የዋህ አዛውንት (ከተስፋዬ ገብረአብ)
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
በስደት በከተምኩባት የስደት ጎጆዬ በፀጥታ ተቀምጬ፣ “የስደተኛው ማስታወሻ”ን የአርትኦት ስራ እየሰራሁ ሳለ አንድ ጓደኛዬ የኢሜይል መልእክት ላከልኝ።
“ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ ስላንተ ተናግረዋልና አንብበው” የሚል ነበር መልእክቱ።
በተጠቆምኩት ሊንክ ገብቼ ቃለመጠይቁን አነበብኩት። እናም በእውነቱ የነጋሶ ቃለመጠይቅ ልቤን ክፉኛ ስለነካው፣ የአርትኦት ስራዬን አቋርጬ ይችን ወግ ጫርኩ።
* * *
የእንባ ከረጢቴ ባይደርቅ ኖሮ በነጋሶ ቃለመጠይቅ ስቅስቅ ብዬ አለቅስ ነበር። ዳሩ ምን ያደርጋል? ማልቀስ ካቆምሁ ቆየሁ። የቀድሞው ፕሬዚዳንት ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ እንዲህ ችግር ላይ ይወድቃሉ ብሎ ከቶ ማን ያስባል? በቃለመጠይቁ ከገለፁልን ጥቂቱን ልቀንጭብላችሁ፣
• ዶክተሩ ጣራው የሚያፈስ ቤት ውስጥ ነው የሚኖሩት? ጣራቸው ላይ ላስቲክ ሸፍነው ነው ክረምቱን ያሳለፉት? አንድ ቀን ጣራው ተንዶ ሊገድላቸው እንደሚችልም ገልፀዋል።
• ሩዋንዳዊቷ የማደጎ ልጃቸውም በችግር ምክንያት የፅዳት ሰራተኛ ሆና ተቀጥራ ትሰራ ነበር?
• ዶክተሩ መኪናም የላቸውም። በታክሲ ነው የሚጓዙት። ባለታክሲዎችም እየተሳቀቁ ሂሳብ አይቀበሏቸውም። ተሳፋሪዎችም ይከፍሉላቸዋል።
• መለስ ዜናዊ የጡረታ መብታቸውን አዘግይቶባቸው ቤት ውስጥ ምግብ የሚገዛውም በሚስታቸው ደሞዝና ልጃቸው የፅዳት ስራ ስትሰራ ውላ፣ ወገቧ ጎብጦ በምታመጣው ገንዘብ ነው።
እንግዲህ ከላይ የተገለፀው ሁሉ በነጋሶ ቃለመጠይቅ ላይ የተነገረ ነው። እና ይሄ አያስለቅስም?
ለዚህ ሁሉ አስለቃሽ ግፍ ደግሞ ተጠያቂው መለስ ዜናዊ ነው’ ብለውናል። ነጋሶ ቃል በቃል “አስር አመት ሙሉ ምግብ ለስራ ስሰራ ነበር” ሲሉ ነው ብሶታቸውን ለጋዜጠኛው የተነፈሱት። እኔ በበኩሌ ይሄን አላውቅም ነበር። ዶክተር ነጋሶ ላለፉት አስር አመታት “ምግብ ለስራ” ላይ እንደነበሩ ጋዜጦች እንዴት ሳይፅፉት እንደቀሩም አይገባኝም። ነጋሶ፣ እንደ ቤተመንግስቱ አንበሳ፣ “መለስ ዜናዊ እስር ቤት ሳይከተኝ፣ በጥይት ሳይመታኝ ‘በረሃብ’ ሊገለኝ ነው!!” ሲሉም እሪታቸውን ለኢትዮጵያ ህዝብ አሰምተዋል።
ዳሩ ግን ያልገባኝ ነገር አለ።
ልጃቸው አልተማረችም እንዴ? በእናቷ ጀርመናዊት፣ በአባቷ ዶክተር የሆነች የቤተሰቡ ብቸኛ ልጅ፣ ተምራ አንድ ደህና ቦታ መድረስ እንዴት አቃታት? ደግሞስ በእናቷ በኩል ስኮላርሺፕ ሊፈለግላት አልተቻለም ይሆን? ጀርመኖች ለዜጋቸው ቀርቶ ለኛ ለስደተኛውም ተርፈዋል። ለነገሩ የፅዳት ስራውን የምትሰራው የት ይሆን? ጀርመን ኤምባሲ ውስጥ ከሆነ መቼም ደሞዙ ከአንድ ሚኒስትር ደሞዝ እኩል ስለሆነ ዶክተር ነጋሶ ማለቃቀስ የለባቸውም። ይህም ሆኖ ነጋሶ ስለልጃቸው የፅዳት ስራ መስራት ሚዲያ ላይ ማወጅ አስፈላጊ ነበር? ምን ጥቅም ይገኝበታል? የማስተዛዘኛ የፖለቲካ ንግድ? በልጅህ መነገድ ግን ያልተለመደ ነው። ሰውም እኮ ይታዘባል መቼም። ስንቱ በ1000 ብር ደሞዝ ስድስት ልጆቹን አሳድጎ፣ አስተምሮ ደህና ቦታ ያድርስ የለም እንዴ? ነጋሶ ረጅም ጊዜ ታስረው የነበረ ቢሆን እንኳ፣ ምክንያቱ ይገባናል። ታስረው አያውቁም፣ ፕሬዚዳንት እያሉ ደግሞ የጠገበ ደሞዝ ነበራቸው። ለኑሮ ድምቡሎ አያወጡም ነበር። ስድስት አመታት ሙሉ ደሞዛቸው ዝም ብሎ ባንክ ነበር የሚገባላቸው። እና ምን አድርገው ጨረሱት?
እሺ ደህና እሱ ይቅር።
አንድ የታሪክ ምሁር እንዲህ ስለ ኑሮ ችግር አንስቶ ሲያለቅስ አያሳፍርም? ሚስቱ ጥሩ ደሞዝ ያላት፣ አንድ ልጅ ብቻ ያለው፣ የዶክተርነትን ማእረግ የለበሰ ሰው እንዲህ ምርር ብሎ ካለቀሰ፣ ሌላው ህዝብ እንዴት እየኖረ ነው ሊባል ይሆን? ለመሆኑ እነ ገብሩ አስራትና ስዬ አብርሃ በምንድነው የሚኖሩት? “ተቸገርን” ሲሉ ሰምተን አናውቅም። የግል ጉዳያቸውን ባደባባይ ማውጣት ስለማይሹ ይሆን ወይስ አልተቸገሩም? የነጋሶ መቸገር እንዴት የተለየ ሆነ?
እስከዛሬ በወያኔ የተፈናቀለው ባለሙያ እንዲህ እንደ ነጋሶ ተማርሮ ሲያለቅስ ሰምተነው አናውቅም። ነጋሶ ገንዘብ ያጠፋሉ እንዳይባል፣ ቀምቃሚ የሚባሉ አይደሉም። የሲጋራ ወጪ በርግጥ ሊጫናቸው ይችላል። ቢሆንም ግን ራሳቸውን ለመቻል መስነፍ አልነበረባቸውም። የታሪክ ምሁር እንደመሆናቸው መፅሃፍ ቢጤ ጫር ጫር ቢያደርጉ፣ መፃፍ ካልቻሉ ደግሞ የአስመሮም ለገሰን “ገዳ” ወደ ኦሮምኛ ቢተረጉሙ ለቀሪ ህይወታቸው፣ ስምና ገንዘብ ባተረፉበት ነበር። “በሚስቴ ደሞዝ ነው የምተዳደረው” የሚለው ማስተዛዘኛ ብዙም አልተመቸኝም። ወንድ ልጅ የፈለገ ቢቸግረው በሚስቱና በልጆቹ ፊት አያለቅስም። ባህላችን አይፈቅድም። አባት መከታና መመኪያ በሆነበት ህብረተሰብ ውስጥ ነው ያለነው። ከማልቀስ መሸፈት ይሻላል። እርግጠኛ ነኝ የነጋሶ ልጅ ቃለመጠይቁን ስታነብ በአባቷ ሁኔታ ትሸማቀቃለች። የኢትዮጵያ ህዝብ በመሰረቱ አልቃሻ አይወድም። “ከባልንጀራው ማታ የተለየ – እንደ አጥቢያ ኮከብ ሲነጋ ታየ!” እያለ በኩራት የሚዘምር ህዝብ መሃል አልቃሻነት ያስንቃል። ሌላው ሁሉ ቢቀር ለኑሮ አንዳንድ ዘዴ አይጠፋም። ለአብነት ቡልቻ ደመቅሳ ሃብታም ናቸው። የነጋሶም ጓደኛ ናቸው። ከእሳቸው ተበድረው ከሙያቸው ጋር የሚሄድ አንድ የአማካሪ ቢሮ ከፍተው መንቀሳቀስ ይችላሉ። የፓርላማውን ደሞዝ ተማምነው ቆይተው፣ እሱ ሲቀር እንደ ህፃን ልጅ “ራበኝ!!” ማለት ግን ያስተዛዝባል።
በተቀረ ነጋሶ በቃለመጠይቃቸው ላይ ቀደም ሲል ስለኔ ተጠይቀው ለአውራምባ ጋዜጣ የሰጡትን ምላሽ፣ “አላልኩም” ብለው ክደዋል። ይሄ አያከራክረንም። ጋዜጣውን በማየት ብቻ ማን እንደዋሸ ማረጋገጥ ይቻላል።
የመጨረሻው የነጋሶ አባባል ግን ልብ የሚነካ ሆኖ አጊንቼዋለሁ።
“ሰዎች መንገድ ላይ ሲያገኙኝ፣ ‘እንወድሃለን’ እያሉ ግንባሬና መላጣዬ ላይ ይስሙኛል” ነበር ያሉት።
ይሄ ትልቅ ሃብት ነው። ነፃነትን የመሰለ አርኪ ነገር የለም – በዚህች ምድር ላይ። መለስ ዜናዊ አዲሳባ ላይ በእግሩ ለመጓዝ ቢሞክር መላጣውን የሚስምለት አያገኝም። ይልቁን ቅንድቡን ለመላጨት በሚቸኩሉ ሰዎች ይከበባል። ቸር ያቆየን!!