[የክቡር ሚኒስትሩ ሾፌር ከቤታቸው ሊወስዳቸው ሲመጣ ግቢው ውስጥ ድንኳን ተጥሎ ይመለከታል]
- ሰላም አይደለም እንዴ ክቡር ሚኒስትር?
- በጣም ሰላም ነው፡፡
- የምን ለቅሶ ነው?
- ምንድን ነው የምታወራው?
- ማን ሞቶ ነው ድንኳን የተጣለው?
- ምን ዓይነት ሟርተኛ ነህ?
- የምን ሐዘን ነው ብዬ ነዋ?
- ኧረ እኔ ቤት ፌሽታ ነው እንጂ ሐዘን የለም፡፡
- አገር ሐዘን ላይ ሆኖ የምን ፌሽታ ነው?
- ስማ እኔ ጋ ሁሌም ፌሽታ ነው፡፡
- አገር እንደዚህ እየተበጠበጠ?
- የእኔ ፀረ ሰላም፣ አገሪቷ ራሷ ሰላም ናት አልኩህ እኮ፡፡
- በአገሪቷ የሉም እንዴ?
- የእኔ ቤት አገሪቷ ውስጥ አይደል እንዴ ያለው?
- አልመሰለኝም ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እንዴት ማለት?
- ታዲያ የምን ፌሽታ ነው ቤትዎ ያለው?
- የፆም መያዣ ነዋ፡፡
- ምን?
- ስማ በውስኪ ተራጨን፡፡
- እየቀለዱ ነው?
- አትሰማም እንዴ በውስኪ ታጠብን አልኩህ እኮ?
- እኔ የምታጠብበት ውኃ አጥቼ በዝናብ ውኃ እየታጠብኩ ነው፤ እርስዎ…
- ምን ታደርገዋለህ? ይታደሉታል እንጂ አይታገሉትም ሲባል አልሰማህም?
- እርሱስ ልክ ብለዋል፤ የታደሉ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ስማ ድል ያለ ድግስ ደግሼ ነበር፡፡
- እስቲ ትንሽ ይንገሩኝ?
- ትልቅ የሐረር ሠንጋ ነው ያረድኩት፡፡
- እሺ፡፡
- ከዛ በቃ በብላክ ሌብል ነው የተጀመረው፡፡
- ብላክ ሌብል ሲሉ ጥቁር ፊሊተሩን ማለትዎ ነው?
- ምን ይላል ይኼ ውስኪ ነው እንጂ?
- እ…የሀብታሞችን ፊሊተር ነው የሚሉኝ?
- ከዛ በቃ ብሉ ሌብልና ጐልድ ሌብል ነበር ሲጠጣ የነበረው፡፡
- ጐልድ ሌብል?
- አዎን፡፡
- ወርቅም ትጠጣላችሁ?
- ስማ ከተመቸህማ አልማዝም ልትጠጣ ትችላለህ፡፡
- እሺ፡፡
- ከዛ ደግሞ መሀል ላይ አንድ ሁለት ሙክት ታረደ፡፡
- ይኖሩታል እኮ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ስማ ኢንቨስተር በል ባለሥልጣን ቤቴ ሲጋፉ ነበር፡፡
- እንዴ እርስዎ ቤት ነበራ ታዲያ ሰላማዊ ሠልፉ የነበረው?
- የምን ሰላማዊ ሠልፍ ነው?
- ይቅርታ እርስዎ መቼ እንደዚህ ዓይነት ነገር ይገባዎታል?
- እኔ ልማት ብቻ ነው የሚገባኝ፡፡
- ክቡር ሚኒስትር እንዴት ግን አልጠሩኝም?
- የት ነው የምጠራህ?
- እንደዚህ ዓይነት ድግስ ሲደግሱ ነዋ፡፡
- ማንን?
- እኔን ነዋ፡፡
- በምን አስታውሼህ?
- አያስታውሱኝም?
- ኧረ በፍጹም፡፡
- ለነገሩ በእንትንስ ተረስቼ የለ?
- በማን?
- በመንግሥት!
[ክቡር ሚኒስትሩ ከአንድ ባለሀብት ጋር በከተማችን ውስጥ በቅርቡ በተከፈተ ሆቴል ምሳ እየበሉ ነው]
- እየበሉ ክቡር ሚኒስትር?
- ሰላጣው ይቅርብኝ ብዬ ነው፡፡
- ለምን?
- ያው አተት ምናምን ብዬ ነው፡፡
- መተት ማለትዎት ነው?
- የምን መተት ነው?
- ማለቴ መደበኛ ተቅማጥና ትውከት ነዋ፡፡
- ቀልደኛ ሆነሃል ልበል?
- ክቡር ሚኒስትር በዚህ ዓመት በጣም ቀናዎት አይደል?
- እኔ ሁሌም እንደቀናኝ ነው፡፡
- አይ ክቡር ሚኒስትር፣ እርስዎ ግን የሚገርም የቢዝነስ ጭንቅላት ነው ያለዎት፡፡
- ለምን ይምስልሃል እንደዚህ የከበርኩት?
- ሁሉም ባንኮች እኮ የሚገርም ትርፍ ነው የተንበሸበሹት?
- ስማ ያኔ ሼር ግዛ ብዬ ነግሬህ ነበር እኮ፡፡
- ክቡር ሚኒስትር የእርስዎንማ ምክር ሰምቼ ቢሆን ኖሮ፣ እንደ እርስዎ አሁን ከአምስትና ከስድስት ባንኮች ዲቪደንዴን በተቀበልኩ ነበር?
- ምክሬን ስማ የምልህ ለዚህ ነው፡፡
- አሁን ነው የገባኝ፡፡
- ሁሉንም እንቁላሎችህን በአንድ ቅርጫት አታስቀምጥ ሲባል አልሰማህም?
- ኧረ ሰምቻለሁ፡፡
- ስለዚህ ኤክስፖርቱ ሲቀዘቅዝ፣ ባንኩ ይደግፍሃል፡፡
- ብልህ እኮ ነዎት ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ሞኝ መሆንማ አያዋጣም፡፡
- ጠፍተዋል ግን ክቡር ሚኒስትር?
- ዕድገቱ ነዋ፡፡
- ውርደቱ ማለትዎ ነው?
- የምን ውርደት ነው? የአገር ዕድገት ነው ያጠፋን፡፡
- ኧረ ብዙ ውርደት ሊኖር ይችላል፡፡
- የምን ውርደት?
- ለምሳሌ ኦሊምፒክ ተጀምሯል፡፡
- ኦሊምፒክ ተጀምሯል እንዴ?
- እንዴ መጀመሩን አልሰሙም?
- ስማ ስንት ነገር እያለ እሱን ልከታተል?
- ለነገሩ ሥራ ይበዛብዎታል፡፡
- በነገራችን ላይ አንድ ነገር በራልኝ፡፡
- ምን ክቡር ሚኒስትር?
- መጋዘኖች አሉ አይደል?
- አሉ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ታዲያ ማተሚያ ማሽኖች ለምን አናስመጣም?
- የምን ማተሚያ ማሽን?
- የቲሸርት ማተሚያ ነዋ፡፡
- እንዴ ክቡር ሚኒስትር እያወቁት?
- ምኑን?
- ኤልሲ እኮ ችግር ነው፡፡
- እሱንማ በእኔ ጣለው፡፡
- ለነገሩ እርስዎ ምን ተስንዎት?
- ስሜ ራሱ ምንተስኖት ነበር መባል ያለበት፡፡
- ለነገሩ ቲሸርት ማተሚያ ማሽን ምን ያደርግልናል?
- ኦሊምፒክ ተጀምሯል አልከኝ እኮ?
- እሱማ ተጀምሯል፡፡
- ስለዚህ ወርቅ የሚያመጣውን አትሌት ፎቶ በቲሸርት አትመን መቸብቸብ ነዋ፡፡
- ክቡር ሚኒስትር ወርቅ ባናመጣስ?
- ብር ያመጣውን ፎቶ እንሸጣለና፡፡
- እንዴ ብር ባናመጣስ?
- ነሀስ ማምጣታችን አይቀርማ፡፡
- እሱንስ ባናመጣ?
- ለእንትን ብለን እንሸጣለን፡፡
- ለምን?
- ለተሳትፎ!
[የክቡር ሚኒስትሩ ጸሐፊ ቢሯቸው ገባች]
- ያ ሰውዬ መጥቷል ክቡር ሚኒስትር፡፡
- የቱ ሰውዬ?
- የኮርፖሬሽን ኃላፊው፡፡
- የምን ኮርፖሬሽን?
- የኪራይ ሰብሳቢ ኮርፖሬሽን ምናምን የሚለው፡፡
- እ… የፀረ ኪራይ ሰብሳቢ ኮርፖሬሽን ኃላፊው?
- አዎን፡፡
- አስገቢው፡፡
[የፀረ ኪራይ ሰብሳቢ ኮርፖሬሽን ኃላፊው ቢሯቸው ገባ]
- በቃኝ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- መቼ ብላ አልኩህ?
- በቃኝ፣ በቃኝ አልኩኝ፡፡
- መቼ ብላ ተባልክ?
- እኮ አልበላም ነው የምለው፡፡
- መጀመሪያስ ማን ብላ አለህ?
- የሚበሉትም ግን ማቆም አለባቸው፡፡
- ምን?
- ሁሉም እኮ ነው የሚበላው፡፡
- ምንድን ነው የምታወራው?
- ከላይ እስከ ታች ኪራይ ሰብሳቢ ነው፡፡
- እኔን ጨምሮ?
- አዎን ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ምን?
- ሁሉም እዚህ መሥሪያ ቤት ያለ ሰው ኪራይ ሰብሳቢ ነው፡፡
- እና ምን ልታደርግ ነው?
- በቃ ለበላይ ኃላፊዎች አጋልጣለሁ፡፡
- ከዛስ?
- የሚሆነውን ማየት ነዋ፡፡
- ስማ እንዲህ ቀላል አይደለም፡፡
- እንዴት?
- ምንም አታመጣም፡፡
- ካላመጣሁማ በቃ እለቃለሁ፡፡
- አንዴ ከገባህማ መልቀቅም በቀላሉ አይቻልም፡፡
- በቃኝ አልኩኝ አልሠራማ፡፡
- ቀላል አይደለም አልኩህ እኮ፡፡
- ካልሆነ ኮርፖሬሽኑ ይፍረስ?
- እንዲያውም ይኼ ኮርፖሬሽን ፈርሶ ሌላ ኤጀንሲ ማቋቋም አለብኝ፡፡
- ምን የሚሉት?
- ሙስናን የሚያሳልጥ ኤጀንሲ!
[የክቡር ሚኒስትሩ የእህት ልጅ ደወለችላቸው]
- ወይኔ ጋሼ፤ ወይኔ ጋሼ፡፡
- ምን ሆነሻል?
- ወሰዱት እኮ?
- ማንን ነው የወሰዱት?
- ልጄን ወሰዱት ጋሼ፡፡
- ማን ነው የወሰደው?
- ወሰዱት ጋሼ፣ ወሰዱት፡፡
- በስኮላርሽፕ ነው የወሰዱት?
- ወሰዱት ልጄን ወሰዱት፡፡
- በፌሎሺፕ ነው የወሰዱት?
- ኧረ ፌዴራሎች ነው የወሰዱት፡፡
- ፀረ ሰላም ነው እንዴ ልጅሽ?
- ኧረ ሰላማዊ ነው፡፡
- ታዲያ እንዴት ወሰዱት?
- ወሬ ሊያይ ወጥቶ ነው የወሰዱት፡፡
- ሥራ እንጂ ወሬ ምን ያደርጋል?
- ሥራ የለውማ ጋሼ፡፡
- ለምን የለውም?
- ምን ወጣቱ ሁሉ ተመርቆ ቁጭ ብሏል አይደል እንዴ?
- ታዲያ የአንቺ ልጅ እንዴት ሥራ ያጣል?
- ሥራ የለማ፡፡
- እኔ ሥራ እሰጠዋለኋ፡፡
- ለማንኛውም አስረውታል፡፡
- ምን አድርጐ?
- ከሌሎቹ ጋር ነው ቀላቅለው የወሰዱት፡፡
[ክቡር ሚኒስትሩ ፖሊስ ጋ ደወሉ]
- ማን ልበል?
- ማን ልበል እንዴት ትለኛለህ?
- ማን ልበል ጌታዬ?
- ክቡር ሚኒስትር ነኝ፡፡
- እንዴ ክቡር ሚኒስትር ምን ልርዳዎት?
- ምን እየሠራችሁ ነው?
- ሥራችንን ነዋ፡፡
- ሰው ዝም ብላችሁ ማፈስ ጀመራችሁ?
- የበጠበጡትን ነው ያሰርነው፡፡
- ሰላማዊ የእኔ ሰዎች ታስረዋል፡፡
- ሰላማዊ ከሆኑ ብጥብጡ ውስጥ ምን ያደርጋሉ?
- ሰላማዊውንና ፀረ ሰላሙን ማጣራት አለባችሁ፡፡
- እሱን ማጣራት ከባድ ሆኗል፡፡
- እንዴት?
- በመንግሥት ውስጥ ራሱ ሰላማዊውን ከፀረ ሰላሙ መለየት ከባድ ሆኗል፡፡
- አሁን በአስቸኳይ ልቀቁት፡፡
- ማንን?
- የእኔን ሰው፡፡
- እሱማ አይቻልም፡፡
- ለምን?
- ማጣራት አለብን!
[ክቡር ሚኒስትሩ ግራ ተጋብተው ሳሉ፣ ፖሊሱ መልሶ ተንቀሳቃሽ ስልካቸው ላይ ደወለ]
- ሄሎ ክቡር ሚኒስትር፡፡
- ማን ልበል?
- አሁን ተደዋውለን ነበር፡፡
- እኮ ማን ልበል?
- ፖሊሱ ነኝ፡፡
- ይኼ እኮ የግል ስልኬ ነው፡፡
- ቢሆንስ ታዲያ?
- እንዴት እዚህ ላይ ትደውላለህ?
- ሕዝብን ለማገልገል የተሾሙ መሰለኝ፡፡
- በጣም ተናንቀናል፡፡
- ቆየን እኮ፡፡
- ምን ካልን?
- ከተናናቅን!