የበረኪና ሽብር ? ( ሄኖክ የሺጥላ )


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


የበረኪና ሽብር ? ( ሄኖክ የሺጥላ ) =======

ድሮ ድሮ ፣ ሕይወት ብርቅ በነበረበት ጊዜ ፣ አባት እና አናትን ማክበር እንዲህ እንደዛሬው ቀልድ ሳይሆን ፣ ያኔ ከጋብቻ በፊት ማርገዝ እንደ ትልቅ ነውር ይታይ በነበረበት ዘመን ፣ ድሮ ማለቴ ነው፣ ያኔ በደጉ ዘመን፣ አንድ ሰው << ዋ !ታንቄ ነው የምሞተው >> ካለ ፣ በቃ የነብስ አባት መጥቶ ይገዘታል ፣ አቡነ ሰበ-ሰማያት ይደገማል ፣ እንደው ጭንቀት ከሆነ ይለቀው ዘንድ እራቅ ወዳለ ዘመድ ጋ ሄዶ ፣ ከርሞ እንዲመጣ በአጃቢ ይላካል ። ፍቅር አጃኢብ የነበረበት ዘመን ። የልብስ በረኪና ፣ የመትረየስ ወይም እንደዛሬው << የፌደራል ፖሊስ ያኸል >> ማስፈራሪያ የነበረበት ጊዜ ።
አንድ ሴት ልጅ << ልጃገረድ > ፣ የአመት’ባል ልብስ ካልተገዛላት ፣ ወይም በድንገት ካረገዘች ፣ ወይም የእንጀራ እናቷ ካስማረረቻት ፣ << በአቅራቢያዋ ከሚገኝ ሱቅ >> በረኪና ገዝታ ጭልጥ ታደርግ ነበር ። አብዛኛውን ጊዜ ታዲያ ፣ እንዳይሞቱ ሆነው ነው የሚጠጡት ። አላማው በቤተሰብ ላይ ሽብር መንዛት ነው ። ልሞት ነው ፣ በቃ ከአሁን በሗላ አታገኙኝም ፣ ጠፍቼ ልሄድ ነው ። የአይጥ መርዝ ነው በልቼ የምሞተው ፣ እሌትሪክ ነው የምጨብጠው ፣ ውሃ ውስጥ ነው የምገባው ፣ በመኪና ነው የምገጭላችሁ እና ወዘተ ።

ያኔ ሽብር በየማጀቱ ነበር ፣ ግን በሬዲዮ አይወራም ፣ መንግስት ባጀት መድቦ ግዳዩን አይከታተልም ፣ በረኪና የሸጠው ሸምሱም ሆነ ፣ በረኪናውን ገዝታ የጠጣችው አስካለ ፣ << ለሽብር ጥፋቱ የሚሆናቸውን መሳሪያ ከዚህ አገኙ >> ብሎ ዜና የሚሰራ የፖሊስ ሬዲዮና ቴሌቪዥን የለም ። ሽብር ግን ነበረ ! ያኔ ሽብርተኛው ፣ <<ግንቦት ሰባት ከሚባል አካል ጋር በመቀናጀት >> አይደለም ሽብሩን የሚሰራው ። ለሽብሩ ማስኬጃም የሚጠቀምባቸውን ግብዓቶች ፣ በድብቅ በነጠላ ሸፍኖ ፣ ከ- ጏዳ በአሳቻ ሰዓት በመግባት ፣ የሽብር ተግባሩን ይፈጽማል ። በአብዛኛው ታዲያ ሽብሩን የሚፈጽመው ፣ ሰው ሲመጣ ጠብቆ ነው ። ምክንያቱም አፋጣኝ የህክምና እርዳታ እንዲያገኝ ።

ለምሳሌ ፣ የዛን ዘመን ሽብርተኛ << ባልቦላ ካጠፋ በሗላ ፣ የዔለትሪክ ገመዱን ሊይዝ ይችላል ። አሁን ግን ባልቦላ ማጥፋትም አይጠበቅበትም ። ለምሳሌ የዛን ጊዜ ሽብርተኛ << እጠፋላሁ >> ብሎ ካለ ፣ መንደሩ በሱ የእጠፋለሁ ዛቻ ይታመሳል ። በቃ እቤት ውስጥ ጠባቂ አብሮት እንዲሆን ይደረጋል ፣ ከቤቱ ድንገት ከወጣ << የሚጠፋው ልጅ !>> ተብሎ ይወራለታል ። እናቶች ፣ << የአከሌ ልጅ እጠፋለሁ አለ !>> ብለው በየ ቡና መጣጫው ያወሩለታል ። ያኔ መጥፋት እንኳ በጣም ብርቅ ነበረ ። በአሁኑ ጊዜ <<እጠፋለሁ!>> ብለህ ብትል ፣ << እስካሁን ምን ትሰራለህ ? እኩዮች ጣልያን ገብተው !>> ትባል ይሆናል ። ወይም ደሞ << እጠፋለሁ >> ብትል << አለህ እንዴ ?>> የሚል ጥያቄም ሊቀርብልህ ይችላል ።
ዛሬ አንድ ሰው በረኪና ጠጥቶ ራሱን ቢያጠፋ ፣ ቤተሰብ ቀድሞ የሚያየው የበረኪናውን ዕቃ ነው << እንዳለ ነው የጠጣችው ወይስ ትንሽ ለማጠቢያ የሚሆን አስተርፋልናለች ይቺ ጨካኝ ፣ በተወደደ በረኪና !>> የሚል ነው የመጀመሪያው ጥያቄው ( first-aid ) ማለት ነው ።

ታዲያ እንዲህ እንደዛሬው ፣ ሕጉ በረቀቀበት ሰዓት ፣ አንድ ሰው በረኪና ጠጥቶ ህይወቱ ከሞት አፋፍ ደርሳ ብትመለስ ፣ ዳኞች ፊት ራስ በማጥፋት ተከሶ ቢቆም ፣ የሚጠይቁት ጥያቄ የሚመስለኝ ። << ከአሸባሪው ግንቦት ሰባት ጋ ግንኙነት አለህ ?>> << ራስህን በበረኪና በማጥፋት ፣ መንግስታችን ፣ ከአምስት ዓመቱ የትራንስፎርሜሽን ግስጋሴ ለመግታት ; ከአልሸባብ እና ግንቦት ሰባት ጋ ተመካክረህ ያደረከው ነገር እንደሆነ ደርስንበታል !>> ። << በረኪናውንም ስትገዛ ገቢው ለኢሳት እንዲሆን ብለሃል አሉ ? ይህ እውነት ነው ? >> በረኪናውን በሰማያዊ ወረቀት ጠቅልለህ ወደቤትህ እንደገባህ ያየ ሰው ነግሮናል ፣ ይህም ለሰማያዊ ፓርቲ ያለህን አጋርነት ለማሳየት ነው !>> ከዚህ ቀደም ራስህን በገመድ ለማጥፋት ስትሞክር ፣ ጀግናው የፌደራል ሰራዊት በቦታው በፍጥነት ደርሶ እንዳተረፈህ ፣ ገመዱም ለግንቦት ስላሴ የተገዛ ሰንጋ የታሰረበት እንደሆነም ደርስንበታል !>> ይሉት ነበር ። ደግነቱ በረኪናም በሬም የለም እንጂ !

አዎ አሸባሪነት ፣ እንዲህ እንደዛሬው ፣ በመጻፍ ፣ በመናገር ፣ ሰላማዊ ሰልፍ በመውጣት ፣ የህዝቦችን እኩልነት በመሻት ፣ ላይ የተመሰረተ አልነበረም ። አሸባሪነት ያኔ በበረኪና እና በገመድ ነበር ። ጊዜው ግን እንዴት ይሄዳል እናንተዬ !