አዎ ! የኤርትራው ፎቶ ይናገራል


መረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ


ከጋዜጠኛ ደምስ በለጠ

ከቀናት በፊት በአንድ ቃለ-መጠይቅ ላይ የአንድ ተዋጊ ድርጅት መሪ እዚህ አሜሪካ ተቀምጦ እንዴት ነው በሪሞት ኮንትሮል ጦር ሊመራ የሚችለው ብዬ ተችቼ ነበር ። ዛሬ ከወሬ አልፎ በአመነበት የትግል ስልት ወደተግባር ተሸጋግሮ ብርሃኑ ነጋ ወደ አስመራ ማቅናቱን አድንቂያለሁ ።

ከብርሃኑ ነጋ ጉዞ ሁለት የሻእቢያ ትያትር ሴናሪዎ እጠብቃለሁ ። አንደኛው ብርሃኑ ነጋን ሻእቢያ ወታደራዊ ዩኒፎርም ያለብሰዋል ። ከዚያም ሰራዊቱን ወደ ሃሬና ማሰልጠኛ ጣቢያ ወርዶ እንዲጎበኙ ያደርገዋል ። በዚያም ሻእቢያ ትልቅ የፕሮፓጋንዳ ስራ ይሰራበታል ።

ቀደም ሲል በአንድ ፅሁፌ ላይ እንደገለፅኩት የአርበኞች ግንባርና የግንቦት 7 ውህደት ተዋጊዎች ቁጥር ዛሬ ግፋ ቢል ከ150 አይበልጥም ። ይህም ቁጥር ሰራዊት አለኝ ብሎ አድምቆ ለመናገር ሙሉ መተማመኛ አይሆንም። ወይም የምንሰማውን አይነት የጦርነት ፕሮፓጋንዳ ግዳይ ሊያስጥል የሚችል ሃይልም አይደለም። ያም ሆኖ ታዲያ ፤ ለፕሮፓጋንዳው ስራና ሰልፍ ድምቀት ሲባል የድምህት ወታደሮች የሰልፉ ተሳታፊ እንዲሆኑ ይደረጋል ። ይህን አይነት የሻእቢያ ፊንታ ከጀመሪያው ጉዞዬ ጀምሮ በተደጋጋሚ አይቻለሁና።

ሁለተኛው ሴናሪዎ ደግሞ ከብርሃኑ ነጋ መምጣት ጋር የአርበኞች ግንቦት 7 ውህደት ከሌሎች ድርጅቶች በተለይም ከድምህት ጋር አሊያንስ ፈጠረ ተብሎ አዋጅ ይነገራል ፤ መግለጫዎች ይወጣሉ ፤ ከበሮ ይደለቃል። ለዚህ ትያትር ማዳመቂያ በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት በምርኮ ከተያዙ የደቡብ ተወላጆች በሆኑ ሰዎች ሻእቢያ ያቋቋማቸው ሁለት ወይም ግፋ ቢል ሶስት አባላት ያላቸው የደቡብና የቤንሻንጉል ድርጅቶችም ተሳታፊ ናቸው ተብለው የአሊያንሱ ማጫፈሪያ ይሆናሉ ። እነዚህን ሁለት ሴናሪዎዎች አብረን እንጠብቅ ።

አምስተኛ ወሩን ያስቆጠረው የአዲሱ ውህደት መግለጫ ደሞ ትንሽ አደናግሮኛል ። እንዲህ ይላል ። ያሰመርኩበትን ደግሞ አጢኑልኝ ።

“አርበኞች ግንቦት 7 አመራሩን ሁኔታዎች በፈቀዱ መጠን እና ትግሉ በሚጠይቀው ቦታ እንዲገኙ የሚያደርግ መሆኑ ሲገልጽ ቆይቷል። አሁን ትግሉ በደረሰበት ደረጃ የአመራሩ በትግሉ ሜዳ ውስጥ መገኘት አስፈላጊ መሆኑ ታምኖበት በዚህም መሠረት የንቅናቄው ሊቀመንበር ዶ/ር ብርሃኑ ነጋ ወደ ትግል ሜዳ ወርዷል። ሊቀመንበሩን ጨምሮ አመራሩን ወደ ትግሉ ሜዳ አንቀሳቅሷል። …በአሁኑ ሰዓት የንቅናቄው አመራር በተሟላ ሁኔታ በትግሉ ሜዳ ውስጥ እንዲገኝ ማድረግ ተችሏል።” ይላል ። የሄዱት ሁለት ሰዎች ናቸው ። አመራሩን ወደ ትግሉ ሜዳ አንቀሳቅሷል ማለት ምን ማለት ይሆን ?

የአመራሩን ወደአስመራ መውረድ በተመለከተ የሚቀርቡ ዜናዎች ከፕሮፓጋንዳና ቅስቀሳ ውጪ ወጥነትና ግልፅነት ሊኖራቸው ይገባል እላለሁ ። አሁን ወደ ተነሳሁበት ነጥብ ላምራ።
Berhanu Nega visit to Eritrea 12012545
ይህን ፎቶ ከቀኝ ወደግራ ይመልከቱ። የኢትዮጵያን ባንዲራ በእጁ የያዘው ሰው የለበሰው ወታደራዊ ዩኒፎርም፤ የሻእቢያ ወታደራዊ ሰርቪስ ዩኒፎርም ነው ከሱ ቀጥለው ሶስቱ የቆሙትና አንዱ የተቀመጠው የለበሱት ቅጠልያ ሬንጀር ዩኒፎርም የአርበኞች ግንባር ዩኒፎርም ነው። ከዛ ቀጥለው በካኪ ዩኒፎርም ያሉት ስድስቱ ደግሞ የድምህትን ዩኖፎርም ነው የለበሱት።

በአርበኞች ግንቦት ሰባት መሪዎች አቀባበል ላይ የሻእቢያው ወታደር ምን አገባው ? በሻእቢያ አሰራር እንደተለመደው በፎቶ የሚታዩትን ሰዎች እንቅስቃሴና አንደበት ለመቆጣጠር የተመደበ ነው ። የሚቀጥለውን ፎቶ ደግሞ ተመልከቱ ።

Berhanu Nega visit to Eritrea 120125495
ከብርሃኑ ነጋና ከነአምን ዘለቀ ኋላ በሰማያዊ ቲ ሸርትና በጥቁር ጃኬት መግቢያው በር ላይ ያለው ኑርጀባ አሰፋ የአርበኞች ግንባር ሰው ነው ። ቅጠልያ ኮፍያ ና አመድማ ዥጉርጉር ልብስ የለበሰውና ብርሃኑ ነጋንና ነአምን ዘለቀን ከድምህትና ከአርበኛች አባላት ጋር እያስተዋወቀ ያለው ደግሞ የሻእቢያ መደበኛ ሰራዊት የበታች ሹማምንት ዩኒፎርም ነው የለበሰው ። ይህ የሻእቢያ የበታች ሹም በምን ስልጣን ነው “ለአርበኞች ግንቦት ሰባት ለአንድነትና ዲሞክራሲ ንቅናቄ” መሪ ለብርሃኑ ነጋ ፤ የራሱን ድርጅት ሰራዊት አባላት የሚያስተዋውቀው ?

“የመኻል አገር ሰው ካከባበርከውና የአቀባበል ስነስርአት ካደረክለት ብሎም ካሞካሸኸው ከፍከፍ ካደረከው ከዚያ በላይ ጠልቆ የሚፈልገውና የሚጠይቀው የለም” ሲሉ ሻእቢያዎች ይመጻደቃሉ ። ከኢሕአግና ከግንቦት 7 ውህደት በኋላ ብርሃኑ ነጋ የድርጅቱ መሪ ሲባል የአርበኞች መሪ የነበረው መአዛው ጌጡ የሰራዊቱ አዛዥ ተብሎ ተመድቦ እንደነበር ሰምተናል ። ወታደሮቹ የሱ ታዛዦች ከሆኑ በእዙ ስር ያሉትን ማስተዋወቅ የመአዛው ስራ መሆን አልነበረበትም?

በነዚህ የፎቶ አቀባበል ስነስራት ላይ መአዛው ጌጡ የለም ። ወዴት ሄደ ? እንደጦር አዛዥነቱ በሰሜን ኢትዮጵያ በወልቃይት ፤ በጠገዴና ፤ በአርማጮሆ ፤ ግንቦት 7 የከፈተው ውጊያ ላይ እያዋጋ ነው እንደማትሉኝ ተስፋ አደርጋለሁ ። መአዛው ጌጡ በውጊያ ላይ ከተሳተፈ ወደ አስራ ሁለት አመታት አልፎታል ።

ምክንያቱም እንዲህ ነው ። የዛሬ አስራ ሁለት አመታት ገደማ መአዛው በኤንትሬ መኪና ተሳፍሮ ሲጓዝ መኪናው ተገልብጦ ከፍተኛ የወገብ አደጋ የደረሰበት ሰው ነው ። ከአመት በፊትም እንዲሁ ሌላ የመኪና አደጋ ደርሶበት እግሩ ተሰብሮ ያለ ሰው ነው ። ምናልባት በሃሬና ማስልጠኛ ጣቢያ ከላይ የጠቀስኩትን የሻእቢያ ሴናሪዎ ትያትር በኮለኔል ፍፁም አቀናባሪነት እያዘጋጀ ሊሆን ይችላል ።

ቀድሞ ወደ አስመራ ተጉዘው የነበሩ ሰዎችን ልምድ መመልከት ወይም መረዳት እስካልቻሉ ድረስ እነ ብርሃኑ ነጋም ተመሳሳይ ስህተት እንዲፈፅሙ ይደረጋሉ ፤ ማኖም ይነካሉ ። አንዴ ሻእቢያ ማኖ ካስነካቸው ደግሞ ሁሌ እያስጎነበሰ ቅጣት ምት ይመታባቸዋል ።

ከላይ ፎቶዎቹ ላይ እንደሚታየው የመጣው ሁሉ የነሱ መስሎአቸው መሞኘት የለባቸውም ። በተለይ በተዋጊዎቹ ስም የሚገናኟቸውን ሰዎች ማንነትና በግንባሩ ያላቸውን ስልጣን ሊያውቁና በመዋቅር ላይ የተመሰረቱ ግንኙነቶች ብቻ ማድረግ ይገባቸዋል ። ይህ የድርጅት ነጻነታቸውን ለመጠበቅ ሊያግዛቸው ይችላል ።

ከልምድ እንደተረዳሁት እንቁላሎችህን ሁሉ ባንድ ቅርጫት ውስጥ አድርገህ ለሻእቢያ ማስረከብ ከፍተኛ አደጋ አለው ።

ዛሬ ሻእብያ የተዋጊዎቹ ተወካዮች ብሎ የሚያቀርባቸውን ሰዎች ነገ በሌሎች ይተካቸዋል ። ስለዚህ ብርሃኑ ነጋም ሆነ ነአምን ዘለቀ ከጀርባቸው ምን እየተሰራ እንደሆነ ገና ሊረዱት አይችሉም ። ዩኒፎርም ለብሶ የመጣ ሁሉ የነሱ መስሎ ታይቷቸው ከሆነ ተሳስተዋል ። ከጊዜ ጋር ግን ይገነዘቡታል ብየ እገምታለሁ ። ያኔ ታዲያ ባቡሩ ሄዷል ።

በዚህ አጋጣሚ ማሳሰብ የምፈልገው ለኢትዮጵያ ነፃነት እንታገላለን የሚል ድርጅት መሪዎች ወደአስመራ ሲገቡ ፤ ከባለስልጣናቱ ጋር በሚያደርጉት ውይይት የኢትዮጵያውያንን መብት ማስቀደም ልዩ ተግባራቸውና ባህላቸው ሊያደርጉ ይገባል ። በኤርትራ እንደነኮለኔል ታደሰ ሙሉነህ አይነቱን በግፍ የታሰሩ ወገኖችን ጉዳይ አንስቶ ስለነፃነታቸው መከራከር የኢትዮጵያዊነት መብት መለኪያ እሴት ማሳያ ስለሚሆን ሊያስቡበት ይገባል እላለሁ ። ይህን የመሰሉ ጉዳዮችን ከግብ ማድረስ መሪዎች ነን በሚሉ ሰዎች ላይ የዜጎችን እምነትና ተስፋ ያለመልማል።

ከአውሮፓም ፤ ከአውስትራሊያም ፤ ከሰሜን አሜሪካም ሄደው የነበሩት ሁሉ ተስፋ ሰንቀው ሄደው በየጊዜው እንዲሁ እየተሸወዱ ነው የተመለሱት ። ይህን ሁሉ ለመረዳት ታዲያ ኮለኔል ፍፁምንና ሻእቢያዊ ተልእኮውን ከዚያም አልፎ የግል ፍላጎቱን እንዴት እንዴት በተዋጊዎቹ ላይ እንደሚያስፈፅም ጠንቅቆ መረዳት የግድ ይላል ። ሰሞነኛዎቹን ሴናሪዎዎች ደሞ አብረን እንጠብቅ ።