ሶማሊያ ስትራቴጂካዊ ናቸው የተባሉ ወደቦችን አሜሪካ እንድትቆጣጠር ጥያቄ አቅርባለች።

ሶማሊያ ስትራቴጂካዊ ናቸው የተባሉ ወደቦችን አሜሪካ እንድትቆጣጠር ጥያቄ አቅርባለች።

ጥያቄው የቀረበውም አሜሪካ ከሶማሊያ ለተለዩ ክልሎች የሃገርነት ዕውቅና እንዳትሰጥ ነው ተብሏል።

ሴማፎር (https://www.semafor.com/article/03/28/2025/somalia-offers-us-control-over-strategic-ports) በመጋቢት 16 የሶማሊያው ፕሬዚዳንት ሃሰን ሼህ ሞሐመድ ለፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እነዚህን ስትራቴጂካዊ ወደቦች እንዲቆጣጠሩ በደብዳቤ  መጠየቃቸውን ዘግቧል።

ለጥያቄ የቀረቡት ወደቦች በይፋ ባይገለፁም የበርበራ እና ቦሳሶ ወደቦች ሊሆኑ እንደሚችሉ ተገምቷል።

በደብዳቤውም አሜሪካ በቀጣናው ያላትን ቁጥጥር እንድታጠናክር እነደሚረዳት እና በወሳኙ የኤደን ባህረ ሰላጤ ላይም የሌሎች ሀገራትን ፉክክር እንድታስቀር እንደሚረዳት ስለመጠቀሱ ተመላክቷል።

የሶማሊላንዱ የበርበራ ወደብ የቀይ ባህር ንግድን ለማሳለጥ እና የሁቲ ጥቃትን ለመቀልበስ ወሳኝ ስለመሆኑ የተመላከተ ሲሆን በ2022 እራሷ ሶማሊላንድ አሜሪካ ዕውቅና እንድትሰጣት እና ወደቡን እንድትቆጣጠር መጠየቃቸው ይታወሳል።

ከወር በፊትም የሶማሊላንድ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር እስራኤል ዕውቅና ከሰጠቻቸው ከጋዛ ፍልስጤማውያንን እንደሚቀበሉ መናገራቸው ቢዘገብም ሚኒስትሩ ዘገባውን አስተባብለዋል።

ሶማሊያ በቀጣይ እርምጃዎች ዙሪያ ከአሜሪካ መንግስት ጋር ለመነጋገር ዝግጁ መሆኗን በደብዳቤው የተገለፀ ሲሆን በጉዳዩ ላይ ተጨማሪ ማብራሪያ የተጠየቁት የሃገሪቱ የማስታወቂያ ሚኒስትር እና በአሜሪካ የሚገኘው የሶማሊያ ኤምባሲ ሃሳብ ከመስጠት ተቆጥቧል።

ምንም እንኳን የበርበራ እና የቦሳሶ ወደቦች በሶማሊያ የፌዴራል መንግስት ቁጥጥር ስር ባይሆኑም የሶማሊያ ፌደራል መንግስት ግን አሁንም ወደቦቹን እንደራሱ ሉዓላዊ ግዛቶች ይቆጥራቸዋል።