“እግዜር ሲጣላ በትር አይቆርጥም…”
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
ከጋዜጠኛ ደምስ በለጠ
ይድረስ ለተከበሩ የአርበኞች ግንቦት 7 አመራር አባል አቶ ሙሉነህ ኢዩኤል ። ሰላምታየ እንዲደርስዎ ምኞቴ ነው። ሰሞኑን በዋሽንግቶን ዲሲና እኔ በምኖርበት በላስ ቬጋስ ከተማ ድርጅትዎ በጠራው ስብሰባ ላይ ያደረጉትን ንግግር በጥሞና አዳመጥኩ ። ስለ እርስዎ ንግግርም በቀረበው ዜና ላይ ፤ ከአስር አመት በፊት በቅንጅት አባልነትዎ ታስረው ሳለ ፤ ይወጡ ከነበሩት ፎቶውች አንዱ የሆነውን ፤ ከቅንጅት V ምልክት ጋር ሳየው ሃሳቤ ወደኋላ ይዞኝ ነጎደ።
እኔ ያኔ በዋሽንግተን ዲሲና አካባቢዋ ሁለት የራዲዮ ፕሮግራሞችን አዘጋጅ ነበር ። “ንጋትና” “አቡጊዳ” ራዲዮ። “ንጋት” በራዲዮ ሞገድና፤ በኢንተርኔትም ይተላለፍ ስለነበር በሳምንት የስምንት ሰአታት ዝግጅት ነበረው ። አለማቀፍ ይዘትም ነበረው ። “አቡጊዳ” ግን ለዋሽንግተን ዲሲ በራዲዮ ሞገድ ብቻ ትተላለፍ የነበረች ራዲዮ ነበረች ። እናም እርስዎ እስር ላይ እያሉ ፤ መብትዎ ይከበር ዘንድ እኔና ብዙ ብዙ ኢትዮጵያውያን ለናንተ መፈታት ታግለናል ። እንደናንተ እስር ቤት በአካል ባንገኝም ፤ በዋሽንግተን ዲሲ ነጩ ቤት መንግስት White House ፊትለፊት ለወራት በየቀኑ “የሻማ ማብራት” ፕሮግራም ተዘጋጅቶ ብርድ ፤ ዝናብ ፤ ቁር ሳንመርጥ ፤ ሻማ አብርተንላችኋል ። ብዙ ኢትዮጵያውያን እህቶች ለናንተ መፈታት ሱባኤ ገብተው ፤ ካልጋቸው ወርደው መሬት ላይ ይተኙ ነበር ። እናንተ ሲሚንቶ ላይ ትተኛላችሁ በሚል ህሳቤ ተጋድሏችሁን ለመዘከር ያደርጉት እንደነበርም አስታውሳለሁ ።ታዲያ እኔም ለአካላዊ ፤ መንፈሳዊና የሃሳብ ነጻነታችሁ ብሎም ሙሉዕ መብታችሁ መከበር ፤ በሙያዬ ታግያለሁ ። ይህን ለማድረግ ደግሞ በሳምንት ለሶስት ቀናት ፤ በየቀኑ ከምኖርበት የሲልቨር ስፕሪንግ ሜሪላንድ ፤ የመጨረሻ ጥግ ተነስቼ ፤ የራዲዮ ጣቢያው እስከ ሚገኝበት ሊዝበርግ ፓይክ ቨርጂኒያ ድረስ ፤ 70 ማይል እነዳ ነበር ። በንፁህ ህሊና ያለምንም ጥቅምና ክፍያ በናንተ በወገኖቼ ላይ ለደረሰው ግፍ እታገል ዘንድ ነበር ይህን ሳደርግ የነበረው ።
እንዲያውም አንድ ትዝታዬን ላጫውትዎ ። እናንተ ከታሰራችሁ በኋላ ተቃውሟችንን ለማሰማት እኔና ሌሎች ኢትዮጵያውያን ባደረግነው ጥሪ መሰረት አንድ ሰላማዊ ሰልፍ በዋሽንግቶን ዲሲ ተደርጎ ነበር ። ኖቨምበር 14 ቀን 2005 እ.ኤ.አ. ።
ኖቬምበር 14 የመፀው አጋማሽ ነው ። የዋሽንግተን ዲሲና አካባቢዋ ዛፎች የበረዶውን ወቅት መቃረብ ለማሳበቅ ቅጠሎቻቸው ረግፈዋል ። ዛፎቹም ላይ የቀሩት ወይበዋል ወይም ወደ ወርቃማ አለያም ቡናማ ወይም ቢጫ ቀለም ተቀይረዋል። እንዲህ ያለው ወቅት ነፋሻማና ብርዳማ እንደሚሆን ይታወቃል ። የሰላማዊ ሰልፉ አዘጋጆቹ ሁሉ በብርዱ ምክንያት ሰዎች ላይመጡ ይችላሉ ብለን ሰግተናል ። አጋጣሚ ሆኖ በእግዚአብሄር ፈቃድ የተረጋጋና ፀሃያማ ቀን ሆኖ ዋለ ። ቀኑ ፅሀያማ ቢሆንም ሞቃት ግን አልነበረም ። ይህም በትግላችን ላይ እግዚአብሄር ከኛ ጋር ነው ብለን እንድናስብ ምክንያት ሆነን ። ዝርዝር አላበዛም ። ሰልፉ ግን ከጠበቅነው በላይ ነበር ። በዲሲና በአካባቢዋ አንድ ሰው በቤቱ የቀረ አይመስልም ነበር ። በዋሽንግቶን ዲሲ ፖሊስ ዲፓርትመንት መረጃ መሰረት ወደ 30 ሺህ ሰው ሰልፉ ላይ ተገኝቶ ነበር ። አሜሪካንን በምስራቃዊ ዳርቻዋን በዋሽንግተን ዲሲ በኩል አልፎ ፤ ከሰሜን እስከደቡብ የሚያገናኘው Route 95 ለሰአታት ተዘግቶ ነበር ። ቨርጂኒያ ዲሲና ሜሪላንድ በቤልት ዌይ ካልሆነ በዲሲ በኩል ለማለፍ የማይቻል ሆነ ። 14 ኛውና 15ኛው መንገድ ላይ ወጣት ኢትዮጵያውያን መንገዶቹን ለመዝጋት አስፋልቱ ላይ ተደርድረው ተኙባቸው ። የዋሽንግቶን ሞል ፈረሰኛ ፖሊሳችም ሆኑ መደበኛዎቹ ፤ ያልጠበቁት ሁኔታ በመፈጠሩ ሃይል እንዲጨመር ጠየቁ ። ከወራት በፊት ወደ ኢትዮጵያ ተጉዘው ኢትዮጵያ ውስጥ እየተደረገ የነበረውን ሁኔታ ባይናቸው ያዩት ኮንግረስማን ክሪስ ስሚዝና ረዳታቸው ግሪጎሪ ስምኪንስም ሰላማዊ ሰልፋችንን ደማቅ ካደረጉት ሰዎች ይመደቡ ነበር ። በአሜሪካ ከተደረጉ እኔ ከማውቃቸው ሰላማዊ ሰልፎች ፤ እንደዚያ አይነት ደማቅ ሰላማዊ ሰልፍ ፤ ከዚያ በፊትም ሆነ ከዛ በኋላ ተደርጎ አላየሁም ። ሰላማዊ ሰልፍ ድሮ ቀረ ብየ ልቀልድ ይሆን ? ወደቁም ነገሩ ።
አጋጣሚ ሆኖ መፈክሮችና ፖስተሮች ሲታደሉ የእርስዎ ፎቶ ያለበት ፖስተር ደርሶኝ ያን አንግቤ እንደነበር ትዝ ይለኛል ። ከዚያም አልፎ በናንተ መፈታት እርግጠኛ ስላልነበርኩ በግሌ አስከ ኤርትራ የጠመንጃውን ትግል ለማየት ከሄዱት ጋዜጠኞች ቀዳሚው እኔ ነኝ ብል ጉራ አይሆንብኝም ። ከዛ ትግል በኋላ ፤ እርስዎ ነፃነትዎን አግኝተው በአሜሪካ ከተሞች እየዞሩ በነጻነት ንግግር ሲያደርጉ ስሰማ ፤ ሰው ነኝና ይኸው የትግል ፍሬዬ ጎመራ ብዬ መኩራራቴን በይሉኝታ መደበቅ አልፈለኩም ። እጅግ ደስ አለኝ ። እግዚአብሄር ይመስገን ።
ደስታዬ እንደተጠበቀ ሆኖ ፤ በነጻነት ባሰሙት ንግግር ላይ ግን የማንግባባባቸው ጉዳዮች እንዳሉ እንዲያውቁልኝ እፈልጋለሁ ። ኤርትራን አይቼ ሻእቢያን አውቄ ከመጣሁ በኋላ ሻእቢያ ዛሬ የመለያያ ነጥባችን ሆኗል።
“I don’t agree with what you say, but I will fight to the death to defend your right to say it” .
ትርጉሙ፡- “ከምትለው ጋር ባልስማማም፤የመናገር መብትህን ለማስከበር ግን እስከ ህይወቴ ፍፃሜ ድረስ እታገልልሃለሁ” ፤ የሚለውን የሰለጠነው አለም መርህ ይቀበሉታል የሚል እምነትም አለኝ ።
ውድ አቶ ሙሉነህ ! በዚህ ከተግባባን አንድ ለማናችንም ግልፅ እንዲሆንልን የምፈልገው ጉዳይ አለ ። ድርጅታችሁ ይመቸኛል ባለው መንገድና በመረጠው የትግል አቅጣጫ ቢጓዝ ተቃውሞ እንደሌለኝ እንዲያውቁልኝ እፈልጋለሁ ። እርስዎ እንዳሉት ከሰይጣን ተስማምቶ ጥሩ ውጤት ይመጣል ብዬ የማምን ሰው ግን አይደለሁም ። ሆኖም ግን የእምነት ነጻነት በሚከበርባት ሐገር የምኖር ሰው ነኝና የድርጅትና የግል መብትዎ ይከበር ዘንድ ፤ እታገላለሁ ። ታዲያ አንባቢዎቼ እርስዎ የተናገሩትን ይሰሙ ዘንድ ይህን ሊንክ ብጋብዛቸው ቅር እንደማይልዎ አምናለሁ ።
አንዳንድ ጉዳዮች እየተጠላለፉ ከኢትዮጵያ ጉዳይ ጋር ስለሚነካኩም ፤ በነዚህ ጉዳዮች ላይ የማንንም ፈቃድ ሳልጠይቅ በዜግነት መብቴ ብቻ የሚያገባኝ ሰው እንደሆንኩ እንዲያውቁልኝ እፈልጋለሁ ። ይህ የኔ አስተሳሰብ ብቻ እንዳይመስልዎ ፤ የብዙ ኢትዮጵያውያን ጭምር እንጂ ።
ስለኤርትራም ስናገር እዚያው ድረስ ሄጄ ፤ በእጄ ዳስሼ ፤ በጆሮዬ ሰምቼ ፤ በአይኔ አይቼ እንጂ ፤ ለፕሮፓጋንዳ በሻእቢያ የተለቀቁ የዩትዩብ ፊልሞችን መነሻ አድርጌ እንዳልሆነ ይገንዘቡልኝ ። ከንግግርዎ ላይ የሸተተኝ ነገር ስላለ ነው ይህን ያልኩት ። የንግግርዎን ቅኝት ከእዚህ በታች ባለው የዘውዴ አርአያ የፊልም ክምችት ፤ የሻእቢያ የፕሮፓጋንዳ ፊልም ላይ ስላገኘሁት አንባቢዎቼን ጋብዣለሁ ። ሊንኩን ይጫኑ ።
አንዳንድ ከርስዎ የምለይባቸውን ጉዳዮች ላንሳ ።
አርበኞች ግንቦት 7እና ኤርትራ በሚል ርእስ የተናገሩትን ሃሳብ ሙሉ ለሙሉ እቃወመዋለሁ ። የምቃወምበትን ምክንያት “በኤርትራ በኩል ለምን” በሚለው ፅሁፌ ላይ በሚገባ ያብራራሁት ስለሆነ እንዲያነቡት እጋብዛለሁ ። ሻእቢያ የቀየሰው የተቃዋሚዎች አደረጃጀት ስልት ለኢትዮጵያ አደጋ አለው ። እርስዎ እንደገመቱት ይህን ጥያቄ ወያኔዎች ከስብሰባቸው በኋላ ሊያነሱት ይችሉ ይሆናል ። እኔም እንደርስዎ በተቃዋሚ ጎራ የምገኝ ስሆን ፤ ወያኔዎቹ ሳያነሱት በፊት አንስቼዋለሁና የኔ ጥያቄ ነው ። ኢትዮጵያ ለምትባለው ውድ ሃገራችን ሻእቢያ እንቅልፍ አጥቶ ይጨነቅላታል ቢሉኝ ፤ ለምን ? ብየ እጠይቅዎታለሁ ። ኢትዮጵያን ይወዳልታል ቢሉኝ ፤ ለምን ? ለመልካም ጉርብትና ቢሉኝ ፤ ለምን? ለምን? አሁንም ለምን ?
የኢትዮጵያን አንድነት የምናስብ ሰዎች ለ30 አመታት በኤርትራ የተደረገውን የጦርነት ታሪክ የምንመለከተው የኢትዮጵያ ሰራዊት የአገሪቱን አንድነት ለማስከበር ያደረገው ተጋድሎ አድርገን ነው ። በኤርትራውያን ቤት ሰማእትነቱ ከኛ በላይ መሆኑን ግን በንግግርዎ ላይ እስክሰማ ድረስ አላውቅም ነበር ። አዎ ! የማንም አገር ሰራዊት የመጀመሪያ ግዴታው የአገር አንድንድትን መጠበቅ ነውና ሰራዊታችን የሃገሪቱን አንድነት ለማስከበር ጠመንጃ አንግቦ ነበር ። ሲተኮስበት ፤ ተኩሷል ። በኤርትራውያን በኩልም እቅፍ አበባ ይዘው ፤ ለአንድነት መጣ ብለው ፤ አልተቀበሉትም ፤ እነሱም ብረት አንስተው ነበር ። ሰራዊቱ የተዋጋው የአለም አቀፉ ህግ በሚፈቅደው መሰረት ፤ የግዛት አንድነቱን ለመጠበቅ ነበር ። የሻእቢያን መስዋእት ፤ በየቤቱ ሶስትና አራት ሙታን ለማድረግም አልነበረም ። ከዚህኛው ቤት ሶስት ከዛኛው ቤት አራት እያለም አልገደለም ። በንግግርዎ ላይ እርስዎ ለኤርትራ ሰማእታት ፤ ቤተሰቦች ፤ ስሜት ጭምር ተከራከሩ ። በሳል ፖለቲከኛ ፤ ሌላው ወገን ያልጠየቀውን ፤ ከፊት ከፊት እየቀደመ ፤ ይህንን ልናገርልህ ተዘጋጅቻለሁ ። መስዋእትነትህን አጎላልሃለሁ ማለት ምን አመጣው ?
አሜሪካ ያለምንም በቂ ማስረጃ ኢራቅን ወረረች ። ወደ 5ሺህ የሚጠጉ ወታደሮቿ መስዋእትነት ከፈሉ። አንድ ሚሊዮን የኢራቅ ሰው ደሞ በዚህ ወረራ ምክንያት አለቀ ። አንድም የአሜሪካ ፖለቲከኛም ሆነ ሚዲያ ፤ ይህን ያህል የገዘፈ እልቂት መናገር አይፈልግም ። ስለሞቱትና ስለቆሰሉት ዜጎች ወታደሮቹ ግን በየቀኑ ጀግንነታቸውን ያወሳል ። የሃገሩ ጥቅም ቀዳሚነት አለውና ። መስዋእትነት የከፈሉ ዜጎቹን አንገትም አያስደፋም ፤አያሳፍርምም ።
አንድ የማውቀውን ነገር ልንገርዎ ። ሻእቢያን ስለተለማመጡት የቆዳ ቀለሙን ቀይሮ እርስዎን ለመምሰል ጥረት አያደርግም ። የሻእቢያን መስዋእትነት ከኢትዮጵያ የአንድነት ተጋድሎ በላይ ስላጎሉለትም ሻእቢያ ነጥብ አይዝልዎትም ። እንዲህ እንደ እርስዎ ሲናገሩ የነበሩ ሰዎችን ፤ እኔ ራሴ ልመሰክር በምችልበት ሁኔታ ፤ በብዛት አስተናግዷልና ይታዘብዎታል ወይም “አልሰሜን ግባ በለው” ሲል ይሳለቅብዎታል ።
ንግግርዎ ላይ አንድ የተምታታ ነገርም ሰማሁ ። አቶ ስብኃት ነጋ አይናቸውን አጥበው ለኤርትራውያን ተከራክረዋል ብለው ከሰሷቸው ። አቶ ስብኃት ነጋ ኤርትራዊ ደም እንዳላቸው ለማናችንም ምስጢር አይደለም። አዎ ኤርትራዊ ደም አላቸዋና ይከራከሩላቸዋል ። እርስዎ ራስዎ ፤ የኤርትራዊ ደም የሌለዎት ሰው ፤ ከኛ መስዋእትነት በላይ ፤ ኤርትራውያን የበለጠ ሰማእትነት ከፍለዋል ብለው ሲናገሩ ፤ የአቶ ስብኃትን ስህተት አልደገሙትም ? ወይስ እርስዎና ድርጅትዎ ስትናገሩት ትክክል ነው ፤ አቶ ስብሐት ሲናገሩት ግን ስህተት ነው ።
አንድ የገረመኝ ጉዳይ ደግሞ ፤ የጃፓንና የአሜሪካ የዛሬ ወዳጅነት ብለው ያቀረቡት ተምሳሌት ነው ። ለዚህም ማስረጃው ቶዮታ መኪና በአሜሪካ ገበያ መሸጡ ነው ። ጃፓን ከጦርነቱ በኋላ ወታደራዊ አቅሟ ሙሉ በሙሉ ተንዶ ፤ ሱሪዋን እንድታወልቅና ቀሚስ እንድታጠልቅ የተደረገች ሐገር ናት ። ምንም አይነት ወታደራዊ እንቅስቃሴ እንዳታደረግ የሚጠብቁ የአሜሪካ ወታደሮች በተለያዩ የሃገሪቱ ክፍሎች የሰፈሩባት ሃገር ነች ።
ለዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ሲባል በድብቅ የሚያዙ ስምምነቶችና ጉዳዮች አሉ ። ለዚህም ሲባል በሚስጥር ተይዟል እንጂ ፤ አሜሪካ በጦርነቱ ጊዜ በጃፓን ምክንያት ያወጣችው ወጪና የጦር ካሳ በየአመቱ እስከዛሬ ድረስ እየተከፈለ ነው ። ገና ተከፍሎ አላለቀም ። በፓሲፊክ ውቅያኖስ ላይ የነበሩ ፤ የግዛት ይዞታዎቿን ሁሉ ፤ ለተባበሩት የጦር ቃል ኪዳን አገራት (Allies Power) አስረክባለች ። በሰሜን በኩል እዚያው አፍንጫዋ ስር ያሉት አራቱ ትላልቅ “የኩሪል” ደሴቶቿ ያኔ በሶቭየት ህብረት የተወረሱ ፤ እስካሁን ድረስ የራሺያ ግዛት ሆነው እንዳሉ ናቸው። ጃፓን ትነግዳለች እንጂ እስካሁን በውርደት ላይ ያለች አገር ናት ። በቶዮታም ውስጥ ሆነ በሌሎች የጃፓን ኢንዱስትሪ ውስጥ ምን ያህል የአሜሪካ ካፒታል እንዳለስ ያውቃሉን ? የአሜሪካና የጃፓን ግንኙነት ፤ እንዳሉት በፍቅር ላይ ይተመሰረተ ሳይሆን ፤ በፍራቻና “ማግኘት የምችለው ፤ የተሰጠኝን ብቻ ነው” በሚል መርህ ላይ የተገነባ ግንኙነት ነው ። ጃፓን Full Capitulation የተፈፀመባት ሃገር ነች ። ውርደቷን ባጭሩ ይመልከቱ ። ለግንዛቤ ይረዳዎ ዘንድ ይህን ሊንክ ይጫኑ ።
በዚህ መሰረት ወደኛ ስንመለስ ፤ ማነው አሜሪካ ማነውስ ጃፓን ? ኤርትራ ዛሬ አርበኞች ግንቦት 7ን ያስጠጋች፤ ለድርጅታችሁ ለክፉ ቀን ደራሽ ስለሆነችና ፤ በኤርትራ ትግል ጊዜ (እንደርስዎ አባባል) ከየቤቷ ሶስትና አራት ሰዎች የሞተባት አገር ስለሆነችም የአንበሳው ድርሻ ይገባታል ። ስለዚህ ኤርትራ አሜሪካ ነች ። ኢትዮጵያ ደግሞ ጃፓን ነች ። አጥፊ ናትና ። ለአንድነት የተዋጋው ወታደሯም ተሸንፏልና Full Capitulation ሊፈፀምባት ይገባል ነው የሚሉን ?
ኢትዮጵያ ልጆቿ እያለን ይህ ሊሆን አይችልም ። ሻእቢያ ሲያምረው ይቅር ! ኢትዮጵያ ለአንድነቷ የተዋጉ ወታደሮቿ በሕይወት እያሉ ፤ በ98 በእብሪት የደረሰውን የሻእቢያ ወረራ የመከቱ ኢትዮጵያውያን እያሉ አገራችን ለሻእቢያ እጇን አትሰጥም ። (የራስዎን ቃል ልጠቀምና) ይህን ጠላትም ወዳጅም ሊያውቀው ይገባል ።
በዚሁ ንግግርዎ ላይ አቶ እፍሬም ማዴቦን ጠቅሰው ፤ “ይህን አሉ ያን አሉ እየተባለ ተፅፏል” ። ዛሬ ግን ኤፍሬምና ኢሳኢያስ በአንድ ጠረጴዛ ዙሪያ እየተነጋገሩ ነው ብለው ደጋፊዎችችሁን አስጨበጨቡና አንድ ነገር እንድጠይቅ ገፋፋኝ ። ይህን ዜና አልሰማሁም ነበር ። ኢሳትም አልነገረንም ። ስለምን ነበር የተነጋገሩት ? ስለኢትዮጵያ ከሆነ ልናውቅ ይገባናል ። ስለድርጅታችሁ ከሆነ አያገባኝምና የምለው አይኖርም ። ሁሌም ግን በድብቅ የሚደረጉ ውሎች ፤ (የራሳቸውን የኤፍሬም ማዴቦን አባባል ልዋስና) የሚያስከፍሉት ዋጋዎች ከፍተኛ ናቸው ። (ይህን ጉዳይ በሌላ ፅሁፌ እመጣበታለሁ ።)
ከወደብ ጉዳይ ጋር በተያያዘ የድርጅታችሁን አቋም አስመልክተውም ፤ ንግግርዎ ላይ “የህዝቡን ውክልና ያገኘ መንግስት እስኪመሰረት ድረስ አንደራደርም” ብለዋል ። ይህን አቋማችሁን ብዙ ጊዜ ላነሳው ያሰብኩት ጥያቄ ነበርና እርስዎ ስላነሱልኝ አመሰግንዎታለሁ ። የወደብ ወይም የአሰብ ጉዳይ የመላው ኢትዮጵያዊ ጥያቄ ነው ። ካልተደራደራችሁ አትንገሩን ጥያቄው የድርጅታችሁ ስላልሆነ ። በኢትዮጵያውያን ጥያቄስ ላይ ይህን አቋም እንድትይዙ ማን ማንዴት ሰጣችሁ ? ሻእቢያም ቢሆን በአሰብ ጥያቄ የዋህ አይደለም ። ግልፅ ያለ የፖለቲካም ሆነ የመንግስት ፖሊሲ ስላለው ፤ ፖሊሲውን እንዲያሳያችሁ ጠይቁትና ወይ ከአቋሙ ትስማማላችሁ ፤ አለያም ቀጣዩን እርምጃችሁን ታስተካክላላችሁ ።
በዚህ ጊዜ ሰላማዊ ትግል ማንሳት ቅንጦት አይደለም ? ሲሉም በዚሁ በንግግርዎ ላይ ይጠይቃሉ ። እንዴት ብሎ ነው ሰላማዊ ትግል ቅንጦት የሚሆነው ። በማህተማ ጋንዲ ፤ ማርቲን ሉተርና፤ በማንዴላም ጭምር የተፈተነ ትግል አይደለም እንዴ ?
ድርጅትዎ እንደመረጠው ሁሉ ፤ ሌሎች የመረጡትን የትግል መንገድ ቅንጦት ነው ብሎ ማጣጣል ምን ይጠቅማል ? ለድርጅትዎ የሚያመጣው የፖለቲካ ትርፍስ ምንድነው?
ከዚያም ወያኔ ለአልሻባብ ገንዘብ አልመደበም ወይ ብሎ አለመጠራጠር የዋህነት ይሆናል ሲሉ ጠረጠሩና ፤ እኔንም እንድጠረጥር ገፋፍተው አንድ ነገር ጠረጠርኩ ። ጥርጣሬዬን ከማጋራቴ በፊት ግን አንድ ነገር ትዝ አለኝ ።
ነገሩ እንዲህ ነው ። ምርቱ በጎተራው የሞላ ፤ ከብቶቹ በደንብ የተያዙ ዶሮዎቹ የበዙ ፤ ቀፎዎቹ የተሰቀሉ ፤ ሁሉ የተትረፈረፈው ገበሬ ፤ ጎንደር ወስጥ ይኖር ነበር ። አንድ ወንድ ልጅ ነበረው ። ልጁ አድጎ ይረዳኛል ብሎ ሲያስበው ዋልጌ ሆነበት ። እድሜው እየጨመረ ቢመጣም በየኮረፌና መሸታ ቤቱ ከማውደልደል በቀር ፤ ችግር የሚሞላ ሆኖ አልተገኘም ። አባትየው ልጁን ጠራውና ይህን ጠባይህን የማታሻሽል ከሆነ ከቤቴ አባርርኻለሁ አለው ። ልጁም መሻሻል አልቻለም ፤ አባትም መጨርሻው ደርሶ አባረረው ። ጓዙን በከረጢት ከቶም ሰጠው ። ለመንቀሳቀሻ የሚሆን ገንዘብ ቸረውና ከቤቱ አሰናበተው ። የገበያ ቀን ነበርና ጓዙን ተሸክሞ ሲሄድ የመደሩ ሰዎች ያገኙታል ። ጓዝህን ጠቅልለህ ወዴት እየሄድክ ነው ሲሉም ጠየቁት ። ኩሩው ጎንደሬ ሲመልስም “ሸዋን ላቀና እየሄድኩ” ነው ነበር ያላቸው ። አባቱ እንዳባረረው ግን ትንፍሽ አላለም ።
የጎንደሬው ጉዳይ እንደተጠበቀ ሆኖ ፤ እንግዲህ ጥርጣሬዬን ልጠረጥረው ነው ። የግንቦት ሰባት ስራ አስፈፃሚ አባላት የሚኖሩት በሰሜን አሜሪካና በአውሮፓ ነው ። አቶ አንዳርጋቸው እስር ቤት ነው ያለው ። ሶስቱም በአሜሪካ ይኖሩ የነበሩት ፤ የስራ አስፈጻሚ አባላት ከአሜሪካ ወደአስመራ (ወደ ትግል) ሙልጭ ብለው ፤ ሲገቡ ምነው አንድ እንኳ የአውሮፓ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል ከአውሮፓ ወደአስመራ (ወደ ትግል) አልገባ ? ብዬ ጠረጠርኩ ። ታዲያ ይህ የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤት Executive Body ስልጣኑን ተጠቅሞ የወሰነው የፖለቲካ ውሳኔ ይሆን ብዬም ጠርጥሬአለሁ። እርስዎ እየጠርጠሩ እኔንም አስጠረጠሩኝ ። ለአውሮፓዎቹ የግንቦት 7 ስራ አስፈፃሚ አባላት የአሜሪካ መግቢያ ቪዛ እንዳይሰጥ መታገዱን መረጃ ስላለኝ ጥርጣሬዬ ውስጥ አልከተውም ። እርስዎ ሲጠረጥሩ እኔም ልጠርጥር ያልኩት ፤ ባለፉት 24 አመታት በተደረጉ የተቃዋሚ ታጋዮች እንቅስቃሴ ላይ ፤ አሜሪካ ተመሳሳይ እርምጃ ወስዳባቸው የነበሩ ሰዎች ትዝ ብለውኝ ነው ። የሚቀጥለውን አባባልዎንም አብረው ያያይዙልኝ ። “አሜሪካኖች የምናደርገውን ትግል በተሳሳተ መንገድ ቢፈርጁ አሁን ትግላችንን እናቆማለን ?” ብለው ጠይቀዋል ። ይሕንን አባባልዎን ከላይኛው ጋር ሳያይዘው ጥርጣሬየን የበለጠ አደመቀልኝ ።
መጨረሻም ላይ እንዲህ አሉ ።”አሁን ካለንበት ውርደት ለመውጣት ፡ ከምናደርገው ትግል አይደለም ምድራዊ ሃይል ሰማያዊ ሃይልም ሊያስቆመን እንደማይችል ወዳጅም ጠላትም ሊያውቀው ይገባል ።”
እውነት ነው ከውርደት ነፃነት ይመረጣል ። ለነፃነት ደግሞ መከፈል የሚገባውን መክፈል ተገቢ ነው ብዬም አምናለሁ ።
ኮለኔል መንግስቱ በስልጣን ዘመናቸው “አድሐርያንንና ተፈጥሮን (እግዚአብሄርን) በቁጥጥር ስር እናደርጋለን ብለው ፈክረው” አድሃርያንንም ሆነ ተፈጥሮን ሳይቆጣጠሩ ዚምባብዌ ገብተው ቀሩ ።
ፕሬዚደንት ኢሳኢያስ የእግዚአብሄርን ስራ ተገዳድረው ፀሓይ አትጠልቅም ፍካሬ ካሰሙን በኋላ ፤ ይኸው ፀሓይ ኡደቷ ሳይለወጥ ስትጠልቅ ስትወጣ ፤ ስትጠልቅ ስትወጣ 17 አመታት አለፏ ። እቡይነት ጥሩ አይደለም ።
ጠንካራ ክርስቲያኖችና ሙስሊሞች ለሰማያዊው ሐያል ሙሉ እምነታቸውን ሰጥተው ፤ በህይወታቸውና በኑሯቸው ላይ ሁሉ ፤ ፈሪኃ እግዚአብሄርና ፈሪሃ አላሕን ለብሰው ፀጋውን እንዲሞላላቸው በሚፀለይባት ኢትዮጵያ ፤ ሌላው ቀርቶ ፤ የቀድሞ ማርክሲስት ሁሉ ዛሬ የእግዚአብሄርን ሃያልነት ተረድቶ ፤ ምህረት ለማግኘት ቤተ-ክርስትያን ባጣበበበት ዘመን ፤ ይህን የመሰለ የትእቢት ንግግር ለማንም አይጠቅምም ። ወሬም አያደምቅም ፤ አያጣፍጥምም ። ያለ የሰማዩ ጌታ ፈቃድ ማንም የትም አይደርስም ። ሰማያዊው ኃይል ፤ ኃያል ነው ።
የአገሬ ባላገር ነገር አልጥም ሲለው እንዲህ ይላል ።
“እግዜር ሲጣላ በትር አይቆርጥም ፤
ያደርጋል እንጂ ነገር እንዳይጥም ።”
ቸር ይግጠመን
ኦገስት 29/2015
ላስ ቬጋስ ኒቫዳ ።