የአሜሪካ ዕርዳታ መቋረጥ በመላው ኢትዮጵያ ከባድ ንዝረት ፈጥሯል

የአሜሪካው የተራድዖ ድርጅት (ዩ ኤስ ኤ አይ ዲ) ዕርዳታ መቋረጥ፣ በመላው ኢትዮጵያ ከባድ ንዝረት ፈጥሯል ሲል ዘ ጋርዲያን ዘግቧል።

በዕርዳታ ዕገዳው ሳቢያ፣ የዓለም ምግብ ፕሮግራም ኢትዮጵያ ውስጥ ለተጠለሉ 800 ሺሕ ለሚጠጉ ስደተኞች ይሰጥ የነበረውን ዕርዳታ በ40 በመቶ መቀነሱን ዘገባው ጠቅሷል።

በተያዘው የአውሮፓውያኑ ዓመት የምግብ ዕርዳታ ፈላጊዎች ቁጥር ወደ 5 ሚሊዮን የተቀነሰበት አንዱ ምክንያት፣ የዕርዳታ ድርጅቶቹ እጅጉን ዕርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ብቻ ዕርዳታ እንዲያቀርቡ የሚያስገድድ ኹኔታ በመፍጠሩ መኾኑንም ጋዜጣው ጠቅሷል።

አሁን ባለው ተጨባጭ ኹኔታ፣ የዓለም ምግብ ፕሮግራም የምግብ አቅርቦቶቹን ከጨረሰ፣ ተጨማሪ የዕርዳታ ምግብ መግዛት እንደማይችልና ማሽላና የምግብ ዘይትን ጨምሮ 2 ነጥብ 1 ሚሊዮን የሚሆኑ ዜጎችን ላንድ ወር መመገብ የሚችል 34 ሺሕ 800 ሜትሪክ ቶን እህል፣ ወደ አገር ውስጥ ለሚያስገቡ ኮንትራክተሮች የሚከፈል ገንዘብ ባለመኖሩ ጅቡቲ ወደብ ላይ መቆሙንም የዜና ምንጩ ጠቅሷል። https://www.theguardian.com/global-development/ng-interactive/2025/feb/21/the-impact-has-been-devastating-how-usaid-freeze-sent-shockwaves-through-ethiopia