ኢትዮጵያ ውስጥ በዝንጀሮ ፈንጣጣ (Mpox) የተያዘ ሰው ተገኘ።
በMpox የተያዘ ሰው የተገኘው ሞያሌ ከተማ ነው።
ጤና ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት Mpoxን አስመልክቶ የጋራ መግለጫ ሰጥተዋል።
በዚህም ኢኒስቲትዩቱ በኦሮሚያ ክልል ሞያሌ ከተማ አስተዳደር ከሚገኙ በህመሙ መያዛቸው ከተጠረጠሩ ታማሚዎች በወሰደው ናሙና በMpox ቫይረስ የተያዘ ሰው ማግኘቱን እንዳረጋገጠ ይፋ ተደርጓል።
ቫይረሱ እንደተገኘበት የተረጋገጠው የ21 ቀን እድሜ ያለው ህፃን ልጅ ሲሆን እናቱም በተደረገው ቀጣይ ምርመራ ለቫይረሱ እንደተጋለጠች ለማረጋገጥ መቻሉ ተገልጿል።
የህፃኑ አባትም ወደ ጎረቤት ሀገር ሄዶ የነበረ መሆኑ መታወቁና የሄደባቸውን አካባቢዎች እንዲሁም ከግለሰቡ ጋር የቅርብ ንክኪ የነበራቸው ግለሰቦችን የመለየትና ክትትል የማድረግ ስራ እንደተጀመረ ይፍ ተደርጓል።
ታማሚው ህፃን እና እናቱ፣ አስቀድሞ በተዘጋጀው የለይቶ ማከሚያ፣ ተገቢው የሕክምና ክትትል እየተደረገላቸው ሲሆን፣ እስካሁን ባለው ሁኔታ የከፋ የጤና እክል አልገጠማቸውም ተብሏል።
የMpox በሽታ ቫይረሱ ካለባቸው ግለሰቦች ጋር ንክኪ ያለው ሰው የሚከተሉት ምልክቶች በሚታዩበት ወቅት ማለትም ፦
– ሽፍታ
– ሳል
– ትኩሳት
– የራስ ምታት
– ድካም እና የጀርባ ህመም ሲያስተውል በአፋጣኝ ወደ ጤና ተቋማት በመሄድ ተገቢውን የምርመራና ህክምና አገልግሎት እንዲያገኝ ጥሪ ቀርቧል።
እንዲሁም የግል እና የእጅ ንፅህና በመጠበቅና ከላይ የተገለፁት ምልክቶች ባሉባቸው ታማሚዎች አካባቢ የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛዎችን በመጠቀም ተገቢውን ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል ተብሏል።
በአሁኑ ወቅት ይህ በሽታ በተወሰነ ቦታ ብቻ የታየ በመሆኑ ህብረተሰቡ ሳይደናገጥ የተለመደውን አኗኗር መቀጠል ይችላል ያሉት ጤና ሚኒስቴር እና የኢትዮጵያ ህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ፤ ወቅታዊ መረጃዎችን በአግባቡ በመከታተል ህብረተሰቡ ራሱን እና ቤተሰቡን ከዚህ በሽታ እንዲጠብቅ አሳስበዋል።