የሃይለማርይም እንባ እና የኔ አጭር ዘገባ ( ሄኖክ የሺጥላ )
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
አቶ <ክቡር ጠቅላይ ሚንስቴር> ሃይለማርያም ደሳለኝ ፣ ጠቅላይ ሚንስቴር ፣ ጠቅላይ ሚንስቴር የሚሸት ነገር ተናገሩ ፣ ልል አልኩና ፣ እስኪ ከመቸኮል ፣ ምን አዲስ ነገር ተናገሩ ? ህዝቡ የማያውቀውን ፣ ወይም ህዝቡ ያጣውን እና ከመሪው መስማት የሚሻውን ምን አዲስ ነገር ተናገሩ ?
እንገምግማቸው ( ማለቴ ከተፈቀደለን ) ፣ እንደ እሳቸው ንግግር ፍቃድ የተሰጠን ይመስላል ።
ንግግራቸው በከፊል ይህንን ይመስል ነበር ( የመጀመሪያው ክፍል ብየዋለሁ )
አሁን ጥናቱ ከሰጠን ኢንፑት አንዱ እና ትልቁ የዚህን ችግር ዴብዝ በአግባቡ አመራሩ እንዲያይ ፣ በውስጡ ድንጋጤ እንዲፈጠር ፣ ለማድረግ የሚያስችል ፣ ከመፈከር የዘለለ ” ከዚህ በፊት መልካም አስተዳደር ችግር አለ ፣ እዛ ጋ ችግር አለ ፣ መሬት ላይ ችግር አለ ፣ ገቢዎች ላይ ችግር አለ ፣ እእእ ፣ ጨረታ ግዢ ላይ ችግር አለ ፣ ከሚባለው አልፈን ፣ ሪሊ ምንድነው ያለው የሚል ፣ ሳምፕል ሊሆን ይችላል <ኢት ዳዝንት ማተር> ፣ ሁሉን አካባቢ አጥነትህ አይደልም ችግር የምታውቀው ፣ ሳይንሳዊ የሚያስብለውም ይሄ ነው ፣ ሳይንሳዊ የሚያስብለውም ጥናቱ ሪፕረዘንታትቪ መሆኑን መራዳት ላይ ብቻ ነው ። በዚህ ደረጃ አጥኒዎቹ እእእ ሙያተኞች እና ሁለቱም መስሪያ ቤቶች ያመጡት ውጤት ከልብ ልንቀበለው የሚገባ ውጤት ነው ነው ። የመጀመሪያው ጉዳይ እኔ እዛ ላይ ነው ያለው ነው ። አሁንም ሊፕ ሰርቪስ ካ ለ ( ሽርደዳ ካለ ) ፣ ይሄ ነገር ፣ ሄዶ ሄዶ መደናቀፉ አይቀርም ። ስለዚህ ከልብ ተቀብለን ( ዋልታ መልዕክቱን ይቆርጠዋል ) ።
ማናቸውም ልማታዊ መንግስት ፣ < ፕሮግሬሲቭ የሆነ > ፣ አገር ፓርቲ የሚመሩ አካላት ፣ የመጀመሪያው ጉዳይ በውስጣቸው የሚፈጠረው ጉልበት ነው ፣ ይሄ በውስጥ የሚፈጠርው ጉልበት ባግባቡ ካልተፈጠረ በስተቀር ፣ ሄዶ ሄዶ < ተከላውሶ > መቆሙ አይቀርም ፣ ይሄ ነገር በጣም < ትሬትኒንግ > ነው ። በጣም < ሲርየስም > ነው ፣ ከውስጣችንም ልንቀበለውም የምንገደድበት ጉዳይ ነው ፣ የሚል ነገር መጀመሪያ መሰመር አለበት ። ለኔ በያንዳንዱ አካባቢ — በሁለት ከፍለን ማየት አለብን ይሄን ጉዳይ ። ይሄ ጥናት ያመጣቸው ፋክቶችን መሰረት አድርገን ጠራርገን የምንፈታቸው ን መፍታት አለብን ። አንደኛው መጀመሪያው ። ፈጣኑ ደሞ ፣ ህብረተሰቡ ውስጥ በፐርሴፕሽንም በሪያሊትም የመጡ ጉዳዮችንን ካላቃለልን እና < እውነትም ተስፋ አለው!> ፣ ወደሚል ደረጃ በስፋት ገብተን አብረን እንፈታል ወደሚል አቋም ካልወሰድነው ሕዝቡን < ፎር ሃው ሎንግ ሻል አይ ቶክ> ስለ መልካም አስተዳደር እንፈታለን የሚል ነገር እስከመቼ ነው ማውራት የምችለው ፣ ሁላችንስ እስከመቼ ነው ምናወራው ? ሶ በሁለት ከፍለን ነው ማየት ያለብን ፣ የመጀመሪያው ሕዝቡን ተስፋ ሊያስጭር የሚችል ኢሚዴት ፣ እንደተባለው ካምፔን ( ንቅናቄ ) ፈጥረን ፣ ህዝቡ ተስፋ ፈጥሬአለሁ ብሎ ፣ ከዚህ በሗላ ከናንተ ጋራ እሟሟታለሁ የሚልበት ደረጃ ላይ እንዲደርስ የመጀመሪያ ሥራ መስራት አለብን ።
ሁለተኛ እንደው ሪ- ኢንቨንት ማድረግ የለብንም ፣ መሬት ላይ እኮ የመሬት ሪ-ፎርም ፣ ምርጥ የመሬት ሪ-ፎርም አዘጋጅተን በ አይ-ቲ የተደገፈ ፣ እያንዳድኑ ፓርስል የሚታወቅበት ፣ ምን የሚሆንበት ፣ ምን የሚሆንበት ፣ ብለን ካርታ ስናነሳ ፣ ምን ስንል ፣ ምን ስንል ፣ ከርመን ፣ መዓት ዓመት በሱ ላይ ስንከላወስ ከርመን ፣ ውጤት ሳናመጣ ቀርተናል ብለን ገምግመናል ፣ ሌላ አሁን ደሞ ካርታ እየሰራን ፣ ሌላ አምስት ዓመት የምንቆይበት ጉዳይ ሊኖር አይገባም ። አለን ሪፎርም ፕሮግራሞች እኮ አሉን ፣ ይሄ መንግስት፣ ድርጅታችን ፣ የ ሪ-ፎርም ፕሮግራሞች ብሎ የያዟቸው እኮ ፣ ስቴት ኦፍ ዘ አርት ናቸው ፣ አለማቀፍ ስታንዳርድ የጠበቁ ሪፎርሞች ናቸው እኮ ፣ ሌላ ሪ-ኢንቨንት ለማድረግ አይደለም መሄድ ያለብን ፣ የያዝነውን ፣ የያዝናቸውን —ማንኛውም ሪ-ፎርም እኮ ሁል ጊዜ ከአንድ ደረጃ ወደ አንድ ደረጃ ያድጋል ፣ የመጀመሪያ የያዝነውን ሪ- ፎርም ግን መጀመሪያ ተግባራዊ ማድረግ አለብን ፣ መቼ አደረግን መሬት ላይ ፣ አዋጅ ፣ የሊዝ አዋጅ ወጥቶ ፣ ስለቀረቀርነው ሪፎርም አደረግን ማለታችን ነው ? አይደለም ! ኢት ኢዝ አ ቱል ሪፎርሙን ማስፈጸም የሚያስ— የሚያስችል አዋጅና እና ደንብ ነው እንጂ የወጣው ሪፎሩሙ በሌለበት አይሰራም ። ስለማይሰራም ነው ፣ ያንን ስንዘጋ ጨረታ አምጥቶ ጨረታዋን ማጫወት ጀምሯል ፣ ካርታ እዛ ላይ ይጫወታል ። ጨረታ ሲባል ማነው ጨረታ የ-ከኪራይ ሰብሳቢነት ነጻ ነው ያለው ? ሁሉ ጨረታ አይደለ እንዴ አገር እያበላሸ ያለው ? ስለዚህ ጨረታ በራሱ ኢሙዩን አይደለም ፣ አሰራሩ ሙሉ ሆኖ ተግባራዊ ሲሆን ነው ጨረታውም ሊያዝ የሚችለው ፣ ሰውም ሊያዝ የሚችለው ፣ ሁሉ ነገር ሊሆን የሚችለው ። ስለዚህ በሁለት ከፍለን እንሂድ የተባለው ትክክል ነው ፣ በዚህ እንሄዳለን ፣ የጀመርነውም ይሄን ነው ። የመጀመርያው ጉዳይ ፣ አሁን አጥኚዎች ያመጡጧቸውን በሳምፕል ደረጃ የተቀመጡትን ነገሮች ውደ ማኗል እንቀይርና ፣ ይሄ ማኗል ተግባራዊ የሚሆንበት በማኗሉ ሰልጥኖ ሰው ወደ ንቅናቄ የሚገባበትን ሁኔታ እንፍጠር ፣ የመጀመሪያው ጉዳይ ። ከስራ ስፈጻሚ ጀምረን እንተማመን ፣
እንግዲህ በዚህ ንግግር ውስጥ የተጠቀሱ አብይ ወይም አንኳር ነጥብ ምንድን ነው ? እኔ እንደሚመስለኝ መንግስት ሕዝብ ፊቱን እንዳዞረበት ከተረዳ ቢያንስ አስር ዓመት ሆኖታል ( በይበልጥ የምርጫ 97 የምርጫ ውጤት በቂ ማሳያ ነው ) ፣ ያም ሆኖ ይዝቡን በተለያዩ ማባበያዎች < ኮንዶሚኒየም ፣ ጥቃቅን እና አነስተኛ ፣ ገለመኔ ፣ ገለመኔ > በማለት ከጋን ሙሉ ወተት ውስጥ በሽራፊ ገል እየጠለቀ ያቀመሰው እንደማይቀበቃ ብቻ ሳይሆን ህዝቡ የምር ወያኔ የሚባለው ነገር እንደበቃው በደንብ ተረድተዋል ። ይህ ባይሆን ኖሮ ምርጫውን 100% ባሸንፉ ( ወይም አሸነፍን ብለው ባወጁ ማግስት በሚባልበት ደረጃ ላይ ) ፣ ይሄን ሞክረን ፣ ይሄን ሞክረን ፣ ይሄን አድርገን ፣ አመታታት ለፍተን — አረ እንደውም የሳቸውን አባባል ልድገመው
< ” መሬት ላይ እኮ የመሬት ሪ-ፎርም ፣ ምርጥ የመሬት ሪ-ፎርም አዘጋጅተን በ አይ-ቲ የተደገፈ ፣ እያንዳድኑ ፓርስል የሚታወቅበት ፣ ምን የሚሆንበት ፣ ምን የሚሆንበት ፣ ብለን ካርታ ስናነሳ ፣ ምን ስንል ፣ ምን ስንል ፣ ከርመን ፣ መዓት ዓመት በሱ ላይ ስንከላወስ ከርመን ፣ ውጤት ሳናመጣ ቀርተናል ብለን ገምግመናል”> ይላሉ ። አዎ መዓት ዓመት፣ መዓት ግዜ ፣ በመዓት ነገር ተንከላውሳችሁ ቀርታችሗል ። እርሶ ራሶ እንዳሉት የኢትዮጵያ ሕዝብ ብቻ ሳይሆን < ፣ ኮሪያ ፣ ቻይና ፣ ብራዚል እና ወዘተ ጭምር እናንተን ሰልችተዋል > ። ለምን ?ምክንያቱም <ተንከላውሳችሁ > ስለቀራችሁ ፣ ለምን ? ህብረተሰቡ ውስጥ በፐርሴብሽንም ይሁን በሪያሊቲ ደረጃ ያሉትን ችግሮች መፍታት አይደልም መራድት ስላቃታችሁ ። ይቅሉንም እርሶ እንደሚሉት ስርዓቱ የግልጽነት ( ትራንስፓረንሲ ) ችግር ስላለበት አይመስለኝም አሁን ያለበት የችግር አረንቋ ወይም ቋት ውስጥ የወደቀው ። በነገራችን ላይ ድርጅቶ < በ ትራንስፓረንሲ አይታማም !> እንደውም በዓለም ላይ በግልጽነት የእርሶን ድርጅት የመሰለም ያለ አይመስለኝም ። ለምሳሌ ምርጫውን በ 100 ፐርሰንት አሸንፌአለሁ ብሎ ለማለት ፣ ይህንንም ለዓለም ለመንገር አንዳች አለማመንታት እኮ የወጣለት ግልጽነት ነው ። መቶ ፐርሰንት ነው ያሸነፍነው ፣ መቶ ፐርሰንት ነው ! ግልጽ መንግስት !
የሆነ ቦታ ላይ ደሞ እንዲህ ይላሉ
< ለኔ ሁለተኛ ከባድ ፈተና የሚሆነው እዚህ እናወራለን እንጂ ፣ ከወጣን በሗላ የተለያየ የራሳችንን ኔትዎርክ እንዳይነካብን እንከላከላለን ፣ አንዱ ትልቁ በሽታ ! ስለዚህ መቆረጥ ካለበት መቁረጥ ነው > ። እንዴ ጋሽ ኃይሌ ምነው ረሱት እንዴ ይሄ ኔት ወርክ እኮ ነው 100 ፐርሰንት የመረጦት እና ያስመረጦት ። ኔት – ወርኩ እንዲቆራረጥ ከፈለጉ እርሶ አይድከሙ ፣ ለኢትዮጵያ ቴሌኮሙዩኒኬሽን ኔትወርኩን ኮንትራት ይስጡት ፣ እሱ አሳምሮ ይቆራርጥሎታል!
ይቀጥላሉ < በብሄር የምንከላከል ከሆነ አይሰራም ፣ በአብሮ አደግነት የምንከላከል ከሆነ አይሰራም ፣ በተለያየ ጥቅም ተሳስረን የምንከላከል ከሆነ አይሰራም > ።
እንዴ ጌታው ሰራ እኮ ፣ 25 ዓመት ሰራ ! ዛሬ ምን ነክቶት ነው የማይሰራው ? ሲሰራ የኖረበትን መንገድ አይሰራም ብሎ መተቸት ምን ማለት ነው? እንደ እርሶ አባባል እኮ ፣ 95 ከ 100 የሚሆነው የመከላከያ ጀነራል ካንድ ብሔር የወጣ/ የመጣ ነው፣ ስለዚህ እንደ ሀገር መከላከያ አይሰራም እያሉ ነው ። በስልጣን ላይ ያሉት ( የህወሓት አስኳል ) ከአንድ አካባቢ የመጡ ናቸው ( ምናላባት ያንድ ሰፈር ልጆች ናቸው) ፣ ስለዚህ እነሱም አይሰሩም ! እያሉ ነው ። እነ ጉና ፣ ዔፈርት ፣ ሞሶቦ ፣ መስፍን እንደስትሪያል ፣ እና ወዘተ ፣ የህወሃት እና ህወሃትን የሚደግፈው “የትግራይ ህዝብን” በጥቅም ያስተሳሰሯቸው የንዋይ ምሰሶዎች ስለሆኑ አይሰሩም! እያሉን እኮ ነው ያሉት ? ያሉት ይገባዎታል ወይስ ይገ-ባዎታል ?
ይቀጥላሉ
< አድርግ ስለተባለ ሰው የሚያደርግበት የሚመስል ፣ የህዝብ ውይይት ፣ የህዝብ ተሳትፎ ነው ያለው ? > እኔ ልሙት ? ከመለስ ቀብር ፣ ከአባይ ቦንድ ግዢ እና ከምርጫው ሌላ ፣ ሕዝቡን ምን አድርግ ብላችሁት ነበር ? ለነገሩ ሶስቱም በጣም የሚሰለቹ ነገሮች ነበሩ ፣ ሁለቱ ላይመለሱ ሄደዋል ፣ ሶስተኛው ዛሬም አለሁ እያለ ይፎክራል ። እሱንም አንድ ቀን አልተሳካልንም ብላችሁ ስትሉ መስማታችን አይቀርም ፣ ከዚያ በፊት < ካልፈረሳችሁ !> ።
አሁንም ቀጠሉ
< ኢህአዲግ ድል ካደረገበት ነገር አንዱ ሰው ፕሮሃቢት ድ ሳይሆን የሚሰማውን ነገር አፍረጥርጦ መናገሩ ነው! > እንዴታ ፣ እኔ ተመስገን ደሳለኝ አፍረጥርጠው ተናግረውማ አይደል በኢህአዲግ የተሸለሙት ? እነ እስክንድ ነጋ ፣ እነ አንዱዓለም አራጌ ፣ እነ ውብሸት ፣ እነ ወዘተ የሚሰማቸውን ፣ ያለ አንዳች ገደብ በመናገራቸው አይደል እንዴ ዛሬ በነጻነት በሕዝብ መሃል ፣ ከህዝብ ጋ እየኖሩ ያሉት ? ልክ ኖት ኢህአዲግ ድል ካደረገበት ነገሮች ውስጥ አንዱ እርሶ እንዳሉት ሰው ያለ ገደብ የሚሰማውን አፍረጥርጦ የመናገር መብት እንዲኖረው ማድረጉ ነው ።
ለማንኛውም ይሄም አፈ ጮሌነት አይሰራም ! ይልቅ እኔን የገባኝ ፣ በካርታ ፣ በጨረታ እና ወዘተ ስም በቅርቡ የሚራገፉ ባለስልጣናት አሉ ማለት ነው ። ስራቸው ያውጣቸው !
ማጠቃለያ
ይሄ የርሶ ንግግር አይሰራም ፣ ምክንያቱም ሕዝብ ያልመረጠው መንግስት ስለ ሕዝብ ነጻነት ማውራት አይችልምና ። ይህ የርሶ ደርሶ ቋጥኝ መፋቅ ጥፍሮትን ያስጨርሶ ይሆናል እንጂ ፣ ተራራውን ( የህዝቡን ልቦና ) ፈቀቅ አያደርገውም ፣ ምክንያቱም አይሰራማ ! በውስጣችሁ ስለሚፈጠረው አዲስ ጉልበት ፣ ስለ አዲስ ሕዝብ መነቃቃት እና እናንተን ስለመከተል ብዙ ልትሸርቡ ትችላላችሁ ፣ ልታሴሩም ትጥራላችሁ ግን እሱም አይሰራም ። ውሃ ማቆር አልሰራም ፣ ውጤት ተኮር አልሰራም ፣ አንስተኛ እና ጥቃቅን አልሰራም ፣ ገጠርን መሰረት ያደረገው የልማት እቅድ አልሰራም ፣ ግብርና መር የልማት ፖሊሲ አልሰራም ፣ ራስ አገዝ የገበሬዎች ማህበር አልሰራም ፣ አዲሱ < የተስፋ ካምፔን> ( ” መነቃነቅም “) አይሰራም ። ለምን ቢሉ እርሶ እንዳሉት እናንተ ተንከላውሳችሁ ቀርታችሗልና !
ቸር እንሰንብት !
ሄኖክ የሺጥላ