በተመደበላቸው የምርጫ ወቅት መሆኑ ስንገነዘብ ነው የመንግስትና የህዝብ የመገናኛ ብዙሃን ባህሪ እና ማንነት መረዳት እምንችለው፡፡ እስኪ ህወሓት በትግራይ ቴሌቪዥን እና EBC ላሰራጨው የወራት ፕሮግራም ክፍያ ፈፅመዋል? ቢፈፅምስ ይህ ተገቢ ተግባር ነውን?

* ይህ የተጠቀሰው ዶክመንት በገፅ 123 ላይም እንዲህ ይላል “መላውን ህዝብ /አብዛኛው ክፍል/ ለአመታት ለአንድ ፓርቲ አመለካከት በማጋለጥ፣ ሌሎችን በመከላከል የሚደረግ አሰራር መከተል በሃሳቦች መካከል ነፃ ውድድር እንዳይኖር የሚያደርግ ነው የሃይለስላሴና የደርግ መንግስታት ይህም ማድረጋቸው የሚያመላክተው ፀረ ዴሞክራስያዊ ባህርያቸው ነው” (ኢህአዴግ፣ 1992 ዓ.ም ገጽ 123) ።

ንዑሳን-ርዕሶች
1. መግቢያ
2.ችግሮቻችን ምንድን ናቸው? መልካም አስተዳደር የወቅቱ ቁልፍ ችግር
2.1 በአሁኑ ግዜ የችግሮቻችን አውራ መልካም አስተዳደር ያለማስፈን ችግር ነው ተብሏል፡፡ ለመሆኑ መልካም/ዴሞክራስያዊ አስተዳደር ምን ማለት ነው?
2.2.የመልካም/ ዴሞክራስያዊ አስተዳደር ችግሮች ስፋትና ጥልቀት
3. የችግሮቻችን መሰረታዊ ምንጭ ምንድን ነው?
4. በኢህአዴግ እሚመራው መንግስት የዴሞክራሲ ምህዳሩ በማስፋት መልካም አስተዳደርን ለምን አላረጋገጠም?
5. የመፍተሄ ሀሳቦች
5.1 ጠንካራ ተቛማዊ ስብእና (Strong Institutional Integrity)
5.2 ምክር ቤቶች የዴሞክራስያዊ እንቕስቃስያችን ወሳኝ አምዶች ናቸው
5.2.1 ህገ መንግስታችን እና የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት
5.2.2 የተወካዮች ምክርቤት ዓይነቶች
5.2.3 የተወካዮች ምክር ቤት እውነተኛ ገፅታ
5.3 የመገናኛ ብዙሃን
5.4 የአንድ ለአምስት ተቋም
6. ንቅናቄው እንዴት ይቀጣጠል?
– ማህበራዊ ንቅናቄ (Social Movement) ምንድን ነው?
የግል መልእክት
– ዋቢ ምንጮች

1.መግቢያ

በኢህአዲግ የሚመራው የኢትዮጵያ መንግስት “ሩቅ አስባ ሩቅ ለመደር እየተጋች ያለች አገር” በሚል መሪ ቃል ስር ላሳካዉ አንፃራዊ መረጋጋት እና ተጠቃሽ ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት ምስጋናየ ላቅ ያለ ነው፡፡ይሄም ስኬት ኩሩው የኢትዮጵያ ህዝብ ደስተኛ እንዲሆን እና ወጣቱም ተስፈኛ እንዲሆን እያስቻለው ነው፡፡ ባለፈው አስር ዓመት ኢትዮጵያ ከአለማችን ፈጣን ኢኮኖሚዎች በመጀመርያ ረድፍ እምትጠራ አገር ሁናለች። ይህ ፈጣን የኢኮኖሚ እድገትም ተጨባጭ እና ሊካዱ እማይችሉና እሰየው እሚያስብሉ ልማታዊ እና ማህበራዊ ለውጦችን አስከትልዋል። ከሞላ ጎደል የተሳካው የምእት አመቱ የልማት ግቦች፣ እንደ ህዳሴው ግድብ አይነት ታላላቅ ፕሮጀክቶች፣ እየተሳለጡ ያሉ ሰፋፊ የሱካርና የማዳበርያ ፋብሪካዎች ተከላ ሲታይ ይህን እዉን ያደረገዉን መንግስት እና አመራሩን ማመስገን ተገቢ ነው ብየ አምናለሁ።

በቅርቡ ጠቅላይ ሚንስቴር ሃይለማርያም ደሳለኝ ያገኙት የ South-South ሽልማትም የዚህ ጥረት ማሳያ ነው፤ ክቡር ጠቅላይ ሚንስቴር እኔም እንዃን ደስ አልዎት ማለት እፈልጋለሁ። የእድገት እና ትራንስፎርሜሽን አንድ (GTP 1) አጠቃላይ አገራዊ ያፈፃፀም ደረጃዉም አበረታች ነበር ማለት ይቻላል፤ በክልሎች መሃል ሊታረም እሚገባው አለመመጣጠን እንዳለ ሆኖ ማለት ነው። በኢኮኖሚው መስክ አገራችን ኢትዮጵያም ገፅታዋንም በፍጥነት እየቀየረች ትገኛለች። GTP 1 አስፍቶ ማስብን እና አግዝፎ መስራትን ያስተማረ እቅድ ስለነበር እያንዳንዱ ዜጋ ላይ የፈጠረው መነሳሳት እንደ ቀላል የሚታይ አይደለም። የተለጠጠ እቅድ ይዘህ እጅግ በጣም ብዙ አልመህ ብዙ ብትሰራ በ ፐርሰንት ሲታይ ትንሽ ቢመስልም ትንሽ አቅዶ እስዋን ብቻ ከማሳካት ግን ሺ እጥፍ ይሻላልም ይበጃልም። ስለዚ ambitious ፕላን መሆኑ ሊደነቅ ይገባዋል። ክጀርባው ያለው እሳቤም ማደግ ካለብን ማህበረ ኢኮኖምያዊ ሽግግር ያስፈልገናል ይህ ለማድረግ ደግሞ ተለቅ ያለ ስራ መስራት አለብን ነው። ይሄም በጎ እሳቤ ነው። ትልቅ ነገር ሳያስቡ ትልቅ አገር መገንባት አይቻልም። ባጠቃላይ በትምህርት መስፋፋት (በተለይ የከፍተኛ ትምህርት ተቛማት መስፋፋት)፣ በጤና ኬላዎች መዳረስ፣ ለ አርሶ እና አርብቶ አደሩ የሚደረጉ ድጋፎች፣ ስፋፊ የትራስፖርት አውታሮች ያሳካ የኢኮኖሚ እድገት፣ ሃብታም ገበሬዎችን መፍጠር የቻለ ግብርና፣ ብዙ ወጣቶችን የፈጠራ እና የሃብት ባለቤት ማድረግ የቻለ ጉዞ ተገቢ እዉቅና ማግኘት አለበት። የኢንዱስትሪ ክፍሉም በብዙ ችግሮች የተሞላ ቢሆንም መንግስት ለዘርፉ የሰጠው ትክረት የላቀ መሆኑ ሊደነቅ ይገባል።Photo - General Abebe Teklehaimanot

አንፃራዊ ሰላም እና መረጋጋት በማስፈን እና ሰላም ላጡ ህዝቦች የሰላም ሃይል በመሆን እሚደረገው የዲፕሎማሲ እና የመከላከያ ሃይላችን ጥረትም እጅጉን እሚመሰገን ነው።ኢትዮጵያ ላይ የሰፈነው አንፃራዊ ሰላም እና መረጋጋት ዝቅ ተደርጎ ሊታይ እሚችል አይደለም፤ እነ ሶርያ እና ሊብያ ከነ ሙሉ ሃብታቸው ምን አይነት ሁኔታ ላይ እንዳሉም መርሳት የለብንም። እነ ኬንያ እና ሶማልያ በአሸባሪዎች ሲታመሱ በሰላም ተኝተን እምናድረው የሰፈነዉን አንፃራዊ ሰላም ተማምነን ነው። ዋናው የሰላማችን ምንጭ ህገ-መንግስታዊ ስርዓታችን ቢሆንም የፀጥታ ሀይሎቻችን ልዩ ምስጋና ይገባቸዋል፡፡

በተለይም ትህዴንን (TPDM ) ለአዲስ ዓመት ስጦታ በማበርከታቸው አድናቆቴን መግለፅ እወዳለሁ፡፡ በተጨማሪም ከአባይ ወንዝ አጠቃቀም ጋር ተያይዞ የሚታየው የሶስትዮሽ ስምምነትም የኢትዮጵያ መንግስት አስተዋይነት እና ለብሄራዊ ጥቅሙ ያለው ተቆርቛሪነት ያረጋገጠበት ድርጊት ተደርጎ ሊቆጠር እሚገባው ነው።ተስፋ ሰጪ በሆነው አጠቃላይ እንቅስቃሴ ምክንያት የተፈጠረው አገራዊ የህዳሴ መንፈስም ከምንም ሳይሆን መሬት ላይ ካለው እዉነታ የሚመንጭ አወንታዊ ቁጭት ስለሆነ ለለዉጥ ጉዞው እጅግ ጠቃሚ ግብአት ነው። ይሁን እንጂ የኑሮ ውድነት እጅግ እየሻቀበ በመሄዱና በሃብታምና ድሃ ያለው ልዩነት በዚህ ፍጥነት ከቀጠለ አድገኛ ስለሆነ ተገቢ እርምት መወሰድ አለበት እላለሁ፡፡

ልማታዊ ስኬቶቹ የመንግስትን ልማታዊነት ያሳያሉ ማለት ግን ዴሞክራስያዊነቱን ይገልፃል ማለት አይቻልም። ባጭሩ ሰላማዊ እና ልማታዊ ማለት ዴሞክራስያዊ ማለት አይደለም።ዴሞክራስያዊ ድባቡ እየሰፋ ነው ወይስ እየጠበበ ነው? የሚለው ማየት ተገቢ ነው። ይህን ለመመለስ መለከያ ያስፈለገናል፡፡ መመዘኛችን ህገ-መንገስታችን፤ የመንግሰትና የገዢው ፓረቲ አቑዋሞች መሰርት አድርገን ብናየው ስርኣቱን በበለጠ ለማየት ያስችለናል ብየ እገምታለሁ፡፡ “በትግላችንና በከፈልነው መስዋዕትነት የተገኘውን ዴሞክራሲና ሰላም ዘላቂነቱ ለማረጋገጥ” እና ለሌሎች ተዛማጀ “ዓላማዎችና እምነቶች ማሰርያ” እንዲሆን ህገ መንግስቱ መፅደቁ መግብያው ላይ ሰፍሮ እናገኛለን። ለዚህም ነው ሰላማችንንና ዴሞክራስያችንን ዘላቂነቱን ለማረጋገጥ የሚደረግ ጥረት ህገ-መንግስቱን ለማረጋገጥ የሚደረግ ጥረት ነው የምለው።

በ 1994 ዓ.ም የማስታወቅያ ሚንስቴር “በኢትዮጵያ የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ጉዳዮች” በሚል ርእስ ባሳተመው ፅሁፍ ‘ዴሞክራሲና መልካም አስተዳደር የህልዉና ጥያቄ ነው’ ይላል።ይህ ሰነድ የተሟላ የዴሞክራሲ አስተሳሰብ የተቀመጠበት በመሆኑ የመመዘኛችን መነሻ እነዲሆን ወድጅያለሁ፡፡ ሰነዱ ዘርዘር አድርጎ የተመለከታቸው የዴሞክራሲ ተቛማት ብዙ መሆናቸው መገንዘብ ይቻላል። ይሄው የ 1994ቱ ሰነድ ምክርቤቶችን በተመለከተ እንዲህ ይላል “ምክር ቤቶች የህዝቡ ሉአላዊነት መገለጫ የዴሞክራስያዊ አስተዳደር እምብርትና የዴሞክራስያዊ አገዛዝ አውራ ተቛሞች ናቸው” ይላቸዋል። ሆኖም መሬት ላይ ያለው እውነታው ግን ከዚህ የራቀ ይመስላል። ለምን?

በተመሳሳይም በ 1992 ዓ.ም ለውይይት በተዘረጋው የኢህአዴግ ፅሁፍ ላይ ትምርህርት ቤቶችን በተመለከተ እሚከተለው ሰፍሮ እናገኛለን “ትምህርት ቤቶችን ወደ ኢህአዴግ ትምርህርት ቤትነትን ለመቀየር የማይቻል ከመሆኑም በላይ ሃቀኛ ዴሞክራስያዊም አይሆንም። መላዉን ህዝብ /አብዛኛው ክፍል/ ለአመታት አንድ ፓርቲ አመለካከት በማጋለጥ፣ ሌሎችን በመከላከል የሚደረግ አሰራር መከተል በሃሳቦች መካከል ነፃ ዉድድር እንዳይኖር የሚያደርግ ነው። የሃይለስላሴና የደርግ መንግስታት ይህን ማድረጋቸው የሚያመላክተው ፀረ ዴሞክራስያዊ ባህሪያቸዉን ነው።” አሁንም እውነታው ከዚህ የራቀ ይመስላል።ለምን?

ከአምስት ዓመት በኃላ በ 1999 ዓ.ም የመልካም አስተዳደር ችግር ፈጦ የወጣ ችግር ነው የሚል ድምዳሜ ላይ ደርሶ ከስረ መሰረቱ እንፈታዋል ተብሎ ተዝምሮለትም ነበር። ነበር ሆኖ ቀረ!! አሁንም በ 2007 ዓ.ም መጨረሻ ኢህአዴግ መልካም አስተዳደር ዋናው ችግሬ ነው እያለ ነው። ይህ ለምን ሆነ? የዚህ ፁሁፍ አላማም ለምን ይህ ችግር ሳይቀረፍ አለ ከተባለበት ግዜ ምንም መሻሻል ሳያሳይ እንደዉም ለምን እየተባባሰ እንደመጣ ለማሳየት እና የመፍትሄ ሃሳቦችን ለመጠቆም ነው።

ኢህአዴግ በኢኮኖሚው መስክ ከሞላ ጎደል ያለመዉን እያሳካ ይታያል፤ ከዴሞክራሲ አዃያ ግን እግሩ ሲጎተት መመልከት የተለመደ ሁነት ከሆነ ሰነባብቷል። በዚህ ዙርያም በዴሞክራሲው መስክ ችግሮች እየታዩ ነው ብሎ ኢህአዴግ በ 1992-93 ዓ.ም ከገመገመበት ወቅት እስከ አሁንዋ ሰዓት ይህ ነው ሊባል እሚችል የሰፋ የዴሞክራሲ ድባብ ሳይፈጠር ካለንበት ደረጃ ላይ ደርሰናል።ችግሩ የክልስ ሃሳብ አለመሆኑ ሰነዶችን በመመልከት መገንዘብ ይቻላል።

GTP 1 በሚፈለገው መጠን እና ፍጥነት እንዳይሳካ ካደረጉት ምክንያቶች የመልካም አስተዳደር ችግር በዋናነት መጠቀስ ይቻላል። ካጠቃላይ የዴሞክራሲ ድባብ መጥበብ ጋር ተያይዘው የሚከሰቱ የመልካም አስተዳደር አለመኖር፣ የሙስና እና የፍትህ መጏደል ናቸው የGTP 1ን አፈፃፀም በሚፈለገው ፍጥነት ያላስኬዱት። መልካም/ዴሞክራስያዊ አስተዳደር ማስፈን ከተበላሸ/ ካልተቻለ GTP 2 አይሳካም ብቻ ሳይሆን ከዚህ በፊት አገራችን የሰራቻቸው የሚያፈርስ፣ሰላማችን እና መረጋጋታችን እንድናጣ የሚያደርግ በመሆኑ እዛ ላይ አተኩሬ ትዝብቴን እገልፃለሁ። ይህ ፅሁፍ በጥልቀት በተሰራ ጥናት እና ምርምር ሳይሆን ባጠቃላይ ቅኝት (General Observation) የተሞረኮዘ ሲሆን፤ የማነሳው ጉዳይ ሰፋ እና ዘርዘር ያለ ምርምር እንደሚያስፈልገውም መጠቆም እወዳለሁ። በጥልቅ ጥናት ላይ ያልተመሰረተ በመሆኑ አንዳድ ሁኔታዎችን በሚገባ ያልገለፅኩት ካለ ወይም በጣም ካጋነንኩት አንባብያንን ከወዲሁ ይቅርታ እጠይቃለሁ።

የዚህ ፅሁፍ ፀሀፊ በዲሞክራሲ ዙሪያ የሚታዩ እጥረቶች (Democratic deficiency) የችግሮቹ መንስኤዎች ሲሆኑ ቀጣይነት ያለው የተሟላ ዲሞክራሲያዊ እና ህገመንግስታዊ ተቋማት መገንባት ደግሞ መፍትሄዎቹ ናቸው ብሎ ያምናል:: ለዚህ ፅሁፍ ሲባል የህዝብ መወከያ ተቋማት (ፓርላማ እና በሁሉም ደረጃ የሚገኙ ምክርቤቶች)፤የመገናኛ ብዙሃን እና የአንድ ለአምስት አደረጃጀት ልቃኝ መርጭያለሁ፡፡ የፁሁፉ አወቃቀር እንደሚከተለው ይሆናል፤ በመጀመርያ አሉ ያልኳቸዉን መሰረታዊ ችግሮቻችንን ከዘረዘረ እና በሁለተኛው ክፍል ዋና መንስኢዎቻቸው ላይ ገለፃ ካድረገ በኃላ በሶስተኛው ክፍል ቀጣይነት ያለው የዴሞክራሲ ግምባታ የችግሮቻችን መፍትሄ የሚል ርእስ ላይ ያተኩራል። በመጨረሻም ንቅናቄው እንዴት መቀጣጠል እንዳለበት የሚያመላክት የመሰለኝኝ ሃሳብ አቀርባለሁ፤ መልካም ንባብ።

2.ችግሮቻችን ምንድን ናቸው? መልካም አስተዳደር የወቅቱ ቁልፍ ችግር

2.1 በአሁኑ ግዜ የችግሮቻችን አውራ መልካም አስተዳደር ያለማስፈን ችግር ነው ተብሏል፡፡ ለመሆኑ መልካም/ዴሞክራስያዊ አስተዳደር ምን ማለት ነው?

የመልካም ወይም ዴሞክራስያዊ አስተዳደር ምንነት በጣም አከራካሪና ሰፋ ያለ ሙግት እሚካሄድበት መስክ እንደሆነ ግንዛቤ ዉስጥ በመክተት ነው በዚህ ንዑስ ርእስ ስር ለዚህ ፅሁፍ ሲባል የተወሰኑ መሰረታዊ ነገሮች ላይ ማተኮር የመረጥኩት። መስተዳድር ወይም አስተዳደር የሚለው ንድፈ ሃሳብ አዲስ ያልሆነና ለተለያዩ ሰዎች የተለያየ ትርጉም የሚሰጥ ነገር ነው። እንደ ናንዳ (Nanda, 2006: 271) ገለፃ አስተዳደር የሚለው ሃሳብ የትርጉም እልባት ያላገኝ እና ትርጉሙም ልናሳካ በምንፈልገው አላማ እና በምንከተለው ዘይቤ እንደሚመሰረት ታብራራለች። አስተዳደር የነባራዊው ፖለቲካዊ ስርዓት ነፀብራቅ ሲሆን በመጠነ ስፋቱ እና ተዛማጅ ትርጉሙም ከግዜ ወደ ግዜ እንዲሁም ከቦታ ወደ ቦታ የሚለያይ ነገር ነው። በፍፁማዊ የዘዉድ አገዛዝ እና ሌሎች የአምባገነን መንግስታት አስተዳደር ሊያሳካ እሚችለው የመጨረሻው አላማ የአስተዳደር ቢሮክራስያዊ ገፅታው፤ ማለትም ዉጤታማነት እና ብቁነት (ቅልጥፍና) ነው።

ማህበረ -ኢኮኖምያዊ እና ፖለቲካዊ እድገቶችን እና የዴሞክራሲ ጅማሬን ተከትሎ ግን አስተዳደር የሚለው ሃሳብ መልካም አስተዳደር ወይም ዴሞክራስያዊ አስተዳደር የሚሉትን በማካተት መልካም አተደዳደርን የዴሞክራሲ ፀጋ አድርጎ መቁጠር የተዘወተረ ነገር መሆን መጀመሩ መገንዘብ ይቻላል። መልካም አስተዳደር ወይም ዴሞክራስያዊ አስተዳደር ከዉጤታማነት እና ብቁነት የሰፋ እና የገዘፈ ሃሳብ ሲሆን፤ ላጠቃላይ የፖለቲካ ስርዓቱ የሚቆምና የዜጎችን ፖለቲካዊ እና ሰብአዊ መብቶች እና ነፃነቶች የሚያስከብርና ማንኛዉምም ዓይነት አድልዎ የማይቀበል ሂደት ነው። ግልፅነት እና ተጠያቂነትም በሲቪል ሰርቪሱ ብቻ የማይታጠር በፖለቲካ አመራሩ እና ተቛማት ሊተገበር እሚገባው ቁልፍ የመልካም አስተዳደር አካሎች ናቸው።

ገብረቭቢ ‘Democracy, Democratic Institutions and Good Governance in Nigeria’ በተሰኘው ፁሁፉ አልካሊ የተባለ ተመራማሪን ጠቅሶ እንደሚለው አስተዳደር ማለት የፖለቲካ ስልጣንን ህዝባዊ ጉዳዮችን ለማስኬድ ማዋል እንደሆነ ይጠቅስና፤ አስተዳደር የሚዳስሳቸው ጉዳዮች ብሎ የህግ የበላይነትን፣ ተጠያቂነትና ግልፅነትን፣ ልማት ተኮር አመራርን፣ ራስን የመግለፅና የመደራጀት መብትን፣ መልስ ሰጪነትን፣ ሃላፊነት መዉሰድን፣ ወካይነትን፣ ዉጤታማነት እና ጥራት ያለው አገልግሎት መስጠትን እንደሚያካትት ይገልፃል። ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚነሳው መልካም አስተዳደር እሚለው ጽንሰ ሃሳብ ነው፡፡ ሻቢር ቼማ እንደሚለው “መልካም አስተዳደር ያለዉን ሃብት ለጋራ ችግሮች እንዴት መዋል እንዳለባቸውና በምን አኳሃን መመራት እንዳለባቸው የሚመለከት እንደሆነ ይጠቅሳል። መገለጫ መርሆቹም አሳታፊነት፣ ግልፅነት፣ ተጠየቂነት፣ የህግ የበላይነት፣ ዉጤታማነት፣ ፍትሃዊነት እና ስትራቴጅያዊ ራዕይ መጨበጥን ያካትታል ይላል።” (2005:33).

አዳምስም በተመሳሳይ ስለ ዴሞክራስያዊ አስተዳደር የሚከተለውን ይላል ዴሞክራስያዊ አስተዳደር የህዝባዊ ተቛማት ግልፀኝነት እና ተጠያቂነት ይፈልጋል። ዜጎችም ስለ መንግስት ፖሊሲ፣ ዉሳኔዎች እና ተግባራት መረጃ የማግኝት መብት ሊኖራቸው ይገባል። በኛ አገር ሁኔታ ይህ እንዳይሆን እንቅፋት ከሆነው አንዱ የመንግስት የመረጃ አያያዝ ደካማነት፣ የዜጎች መረጃ የማግኘት መብት እንዳላቸው አለመገንዘብ እና በዋናነት ደግሞ ሚስጢራዊ እና ሚስጢራዊ የሆኑ መረጃዋች መለየት አለመቻል ነው፤ ይህ ሁኔታ ካልታረመ መሰረታዊ የዜጎች መረጃ የማግኘት መብት ስለሚጋፋ ለዴሞክራሲ ምህዳር መጥበብ የራሱ አስተዋፅኦ ማድረጉ አይቀርም። አዳምስ አያይዞም በሃላፊነት ያሉ ሰዎች ለድርጊታቸው እና ላፈፃፀም ግብራቸው ተጠያቂ መሆን አለባቸው ይላል። የተጠያቂነት እና ግልፀኝነት መርህ መንግስት አካባቢ ለሚኖረው ሙስና ለመግታት እና የዜጎች ተሳትፎ ለማበርታት ጠቃሚ ነገሮች ናቸው ይላል። ዜጎች ሃሳብን እና ራስን በነፃ የመግለፅ፣ የመደራጀት እንዲሁም ማንንም ሳይፈሩ ድርጅት የመመስረት እና የተመቻቸውን ድርጅት የመቀላቀል መብት ሊኖራቸው እንደሚገባ ያትታል።ከዚህ መረዳት እምንችለው መልካም/ዴሞክራስያዊ አስተዳደር ሲባል ቁንፅል ፖለቲካዊ ሃሳብ ሳይሆን የዜጎችን ስብአዊ እና ዴሞክራስያዊ መብቶችን በአስተዳደር መዋቅር እና ትግበራ ከግምት ማስገባት ማለት እንደሆነ ነው::

እንደ ተመዱ የኤስያና ፓስፊክ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ኮሚሽን አረዳድ መልካም አስተዳደር ስምንት ዋና ባህርያት አሉት ይላል። እነዚህም አሳታፊነት፣ መግባባት ላይ ያተኮረ (Concensus oriented) ፣ ተጠያቂነት፣ ግልፅነት፣ መልስ ሰጪ (Responsive)፣ ዉጤታማ እና ብቁ (ቅልጥፍና)፣ፍትሃዊ እና ሁሉን አቃፊ (equitable and inclusive) እንዲሁም የህግ የበላይነት ናቸው ይላል። መልካም አስተዳደር የህዳጣን (Minorities) እና የሌሎች ተጋላጭ የህብረተሰብ ክፍሎች ሃሳብ እና ድምፅ በዉሳኔ መስጠት ሂደት ላይ ግምት ዉስጥ መክተትንም ይጨምራል ይላል። አሁን ላለው እና ወደፊት ለሚመጣው ማህበረሰባዊ ፍላጎትም ጭምር ዝግጁ የሆነና መልስ መስጠት የሚችል አቅም እና መዋቅር መፍጠር ነው መልካም አስተዳደር። ሰለዚ አንድን ሰርአት መልካም ነው ወይስ መጥፎ አስተዳደር ነው ያለው የሚለዉን ለመገንዘብ ከነዚህ መለክያዎች አንፃር ነው ማየት ያለብን።

ዴሞክራስያዊ ፖለቲካዊ ስርዓት መንግስታዊ ስልጣን የያዙ ሰዎች ላይ ህጋዊ ገድብ ያስቀምጣል። ስልጣን ለተለያዩ የመንግስት አካላት የሚሰጥበት ምክንያትም በተወሰኑ ተቛማት ወይም ግለሰቦች ብቻ ሃይል እንዳይከማች ከሚል እሳቤ ነው። የተለያዩ የመንግስት አካላት በቂ የሆነ አቅም እና ነፃነት ኑሮዋቸው አንዱ መዋቅር ሌላኛዉን እሚቆጣጠርበት እና ህገ መንግስታዊ ሚዛን እሚጠብቅበት አሰራር ያስፈልገዋል። ወታደራዊ ተቛሙም በ ሲቪልያን ቁጥጥር ስር ማድረግ መቻል ለዴሞክራስያዊ አስተዳደር በጣም ወሳኝ ነው ይላል ፍራንሲስ አዳምስ። እንደ አዳምስ አነጋገር ወታደራዊ ሃይሉን በበላይነት የማዘዝ ስልጣኑ በምርጫ በሚቛቛመው አገራዊ ፖሊሲዎችን በሚያወጣው እና ያለ ወታሃደራዊ ጣልቃ ገብነት ስራዉን በሚተገብረው ሲቪል አስፋፃሚ መሆን አለበት ይላል።

[የኢፌዴሪ ህገ መንግስት አንቀፅ 74/1 እንደሚለው “… ጠቅላይ ሚኒስቴሩ የጦር ሃይሎች ጠቅላይ አዛዥ ነው” እንዲሁም በአንቀፅ 87/2 መሰረት “የመከላከያ ሚኒስቴር ሆኖ የሚሾመው ሲቪል ይሆናል” ይላል።]

2.2.የመልካም/ ዴሞክራስያዊ አስተዳደር ችግሮች ስፋትና ጥልቀት

ባጠቃላይ የሃገራችን ሁኔታ ሲታይ መልካም አስተዳደር ማረጋገጥ አለመቻል፣ ሙስና፣ እና የፍትህ እጦት ሶስት አደገኛ የስርዓቱ በሽታዎች ናቸው፡፡ እነዚህ በሽታዎች አጠቃላይ የዲሞክራሲ ሁናቴው ሲቀጭጭ ከቁጥጥር ውጪ የመሆን እድላቸው ይሰፋና ማስተካከያ እርምጃ ለመውሰድ አዳጋች ይሆናል፡፡ እነዚህን ሶስት አደገኛ በሽታዎች ለዘመናት ከኛ ጋር የኖሩ እና አሁንም በከፍተኛ ሁኔታ እየተፈታተኑን የሚገኙ ስለሆኑ ኢኮኖሚያዊ ከሆኑ መንገዶች በተጨማሪ ሌላ መፍትሄ ማበጀት ካልተቻለ በቀጣይነት ግዝፈታቸው እየጨመሩ መሄዳቸው እማይቀር መሆኑ መገንዘብ አለብን:: ባጭር አማርኛ ችግሮቹ አብረውን የነበሩና አሁንም እያኗኗሩን ያሉ በሽታዎች ናቸው፡፡ ኢህአዲግ መሰረታዊ የስርዓቱ በሽታ ብሎ የዘረዘራቸው ሙስና፤ መልካም ያልሆነ አስተዳደር እና የፍትህ መጓደል እስካሁኑ የተገኙት ድሎችን መና ሊያስቀር እንደሚችል እውቅና መስጠቱም ይብል የሚያስብል ነው፡፡

አሁን ኢትዮጵያ ላይ ያለው የዴሞክራሲ ድባብ ሲታይ ዜጎች የሚስማቸውን ቅሬታ ለመግለጽ አብዛኞቹ መንገዶች የሳሱበት ፣ አማራጭ የመረጃ ምንጮች በከፍተኛ ፍጥነት እየቀጨጩ፣ የማበህራት ነፃነት እተገፋፋ፣ የመናገር እና ባጠቃላይ ሃሳብን የመግለጽ መብቶች በሚታዩ እና በማይታዩ ዘዴዎች እየተዳከሙ ያለበት ሁኔታ እታዘባለሁ፡፡ መልካም አስተዳደር ህልም የሆነበት ሙስና የያንዳንዱ መንግስታዊ መዋቅር እና ሰዎች “ልሙድ ተግባር” የሆነበት፣ ፍትህ ከርትዕ ርቆ የጉልበተኞች መጫወቻ እየሆነ ባጠቃላይ ዜጎች በፍርሃት የተሸበቡበት ፖለቲካዊ ሁኔታ ነው ያለው፡፡ የፍርሃት ዋና መንስኤ ደግሞ ጤንነቱ የተዛባ የፖለቲካ ሁኔታ ነው።

አካፋን አካፋ ካላልን ግብዝነት ይነግሳል፣ ውሸት ሃይል አግኝቶ እውነትን ይተካል፡፡ በመንግስት በኩል ደግሞ የ “ማን አለብኝነት” ትእቢት እና ተቛሚዊ አሰራር መጥፋት እና ሌሎች ተደማምረው የአምባገነንነት ዝንባሌዎች (Dictatorial Tendency) እየታዩ ነው፡፡ 10ኛው የኢህአዴግ ጉባኤ ችግሮች ብሎ የለያቸው ሰናይ ከላይ የገለፅኩት ምስል ነው የሚያሳየን:: ለምሳሌ መቐለ በተካሄደው በኢህአዴግ 10ኛው ጉባኤ ዋና ዋና ድክመቶች ተብለው በጉባኤው ተቀባይነት ካገኙት ካነሳነው ጉዳይ ተያያዥ የሆኑትን ልጥቀስ፡፡ ምንጮቼ በጉባኤው በታዛቢነት ተሳትፎ አድርጎ የነበረዉ ሪፖርተር ጋዜጣና ያነጋገርዃቸው ተሳተፊዎች ናቸው።

* “ህዝባዊነት በግለኝነት እየተሸራረፈ ነው፡፡ ህዝብ የበላይ ወሳኝና ተቆጣጣሪ መሆኑ እየተዘነጋ የግል ጥቅም እና ምቾት ለማሳካት መንቀሳቀስ በኢህአዴግ ውስጥ እየተስፋፋ መጥቷል፡፡

* ኪራይ ሰብሳቢነት እና ሙስና እየተስፋፋ ነው፡፡

* መልካም አስተዳደር እየጠፋ ነው፡፡

* የፍትህ ስርአቱ እየተዳከመ ነው፡፡

* ተጠያቂነት እየጠፋ ነው፡፡

* የማህበራዊ አገልግሎት አቅርቦት ችግር አለ፡፡

ኢህአዴግ ባጭሩ እያለን ያለው “የሙስና፣ መልካም አስተዳደር የማሰፋን እና የፍትህ ችግሮች እየተባባሱ ነው” ነው፡፡ይህም በመሰረቱ ትክክል ነው። ህዝብን እሚሰማ እየጠፋ ‘እኔ አውቅልሃሎህ’ ባይ እየበዛ፣ ህዝቡ ችግሩ ሲናገር ከተቃዋሚዎች ጋር እያስተሳሰሩ ማሳደድ፣ ዝም ሲል ደግሞ እንደተመቸው አድርጎ ማሰብ፣ እንደ ፓርላማ የመሳሰሉ የዴሞክራሲ ተቋማት ግዴታዎችን በበቂ ሁኔታ አለመወጣታቸው የስራ አስፈፃሚውን ጡንቻ እያሳበጠ ሄዶ ሄዶ አሁን ላለንበት ሁኔታ አድርሶናል፡፡ የዚህ ሁሉ ድምር ውጤት ነው ዴሞክራሲያዊ ሁኔታውን ያጠበበው፣ የዚህ መጥበብ ልጆች ናቸው እነ ፍትህ ማጣት፣ ሙስና እና መልካም ያልሆነ አስተዳደር እሚባሉ በሽቶች፡፡

3. የችግሮቻችን መሰረታዊ ምንጭ ምንድን ነው?

ለበሽታዎቻችን እንደ የአቅም ማነስ፣ ድርጅታዊ ድክመት፣ ያልዳበረ ህዝባዊ የተሳትፎ ባህል የመሳሰሉት ነገሮች መነሻ ምክንያት ሊሆኑ ቢችሉም ዋናው እና ተጠቃሽ ምክንያት ግን አጠቃላይ የዴሞክራሲያዊ ሁናቴ እጥረት ነው፡፡ እንከን የለሽ ዴሞክራሲ እሚባል ነገር እንደሌለና ኢትዮጵያችንም ጀማሪ ዴሞክራሲ መሆንዋንም እረዳለሁ፡፡ በዚህ ምክንያትም ነው በኢትዮጵያ ዴሞክራያዊ ስርዓት ለመገንባትም ለመቀልበስም ሊያግዙ እሚችሉ ነገሮች በብዛት እሚገኙት፤ ለዚህም ነው ጀማሪ ዴሞክራሲያችንን ሊቀለብሱ እሚችሉ ሃይሎች እና ሁኔታዎችን በቅጡ ተገንዝበን እና ለይተን በቁርጠኝነት አረንቋውን ማድረቅ ያለብን፡፡ ለዚህም ነው ቲሊ ዴሞክራታይዜሽን መቼም ሙሉ መሆን እማይችል እና የ ኢ ዴሞክራታይዜሽን አደጋ ሊያጋጥመው የሚችል ተለዋዋጭ ሂደት ነው የሚለው። ኢ ዴሞክራታይዜሽን ማለት ቅልበሳ ማለት ነው። በተለያየ አቅጣጫ ተቀራርበው እሚንቀሳቀሱ ሂደቶች ዴሞክራታይዜሽንን እና ቅልበሳዉን ሊያመጡ ይችላሉ ይላል። “Closely related processes, moving in opposite directions, produce both democratization and de democratization”፡፡ ሙለር እና በርግማን እንደሚሉት ዴሞክራሲ ቀላልም ቀጥ ያለም ያልሆነ ግን ደግሞ ሊሳካ የሚችል ነገር ነው:: በነዚህ እና በሌሎች ምክንያት ነው አገሬ ላይ እዉን ሆኖ ማየት እምፈልገው ዴሞክራሲ ሃሳባዊ የሆነና ምንም እንከን የሌለው ዴሞክራሲ አይደለም የምለው፡፡

የአገራችን የዴሞክራሲ ሁኔታ ለጋ ነው ስል የሚከተለውን የቲሊ አባባል ያስታዉሰኛል፤ በቲሊ አረዳድ “We are not trying to explain yes-no swiches between undemocratic and democratic conditions. We are not trying to explain degrees and changes of democracy” ስለዚህ ስለ አገራችን የዴሞክራሲ ሁኔታ ሳወራ ስለ ሂደት እንጂ ህልመኛ ሆኜ መሆን የማይችለውን እና እስከአሁን አለም ላይ የሌለውን ገነት መሳይ ዴሞክራሲ ፈልጌ አይደለም፡፡ ለምሳሌ እ.ፋ.አ ከ 1789 ጀምሮ ፈረንሳይ በትንሹ አራት የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ክፍሎች ስታይ በትንሹ ደግሞ ሶስት የዴሞክራሲ ስርዓት ቅልበሳ ግዝያቶች አሳልፋለች፡፡ ዘመናችን የዴሞክራሲ በመሆኑ እንደዚህ ኣይነት የቅልበሳ የቅንጦት (luxury of de-democratization) አማራጭ ግን የለንም። በኛ ሁኔታ ተደጋግሞ እንደተገለጸው ዴሞከራሲ የህልውና ጉዳይ ነው፡፡ እየተንገራገጨ ቢሆንም ሁሉ ግዜ ወደፊት መጏዙን ማረጋገጥ ይኖርብናል እንጂ አጠቀላይ ቅልበሳ አገሪቱ ወደ አደገኛ ቀዉስ ይመራታል፡፡

የዲሞክራሲ እጦት የተመረጠ እና ልዩ የመጥፎ አስተዳደር ማዳበሪያ ነው፡፡ የፈለገው ልማት ቢመጣ ዲሞክራሲያዊ ምህዳሩ መጥበብ ካሳየ ሶስቱም በሽታዎች አለን!! አለን!! አለን!! ምን አባታቹህ ታመጣላቹህ! እያሉ መፈንጨታቸው አይቀርም::በሽታዎቹ እንዳይፈነጩብን በመሰረቱ የሚከላከልልንን ዲሞክራሲያዊ ህገ መንግስት አለን፡፡ ችግሩ ተግባር ላይ ሲዉል ህገ-መንግስቱ ባስቀመጠው መንፈስ (Sprit of the Constitution) አለመተግበሩ ነው፡፡ ከፍ ያለ ኢ-ህገ-መንግስታዊነት ሲበረታ ሶስቱ በሽታዎች የራሳቸው ሰንደቅ አላማ እያውለበለቡ ‘አሸናፍናቹህ፤ ረታናችሁ’ ይሉናል:: አጠቃላይ የዲሞክራሲ ከባቢው እየጠበበ ሲሄድ ሶስትም በሽታዎች ተጠናክረው፤ ተበረታተው፤ ተባዝተው እና ተኳኩለው ይፈነጩብናል፡፡ በዴሞክራታይዜሽን እና ኢ-ዴሞክራታይዜሽን ሂደቶች ሁሌም መሳሳብ እና ዉጥረት ይኖራል። መንግስት እንደ መንግስት ግን የዴሞክራታይዜሽን አጋዥ አልያም የኢ-ዴሞክራታይዜሽን አሳላጭ ነው መሆን እሚችለው፤ መሀል ላይ የሚንገዋለል መንግስታዊና ተቛማዊ አቛም ሊኖር አይችልም። ስለዚ ምርጫው አንድ እና አንድ ነው፤ ለዴሞክራሲ መስራት ወይም የፀረ ዴሞክራሲ ሃይል መሆን።

ዲሞክራሲያዊ ሁኔታ እና ሶስቱ በሽታዎች በተቃራኒ መንገድ ነው ጉዞአቸው፡፡ ዲሞክራሲያዊ ሁኔታው ሲሰፋ በሽታዎቹ መጠጊያ እና መሸሸጊያ ፍለጋ ይኳትናሉ፡፡ ምሽግ ፈልገው ወይም ቆፍረው ይደበቃሉ፤ልክ የወባ በሽታ ከህክምና በኃላም ቢሆን በሆነ የሰውነታችን ክፍል እንደምትደበቀው፤ ይሄ ለመደበቅ እምታሳየው ባህሪ ነው፡፡ ዲሞክራሲያዊ ምህዳሩ ሲጠብ ደግሞ በሽታዎቹ ወደ አደባባይ እየወጡ ህጋዊ ልባስ እየተጎናፀፉ መገናኛ ብዙሀንን ጭምር እየተጠቀሙ ይፈነጫሉ፤ ህዝብንና አገሪትዋንም በኃሊት ማርሽ ወደ አዘቀት ይከቷታል፡፡ ከስር እምታዩት ስእላዊ መግለጫ ይህንን ሃሳብ የበለጠ ለማስረዳት በፀሃፊው የተዘጋጀ ነው::

Diagram one

[ምስል አንድ: የዴሞክራሲ ምህዳር ሲሰፋ በሽታዎቹ ይቀጭጫሉ፤ በተቃራኒው የዴሞክራሲ ምህዳሩ ሲጠብ በሽታዎቹ ጎልተው እና ጠንክረው ይወጣሉ።]

ልማት የዴሞክራሲ አካል መሆኑ ሳንዘነጋ፤ ህገ-መንግስቱን የመተርጎም ችግር አለ ሲባል ከዲሞክራሲ አኳያ የተደነገጉት የሲቭል እና ፖለቲካዊ መብቶች ተፈፃሚ አለማድረግ ማለት ነው:: በተጨማሪም በየጊዜው መንግስትን ለማቋቋም በሚደረገው ምርጫ የፍትሃዊነት እና የህዝባዊ ተቀባይነት (Legitimacy) ችግር ሲኖር ነው ህገ-መንግስቱ በአግባቡ እየተተረጎመ አይደለም የሚባለው፡፡

የ2007 ምርጫ ማሸነፍ ያለበት ፓርቲ አሸነፎል፡፡ በእጅጉ ከፍተኛ ድምጽ መመረጡም ይገባዋል እላለሁ፤ ይችን አገር ከውድቀት አስነስቶ በመግቢያ እነደገለጽኩት ወደ ተስፋ ያላት አገር ወደ መሆን እቅጣጫ እየመራት ነው፡፡ አሸናፊነት አይበዛበትም፡፡ የተቃዋሚዎች ድክመት ተጨምሮበት በእጅጉ ከፍተኛ ድምፅ ቢመረጥ አያስገርምም:: ነገር ግን ለምሳሌ ያህል እኔ በመረጥኩበት የምርጫ ክልል እቤት ድረስ የዘለቀ የነበረው መዋከብ እና በኣንዳንድ ምርጫ ክልል አንድ ላምሰት የነበረው አሉታዊ ተጽእኖ ስሰማ፣ የመገናኛ ብዙሃን አጠቃቀም የነበረው ከፍተኛ ኣድልዎ ስገነዘብ ምርጫው እንከን የለሽ ነው ሲባል እስቃለሁ። ህዝቦቻችን መብታቸውን ለማስጠበቅ ባልቻሉበት፡ ህገ-መንግስታዊ እና ዴሞከራሲያዊ ተቓሞቻችን ባልጠነከሩበት ሁኔታ፡ የመልካም አስተዳድር ችግር ባለበት ሁኔታ ሙሉ ለሙሉ ዴሞክራስያዊ ነው ማለት አይቻልም።

ባጠቃላይ ሲታይ ብዙ ማንነቶች፤ በርካታ ፖለቲካዊ ፍላጎቶች፤መልስ እንሻለን የሚሉ የተለያዩ ጥያቄዎች ባሉበት አገር አንድ ግንባር (ኢህአዴግ) እና አጋሮቹ 100% መቀመጫውን መቆጣጠር እሚያሳየን ነገር፤አንድም ባጠቃላይ ፖለቲካዊ ስርዓቱ ላይ ችግር መኖሩን አልያም የምርጫ ስርዓቱ ችግር እንዳለበት ወይም ተግባራዊነት ላይ ችግር እንደነበረበት ነው፤ 100% እሚባል ውጤት አስቂኝ ግን ደግሞ አደገኛ ነው ፡፡ ይሄ ዉጤት አርቆ ለሚያስብ ሰው የአደጋ እንጂ የድል ምልክት ተደርጎ መቆጠር አይችልም። መሬት ላይ ያለዉን የተለያየ ፖለቲካዊ ፍላጎት እማያንፀባርቅ የምክር ቤት ሁኔታ የስጋት እንጂ የኩራት ምንጭ መሆን አይችልም።

የሰፋ ዴሞክራስያዊ ምህዳር ሲኖር የተለያዩ የፖለቲካ ድርጅቶች እና ግለሰቦች በእኩልትን አለን የሚሉትን አማራጭነት ለህዝቡ እንዲያቀርቡ ያስችለዋል፡፡ ዴሞክራሲ ማለት እኮ የተለያዩ ሃሳቦች በእኩልነት ለዉድድር እሚቀርቡበት ፖለቲካዊ ገበያ ማለት:: ይህ ተጨባጭ ምሳሌ የሚነግረን ነገር አንድ እና አንድ ነው፤ እሱም አጠቃላይ የዲሞክራሲ ምህዳሩ ሲጠብ ሶስቱም በሽታዎች በግላጭ ባንዲራቸውን ለማውለብለብ እንደማይቸገሩ ነው፡፡

ህዝቡ በሶስቱም በሽታዎች ሲጠቃ ለምንድን ነው በሚሰማ ሰላማዊ ሰልፍ ፤ህዝባዊ ስብሰባዎች ፤ተወካዮችን በመሳብ (recall) እና ሌሎች መንገዶች ተጠቅሞ ምሬቱን ማሰማት ያልቻለው? እሚለው በደንብ መጤን አለበት ፡፡ ልክ በ10ኛው የኢእሀዴግ ጉባኤ እንደተገለፀው ‘ደህና ፤ ይስተካከሉ ይሆናል’ ከሚል መነሻ ሊሆን ይችላል፤ ሌሎች ምክኒያቶች ግን ሊኖሩ እንደሚችሉ መገመት አለብን፡፡ለምሳሌ ህዝብ ዝም ያለው መብቶቹን እሚያረጋግጥበት ሁኔታ ስላላገኘ ሊሆን ይችላል፡፡ አንዳንዴ መሰረታዊ በሆኑ የመኖር ጉዳይ ላይ እያማረረ እለታዊ እንቅስቃሴውም ጭምር ማከናወን እየተሳነው እያለም በግልጭ ተቋውምውን ማሰማት ያልቻለው ለምን ይሆን? ወይስ ተቓዉሞ መግለፅ እሚያስከፍለው ዋጋ ካቅሙ በላይ ስለሆነበት ነው? ወይስ ተባብሮ የመስራት ችግር (Collective Action Problem) ነው? ወይስ አፋኝ መዋቅሮች አላንቀሳቅስ ብለዉት ነው?

በውሃ ፤መብራት እና ሌሎች አገልግሎቶች በብዛት የሚማረር ህዝብ እንኳን መብቴ ተጣሰ ብሎ ውስጥ ለውስጥ ከማንሾካሾክ አልፎ መብቱን ሲያስከበር አይታይም:: ለምን? እሚለው ጥያቄ በጥልቀት ስንመረምር ነው ብዙ ነገር ሊገባን የሚችለው:: ይህ በንዲህ እንዳለህ አጠቃላይ ዲሞክራሲያዊ ሁኔታው እየሰፋ እና አመቺ እየሆነ ካልሄደ ሶስቱም በሽታዎች ህዝብ ላይ መፈንጨታቸው አይቀርም፡፡ ሁኔታዎች እንዲህ ባለ ጠባብ የዲሞክራሲ ምህዳር ሲቀጥል እሚያስከትሉት መዘዝ ዘርፈ ብዙና ብዙ ዋጋ ያስከፈለና ወደ ፊትም እሚያስከፍል ስለመሆኑ ለመተንበይ ነብይ መሆን አይጠበቅብንም፡፡ GTP 1 በሚፈለገው መጠን ተግባራዊ እንዳይሆን ብቻ ሳይሆን GTP 2ንም ጭምር አደጋ ላይ ሊጥለው እሚችለው ይሄው ጠበብ የዲሞክራሲ ምህዳር ነው፡፡

ዲሞክራሲያዊ ምህዳሩ በጠበበ ቁጥር የዜጎች ተስፋ እተሟጠጠ ስጋታቸው እና ፍርሃታቸው እየጨመረ ከቁጥጥር ውጪ የመሆኑ እድል ይሰፋል፡፡ ይህን መሰል ሁኔታም ከውስጥም ከውጪም ለነሱ ለሚችሉ ፅንፈኛ ሃይሎች ምቹ ሁኔታ ስለሚፈጥር አገሪትዋን ወደላስፈላጊ መንገድ ሊመራ ይችላል፡፡ ፍትህ ተራ ፍርድ የማግኘት ጉዳይ አይደለም፡፡ ፍትህ የማህበራዊ ተቛም የመጀመርያ ፀጋው ነው ይላል ጆን ራዉልስ፡፡ ሙስናና መልካም ያልሆነ አስተዳደርም ሃገርን ሊበትን የሚችል፤እየታየ ያለውን ኢኮኖሚያዊ እድገት ገደል የመክተት አቅም ያላቸው ስርዓታዊ በሽታዎች ናቸው፡፡የሶስቱም እናት ደግሞ የጠበበ ወይም የኮሰመነ የዲሞክራሲ ምህዳር ነው፡፡

4. በኢህአዴግ እሚመራው መንግስት የዴሞክራሲ ምህዳሩ በማስፋት መልካም አስተዳደርን ለምን አላረጋገጠም?

አሁን ካሉት በርካታ ፓርቲዎች የ ሃያኛው እና ሃያአንደኛው ክፍለ ዘመን ቅይጥ አተሳሰብ ያላቸው ናቸው። የ1960ዎቹ ትውልድ “እኔ ያልኩት ካልሆነ ሌላው ዉድቅ ነው” የሚለው አስተሳስብ በትጥቅ ግዜ በነበረው ሁኔታ የድርጅቶች የመጥፋት አጋጣሚ በነበረበት ግዜ የተለያዩ ሃሳቦች እንዳይንሸራሸሩ እማያበረታታ ሁኔታ ሲፍጠር እየጎለበተ ሁኔታዎች ሲረጋጉ አየቀነስ እንደገና ድርጅቶቹ ከዓላማዎቻቸው በላይ ሲሆኑ “ድርጅታችን ልትጠፋ ነው፤ እንዳትጠፋ እናድናት” የሚለው አስተሳሰብ አሁንም በሰላሙ ግዜ ሲንጸባረቅ ይታያል:: ዴሞክራሲ የሚጠይቀው ተጣጣፊነት፣ መቻቻል እና የጋራ መግባባት በተወስኑ ኣመራር እና ወጣት ክፍል ቢንጸባርቀም አሁን ያለው ገዢ አስተሳሰብ ግን ያለመታረቅ ባህል፣ የመጋፈጥ ፖለቲካ እና መራራቅ (uncompromising militancy, confrontational politics and polarization) ነው።

ፈጣሪ ለኢህኣደግ ብቻ ልዮ ስጦታ እንደሰጠ በሚያስመስሉ ሁሉ “ከኢህአዴግ መንገድ ውጪ ሁሉም የጥፋት መንገድ ነው” እሚል አስተሳሰብ ህዝቦቻችን አማራጭ ሓሳቦችን ተዘርዝረው እና ተደራጅተው በዚህ መሰረት በፈለጉት ጉዳይ ላይ ይህን አማራጭ መሰረት አድርገው እንዲወስኑ ዕድል አይሰጣቸዉም። 1992-1993 በኢህአዴግ ዉስጥ የነበረው የዉስጥ ቀዉስ (Intra-party crisis) አፈታት እሚያሳየንም ይህንኑ ነው። “አንጃዎች” የተባሉት ከሌላኛው የፓርቲው ወገን የነበራቸው ልዩነት ለህዝቡ ለማቅረብ የመንግስት ሚድያ እድል ነፈጋቸው። ያሸነፈው “አንጃ” ግን የመንግስት ሚድያ ልክ የኢህአዴግ ሚድያ እንደሆነ በማድረግ እንደፈለገ ሲጠቀምበት ያለ ምንም ሃፍረት ነበር። ይህ አስተሳሰብ እስካልተወገደ ድረስ የዴሞክራሲ ምህዳሩ መስፋት አጠራጣሪ ነው።ዲሞክራሲያዊ ምህዳሩን በሁሉም መልኩ እየኮሰመነ እንዲሄድና ህገ-መንግስቱም በታለመለት መንፈስ እንዳይተገበር እያደረገ ያለ ይመስለኛል፡፡ በመቐለ ከተማ በግላጭ ባደባባይ ተቋዋሚዎች ኳኺቶ (አደገኛ እሾህ) የሚል ስያሜ ተሰጥቷቸው መወገድ እንዳለባቸው አረም ተቆጠረው መቅረባቸው አሳፋሪ እና ፀረ ህገ-መንግስት የሆነ ድርጊት ነው፡፡

ዴሞክራሲ በአለም ዋና አጀንዳ በሆነበት ሁኔታ በኛ ሃገርም ተደጋግሞ ይዘመራል። በ 1992 ዓ.ም እና 1994 ዓ.ም በኢህአዴግ እና በመንግስት የቀረቡት ፁሁፎች በ ቀዉስ ማግስት የተፃፉ ናቸው። ቀደም ብሎ እንደተገለፀው በተነፃፃሪ ስለ ዴሞክራሲና ተቛሞቹ ጥርት ያለ ሃሳብ አለው። እነዚህ ዶክመንቶች ቀዉሱ ካለቀ በኃላ፤ ማለት መረጋጋት ከተረጋገጠ በኃላ፤ ሳይተገበሩ ሲቀሩ ሸልፍ ማሳመርያ ይሆን እንዴ የተፃፉት? እንድል ያደርገኛል። ዋናው ችግሩ ዴሞክራሲ እሚባል ነገር ከአፋ በላይ ሄዶ ሊዋሃደን አለመቻሉ ነው። Internalize አልተደረገም።

ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግ በትጥቅ ትግል የነበረዉን አደረጃጀት እና አስተሳሰብ በመሰረቱ ሳይቀይር ነው መንግስትነትን የቀጠለው። እዚህ ጋ መሰመር ያለበት ጉዳይ የትጥቅ ትግል task እና መንግስት ከተሆነ ወዲህ የሚኖሩት tasks በአጠቀለይ በተለይ ከዴሞከራሲ ስርኣት በመሰረቱ የተለያዩ መሆናቸው ነው። በትጥቅ ትግል ወቀት እንድን ህዝብ ወይ አከባቢ በብቸንነት እንድትቆጣጠር የሚያስገድድ ህዝቡን በዋናነት ደርግን ለመድምስስ ሞቢሊዝ ማድርግ ሲሆን በኢፊዴሪ ሕገ-መንግሰት ግን ሕብረ-ፓርቲ ስርኣት መሆኑን መገንዘብ አለብን፡፡ ኢህአዴግ ለሕብረ-ፓርቲ ስርኣት በተማላ አልተዘጋጀም፡፡

ከድህነትና ከስላም ማጣት የባሰ የህዝብ ጠላት የለምና፤ በፀረ-ድህነት ትግሉ በስላም ማረጋግጥ አመረቂ ወጤት እየተመዝገበ በመሆኑ ህዝባዊነትና የዓላማ ፅናት የሚያሳይ ቢሆንም በዴሞክራሲና በመልካም አስተዳደር ዙሩያ እየታዩ ያሉት መሰረታዊ ችግሮች ህዝባዊነቱ እየተሸረሽሩ ድርጅቱ በመንታ መንገድ እየተጓዘ የገኛል:: በቀጣይነት እሚማር ተማሪ የሆነ ድርጅት (learning organization) መሆኑ እያቛረጠ በመምጣቱ አቅሙ እያሟጠጠ ምናልባትም ከ GTP2 በሃላ ወገቤ የሚል ደርጅት እንዳይሆን ያስጋል፡፡ ሁኔታው መሰረታዊ ለውጥን ይጠይቀል፡፡ የትውልድ እና ያስተሳሰብ መተካካት የሚጠይቅ ሁኔታ ተፍጥሯል፤ እያየን ያለነው መድረኩ የሚፈልገው መተካካት ሳይሆን መሸጋሸግ ነው። ዴሞከራቲክ አስተሳሰብ እና ብቃት ያለው መጪዉን ለመምራት የሚችል በአንፃራዊነት ሲታይ በዴሞክራቲክ ሁኔታ ያደገ ወጣት ሆኖ ህዝባዊ ተቆርቛሪነቱ የላቀ ሙሁር ወደ ስልጣን ከማምጠት እርስ በረሱ ይህ ይሻለል ያኛው እኬል ቡዙ ኣመት ስርተዋል ይተካ አይነት አባካኝ የሰዎች ዝውወር ነው እየተመለከትን ያለነው፡፡ ግዜው ቀጣይነት የለው የአስተሳሰብ ለወጥ ሲጠይቅ ይህን የሚያቀለጠፍ ሂደት ኣልተደራጀም፤ በኔኣረዳድ ወጣት ሆኖ ህዝባዊ ተቆርቛሪነቱ የላቀ ሙሁርና ኢህአዴግ ገና አልተቀራረቡም።ኢህአዴግ ያለማውን ሙሁር ወጣት መጠቀም የማይችል ድርጅት ይመስለኛል፡፡

በመንግስት መስርያ ቤቶች ያለው አመዳደብ በብቃት ሳይሆን ከገዢው ፓርቲ ባለው ቅርርብ በመሆኑ ጥቅመኛ (Opportunist) እንዲነግስ ያደርጋል። በማይገባው ቦታ የተመደበ ብቃት የሌለው ሰው ዋናው መሳርያው ኢ-ዴሞክራስያዊ አካሄድ ነው። ይህ እሚሆነው በራሱ ስለማይተማመን ነው። ተቛማት ማእከል ተደርጎ የተሰራ ስራ በጣም ደካማ በመሆኑ የተሻለ አስተሳሰብ እና ብቃት ያላቸው እየደገፉ ወሳኝ ቦታዎችን እንድይዙ ማድረግ አልተቻለም። እላይ የተጠቀሰው አስተሳሰብ እስካልተቀየረ ድረስ ዴሞክራሲ ሊስፋፋ አይችልም። አዲስ አስተሳሰብና ብቃት ባለው አዲስ ትውልድ ሲተካ ነው ዴሞክራሲ የሚያብበው። ይህ ለማድረግ 24 ዓመታት እጅግ ቡዙ ነው ባይባልም ትርጉም ያለው ለውጥ ሊመጣ ይችል ነበር፡፡

5. የመፍተሄ ሀሳቦች

ብዙ ጊዜ ሃላፊነትን ወደታችኛው እርከን ማሻገር በተለመደበት አህጉር ኢህአዴግ በድፍረት ዋናው ተጠያቂ የበላይ አመራር ነው ብሎ ማለቱ ምስጋና እንድቸረው ያደርገኛል፡፡በሽታውን እና ምልክቶቹን እውቅና ሰጥቶ ሃላፊነት መውሰድ ለለውጥ ሂደቱ እንደ መጀመሪያ እርምጃ መቆጠር አለበት፡፡ ከባዱ ስራ ግን ቀጥሎ መከሰት ያለበት እርምጃ ላይ ነው፤ ከባድ እና ውስብስብ እሚሆነብት ምክኒያትም ትግሉ ከሞላ ጎደል ግልፅ ከሆነ ዉጫዊ ሃይል ወይም ተቛም ጋር ሳይሆን ከገዢው ፓርቲና መንግስታዊ መዋቅር ይዘው ከሚገኙ አመራር እና የነሱ ተባባሪዎች ጋር መሆኑ ነው። ባጭሩ ሃላፊነት የወሰደው የበላይ አመራር ከሆነ ትግሉም እዛ ጋር ስለሚሆን ፈታኝ እና ውስብስብ እንደሚሆን ግልፅ ነው፡፡ የኢህአዲግ 10ኛው ጉባኤም ያስተጋባውም ወደፊት ብዙ መሰራት ያለባቸው ነገሮች እንዳሉ ነው፡፡

ከፍተኛ አመራሩ (በደፈናውም ቢሆን) አደገኛ ሆነው ለተገኘት በሽታዎች ዋና ሃላፊነት ወሳጆች እኛው ነን ብለዋል። በርግጥ ስልጣን ሃላፊነትን ጭምር ተሸክሞ ስለሚመጣ በዴሞክራሲ በበለጸጉ አገራት ይህ የተለመደ ተግባር ነው፡፡ እንደ ምልአት ህዝቡና የአህአዴግ አመራር ግንዛቤ በግዜ ተፈትኖ ስራውን በአግባቡ ማከናወን ሲገባው ድክመት ያሳያው አመራሩ ነው ማለቱ ባጭር ግዜ ሲታይ ህዝባዊ ተቀባይነት እና እምነት ሊጣልበት ቢችልም (ሃቅን በመቀበላቸው ምክንያት) ተከትሎ ሊመጣ እሚገባው ቀጣይ እርምጃ ካልተከላበት ግን ሃላፊነት ወስደናል እሚለው ውሳኔ ትርጉም አልባ ከመሆን አልፎ ተመልሶ ከፍተኛ አመራሩን ጥርስ ውስጥ እሚያስገባ ነገር መሆኑ አይቀርም፡፡

ካለው ነባራዊ ሁኔታ ተነስቼ ስቃኝው መንግስት ከሁለት እና ሶስት አመት በሃላ ‘እንዲህ ብለን ነበረ’ እያለ ችግሮቹ ሳይፈታ ሸፋፍኖ የመሄድ እድል አይኖረውም ማለት ይቻላል፡፡ከፍተኛ አመራሩ ሃላፊነት ወስጂያለው ሲል ከሙስና፣ መልካም ካልሆነ አስተዳደር እና የፍትህ መጏደል አኳያ እንዴት ነው በዝርዝር መታየት ያለበት? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው:: ሃላፊነት እምንወስደው እኛ የበላይ አመራር ነን የሚለው ውሳኔ በሆነ አይነት ህጋዊ፣ አስተዳደራዎ ወይም ፖለቲካዊ እርምጃ ካልታጀበ ትርጉሙ ምንድ ነው?

መፍትሄው ህዝብን ማእከል ያደረገ እንቅስቃሴ መሆን እንዳለበት የኢህአዴግ 10ኛው ጉባኤ ጭምር አመላክተዋል፡፡ ሆኖም የመፍትሄው እንቅስቃሴ (ንቅናቄ) ህገ መንግስታዊና ዴሞክራሲያዊ ተቋማትን መሰረት ያደረገ ካልሆነ ዘላቂነት ባለው መንገድ የሚፈለገው ውጤት አይገኝም፡፡ እነዚህ ተቋማት ለዴሞክራሲ ንቅናቄው ዋስትና መሆን እንደሚቻሉት ሁሉ፣ እየጎለበተ ላለው ፀረ ዴሞክራሲ ዝንባሌም መሳርያ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ህገ መንግስታዊ ዴሞክራያዊ ተቋማት ስል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፣ ስራ አስፈፃሚው ህግ ተርጓሚ በየእርከኑ ያሉትን ኮሚሽኖች እና ባለስልጣን መስርያ ቤቶች የፖለቲካ ድርጅቶች እና የሲቪል ማህበረሰቡን የሚያካትት ሰፊ ሃሳብ ነው፡፡

ለዚህ ፅሁፍ ሲባል ግን የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤቶች፣ የመገናኛ ብዙሃን እና የአንድ ለአምስት አደረጃጀትን ብቻ ለማየት መርጭያለሁ፣ ምክንያቱም ሁሉንም ተቋማት ማየት እማይቻልና የተመረጡበት መሰረታዊ ምክንያት ደግሞ ለነዚህ ሶስት ተቋማት እሚደረግ መሰረታዊ ለውጥ ላጠቃላይ የዴሞክራሲ ንቅናቄው እንደ መነሻ ከመጥቀም አልፎ የንቅናቄውን ቀጣይነትም ስለማያረጋግጥ ጭምር ነው፡፡ ይህ ሰላማዊ ንቅናቄ ካለ ስራ አስፈፃሚው ቅን እይታ ተሳትፎና አመራር ሊሳካ እንደማይቻል እምነነቴ ነው፡፡ ሆኖም መደረግ ላለበት የዴሞክራሲ ንቅናቄ የጎላ ተቃውሞ እሚመጣዉም ከስራ አስፃሚው እንደሚሆን ይገባኛል፡፡ ይህ ቀላል ነገር አይደለም፡፡ ስራ አስፈፃሚ አካል ብዙ ስልጣኖች፣ አለም አቀፍ ትስስሮች፣ ጠንካራ የፋይናንስ አቅም፣ አደረጃጀት፣ ታንክ ያሉትና የደህንነት ተቋማት የሚያንቀሳቅስ አካል በመሆኑ የዚህ ክፍል ተቃውሞ ክብደቱ እጅግ የጎላ ያደርገዋል፡፡

ላሉት ዘርፈ ብዙ ችግሮች ዕውቅና መስጠት እና ተያይዞ የመጣው የአመራሩ ሃላፊነቱ የኛ ነው የሚል ድምዳሜ ትልቅ እርምጃ ቢሆንም የችግሮቹ መሰረታዊ መንስኤዎች እና ሊወሰዱ ስለሚገባቸው መፍትሄዎች ግን በጥልቀት የታየ አይመስለኝም። በተለይ ከ 10ኛው የኢህአዴግ ጉባኤ ማግስት በአንድ በኩል የመቀዛቀዝ በሌላ በኩል ደግሞ ችግሮች ቢኖሩም ብዙ እሚያስጨንቁ አይደሉም የማለት እና የማጣጣል አዝማምያዎች እየታዩ ነው። ጠቅላይ ሚንስቴር ሃይለማርያም ደሳለኝ ምክርቤቶችን አስመልክተው፤ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስቴር አቶ ደመቀም ሚድያን አስመልክተው የተናገሩት ነገር ገምቢ እና አበረታች ቢሆንም ሌሎች የመንግስት አካላት ግን ችግሩ ቀለል አድርገው ሲመለከቱ እያየን ነው። ይሄ ተቃርኖም የራሱ ተፅእኖ ሊያሳድር ስለሚችል ሊታሰብለት ይገባል። አሉን ለተባሉት ችግሮቻችን ተቛማዊ መልክ ያለው የዴሞክራሲ ተቛሞች ግንባታ ነው መሰረታዊው መፍትሄ። እነዚህ ተቛማት ገንቢ ሚና ሊጫወቱ እሚችሉት ተገቢ ስራቸዉን በአግባቡ ማከናወን ሲችሉ ነው። ይህ ለማድረግ ደግሞ ጠንካራ ተቛማዊ ስብእና መላበስ ይኖራቸዋል። ይህ ምን ማለት ነው?

5.1 ጠንካራ ተቛማዊ ስብእና (Strong Institutional Integrity)

ቀደም ብሎ እንደተገለጸው የዴሞክራሲ ተቋማት ግንባታ ሙስና፣ ብልሹ አስተዳደር እና የፍትህ እጦት ለሚባል በሽታዎች ዋና መፍትሄ ነው፡፡ ተቋም ሲባል ግን እምነት እሚጣልበት እና ቅንነት ያለው ሲሆን ብቻ ነው፡፡ በእንግሊዝኛው Institutional intergirty እንደሚባለው፡፡ ለአንድ ተቛም ስብእና ማለት የልቀት፣ የታማኝነት እና ህጋዊነት መመዘኛዎችን አካቶ ለመልካም የስራ ባህሪ ሁኔታዎችን ለማመቻቸት የሚይሳየው ቁርጠኝነት ነው።ሮቢን ክረይኪ ውጤታማ የ ተቛማዊ ስብእና መለክያ አለ ይለናል፡፡ እንደሱ አገላለፅ መጀመርያ የስርዓቱ ጤንነት እንደ መፈተሻ ሊጠቅሙን እሚችሉ ስራዎች መለየት፣ በሁለተኛ ደረጃ የስራዎቹ ስኬታማ አፈፃፀም ሊያመላክቱ እሚችሉ መመዘኛ ወይም መለክያዎችን ማበጀት፣ በሶስተኛ ደረጃ ያስቀመጥነዉን መለክያ መሰረት አድርገን ሪፖርት እምናቀርብበት ስርአት መገንባት፣ በመጨረሻም ተሰሩ የተባሉትን ስራዎች በተጨባጭ መስራታቸዉን (መሬት ላይ መኖራቸዉን) ቀድመን ካዘጋጀነው መለክያ ወይም መመዘኛ አንፃር ምን እንደሚመስሉ መገምገም ነው ይለናል። (2013).

የግለሰብ ስብእና የፓርቲ ስብእና እና ለመረጠው ተቛም ያለው ስብእና ተፃራሪ ሊሆን ይችላሉ። በቀጣይ ዉጥረትም ይኖራሉ። ለምሳሌ በተወካዮች ምክር ቤት ብንወስድ ከህገ መንግስታዊ ግዴታ ስንነሳ በአንድ በኩል ለህሊናው መቆም አለበት ይላል፤ በሌላ በኩል ለህገ መንግስቱ ይላል፤ በተጨማሪም የፓርቲ አደረጃጀት አባሉ ለፓርቲው ማሳየት ያለበት ስብእና አለ። በነዚህ ሶስት መሃል ያለው ቅራኔ አፈታት ዴሞክራሲዉን ወደፊት ወይም ወደሃላ ሊያስቀጥለው ይችላል። በአንድ በኩል ያለምንም ጥያቄ ለፓርቲ አቛም ድምፅ መስጠት አማራጭ ሃሳቦችን ያቐጭጫል፤ በሌላ መንገድ እያንዳንዱ የመሰለዉን ብቻ ከወሰነ ተደራጅቶ መታገልን ዉድቅ ያደርጋል። ጤናማ ዴሞክራሲ በነዚህ መሃል ያለዉን ዉጥረት አቻችሎ ይሄዳል። አብዛኛው ግዜ ለፓርቲ ዉሳኔ ድምፁን ቢሰጥም ከፓርቲው ወይም ከህገ መንግስታዊ መርሖች ወይም ስብእናው ተነስቶ ሊቃወም ይችላል። እንዲህ ዓይነት አቻቻይ ስርዓት ሲዘረጋ ጤናማ ዴሞክራሲ በተቛማት አለ ሊባል ይችላል።

የማዂዋየር መዝገበ ቃላት ስብእና ማለት የሞራል መርሆች እና ባህሪዎች ጥንካሬ፣ ቀናነት እና ቅንነት ነው ይላል። ሙሉ እና ሳያንሱ መገኘት ወይም አለመታወር ነው ይላል።. እያንዳንዱ ተቛም ስብእናዉን ጠብቆ የተጣለበትን ሃላፊነት መወጣት እና መብቶቹን ባግባቡ መጠቀም እሚችልበት ድባብ መፍጠር ቁልፍ መፍትሄ ነው። መንግስት የተቛማቱን ተገቢ ስብእና እሚጠብቁ እርምጃዎች እያከበረ የዴሞክራታይዜሽን ሃይል መሆን ገንቢው አማራጩ ሲሆን ይህን ችላ ካለ ግን መሃል ላይ መስፈር ብሎ ነገር ስለማይኖር የኢ-ዴሞክራታይዜሽን ሃይል ነው ሊሆን እሚችለው።

ያለን ህገ መንግስት በጥብቅ ተግባራዊ ማድረግ ዋናው መፍትሄ ነው፤ ይህን ለማድረግ ህገ መንግስቱ በጥብቅ ተግባራዊ ሲሆን ለበሽታዎቻችን መፍትሄ ማግኘት እንደሚቻል እሚያምን ቁርጠኛ አመራር ያስፈልጋል፡፡ ይህ ማለት የህግ አስፈፃሚው አካል ቁርጠኝነት በጣም ያስፈልጋል ማለት ነው። ቀደም ብሎ በተጠቀሰው የኢህአዴግ ፅሁፍ የሚከተለውን ሰፍሮ እናገኛለን፡፡ “የህግ አስፈፃመሚ አካል የህግ የበላይት ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስፈልጉ እንደ ፖሊሲና የመከላከያ ሃይል ያሉ ተቋሞችን የሚቆጣጠር በመሆኑ ለዴሞክራያዊ ስርዓት ግንባታው ታማኝ ካልሆነ የዴሞክራሲ ተቋሞችን አፈራርሶ ስርአቱን ለአደጋ ሊያጋልጠው ይችላል፡፡ በተግባርም የዴሞክራሲ ስርአትን የመፈታተን አደጋ የሚመነጨው በአብዛኛው ከህግ አስፈፃሚው አካል ነው” ይላል በገጽ 70 ላይ፡፡

ስለዚህ ህገ መንግስት በጥብቅ ተግባራዊ ማድረግ ማለት ህገ መንግስታዊነት በተግባር ማረጋገጥ እና ለሁሉም ዘላቂ ዋስትና መሆን የሚችል ህገ መንግስታዊ ዴሞክራሲያዊ ስርአት መገንባት ማለት ነው፡፡ ይህ ሲሆን ብቻ ነው አንድ ህገ መንግስት ትርጉም እና አርባና የሚኖረው፡፡

አገራዊ እና መንግስታዊ መዋቅሮች ከፓርቲ ተፅዕኖ አንፃራዊ ነፃነት እንዲኖራቸው ማስቻል፡፡ አንዱ የዴሞክራሲ ስርአት ግንባታ ምሰሶ የሆነው የተቋማት እርስ በርስ የመቆጣጠር እና ሚዛን የመጠበቅ ነው፡፡ ይህን እውን ለማድረግ የሚቻለው ደግሞ የመንግስት፣ የፓርቲ እና አገራዊ የሆኑትን ተቋማት ተገቢ ድንበራቸው ጠብቀው በተለይ ከፓርቲ መዋቅር ተነፃፃሪ ነፃነት ሲያገኝ ነው፡፡ ፓርቲ መንግስታዊ እና አገራዊ ተቋማትን በብቸኝነት ሲቆጣጠር በእኩልነት የተመሰረተ የምርጫ ውድድር አይኖርም በዚህም ምክንያት የህዝብ መሰረታዊ ዴሞክራያዊ እና ህገ መንግስታዊ መብቱ ይጣሳል፡፡ ይህ አንድ ምሳሌ ነው፡፡ በተጨማሪም ፓርቲ፣ መንግስት እና ቋሚ አገራዊ ተቋማት አንድ እና አንድ ሆነው የፓርቲው መሳርያ ከሆኑ፣ በፓርቲው ውስጥ የሚከሰቱ ችግሮች ባጭር ግዜና በቀጥታ ወደ መንግስታዊ እና አገራዊ ተቋማት ተዛምተው መላ አገሪትዋን ሊበታትን የሚችል ክፍተት እና ተጋላጭነት ሊያስከትል ስለሚችል ጉዳቱ በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ ይሄም ለዴሞክራያዊ ስርዓት ግንባታ እንቅፋት ይሆናል፡፡

ሎርድ አክተን የሚባል ሰውዬ “Power corrupts, and absolute power corrupts absolutely” ይላል፡፡ የፓርቲ መዋቅር የመንግስት እና አገራዊ ተቋማትን ነፃነት ነፍጎ የግሉ ካደረገ ፍፁማዊ ሃይል ሆኖ ለቁጥጥር እሚያስቸግር ፈላጭ ቆራጭ የሆነ ፀረ ዴሞክራሲያዊ አስፈፃሚ ነው እሚሆነው፡፡ በዚህ እና በብዙ ሌሎች ምክንያቶች ምክንያት ነው የመንግስት እና አገራዊ ተቋማት ከፓርቲ መዋቅር አንፃራዊ ነፃነት ያስፈልጋቸዋል የምንለው፡፡ከስር እምታዮት ምስል በዴሞክራስያዊ አስተዳደር ተቛማት እና ሂደቶች፣ የነዚህ ጥራት እና ጥራቱ ላይ ተፅእኖ እሚያሳድሩ አላባውያን መሃል ያለው ግንኙነት እሚያሳይ ሞዴል ነው። በተለይ የቡዙሓነት ፀጋ በተጎናፀፉት እንደኛ ያሉ ታዳጊ አገሮች የሚገኙ የዴሞክራሲ ተቛማት በህዝቦች መሃል ሊገኝ የሚችለዉን የተለያዩ ፍላጎቶች እና እሴቶችን መሰረት አድርገው መንቀሳቀስ ይኖርባቸዋል።

Diagram two

የአስተዳደር ይዘት እና ጥራት ላይ ተፅእኖ እሚያሳድሩ ዓዉዳዊ አላባውያን የሚለው፤ የተለያየ ማንነት ያላቸው የብሄር፣ በሄረሰብ፣ሃይማኖት፣የፆታ እና ሌሎች የማንነት ጥያቄዎች ሊያነሱ የሚችሉ ጉዳዮች ስርዓቱ እንዴት ያቻችላል (Accommodate ያደርጋል) የሚለዉን ማየት ጠቃሚ ነው። በተለይ የተለያዩ ቁሳዊ ፍላጎቶች እና የእሴት ጥያቄዎች ባለበት እነዚህ ሃይሎች ፍላጎታቸውን እና እሴቶቻቸዉን ማራመድ የሚችሉበት ድባብ መፈጠር አለበት። ሃሳባቸዉን ሳይሸማቀቁ መግለፅ መቻል አለባቸው፤ ይህ እንዲሆን የዴሞክራሲ መስተዳድር መኖር እና ዉጤታማ ተቓሞችና ሂደቶች በስምነቱ ባህርያት መለካት ያስፈልጋቸዋል:: ሃሳባቸዉን ሳይሸማቀቁ መግለፅ መቻል አለባቸው፤ ጠባብ፣ ትምክህተኛ፣ አክራሪ ተብለው ሳይፈረጁ። ጠባብነት፣ ትምክህት እና አክራሪነት ቢኖርም እኚህ ታርጋዎች እሚለጠፉት የማስረዳት አቅም ሲታጣ እንደሆነ እየተገነዘብን ነው።

ጠባብነት፣ ትምክህተኝነት እና አክራሪነት እንዲያብቡ እና ጉልበት አግኝተው የስጋት ምንጭ ሊሆኑ እሚችሉት መልካም አስተዳደር ሲጠፋ እና ፍት ሃዊ ልማት ማረጋገጥ ሳይቻል ሲቀር ነው። አሳታፊ፣ ግልፅ፣ ተጠያቂነት ያለው ለሚነሱ ጥያቄዎች ባፋጣኝ መልስ መስጠት የሚችል ብቁ እና ቀልጣፋ አስተዳደር ካለ ጠባብነት፣ ትምክህተኝነት እና አክራሪነት ሊፋፉበት እሚችሉበት እድል ስለሚዘጋ የስጋት ምንጭ አይሆኑም። ስለዚ ለጠባብነት፣ ትምክህተኝነት እና አክራሪነት ምቹ ሁኔታ የሚፈጥረው የቀጨጨ የዴሞክራሲ ሁኔታ ስለሆነ እነዚህ ችግሮች ማስወገድ ካለብን ምንጫቸው የቀጨጨ ዴሞክራስያዊ ሁኔታ መሆኑ መገንዘብ አለብን። መሰረታዊ ምንጩ ሳይገባን ችግራችን ጠባብነት፣ ትምክህተኝነት እና አክራሪነት ነው ማለት ግን አጠቃላይ ሁኔታው እንዳለመረዳት ይቆጠራል።

5.2 ምክር ቤቶች የዴሞክራስያዊ እንቕስቃስያችን ወሳኝ አምዶች ናቸው

በኢፌድሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 8 መሰረት የኢትዮጵያ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦች፣ ሕዝቦች የኢትዮጵያ ሉዓላዊ የስልጣን ባለቤቶች ናቸው ይላል፡፡ በዚህው አንቀጽ ንኡስ አንቀጽ 3 መሰረትም “ሉዓላዊነታቸውም የሚገልፀው በዚህ ሕገ መንግስት መሰረት በሚመርጧቸው ተወካዮቻቸውና በቀጥታ በሚያዳርጉት ተሳትፎ አማካይነት ይሆናል” ይላል፡፡ ህዝቦች የሚወከሉባቸው ምክር ቤቶች (በየደረጃው ያሉት) መንግስት ወይም አስፈፃሚው አካል በሚያከናውናቸው ተግባራት ዙርያ ይወያያሉ፣ ይራከራሉ፣ ቁጥጥር ያደርጋሉ፣ የተሰራውን ለህዝብ ያስተውቃሉ፣ የህዝብን አስተያየት እና ፍላጎት ላስፈፃሚ ያደርሳሉ፣ እንዲሁም አስፈፃሚው አካል ገቢ እሚሰበሰብበትን እና ስራ ላይ እሚያውልበትን አግባብ አሳይተው ተግባሩ እንዲያከናውን ስልጣን ይሰጣሉ፡፡ ይህንን ትልቅ ሃላፊነት ከሚወጡበት የአሰራር አይነቶች ደግሞ መንግስት በሚያቀርባቸው ረቂቆች ላይ ተወያይቶ መወሰን፣ የጥያቄ /ተጠየቅ መድረኮችን ማሰናዳት እና ቋሚ ኮሚቴዎችን አቋቁሞ ክትትል እና ቁጥጥር ማድረግ ነው፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞ በነሐሴ 1992 ዓ.ም “የዴሞክራሲ መሰረታዊ ጥያቄዎች በኢትዮጵያ” በሚል ርዕሰ ለውይይት በቀረበው የኢህአዴግ ፅሁፍ ላይ የሚከተለው ሰፍሮ እናገኛለን “አብዮታዊ ዴሞክራሲ ይህ (የህግ የበላይነት መርህ) በተሞላ መልክ ሊተገበር የሚችለው ከግልፅነትና ከተጠያቂነት ጋር ተዛምዶ መፈፀም ሲችል ነው የሚል እምነት አለው:: ግልፅነት ሲባል በየደረጃው ያሉ የመንግስት ሃላፊዎች የሚወሰንዎቸው ውሳኔዎች ምን እንደሆኑ፣ በየትኛው አግባብ እንደሚወሰኑ፣ ለምን እንደሚወሰኑ፣ ውጤቱ ምን እንደሆነ ግልፅ መሆን አለባቸው መደበቅ የለባቸውም ማለት ነው” (1992፡42) ይላል፡፡ ባጭሩ ተጠያቂነት በሌለበት የህግ የበላይነት በተሟላ መልክ ለመተግበር አይቻልም ይላል፡፡ ይህ ሰነድ አስከትሎም አብዮታዊ ዴሞክራሲ ህዝቡ ተወካዮችን እንዲመርጥ ብቻ ሳይሆን በሚገባ የሚቆጣጠርበት አሰራርም ይከተላል …. በዚህ መስክ አብዮታዊ ዴሞክራሲ የሚከተለው አሰራር ሊበራል ዴሞክራሲን መድረስ ወደሚችለው ከፍተኛ ጫፉ የሚያደርሰስና ህዝባዊ ባህሪ እንዲኖረው የሚያደርግ ነው” (1992፡62) ይላል።

መሪው ድርጅት ኢህአዴግ የምክር ቤቶችን የበላይነት አስመልክቶ ቅድም በተጠቀሰው ፅሁፍ እንዲህ ይላል “አብዮታዊ ዴሞክራሲ በህዝብ የተመረጡ ምክር ቤቶች ብቸኛ ህጋዊ የሆኑ ወሳኝ አካላት መሆናቸውንና በዚህ መንፈስ መስራት ያለባቸው መሆናቸውን ይቀበላል” (1992፡63) ይላል። አያይዞም ህዝቡ ምን እንደተወሰነ ብቻ ሳይሆን በማንና ለምን እንደተወሰነም ሊያውቅና ሊከታተል ይገባል፡፡

5.2.1 ህገ መንግስታችን እና የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት

የኢፌድሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 50/3 ላይ የፌዴራል መንግስት ከፍተኛ የስልጣን አካል የፌዴራሉ መንግስት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ነው፡፡ ተጠሪነቱም ለሀገሪቱ ህዝብ ነው፤ የክልል ከፍተኛ የስልጣን አካል የክልሉ ምክር ቤት ነው፤ ተጠሪነቱም ለወከለው ክልል ህዝብ ነው ይላል፤ ቀደም ብለን እንደጠቀስነው ገዢው ፓርቲ ኢህአዴግም ህገ መንግስታዊ ድንጋጌውን እንደሚቀበል አይተናል፡፡ ህገ መንግስቱ አስከትሎም የምክር ቤቱ አባላት የመላው ህዝብ ተወካዮች ናቸው፡፡ ተገዥታቸውም፤

ሀ. ለሕገ መንግስቱ

ለ. ለሕዝቡ እና

ሐ. ለሕሊናቸው ብቻ ይሆናል” ይላል ።

በሕገ መንግስቱ አንቀጽ 55 መሠረትየሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሰፋ ያለ ሥልጣንና ተግባር የተሰጠው ሲሆን፤ በአንቀፅ 72/2 መሰረት ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትሩና ካቢንያቸው ተጠሪነነታቸው ለተወካዮች ምክር ቤት መሆኑ ይደነግጋል። በማስታወቅያ ሚኒስቴር ፕሬስና ኦድዮቪዥዋል መምርያ በ 1994 ዓ.ም በታተመው “በኢትዮጵያ የዴሞክራስያዊ ስርአት ግንባታ” እሚለው ፁሁፍ ላይ የሚከተለዉን ሰፍሮ እናገኛለን። “ምክር ቤቶች የህዝቡ ሉአላዊነት መገለጫ የዴሞክራስያዊ አስተዳደር እምብርትና የዴሞክራስያዊ አገዛዝ አዉራ ተቛሞች ናቸው። ሌሎች የዴሞክራስያዊ አገዛዝ ተቛሞች እና ድርጅቶች የሚመሰረቱት በምክር ቤቶቹና ምክር ቤቶቹ በሚስርዋቸው ስራዎች ላይ ነው። በመሆኑም የነዚህ ምክርቤቶች መቛቛምና መጠናከር ለዴሞክራስያዊ ስርአታችን መጠናከር ወሳኝ ነው።” (ገፅ, 58-59)

5.2.2 የተወካዮች ምክርቤት ዓይነቶች

ዊልያም ሮቢንሰን እና ኔልሰን ፖልስፐይ በዓለም ላይ ያሉ የተወካዮች ምክር ቤቶችን በአራት ይከፍላዋቸዋል። እነዚህም፡- A. Transformative Legislature; B. Arena Legislatures; C. Emerging Legislatures; D. Rubber Stamp Legislature በማለት ይዘርዝርዋቸዋል።

1.Rubber Stamp Legislature

ማህተም መቺ ምክርቤቶች (Rubber Stamp Legislature) በጣም ቀላል የምክርቤት አይነቶች ናቸው። እነዚህ ምክርቤቶች ሌላ ቦታ የተወሰነን ዉሳኔን ማፅደቅ ነው ስራቸው። የዚህ ዓይነት ምክር ቤቶች ዓይነተኛ ምሳሌዎች በአምባገነን መንግስታት ስር የሚገኙ ምክርቤቶች ሲሆኑ የስራ አስፈፃሚው ዉሳኔዎችን ሳያንገራግሩ ለይምሰል ከማፀደቅ ያለፈ ሚና የላቸዉም። እንዲህ አይነት ምክር ቤቶች ኢ-ዴሞክራስያዊ በሆኑ አገሮች ብቻ እሚገኝ አይደለም ይላሉ አጥኚዎቹ። ለምሳሌ ባደጉ አገራት እሚገኙ የሰራተኞች ህብረት ምክርቤቶች የመሪዎቻቸዉን ዉሳኔ ለማፅደቅ ነው እሚሰበሰቡት ብለው እንደ አብነት ይጠቅሱታል። ዓይነተኛ አብነት ተድርጎ እሚወሰደው ደግሞ የ ቀደሞው ሶቭየት ህብረት ምክር ቤት ነው።

2.Arena Legislatures

እንዲህ አይነት ምክርቤቶች ደግሞ በማህበረሰቡ ዉስጥ ያሉ የተለያዩ ሃሳቦች እሚወከሉበት እና ተናጋሪ እሚያገኙበት ዓይነት ምክር ቤት ነው። ሞቅ ያለ የፖሊሲ ክርክር እና መንግስትን በተለያየ መለክያ መገምገም እሚችል ዓይነት ፓርላማ ነው። ዓይነተኛ አብነት ተድርጎ እሚወሰደው ደግሞ የኢንግሊዝ የታችኛው ምክር ቤት (House of commons) ነው። እንዲህ ዓይነት ምክርቤቶች በማህበረሰቡ ያሉ የተለያዩ ፍላጎቶች መወከል ስለሚያስችሉ ነው እንዲህ ተደርገው እሚተገበሩት። ስለዚ ዋና ስራቸው በጉዳዮች ዘርያ መከራከር እና ከተለያየ አቅጣጫ ግምገማ ማካሄድ ነው። ስለዚ እንዲህ ዓይነት ምክር ቤቶች ስራቸዉን በአግባቡ ማከናወን እሚያስችላቸው ዉስጣዊ አደረጃጀት እና አሰራር ያስፈልጋቸዋል።

3. Emerging legislatures

እንዲህ ዓይነት ምክርቤቶች በሽግግር ወቅት እሚፈጠሩ ዓይነት ምክርቤቶች ናቸው። በዚህ አዃሃን የተለመደው መንገድ ብዙ ዉስጣዊ መዋቅር እና አቅም ሳይኖረው ማህበረሰቡን በመምራት ረገድ የራሱን አስተዋፅኦ ለማድረግ እሚሞክር የምክር ቤት ዓይነት ነው። የቦሊቭያው እና በርከት ያሉ የላቲን አሜሪካ እንዲሁም የቀደሞ ሶቭየት ህብረት አባል ሃገራት የነበሩ ምክርቤቶች የዚህ ዓይነት ምክር ቤት ተጠቃሽ አብነቶች ናቸው። በቅርቡ ሜክሲኮ ላይ እየታየ ያለ ከ አንድ ፓርቲ የበላይነት በዉድ ድር ወደሚመሰረት ስርዓት የሚደረገው ሽግግርም የምክርቤቱን አቅም እሚገነባ እና ከአስፈፃሚው ጥገኝነት እሚያላቅቀው ነው ይላሉ አጥኒዎቹ።

4. Transformative legislatures

ይህ ዓይነት ምክርቤት ደግሞ ብርቅየና እምብዛም እማይገኝ የምክርቤት ዓይነት ነው ይሉታል። እንዲህ ዓይነት ምክር ቤቶች የዉክልና ዓቅማቸዉም የማህበረሰቡን ፍላጎት ቅርፅ ማስያዙንም የሚችል ዓይነት ምክር ቤቶች ናቸው። ባጭሩ እንዲህ አይነት ምክርቤቶች የዉክልና ባህሪያቸው እንደተጠበቀ ሆኖ መምራት ላይም ይሳተፋሉ። ይህ ለምድረግ እንዲህ ዓይነት ምክር ቤቶች ስራቸዉን ባግባቡ ለማከናወን እሚያስችል ዉስጣዊ መዋቅር እና ግጭቶችንና ልዮነቶችን እሚያስተናግዱበት አሰራር ይፈልጋል። የአሬናው ዓይነት ምክርቤት ባካባቢው ያለዉን ሙቀት እንደሚለካ ቴርሞሜትር ሲሆን የ ትራንስፎርማቲቩ ምክርቤት ደግሞ አካባቢው ላይ ምን ያህል ሙቀት መኖር አለበት ብሎ እንደሚወስን ተርሞስታት ነው ይላል። እንደኔ እምነት የአሜሪካው ምክርቤት ለሰርዓቱ የቆመ ምክርቤት እና ዉግንናው ከጭቁኖች ያልሆነ መዋቅር ስለሆነ ትራንስፎርማቲቭ እሚሆነው ስርዓቱን ለመጠበቅ እና የዋና ፖለቲካዊ ተዋንያንን ጥቅም ለማስከበር የቆመ መዋቅር ነው እላለሁ።

5.2.3 የተወካዮች ምክር ቤት እውነተኛ ገፅታ

የኢትዮጵያ ምክርቤት በ Emerging እና በ Rubber Stamp መሃል እሚገኝ፤ አስፈላጊ መሰረታዊ ለውጥ ከተደረገለት ተገቢ ሚናዉን መጫወት እሚችል ምክርቤት ነው ያለን። ተወካዮች ምክር ቤት ከላይ በህገ መንግስቱ እንደተዘረዘረው ግዴታዉ እየተውጣ ነዉ የሚለዉ ለመመለስ መዋቅራዊ መነሻዉ ማጥናት ተገቢ ነዉ፡፡ መንግስትና ገዢ ፓርቲ አንድ እና አንድ ሆነዉ የማይለዩበት በሆኑበት ምክር ቤት አባላት አንድ የሚታይ ዉጥረት ነዉ፡፡

ይሄ ውጥረት በተወካዮች ህሊና፣ ለወከሉት ማህበረሰብ እና ለህገ መንግስቱ ባላቸው ታማኝነት፣ ለፓርቲ ማስመስከር በሚገባቸው ታማኝት እና የኑሮ ጉዳይ በሚፈጥረው ግፊት ምክንያት የሚፈጠር ውጥረት ነው፡፡ ባጭሩ ሲገቡ በሚፈፅሙት መሃላ እና የፓርትያቸው ዲሲፒሊናዊ አሰራር እና ኑሮ መሃከል የሚከሰት ውጥረት ነው፡፡ ይህ ነው ስብእናዎችን ሚዛናዊ በሆነ መልኩ አቻችሎ አለመሄድ እሚያስከትለው መዘዝ። እዚህ ላይ ልብ ማለት ያለበን ጉዳይ መንግስት ዋና ኢንቨስተር መሆኑን ብቻ ሳይሆን የElected dictatorship”ም አለማዊ እውነታ መሆኑ ነው፡፡

ከዚህ ተነስተን ፓርላማው ባለፈው የGTP1 ዘመን በኢኮኖሚ አድገቱ እና በዴሞክራሲ ዙሪያ ምን ሚና ነበረው? ስንል የሚሰጠን ምስል ደብዛዛ ነው፡፡ በተመዘገበው የኢኮኖሚ እድገት አወንታዊ ሚና ነበረው አልነበረዉም ብሎ አስተያየት ከመስጠት በፊት፤ በመጀመርያ ምክር ቤቱ አሳታፊ፣ ግልፅነት እና ተጠያቂነት የነበረው አሰራር ነበረው ውይ? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው። እኔ እስከማውቀው ድረስ ከአስፈፃሚው የመጣዉን አዋጅ/ሹመት ወይም ሌላ ነገር ምክርቤቱ ተገቢ ከመሰለው ሳይቀበል ቀርቶ reject ሲያደርግ፤ መስተካከል ካለበት ማስተካከያ እንዲደረግ መልሶ ወደ ስራ አስፈፃሚወ ልከዋል የሚል በመገናኛ ብዙሃን የሰማሁበት ግዜ አላስታዉስም። ህዝቦች የማወቅ መብት እና ምክር ቤቱ የማሳውቅ ግድታ እነዳላቸው ልብ ይሏል::

ሁልግዜ የምንሰማዉ በሙሉ ወይም በአብላጫ ድምፅ ፀደቀ ሲባል ነው። ከቅርብ ግዜ ወዲህ አስፈፃሚዉን የመቆጣጠር አዝማምያ ቢኖርም ወጥነት የሌለው እና የተቆራረጠ ነገር ነው።ባጠቃላይ ሲታይ ምክር ቤቱ የመጣለትን የየዉሳኔ ሀሳብ ሲቅረብ ለዝረዝር እይታ ወደ እሚመለከተው ኮሚቴ መስተላለፍ እና የህዝብ ድምፅ የሚስማበተ መድርክ ማዝጋጀት እንደ ጥሩ አስራር ሊወሰድ የሚችል ሆኖ ድመፁ መከብሩን ግን የምናዉቅበት መንገድ የለም። የምክር ቤት አባሎች ለህገ-መንገሰቱ ና ለህሊናቸው ተገዥ መሆንና የመረጣቸው ህዝብና የፓርቲያቸው መመረያ በሚጋጭበት ሁኔታ የሚከተሉት አቅጣጨ ምን እንደሆነ የሚታወቅበት ሁኔታ የለም፡፡ እንደ ተቛም እለይ በተቀመጡት መስፍርቶች ሲመዘንም መልሱ ያው ነው፡፡እጅ እያወጡ ከማፅደቅ የዘለለ ከፍተኛ ትርጉም ያለው ሚና ነበረው ለማለት ያስቸግራል፡፡ በቅርብ ግዜ ት ዝታችን የተባበሩት የአሜሪካ መንግስታት ኮንግሬስ የኢራን ኑክሌር ስምምነት እነ እከሌ የሚባሉት ዴሞክራቶች ተቃወሙት ሲባል እንስማልን፡፡ የተባበሩት ኪነግደም ገዢው ኮነስረቫቲቭ ፓርቲ አውሮፓ ሕብረት ሪፈረነደም አካሄድ እሚመለከት የቀረበው የውሳኔ ሃሳብ የተወሰኑ አባሎቹ ስላልደገፉት ውድቅ ሆነ እነስማልን ወ.ዘ.ተ። እኛ አገር ዝምታ ነው ምናወቀው ነገር የለም:: የመረጥነዉን ወኪል እምንመዝንበት መረጃ የለንም፤ ለፓርቲ ነው የመረጣቹሁት ካልተባለን በስተቀር!! ድበቅነት በዛ ከልክ ያለፈ ሆነ!!!

ከዴሞክራሲ አኳያ ፓርላማው በ GTP 1 የነበረው ሚና ካነሳን ግን ምንም ሚና አልነበረውም ለማለት ያስደፍራል፡፡ እጅግ ብዙ ችግሮች እያሉ ሁሉም ነገር ሰላም እንደሆነ በሚያስመስል መልኩ “ዝምተኛ” ሆኖ አልፎታል፡፡ ፍትህ ሲጠፋ፣ ዜጎች ሲበደሉ፣ አስፃሚውን ደፍሮ የታገለበት አግባብ ስላልነበረ በዚህ ረገድ “የሉዓላዊ የስልጣን ባለቤትነቱ” ሳያረጋግጥ እንዳለፈ ይቆጠራል፡፡

የህዝቡ ተወካዮች ምክር ቤት የመረጣቸውን መራጭ ህዝብ ንቁና ቀጣይነት ያለው ተሳትፎ እሚያደርጉበትን ሁኔታ ማመቻቸት አለበት፡፡ አሁን ባብዛኛው እንደምታዘበው የመራጭ ህዝብ እና የተመራጭ ግለሰብ ግንኙነት ጎልቶ የሚታየው በምርጫ ሰአት ግዜ ነው፡፡ መራጮች ተወካዮውን በቀጣይነት እያገኝ ወቅታዊ ሁኔታቸውን ፍላጎታቸውንና ስጋቶቻቸውን እሚያስረዱበት አሰራር እና ሁኔታ መፈጠር ተገቢ ነው፡፡ ሲጀምር የህዝብ ተወካዮች እንደመሆናቸው መጠን የህዝቡን የልብ ትርታ ተቋማዊ በሆነ መልኩ በቀጣይነት እንዲገነዘቡ መራጩ ህዝብ ለተሳትፎ እና ቁጥጥር እሚመች ሁናቴ ማግኘት መቻል አለበት፡፡ አለበለዝያ በየአምስት አመቱ ምርጫ በመጣ ቁጥር ብቻ እየተገናኘ ትክክለኛ የመራጩን ህዝብ ተወካይ ናቸው ለማለት ያስቸግራል፡፡

ያገሪትዋን ከፍተኛ ስልጣን በህገ መንግስት የተረጋገጠለት ተቋም አሁን ያሉት አማራጮች ሁለት ናቸው፡፡ አንደኛው አማራጭ ህገ መንግስታዊ ስልጣኑን ተጠቅሞ የዜጎችን ጥቅም ማስከበር ሁለተኛው አማራጭ ህገ መንግስታዊ ስልጣኑን መጠቀም እማይቻል እና የህዝባችን አደራ መሸከም ካልቻለ ያገሪትዋን ሃብት ያላግባብ ከሚባክን ህዝበ ውሳኔ አዘጋጅቶ አይረቤነቱን ህጋዊ ድጋፍ ሰጥቶ ተቋሙን ማፍረስ፡፡ ልማታዊ ዴሞክራሲያዊ መንግስትነት ነው እሚከተለው በሚል ሃገር በልማቱም በዴሞክራሲውም ላይ የጎላ ሚና መጫወት እማይችል ፓርላማ ትርፉ ሃብትን፣ ጉልበትን እና ግዜን ማባከን ነው፤ በዚህ ምክንያትም ነው “እውን ኢትዮጵያ ፓርላማ አላትን?” ብለው ብዙዎች የሚጠይቁት፡፡ ምክርቤቱ ህገ መንግስታዊ ሃላፊነቱ እየተወጣ መሆን ያለበትን እየሆነ ከሄደ የዴሞክራታይዜሽን ሃይል መሆኑ አይቀርም፤ ይህን ችላ ካለ ግን መሃል ላይ መስፈር ብሎ ነገር ስለማይኖር ሃብት አባካኝ ተቛም ከመሆን አልፎ የኢ-ዴሞክራታይዜሽን ሃይል ነው ሊሆን እሚችለው።

የኢትዮጵያ መንግስት በ 1994 ዓ.ም ባሳተመው ፁሁፍ ላይ የሚከተለዉን ይላል “በመጀመርያ መቀመጥ ያለብት ችግር የአባላቱ (የምክር ቤቱ) ብቃት ነው። የምክር ቤቶቹ ስልጣንና ተግባር ምን ያህል ሰፊና ወሳኝ እንደሆነ፤ ምክር ቤቶቹ ሃላፊነታቸዉን በሚገባ መወጣታቸው ለዴሞክራስያዊ ስርአታችን ማበብ ምን ያህል ወሳኝ እንደሆነ በመገንዘብ ረገድ በምክር ቤት አባላትም ሆነ በሌላው የህብረተሰብ ክፍል፣ በየደረጃው ባሉ የህግ አስፈፃሚ አካላት ወዘተ በቂ ግንዛቤ የተያዘበት ጉዳይ አይደለም።” አሁንስ ከ 14 ዓመት በኃላ የተለየ ሁኔታ አለ ወይ? ለዚህም ነው ተቛማቱ ስለ ተግባር እና ሃላፊነታቸው ጠንከር ያለ ግምገማ እና ራስን መፈተሽ አስፈላጊ ሆኖ የሚገኝው።

5.3 የመገናኛ ብዙሃን