አምስት የኢቢኤስ ቴሌቪዥን ጣቢያ ሰራተኞች “በሽብር ወንጀል” ተጠርጥረው ፍርድ ቤት ቀረቡ
የፌደራል ፖሊስ “በሽብር ወንጀል ጉዳይ” ጠርጥሬያቸዋለሁ ያላቸውን አምስት የኢቢኤስ ቴሌቪዥን ጣቢያ ሰራተኞችን፤ በዛሬው ዕለት ፍርድ ቤት አቀረበ። ጉዳዩ የቀረበለት የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት፤ ፖሊስ በጠየቀው የ14 ቀናት የጊዜ ቀጠሮ ላይ ብይን ለመስጠት ለመጪው ሰኞ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።
የፌደራል ፖሊስ የጊዜ ቀጠሮውን የጠየቀው፤ በስምንት ተጠርጣሪዎች ላይ እያካሄደ ያለውን የምርመራ ስራ “በሰው እና በሰነድ ማስረጃ በስፋት ለማጣራት” በሚል ነው። ከስምንቱ ተጠርጣሪዎች ውስጥ ባለፈው ሳምንት እሁድ በኢቢኤስ ቴሌቪዥን ጣቢያ በተሰራጨ ዝግጅት ላይ “የሀሰት ታሪኳ” ቀርቧል የተባለው ብርቱካን ተመስገን ትገኝበታለች።
የኢቢኤስ ቴሌቪዥን ጣቢያ ዋና ስራ አስኪያጅ እና የመገናኛ ብዙሃኑ አንዱ ባለድርሻ የሆኑት አቶ ነብዩ ጥዑመልሳንም በተጠርጣሪነት ፍርድ ቤት ቀርበዋል። በቴሌቭዥን ጣቢያው በፕሮግራም ዳይሬክተርነት የሚሰራው ጋዜጠኛ ታሪኩ ኃይሌ፣ የስቱዲዩ ዳይሬክተሩ አቶ ንጥር ደረጀ፣ ረዳት የፕሮግራም አዘጋጇ ህሊና ታረቀኝ እና የካሜራ ባለሙያ የሆነው ቶማስ ደመቀም ፍርድ ቤት ቀርበው የዛሬውን ሂደት ተከታትለዋል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)
🔴 ለዝርዝሩ ➡️ https://ethiopiainsider.com/2025/15550/