መለስ ሰጠ! መለስ ነሳ! (ከተስፋዬ ገብረአብ)
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
በዚህ ሰሞን “የዋህ አዛውንት” በሚል ርእስ ያሰፈርኩትን አጭር መጣጥፍ አስመልክቶ አንዳንድ አሉታዊ አስተያየቶችን አንብቤያለሁ። እናም “ዶክተር ነጋሶ ተርበዋል፣ ተጠምተዋል” በሚል ርእስ ታትሞ ያነበብኩት ቃለመጠይቅ እጅግ እንዳስገረመኝ ተጨማሪ አስተያየት ማከሉን ወደድኩ።
ዶክተር ነጋሶ የቤታቸው ጣሪያ ውሃ እንደሚያፈስና ቀዳዳውን በላስቲክ እየሸፈኑ ክረምቱን እንዳሳለፉ ተናግረዋል። እስኪ በድጋሚ እናጢነው? በርግጥ ለጣራ ቆርቆሮ መበሳት ችግር የነጋሶ አቅም ላስቲክ መሸፈን ብቻ ነበር? እኔ እስከማውቀው ለቆርቆሮ መቀደድ ችግር መፍትሄው ሌላ ቆርቆሮ መተካት ነው። ያን ማድረግ ደግሞ ከነጋሶ አቅም በላይ አልነበረም። ነጋሶን ከሚያክል የተቃዋሚ ድርጅት መሪ በዚህ ደረጃ ስለ ግል ችግር መስማትም የሚጠበቅ አልነበረም። ምክንያቱም የዚህ ዘመን አንገብጋቢ ጉዳይ የሃገሪቱ የህልውና ጣሪያ መቀደድ እንጂ የነጋሶ ጣሪያ ጉዳይ አይደለም።
“ነጋሶ ጊዳዳ የተሰናባች ፕሬዚዳንት ጥቅማ ጥቅማቸውን በመተዋቸው መስዋእትነት ከፍለዋል” በሚል ጀግንነታቸውን ማጉላት የሚፈልጉም አሳባቸውን ሰንዝረዋል። የ80 አመቱ አዛውንት አቶ ፅጌ ሃብተማርያም ጥረው ግረው ያፈሩትን ንብረት ሰውተው እስርቤት ተቀምጠው የለም እንዴ? ጄኔራል ተፈራ ማሞ አይነስቡ ላይ በቡጢ እየተደበደበ ማጎሪያ ቤት ተጥሎ የለም እንዴ? የጄኔራሉ ንብረት በመወረሱ ልጆቹ የሚጠለሉበትና የሚበሉት ተቸግረው ወድቀው የለም እንዴ? ለመሰረታዊ መብቶች መከበር ሲታገሉ ከባድ ስቃዮችን የሚቀበሉ ዜጎች ባሉበት ሃገር፣ እንዴት ነው ስለነጋሶ ጣሪያ መቀደድ መቆርቆርና ማዘን የሚቻለው? ይሄ ምፀት እና ፌዝ ነው።
ዶክተር ነጋሶ በቃለመጠይቁ ላይ፣ “ስለመለስ ዜናዊ የፖለቲካ ሰብእና” እንዲገልፁ ተጠይቀው ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል። የግል ችግራቸውን ለመተንተን ግን ሙሉ ገፅ አልበቃቸውም። “የዶክተር ነጋሶ መስዋእትነት” የሚባለው በኔ በኩል ተቀባይነት የለውም። የመስዋእትነትን ክብር ማዋረድም ይሆናል። ነጋሶ ሂሳባቸውን ያሰሉት፣ በየአምስት አመቱ እየተመረጡ የፓርላማ ወንበር ማሞቁን ነበር። በ1997 ፓርላማ ገብተው የፈየዱት አንድም ሊጠቀስ የሚችል ጠቃሚ ነገር አልነበረም። አምስቱንም አመት ሲሟገቱ የነበረው የተሰናባች ፕሬዚዳንት ጥቅማጥቅማቸውን ለማስከበር ነበር። በ2001 ምርጫ መለስ ሳይፈቅድላቸው ቀረ። በመሰረቱ ከስራ መባረር በነጋሶ የተጀመረ አይደለም። ዩኒቨርሲቲ መምህራን የነበሩ ከ40 በላይ ምሁራን ሲሰናበቱ ነጋሶ ስልጣን ላይ ነበሩ። እነዚያ የተባረሩ ምሁራን በመባረራቸው ችግር እንደደረሰባቸው ሲናገሩ አልሰማንም። ያልተናገሩት ችግር ስላልደረሰባቸው አይመስለኝም። ጉዳዩ በሃገር ደረጃ የመጣ ችግር ስለነበር፣ አጠቃላይ መፍትሄን የሚጠይቅ መሆኑን በመረዳት ይመስለኛል። በርግጥም አብዛኞቹ ወደ ትግሉ ነው የገቡት።
በተቀረ መለስ ዜናዊ የነጋሶ ጊዳዳን ጥቅማጥቅም በማስቀረቱ ጥፋተኛ ነው ብዬ አላምንም። ነጋሶ ጊዳዳ ፕሬዚዳንት የሆኑት በህዝብ ተመርጠው ሳይሆን፣ አንቀፅ 39 እንዲፀድቅ የህገመንግስቱን ጉባኤ በተሳካ ሁኔታ ስለመሩ መለስ ያበረከተላቸው ስጦታ ነው። ስልጣኑን ራሱ ሰጣቸው፣ ጥቅማጥቅሙንም ራሱ ነፈጋቸው። ዶክተር ነጋሶ የተነጠቁት ህዝብ የሰጣቸውን መብት ሳይሆን፣ መለስ የፈቀደላቸውን ነው። እናም “መለስ ሰጠ – መለስ ነሳ”።
(ፀሃፊውን ለማግኘት፣ [email protected])