አደርባይ ታማኝ ተቃዋሚዎች ከሃዲዎችን ማንቆለጳጰሳቸው የተለመደ የፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ነው::(ምንሊክ ሳልሳዊ)
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
በሃገር ቤት የሚንቀሳቀስ ፓርቲዎች ናቸው የተባሉ አራቱ በሕዝብ ዘንድ የተጠሉ እና የተተፉ ታማኝ ተቃዋሚዎች የወያኔ የፕሮፓጋንዳ ማድነቂያ ሆነዋል::ይህ ሰሞ ከአዲስ አመት ይልቅ በአዲሱ የሞላ ፕሮፓጋንዳ እየጎዳደለ የሚገኘው ወያኔ ደልሎ ይሁን ገዝቶ አፍኖ ይሁን መንገድ አሳስቶ ያመጣውን ሞላን እንደ ትልቅ ድል ቆጥሮ አደርባይ ታማኝ ተቃዋሚዎች ለአላማ ጽናት የሌለውን ሞላን እና ተከታዮቹን እንዲያንቆለጳጵሱ በማድረግ እኩይ የፕሮፓጋንዳ ተግባሩን ተያይዞታል::ታማኝ ተቃዋሚዎች በዚህ በሰለጠነ ዘመን ለሆዳቸው ከመንከባለላቸው በተጨማሪ ለመረጃ እጅግ የራቁ መሆናቸውን ከወያኔ ጋር የሚጋፈፉት አንሶላ ፊትለፊት ታይቶባቸዋል::
አደርባይ ታማኝ ተቃዋሚዎች የትሕዴን ታጋዮች ወደ ሃገር ቤት በሞላ አስገዶም እየተመሩ ገብተዋል የሚለውን ጡዘት ወያኔ ጠቅልሎ ባጎረሳቸው ፕሮፓጋንዳ ተጨፍነው ሙሉ በሙሉ መቀበላቸው ምን ያህል የድፍን ፖለቲካ ባዶነት እንደሚታይባቸው ያሳብቅባቸዋል:: ከበፊት ጀምሮ እንደምናውቀው በፍላጎት እና በአፈና ጦሩን የሞላው ትሕዴን ወደ ሃያ ሺህ ጦር እንዳለው የምንሰማው የምናውቀው የተነገረ ነው ታዲያ ሞላ አስገዶም 600 ወታደሮቹን አስከትሎ መጣ ማለት ትሕዴን ካለው ሰራዊት ሶስት ፐርሰንት (3%) የሆነው ከዳ/ተሰናበተ/ተላልፎ ተሰጠ/መንገድ ተሳሳተ/ተደለለ ወዘተ…. ማለት ስለሆነ ይህ ደግሞ አደርባይ ታማኝ ተቃዋሚዎች እንዳሉት ትሕዴን ጠቅልሎ አልገባም::ታማኝ ተቃዋሚዎች ፖለቲካ ቢያውቁ ኖሮ ግን ጠንከር ያለ ንግግር ባስቀመጡ ነበር::
ለትጥቅ ትግል በረሃ ገብተናል ያሉ ሃይሎች የራሳቸውን አሳማኝ ነው የሚሉትን ምክንያት ማስቀመጣቸው ይታወቃል::የሚደግፋቸው ይደግፋል የማይደግፍ ደሞ የራሱን መስመር ይዞ ይሄዳል::ከሞላ አስገዶም ያልተለየ ስራ በአንድነት ፓርቲ ላይ የሰራው ከሃዲው ትእግስቱ አወሉ በየትኛው ሞራሉ ነው ከበረሃ ወደ ከተማ ስለሚገቡ ጭፍን ዘረኞች ሊመሰክር የሚችለው? በሕዝብ ልጆች አንድነት ተገንብቶ ከፍተኛ መስዋትነት ተከፍሎበት በሕዝብ ድምጽ የተመረጠውን ቅንጅት ለውድቀት የዳረገ የልደቱ አያሌው ኢዴፓ በየትኛው ሕዝባዊ አመኔታው ስለ ሞላ አስገዶም ይናገራል? በአንድ ጉዳይ ላይ መግለጫ ሲሰጥ መረጃዎች ተመዝነው እንደሆነ እሙን ነው ፖለቲካ ጥንቃቄ ይፈልጋል በድመነብስ እና በእከክልኝ ልከክልህ በጉርሻ ድለላ ተናግረው የሚወጡት አይደለም ነገን ከተጠያቂነት አያስተርፍም::የመድረክ ፓርቲ አመራሮች ከጅምሩ ጀምሮ በፖለቲካው አለም ያሉ ቢሆንም ብስለታቸው በፍርሃት እና በጥቅም የተያዘ እስኪመስል አሊያም አረናን ላለማስቀየም ይመስል ለሞላ አስገዶም እና ለወያኔ ሲያሽካልሉ ይታያሉ::መድረክ የትጥቅ ትግል በረሃ የገቡ ኢትዮጵያውያን ለምን እንደገቡ የት እንደነበሩ ጠንቅቆ የሚያውቅ ፓርቲ ሆኖ ሳለ ጭልጥ ባለ አደርባይነት ውስጥ ተነክሮ ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ውሏል::ሌላኛው ኢራፓ የምባል ነኝ ያለ ፓርቲም ከገዢው ፓርቲ አጋር ተለጣፊዎች አንዱ አብሮ ሲያንቆለጳጵስ ተስተውሏል:: ፓርቲዎቹ ምን ያህል ሞራላቸው እንደወረደ እና ለገዢያቸው ወያኔ ምን ያህል ታዛዥ እንደሆኑና ለሕዝብ ሳይሆን ለራሳቸው የኑሮ ለውጥ እንደሚታገሉ ይመሰክርባቸዋል::
ወያኔ ከራሱ እና ተለጣፊ ፓርቲዎቹ አልፎ በተፎካካሪ ፓርቲ ስም የሚደግፋቸው አጋር ታማኝ ተቃዋሚዎችንም ለሞላ አስገዶም የፕሮፓጋንዳ ፍጆታ መጠቀሙ ስርኣቱ ውዥንብር ውስጥ መግባቱን ያሳያል::የወያኔ ካድሬዎች ራሳቸው ፕሮፓጋንዳውን እየተቹ ባሉበት በዚህ ወቅት ላይ በተፎካካሪ ስል አጋር ተቃዋሚ ፓርቲዎች ሰጡ የተባለው መግለጫ ፖለቲካን ውስጥ ምን ያህል አደርባይ ሆዳም ሰዎች እያቦኩት እና ለለውጥ የሚደረገውን ትግል እየተጋፉት እንደሚገኙ ምስክር ነው::አስተዋይነት የጎደላቸው እንደ ትግስቱ አወል እና ኢዴፓ የመሳሰሉ ፓርቲዎች ለስላም እና ለዲሞክራሲ በሚደረጉ ትግሎች ውስጥ በሞት ያለፉ እና በእስር ያሉ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች ላይ ዛሬም እየተዘባበቱ ነው::የለውጥ ሃይሎች ሕዝብን አስከትለው በሚያደርጉት ትግል በሚገኘው ድል ወያኔ ሲደመሰስ ከታሪ እና ከሕግ ተጠያቂነት እንደማያልፉ ላስገነዝባቸው እወዳለሁ::