የሃውልት ጉዳይ (ከተስፋዬ ገብረአብ)


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


ሰሞኑን “አዲስ ነገር – ድረገፅ” የለጠፋቸውን የዜና ጭማቂዎች ሳነብ ትኩረት የሚስብ ርእስ ገጠመኝ። ይህም ካርል ሄንዝ ለተባሉ ጀርመናዊ አዲሳባ ላይ ሃውልት ሊቆምላቸው የመወሰኑ ዜና ነበር።

ለመሆኑ እኒህ ሰው ማናቸው? ማነው የወሰነላቸው? በምን መለኪያ? ከማን ጋር ተወዳድረው? ለኢትዮጵያ ምን በጎ ቢሰሩ ይሆን፣ ለሃውልት የበቁት? የሚታወቅ ዝርዝር ነገር የለም።

ታሪካቸውን ለማንበብ ስሞክር፣ “ሰዎች ለሰዎች” የተሰኘ የበጎ አድራጎት ድርጅት መስርተው ብዙ ሰዎችን ህይወት ለውጠዋል ተባለ። የሰሩት መልካም ነው። ግን በመንግስት ደረጃ “እግዚአብሄር ይስጥልን” ቢባሉ አይበቃም?

በርግጥ መለስ ዜናዊ በጣም ያደንቃቸዋል። በመሆኑም ከሳር ቤት ወደ መካኒሳ በሚወስደው መንገድ ላይ አንድ አደባባይ ሸለማቸው። አደባባዩ ላይ የሚቆምላቸውን ሃውልት የመሰረት ድንጋይ ለማኖር ኩማ ደመቅሳ መታዘዙም ተዘግቦአል።

እንግዲህ ሌላ ያመለጠኝ ዜና ከሌለ በቀር፣ ኢህአዴግ በ20 አመታት ውስጥ እንዲገነቡ ካፀደቃቸው ሃውልቶች ውስጥ የካርል ሄንዝ 5ኛ መሆኑ ነው። ቀደም ሲል፣ የጄኔራል ሃየሎም፣ የአቡነ ጳውሎስና የአሉላ አባነጋ የተገነቡ ሲሆን፣ የአፄ ዮሃንስ በግንባታ ላይ መሆኑ ተሰምቶአል። ከቀዳሚዎቹ አራት ሃውልቶች አከራካሪው የአቡነ ጳውሎስ ብቻ ነው። 5ኛው ካርል ሄንዝ የሚያከራክር ሳይሆን የሚያስተዛዝብ ነው።

ሃውልቶች የአካባቢውን ህዝብ ስነልቦና ግምት ውስጥ ማስገባት አለባቸው። ለምሳሌ መለስ ዜናዊ የራሱን ሃውልት አዲሳባ ላይ ሊተክል አይችልም። ለመትከል ከወሰነ 24 ሰአት በታንክና በመትረየስ ማስጠበቅ አለበት። በመሰረቱ ግን በሃገር ደረጃ ሃውልት የሚተከልለት ሰው ማን መሆን እንዳለበት ጥናት ማድረግ ጠቃሚ ይመስለኛል። መለስ ስለፈቀደ ብቻ የተተከለ ሃውልት፣ የአካባቢው ህዝብ ድጋፍ ከሌለው ውሃ እንዳጣ ችግኝ መድረቁ አይቀርም።

በቅን ልቦና እናስብ ከተባለ ካርል ሄንዝ ከበአሉ ግርማ እና ከአፄ ቴዎድሮስ በፊት ሃውልት እንዲሰራለት መወሰኑ ለኢትዮጵያ ህዝብ ስድብ ነው። ለነገሩ የጥበብ ሰዎቻችን የተረሱ ናቸው። ከበደ ሚካኤል ከፑሽኪንና ከቦድሌር የሚያንሱ አልነበሩም። ጥላሁን ገሰሰና ፀጋዬ ገብረመድህን ሃውልቱ ቢቀር የመንገድ እና የሙዝየም ስም እንኳ ቢሰጣቸው መልካም ነበር።

ወያኔ በነበርኩበት ዘመን፣ “መቱ” የተባለችው ከተማ በበአሉ ግርማ ስም እንድትሰየምና ከሞጆ እስከ ዱከም ያለው መሬት “መዳወላቡ” የተባለ ስም ተሰጥቶት የኦሮሚያ ዋና ከተማ ሆኖ እንዲታወጅ የሚጠቁም አሳብ እፎይታ ጋዜጣ ላይ ፅፌ ነበር። ስለበአሉ ግርማ ሃውልት ማንሳቴ፣ ኩማን በጣም እንዳበሳጨው ትዝ ይለኛል። በስልክ “መነሻህ ምንድነው?” ብሎ ሲጠይቀኝ፣ በአሉ ግርማ ለእውነት ሲል ህይወቱን ስለከፈለ ይገባዋል። መቱን የመረጥኩለት ስለተወለደባት ነው። በአናቱ ደግሞ በአሉ ግርማ ኦሮሞ ነው” አልኩት። የመጨረሻዋ ነጥብ የኩማን ቀልብ ከሳብኩ በሚል የጨመርኳት ነበረች። አልተሳካልኝም። ምክንያቱም የኩማ ጆሮ ከበላይ አካል የሚመጣን አሳብ ብቻ ነው የሚያዳምጠው። ይኸው አሁን ኩማ ለካርል ሄንዝ ሃውልት እንዲተክል ሲታዘዝ በደስታ መቀበሉን ሰማን። ርግጥ ነው፣ህዝቡ ተባብሮ ለበአሉ ግርማ ሃውልት ለመስራት ቢጠይቅ እንኳ፣ አዲሳባ ላይ አደባባይ እንደማይፈቀድ ግልፅ ነው። በአሉ ግርማ ለኤርትራ ህዝብም ውለታ የሰራ እንደመሆኑ፣ አስመራ – ፓራዲዞ የተባለው ሰፈር ላይ ሃውልት እንዲያቆምለት ሻእቢያን በደብዳቤ የመጠየቅ አሳብ አለኝ። ምክንያቱም መቃብሩ ያልታወቀው በአሉ ሃውልት ሊኖረው የግድ ይላል። ወጣቶች የበአሉ ግርማን ሃውልት ሲመለከቱ፣ የመንፈስ ብርታት እንደሚያገኙ ምንም ጥያቄ የለውም። በርግጥም በዚያ በጨለማው ዘመን በአሉ ግርማ ጭል ጭል የምትል የሻማ ብርሃን ነበር። የኤርትራ እና የኢትዮጵያ ጉዳይ ወዴት እያመራ እንደሆነ ማየትና ያየውን መናገር የቻለው፣ ሻእቢያ ገና ናቅፋ ተራራ ላይ ሳለ መሆኑ ሲታሰብ በአሉ ነቢይ ነበር ያሰኛል።

ከ15 አመታት በፊት “እፍታ” በተባሉ የመፃህፍት ቅፆች ላይ ይህንኑ የሃውልት ጉዳይ አንስቼ በጠነከሩ ቃላት መተቸቴን አስታውሳለሁ። ለመጪው ትውልድ አርአያ ሊሆኑ ለሚችሉ ሰዎች ሃውልት ለማቆም የሚወሰነው በምን መለኪያ ነው?

የግጭት ሰበብ መፍጠሪያ ፈንጂ ለመቅበር ካልሆነ በቀር፣ የአቡነ ጳውሎስ ሃውልት አስፈላጊ አልነበረም። ሃውልት የሚተከልለት ሰው አበባ ሲቀመጥለት ነው የምናውቀው። በዚህ ዘመን “በሽብርተኞች” እንዳይመታ ጥበቃ የሚደረግለት ሃውልት ቢኖር የአቡነ ጳውሎስ ሳይሆን አይቀርም። ወደፊት የአቡነ ጳውሎስ ሃውልት መፍረሱ እንደማይቀር ወያኔ ያውቃል። ያን ጊዜ ግን፣ “አቡነ ጳውሎስ ትግሬ ስለሆኑ አማራዎች ሃውልቱን አፈረሱት” በሚል ሊቀሰቅስበት ይሞክር ይሆናል።

እየቆየ የሚፈነዳ ፈንጂ የሚባለው እንግዲህ እንዲህ ያለው ነው። ነገር ፍለጋ ካልሆነ፣ ሰውየው እንዲህ በህዝብ እንደተጠሉ እየታወቀ ሃውልታቸውን አዲሳባ መሃል መትከል ምን አመጣው? የልዩነት ሰበብ እንዲሆን?

በሺህ ዘመን ትውልድ ህያው የሚሆን ታሪክ ሰርተው ያለፉ፣ ሃውልታቸውን የተከሉት በሰው ልጅ መንፈስ ውስጥ ነው። በጎ ተግባር እንጂ ሃውልት ህያው አያደርግም። መለስም ቢሆን፣ በባከነ ሰአት ተጠቅሞ፣ ከእልህ ፖለቲካ ወጥቶ፣ አንድ ጎል ቢያስቆጥር በመትረየስ የማይጠበቅ ሃውልት መገንባት በቻለ ነበር። ለዚህ ግን የታደለ አይመስልም። ከህዝቡ ፍላጎት በተቃራኒው ጎዳና መጓዙን ቀጥሎበታል።

በመጨረሻ በአለም ፀሃይ ወዳጆ አንዲት የምወዳት ግጥም ልሰናበት፣

አክሱም ላሊበላን – የቀየሰ አእምሮ፣
ያነፀው አዋቂ – ዛሬ ቢኖር ኖሮ፣
ይወቀስ ይሰደብ – ይወገዝ ነበረ፣
እንኳን እሱ ሞቶ – ስራው ብቻ ቀረ።

ፀሃፊውን ለማግኘት፡ [email protected]———————————————————————