የሰይፉ ትዕይንተ-ወግና የሠርግ ድግሱ – ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
ትናንት ምሽት ጳጉሜ 1, 2007 ዓ.ም. ሰይፉ በትዕይንተ ወጉ (talk show) ለየት ያለ ዝግጅት አቅርቦ ነበር፡፡ ይህ ዝግጅቱ ጋብቻውን የተመለከተ ቢሆንም የሠርግ ድግሱ ወጭ በባለሀብቱ በሸክ ሙሐመድ አልአሙዲ በመሸፈኑ ሰይፉ ለሠርጉ አስቦት የነበረውን ወጭ 300,000 (ሦስት መቶ ሽህ) ብር ለሙዳይና ለመቄዶኒያ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች በማበርከት ሌሎች ግለሰቦችና ለጋሽ ድርጅቶችንም እንዲለግሱ በመገፋፋት በማበረታታት ማግኘት የተቻለውን ያህል ድርጅቶቹ መረዳት እንዲችሉ ሕዝቡም የተቻለውን በማድረግ እንዳይለያቸው አበክሮ በማሳሰብ የበጎ አድራጎት ድርጅቶቹን ለመርዳት ጥረት በማድረግ አስመስጋኝ ተግባር ከውኗል፡፡
የሚያሳዝነው ነገር ግን ዜጎች ለእነኝህና ለሌሎችም በጎአድራጎት ድርጅቶች በመለገስ የቱንም ያህል ብንረባረብ ይህ ችግር የሚቀረፍ ዘላቂ መፍትሔ ማምጣት የሚችል አለመሆኑ ነው መጥፎው ዜና፡፡ ምክንያቱም ከስር ከስር ይሄንን ችግር በማባባስ ጎዳና ላይ የሚወድቁ ወላጅ አልባ ወይም ወላጅ እያላቸውም በአቅም መዳከም ምክንያት ለጎዳና የሚዳረጉ ሕፃናት፣ ጧሪ ሰብሳቢ ያጡ አረጋዊያን፣ ያለ አንዳች ሀይ ባይና ከልካይ በከፍተኛ ደረጃ እየተስፋፉ በመጡት ሱስ አማጭ ንጥረ ነገሮችን በሚያቀርቡና በሚያስጠቅሙ ፍጹም ፍጹም ኃላፊነት የጎደላቸው የአገዛዙ መርዘኛና መሠሪ የአስተዳደር ዘይቤና አስተሳሰብ መጠቀሚያ የሆኑ የንግድ ቤቶች በሚያቀርቡት የጥፋትና ትውልድ በካይ አገልግሎት ሰለባ ሆነው ሱሰኛና የአእምሮ እክል ተጠቂ በመሆን ለሀገርም ለቤተሰብም ለማኅበረሰብም ለራሳቸውም የማይጠቅሙ ይልቁንም ሀገራችንና ኅብረተሰባችን ባለበት በዚህ ድህነቱ ላይ ተጨማሪ ፈተና የሆኑ የነፈዙ የነሆለሉ የአእምሮ ጤናቸውን ያጡ ለምንም የማይጠቅሙና ሸክም ወጣቶች እንዲኖሩ ተግቶ የሚሠራ ዕኩይ አካል አለና፡፡
ወላጆች እንደወላጅነታቸው ይህ ሁኔታ እጅግ አሳስቧቸው በእነዚህ በየሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶችና በየ ዩኒቨርስቲው (መካነ ትምህርቱ) ደጆች ላይ ተከፍተው ትውልድ እየበከሉ ያሉ ድርጅቶች እንዲዘጉ “የልጆቻችን መባለጊያ መደፈሪያ መበከያ ማዕከላት ሆነዋል” በማለት ፊርማ አሰባስበው “ለመንግሥት አካላት” ባቀረቡ ጊዜ “አርፋቹህ ተቀመጡ! ግብር ከፋዮች ማቸው!” የሚል ፍጹም ኃላፊነት የጎደለው በድንቁርና እብሪት የተሞላና ሸረኛ ምላሽ እየሰጠ ነው እያስፈራራ የመለሳቸው፡፡ ይህ ምላሹም አገዛዙ ትውልዱ የከሰረ እንዲሆን ሆን ብሎ እየሠራበት ያለ መሆኑን በሚገባ ቁልጭ አድርጎ አሳይቷል፡፡
በመሆኑም እንደዜጋ እውነት እነኝህ ችግሮች የሚያሳስቡን የችግሮቹ ተጎጂና ሰለባ ወገኖቻችንም የሚያሳዝኑን ዘላቂ መፍትሔ የምንሻ ከሆነና በዚህ ማኅበራዊ ችግር በከፍተኛ ማኅበራዊ ቀውስ ከመናጣችን በፊት ሀገርን ትውልድን አራሳችንንም መታደግ የምንሻ ኃላፊነት የሚሰማን ዜጎች ከሆንን መፍትሔው ለበጎ አድራጎት ድርጅቶች ገንዘብ ማዋጣትና ተመሳሳይ የበጎ አድራጎት ድርጅቶችን እንዲከፈቱ ማድረግ ማበራከት ሳይሆን እንደ ኢሕአፓ ዘመን ወጣቶች ጠያቂ፣ ተሟጋች፣ ሀገር ወዳድ፣ ትውልድ ኖሮ ቁም ስቅሉን እንዳያይ ሲል እንዲህ ዓይነት ትውልድ እንዳይኖር ማለትም በሱስና ተመሳሳይ ችግሮች የተተበተበ ትውልድ በማፍራት ላይ ተግቶ እየሠራ ያለውን፣ ዜጎች በገዛ ሀገራቸው የአገዛዙ ደጋፊ ካልሆኑ በስተቀር ሠርተው ማደር እንዳይችሉ በማድረግ እራሳቸውን ልጆቻቸውን ማስተዳደር መመገብ የማይችሉና ለጎዳና የሚዳርጉ ድሀ ኅብረተሰብ እያመረተ ያለውን፣ ሀገሪቱን የአንድ አናሳ ጎሳና ፍርፋሪ የሚለቅሙ የአገዛዙ ኅሊና ቢስ ደፋፊዎች ብቻ አድርጎ ሕዝብ እያሰቃየ ያለውን ጨቋኝ ፈላጭ ቆራጭ አንባገነን አገዛዙን አስወግዶ ዜጎች በዜግነታችን ብቻ በገዛ ሀገራችን በእኩልነት ልንስተናገድ የምንችልበትን ሰብአዊና ፖለቲካዊ መብቶቻችን ተከብረው በነጻነት ልንኖር የምንችልበትን ሀገርና ሥርዓት ማምጣቱ ላይ ተግተን መሥራቱ ብቻ በመሆኑ ይሄንን በማድረግ የዜግነት ኃላፊነትና ግዴታችንን መወጣቱ ላይ እንድንረባረብ በጥብቅ ማስገንዘብ እወዳለሁ፡፡
ይሄንን የዜግነት ኃላፊነትና ግዴታ የማንወጣና ከቶውንም መወጣት የማንፈልግ የማንሻ ጭራሽም ለዚህ ግፈኛ አገዛዝ መኖር ድጋፍ የምንሰጥና ምርኩዝ የምንሆን ሆነን ግን የቱንም ያህል የገንዘብም ይሁን የሌላ ድጋፍ ለበጎ አድራጎት ድርጅቶቹ ብናበረክት የዚህ ማኅበራዊ ችግር መንስኤዎች እንጅ የመፍትሔ አካል አለመሆናችን፤ በሀገርና በሕዝብ እየተሳለቅን መሆናችንን ጠንቅቀን ልናውቅ ይገባል፡፡ ዛሬ በሌሎቹ ላይ ያየናቸው ችግሮችም እነኝህ ችግሮች እንደ ማኅበራዊ ችግርነታቸው ነገ በየራሳችን ላይ የሚደርሱ ይሆናል፡፡
https://www.youtube.com/watch?v=R_Im1bI0AKc