ጣይቱ ( ከሄኖክ የሺጥላ ) ክፍል አንድ
የመረጃ ቲቪ አባል በመሆን የሳተላይት ቲቪውን ቀጥታ ስርጭት፣ ወቅታዊ ዜናዎችን እና ትንተናዎችን፣ የመዝናኛ ፕሮግራሞችን፣ ስፖርት እና ሌሎችንም ዝግጅቶቻችንን በፍጥነት እና ጥራት ስልክዎ፣ ኮምፒዩተርዎ ወይም ቲቪዎ ላይ ማየት ይችላሉ። እዚህ ሊንክ ላይ በመጫን አባል ይሁኑ።
(ከሄኖክ የሺጥላ)
ጸሐይቱ
የድል ብርሃኒቱ
የነጻነት ቀንዲሊቱ
እምቢታሽ ያስጨነቃቸው
ድልሽ የረበሻቸው
ባንዳነት የወለዳቸው
ባንዳነት ያሳደጋቸው
ባንዳነት የሰየማቸው
ይኸው ምን ቀራቸው ?
እንደ እባብ እየተሳቡ
ጠግበውም ስለ ተራቡ
የማጀትሽ እንጀራ ሞሰብሽ ባይመልሳቸው
እልፍኝሽን አቃጠሉት ያው በለመደ እጃቸው !
ጣይቱ
አንቺ እናቲቱ
የአፍሪካ እልፍኝቱ
ጣይቱ የትናንትናዋ
የክንደ ብርቱ ማዳሪያ የጀግናዎች መጠጊያዋ
ይኸው በዘመን መተት
ዛሬም በጊዜ ንፍገት
ዛሬም በታሪክ ዝቅጠት
እልፍኝሽ ላይ የባንዳ መርዝ ፣ የቂም እሳት ወረደበት !
አንቺ የእምሩ ጉልበት
አንቺ የአበበ አረጋይ ፣ የራስ ሙልጌታ ሹመት
አንቺ የአንባላጌ ፣ የአድዋ ድል ቁመት
ዛሬ ገበየሁ የለም፣ ያ የጦሩ ባፈና
እሳትሽን እንዲውጠው ይስማ ነገሩን ጎበና ?
ለብዲሳጋ እንንገረው ፣ የ እልፍኝሽን መንደድ
ዛሬም እንደ ትናንቱ በጎራዴው ላንቺ እንዲፈረድ ።
ሃይለማርያም ማሞ ይምጣ ከመንዝ አፈሩን አራግፎ
እሳትሽን እንዲያወጣ በሳት እጁ እሳት አቅፎ ?
ጣይቱ የስምሽ በረከት ፣ የስያሜሽ አፈ ጽጌ
ምሕዋሩ ተገርስሶ ፣ ቁመቱ አመድ ሆነና ዛሬ አደረ ከግርጌ !
አንቺ የ ደርመሙሳ የሸኖ አምባ ጀግና
የዳስሽ እሳት ሰማዩን አረገው ጥቁር ደመና ።
ይኸው ቤትሽ ፈረሰ
መሰረቱ በወላፈን ቁ’ዋሚው ተደረመሰ
ጴጥሮስን ትናንትና በመንገድ ስም ፈነቀሉት
ወመዘክርን በኪሎ እየሰፈሩ ሸጡት
ደሞ ዛሬ በትሽን እንደ ደመራ ከበው ፣ እንደ ችቦ አቃጠሉት
ገና በርሃ እያሉ ነው ጣይቱ ስምሽን የጠሉት !
ለነገሩ የቤትሽ የማጀትሽ ባለቤቶች
እነሱ ሆነውማ አይደል የዘንድሮ ባለ ‘ርስቶች
ገዝተው ያስተዳደሩሽ
እንዳቀዱት እንዳለሙት ደሞ ዛሬ አቃጠሉሽ !
ምን ይሰራል ታዲያ ቤቱ ባንዳ እየቀለበ
ምን ይሰራል ያንቺ ጉዋዳ ፣ ያንቺን ቀሚስ እየሳበ
ምን ይሰራል ጣይቱ ሆቴል ፣ ባንዳ ተሰይሞበት
ምን ይሰራል ቤተ ጊዮርጊስ ፣ ፓስታ እየተሳበበት !
ምን ይሰራል የጨዋ ቤት ፣ ባለጌ እያዘዘበት
ምን ይሰራል ያንቺ ማጀት ፣ ከንፈር እየተሳመበት !
ጣይቱ
ብርሃኒቱ
አንቺ ጸሐይቱ
መቀነትሽ ተፈታ
ህዝብሽ ስሙን ረስቶ ፣ ለሆዳም ባንዳ ተራታ !
ጣይቱ
ብርሃኒቱ
አንቺ የአድዋ ጽላት ፣ የነጻነት ቤተ መቅደስ
ወጣት ነበርኩ ስትቃጠይ ፣ መጠሪያሽ በእሳት ሲፈርስ !
ወጣት ነበርኩ ጉልበት ያለኝ
ልጠቀመው ያላደለኝ !
ፈሪ ሆኘ ራሴን አጣሁ
ፈሪ ሆኘ ካገር ወጣሁ
ይኸው ዛሬም ፈሪ ሆኘ ስትቃጠይ
በሰቀቀን ራሴን ቀጣሁ !
ጣይቱ ልጆችሽ አልተወለዱም
እሳትሽን የሚያጠፉት
አሁን ያሉት የሚዘርፉሽ አፈርሽን የሚገፉት
እነሱ ናቸው ጣይቱ አመድሽን ያረቀቁት
በአደባባይ ስትቃጠይ ፣ በንዳድሽም የሳቁት !
ጣይቱ
ብርሃኒቱ
አንቺ ጸሐይቱ
መቀነትሽ ተፈታ
ህዝብሽ ስሙን ረስቶ ፣ ለሆዳም ባንዳ ተራታ !