Ethiopian News, Current Affairs and Opinion Forum
Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 20 Nov 2019, 03:38

የኒህን ቆፍጣና የታሪክና የስነጽሑፍ አርበኛ ተስፋሚካኤል ትኩእ ታሪክ ምዕራፍ 31 ደርሰናል፡ ስለ ድንቁ ዲፕሎማት ሎሬንሶ ታእዛዝ ገድል ከባህር በጭልፋም ያቋድሱናል። መልካም ንባብ። :mrgreen:

“የተስፋ ሚካኤል ትኩእ መጨነቅ እየተጨመረበት ሔደ። የእንግሊዝም መንግሥት ባለሥልጣኖች ከኢትዮጵያ አርበኞችና በየሀገሩም ስደት ተሰደው ካሉትም ጋር በጽሕፈት እንዳልላላክ በቁጣ ከልክለው፣ አጥብቀውም በስውር ስለተጠባበቁኝ ከፍ ያለ የማያቋርጥ ስጋት ጣለብኝ። የመረረ ንዴት መናደድና ችግርም ዙሪያየን ከበው አጠቁኝ፤ ነገ ተነገ ወዲያ ምን እመገብ ይሆን በማለትም የልብ እረፍትና እንቅልፍም አሳጥቶ ኅሳብ ቢማርከኝም ሰማያዊ አምላክ የዕለት ቁርስ ምንም አልነሳኝም ነበር” ገጽ 153

“ከኔ ይልቅ ባለቤቴ ወይዘሮ ቀደስ ባህታና ልጆቼ ወይዘሪት አበባ ተስፋ ሚካኤል፣ ወይዘሪት ፀሐይ ተስፋ ሚካኤል ጉድለት በሌለበት እምነታቸው የእግዚአብሔርን ታዳጊነት ብቻ ምግብ አድገው የጠላት ፈጣን ጥፋት አመኑ። ምልካም አብነትና መልካም አርአያም ሆኑ።” ገጽ 153

የፊተውራሪ መብራህቱ ታእዛዝ መምጣት፦ የኢትዮጵያ መንግሥት ዋና አማካሪና ጠበቃ ዶክተር ሎሬንዞ ታእዛዝ ግርማዊነታቸውን ይዞ በሎንዶንና በቡሩክስለስ ከፓሪስም መንግሥት ጋር ስለ የኢትዮጵያ በግፈኛው ወረራና ወንበር መከልከልዋም ምክንያት በፖለቲካዊ ዲፕሎማሲ ጉዳይ ክርክር እየተመላለሰ ከተከራከረ በኋላ፣ የህግ ሊቁ ዶክቶር ሎሬንዞ በፊታውራሪ መብራህቱ ስም መንገድ አሳብሮ ከሎንዶን ተነስቶ በመብረቃዊ ያልታሰበ አመጣጥ በግብፅ መንገድ ገዳሪፍ ገባ። “ ገጽ 153

“አመጣጡም እንደ ህልም ሆነብኝ፤ ከጨካኙ የኢትዮጵያ ጥንታዊ ጠላት ከጣሊያን ፋሽስቶች የሚደርስበትን ስቃይና ውርደት፤ ጨካኝ በሆነው መጥፎ አገዳደል መገደሉንም ሳያስብ፣ ሕይወቱን ሳይቆጥብ፡ ስለ ውዲቱ ስለ ኢትዮጵያ ሀገሩ ነፃነት ወጣቱ ሊቅ ሎሬንዞ ታእዛዝ መሞቱን መረጠ። የኢትዮጵያ ሴቶች መመኪያ፣ የጀግናይቱ የትግሬ ሴት የቴጌ ጣይቱ ብጡል ኃይለ ማርያም ገብሬና የራስ አሉላን ደፋር ሕያው ተዋጊነት በመላው የአለም ነገሥታት ዘንድ በስመ ጥሩነታቸው እጅግ የተከበሩ መሆናቸውንና ከዚሁም የበለጠ አንዳች ነገር ምንም በዓለም አለመገኘቱን እየደጋገመ በሰፊው አጫወተኝ።” ገጽ 154

ስለዚህ ወታደር፣ የወታደር ልጅ የሆነው የአከለጉዛይ ሊቅ ፊታውራሪ መብራህቱ ታእዛዝ ቆራጥና ደፋር በሆነው ውሳኔው በዚሁ የመከራ ግዜዋ ኢትዮጵያ ውስጥ ገብቶ ደሙን ለማፍሰስ፣ ያለማቋረጥ ስለነፃነታቸው በሚጋደሉትም የኢትዮጵያ አርበኞች መካከል ተገኝቶ ለማጽናናት፣ ለማበረታታትና አብሯቸው በትልቅ ሰልፍ ተሰልፎ ስእል ለመነሳትና ኢትዮጵያም በጣሊያኖች አለመገዛትዋን ሊያስፈርማቸው በአማርኛና በፈረንሳይኛ ፰፣፰ (ማመልከቻ) አሰናድቶ ቁምጣ ታጥቆ ተነሳ። ሲነሳም ሳለ ለዚሁ የረቀቀ የዲፕሎማሲ ስራው ምስክሮች የሚሆኑት ፫ት ፈረንጆች የአረብ ልብስ አልብሶ፣ ራሱን የቱርክ ቆብ ደፍቶ፣ ሀገሬውን መስሎና እነዚህን ሰዎች አስከትሎ በቅጽበት ሌሊት ተነሳ።” ገጽ 154

“አቶ ዓድሐኖም ክፍለዝጊ አብሮት እንዲነሳ አስገደደኝ። እኔ ግን “ዓድሐኖም ከዚህ ሔዶ እስከወንድሞቹ ኤርትራን አቋርጦ ከዓጋሜ ያመጣውን መሣሪያና ወንድሞቹን ከሠላ ትቶ በድንገት ስለመጣ፣ እነዚያም ልጆች ወደ ጠላት ግዛት ተመልሰው ገብተው ይጠፋሉና እነሱን እስክያመጣ ድረስ ቆይ ጠብቀው። ከዓድሐኖም ይልቅ አርማ ጭሆንና ጐንደርን ጐጃምንም ስለማውቅና አንተን ለመርዳት ስለምችል። ሰውንም ስለማውቅ አብሬህ እሄዳለሁ” ብለው “እኔ ብሞት ግድ የለንም፤ አንተ ግን እኒህን ሴትና ሕፃናት በሱዳን ጥለህ ከኔ ጋር ለመሄድ አይሆንም። አቶ ኣድሐኖም ብቻ ይበቃኛል አንድ ሰዓትም ለመጠበቅ አልችልም ሲል አጥብቆ ተከራከረኝ እና እለቱን ከዓድሐኖም ጋር ተነስቶ ሔደ።” ገጽ 155

“ዓድሐኖምም ለፊታውራሪ መብራህቶም ታእዛዝ ሕይወት በብዙ ስለሳሳ ወንድሞቹንና በወንድነቱ ከጠላት ማርኮ ያመጣውን መሣሪያውን ጥሎ አብሮት ሔደ። ጊዜው ክረምት ስለነበረ ጓንጊ ሞልቶ መሻገሪያ አጥተው በምድር ላይ እየተኙ በዝናብና በረኃብ ተጨነቁ። ከፈረንጆቹ አንዱ ዛፍ ቆርጦ በግንድ መሸጋገሪያ ለማበጀት ሲደክም ከነግንዱ ጐርፍ ይዞት ስለሄደ ፈረንጆቹ በብዙ ስለደነገጡ፣ የህግ ሊቅ ፊትውራሪ መብራህቶ “ወንድሜ ዓድሀኖም ያወጣዋል እና ኣይዟችሁ፣ አትደንግጡ” ኣላቸው። እነሱ ግን ከዚህ የጐርፍ አደጋ ይድናል ብለው ተስፋ ሳያደርጉ የዛሬው ካፒቴን አቶ ዓድሐኖም ክፍለእግዚ እመር ብሎ እንደ ጥይት ተወንጭፎ የጓንጊ ውሃ የበላውን ሰው መንጥቆ በኃይል ሲያወጣው ሳለ፣ የስፓኛ ተወላጅ የጣሊያን ጠላት የሆነው ኮሎኔል እንድሪያስ ዓድሐኖምን ሲያወጣው ሳል አነሳቸው፤ በብዙ ተጨበጨበለት። ኮሎኔል እንድራያስም ከዓድሐኖም ብርታትና ጉብዝና የፊታውራሪ መብራህቱን ትንቢት በብዙ አመሰገነ፤ ዓድሐኖምም ንዳድ ታሞ ስለወደቀ በመከራ ገዳሪፍ ተመልሶ ሆስፒታል ገብቶ ዳነ። ከእግዚአብሔርም በታች ኤርትራዊ አፈንድ ሚካኤል በኪት ሐኪሞቹን በጥብቅ አዞ ስለደከሙለት ለመዳን ተስፋ ያልነበረው ዓድሐኖም ተረፈ።” ገጽ 155

“ፊታውራሪ መብራህቱም ፫ት ፈረንጆች ይዞ ጥቂት ሰዎች አስከትሎ ወሰንና መሳይ በሌለው መከራ የፊታውራሪ ባህታ ሀገር ሐውሳ ሲገባ ሁሎቹም ንዳድ ታመው ወደቁ። ለሐውሶች አደራ ብሎ ፈረንጆቹን ትቶ ፪ ሰዎችን አስከትሎ በአርማ ጭሆ ጣቁሳና አለፋን አቋርጦ፡ በአሸፈር ጐጃም ወደ ደጃዝማች ነጋሽ ከበደና ወደ አቶ ጊላጊዮርጊስ፣ ወደ ፊታውራሪ መንገሻ ጀምበሬ ዘንድ ገብቶ በሰልፍ እየዞረ ከጐበኛቸው በኋላም፣ በሕዝብ መራጭነት በጀግናነቱም ብዛት “የኢትዮጵያ ደም መላሽ አጼ በጉልበቱ በላይ ዘለቀ” ተብሎ ብዙ ፊታውራሪዎችና ደጃዝማቾች ራስ ብሎ እየሾመ ጣሊያንን ያለልክ ያረደና ያንቀጠቀጠ ኢትዮጵያዊው ጀግና ዘንድ አቶ አማኑኤል መንገሻን ብሸና ልኮ በፕላኑ መሠረት በሠልፍ ሥዕላቸውን አንሥቶ፣ ማኅተም ማኅተማቸውን አትመውና ፈርመው እንዲልኩ አደረገ፤ በአቶ አማኑኤል መንገሻ ብሩም በቤጌምድር እና በሰሜን፣ በጐጃምና በቋራ የተፈጸሙት ቁጥር የሌላቸው የጀግንነት ሥራዎች ምንም እንኳ ግርማዊነታቸው ቢያውቋቸውም በታሪክ መሥመር ሳይጻፉ በመቅረታቸው እጅግ ያዝናል።” ገጽ 155

“የአከለጉዛይ ሊቅና የዲፕሎማሲ አርበኛም የሆነው ደፋር ፊትውራሪ መብራህቱ ታእዛዝ የጐጃምን ሥራ ከፈጸመ በኋላ በትግሬ መኮንን ኃድጉ ልጅ በፊታውራሪ አየለ ሀገር በአሸፈር አቋርጦ አርማ ጭሆ ሲመለስ፣ ኮሎኔል እንድሪያስ የጣልያን መንግሥት ፈጽሞ ኢትዮጵያን አለመያዙንና ራሱ ጣሊያን ዙሪያውንም በኢትዮጵያውያኖች ተከቦ መጨነቁን ፈርሞ ለዓለም መንግሥታት መስክሮ አስታውቆ የነበረው ሙቶ ስለቆየው ብዙ ኅዘን አዘነ። ይህ ባለ ታሪክ የሆነ ዶክቶር ሎረንሶ ታእዛዝ ከበደ ቸኮልንና ወልደ ኪዳንን አስከትሎ ወደኛ ገዳሪፍ ተመልሶ ከመድረሱ፣ ጀኔራል ናዚ በጎንደር ሆኖ “ዶክቶር ሎሬንዞ ታእዛዝ በፊታውራሪ መብራህቱ ስም ወደ ኢትዮጵያ ውስጥ ገብተዋልና እጃቸውን ይዞ ላመታልኝ ሰው ወረታውን ሚሊዮን ሊሬ እሰጣለሁ” ብሎ በከንቱ ለኢትዮጵያዊ ህዝብ አዋጅ አናገረ።” ገጽ 155

“ዶክቶር ሎሬንዞ ታእዛዝ ግን የዲፕሎማሲ ስራውን ሳይለቅ ከፍ ያለውን ደፋር የአርበኝነት ስራ አጣምሮ ከፈጸመ በኋላ ህዳር ፲፰ ቀን ፲፱፻፴፩ ዓ.ም. ከገዳሪፍ ተነስቶ በካርቱም፣ በግብጽ፣ ፓሪስ ሲደርስ ስለ የኢትዮጵያ ወዳጅ ስለ ኮሎኔል አንድርያስ መሞትና ኢትዮጵያ በጣሊያን አለመያዝዋን ምስክርነት ተጠይቆ ካስረዳቸው በኋላ፣ አርበኛው ዶክቶር ሎሬንዞ ኢትዮጵያ በጣሊያን ከመያዝ በእግዚአብሔር ኃይልና በአርበኞቹዋ ወሰን የሌለው ብርታትና ጀግንነት ነፃ መሆንዋን ለግርማዊ ጃንሆይ የምስራችነት አበረከተ። በዓለም ነገሥታት ፊትም ጀግናው ዶክቶር ሎሬንዞ ታእዛዝ ክብርና ምሥጋና አገኘ፤ ሀገሩንም አስከበረ። ደፋር በሆነው ብርታቱና ወንድነቱም የሊቁ ሎሬንዞ ታእዛዝ ፖለቲካ እጅግ አስደነቀ።” ገጽ 156

“የፈረንሳይና የእንግሊዝ ማንቀላፋትና ስሕተት፦ በኤውሮጳ ጦርነት እንዳይነሳ በመፍራት እሳት ጫሪ ጣልያንም በናዝስቲና በየኤሮጳ ዲሞክራሲ መንግሥታቶች መሐከል ገብቶ እንዳይበጠብጣቸው አቆላመጡት፤ ኢትዮጵያን እወራለሁ ሲላቸውም ፈቀዱለት። የሚያስፈልገው ፖለቲካና ምክር አቀበሉት፤ አበዳሪና ዋስ ሆነውም ገንዘብ አበደሩት፤ የሚያስፈልገውን ርዳታ ሁሉ አደረጉለት፤ ላፋቸው ግን ጣሊያን ኢትዮጵያን እንዳይወጋ አደረግን፣ አስወሰን ሲሉ አውርተው አስወሩ።” ገጽ 156

ወዳጃቸው የጣሊያን መንግሥት በተምቤን ድል ሆንኩ ብሎ በ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ስልክ ባሳለፈላቸው ቀን የርዳታቸውን ምስክርነት ጉልህ አድርገው ሲገልጹ፣ እንግሊዝና ፈረንሳይ “የጣሊያን በኢትዮጵያ ድል መሆን ለድፍን ኤውሮጳ ውርደትና እፍረትም ስለሆነ “በመረዝ” በርትታችሁ ውጉዋት” ሲሉ በቁጣ ቃል ለጣሊያን ማስተላለፋቸው ከማንም ሰው የተሰወረ አልነበረም። የኢትዮጵያ ዘር ሁሉ ምንጊዜ ሊረሳው ምንም አይችልም። የኢትዮጵያን መንግሥት መስዋእት ለጣሊያን አሳልፈውን ሰጥተን በሀገራችን ጦርነት ሳይነሳ በሰላም እንኖራለን፤ ጀርመንም ለጦርነት እንዳይነሳ ከፋፍለን፣ በጭቆናና በርኃብ ገድለን አስረነዋልና ለመነሳት አይችልም በማለታቸው ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያን አሳልፈው ለጣሊያን በመስጠታቸው በአርእስቱ “የፈረንሳይና የእንግሊዝ ማንቀላፋትና ስህተት” ተባለ።” ገጽ 157

“በዚሁም የፈረንሳዊና የእንግሊዝ በማንቀላፋት መሳሳት ኢትዮጵያን በጣሊያን በማስወሰዳቸው ምክንያት የናዚስት መሪ የሆነው ጀርመናዊ አዶልፍ ሂትለር “ፍላይት ቦምብ” የተባለ ሐዲስ እሳታዊ በራሪ ዲስክ ሲያጥለቀልቃቸው ጊዜ፤ በመጸጸት እንዲህ ሲሉ ኑዛዜ ተናዘዙ። “ዙሪያውን በአረመኔዎች የተከበበቺው የኢትዮጵያ ክርስቲያናዊት ደሴት አምላክ ከባህር ዛፍ በታች ሆኖ ከጠላቶችዋ ጠበቃት” ሲሉ ራሳቸው መሰከሩላት። በብዙም እግጅ ተደነቁ።” ገጽ 157

በቀጣዩ የምዕራፍ ሠላሳ ሁለት ትረካ “ከኔ ከተስፋ ሚካኤል ለግርማዊ ጃንሆይ የተጻፉት ደብዳቤዎችና በጸሐፊያቸው ራሳቸው የሰጡኝ መልስ” በሚል ርእስ ስር የተካተተውን ታሪክ እናያለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 29 Nov 2019, 08:56

አርበኛው ተስፋ ሚካኤል ትኩእ ያመኑበትን ጉዳይ በግልጽ በማቅረብና ከ “ሞዓ ኣንበሳ"ዉና ከጠሐፊዎቻቸው ጋር የተጣጣፏቸውን ደብዳቤዎች እንቃኛለን። መልካም ንባብ። :mrgreen:

“ለግርማዊ ጃንሆይ። ቸሩ እግዚአብሄር የልቦናዎን ኅሳብ ሰምቶ በቅጽበት እንዲፈጽምልዎ የኢትዮጵያ ወጣቶች ሁሉ በትልቅ ኅዘን ፈጣሪን ከመለመን ምንም አላቋረጡም። የፍፃሜው ቀኑም ባይደርስ ነው እንጂ ደህና ከሆነ ነገሩ በቶሎ ይፈጸማል። በየምክኒያቱም ከሸዋና ከሰቆጣ፣ ከበጌምድርና ከጐጃም ተልከው የመጡ ሰዎች ጉዳያቸውን ሳይፈጽሙ ገዳሪፍ ላይ በእንግሊዝ ተይዘው ታስረው በብዙ የኦባ(ወባ) በሽታና ጨካኝ ረሃብ በመገረፋቸው ችግራቸውን ለግርማዊነትዎ እንዳስታውቅ ኅልናዬ አጥብቆ አስገድዶኛልና በቸርነትዎ የእነዚህኑ ፍጥረቶች ብርቱ ችግር እንዲያቃልሉላቸው አሳስበዎታለሁ።” ገጽ 158

ከሸዋ ልጅ ነጋ ኃይለ ሥላሴና እንግዳ ወርቅ ወልደማርያም፣ መኮንን ደስታ፣ ተስፋዬ በላቸው፣ ከሰቆጣ ፊታ. ኃይሉ ክብረት፣ አቶ ስጦታው፣ ልጅ መጐስ አሊ፣ አቶ ላቀው። ከበጌ ምድር ግራዝማች አስማረ ዘረፋና አቶ በለጠ ሣህለሚካኤል ከጐጃም አቶ መኮንን ደስታ፣ ከበደ ወልደ ሰማያት፣ አቶ ታደሰ ገብረ መድኅንና ሌሎቹም ብዙ ሰዎች ናቸው የመጡ።” ገጽ 158

“የግርማዊ ጃንሆይን ልክ ለማወቅ ከየክፍሉ የመጣ ሰው ቁጥና ወሰን የለውም። በኦባ ህመም ተሸንፎ ካልወደቀ ወይም ካልሞተ በቀር ወደዬ ሀገሩ እየተመለሰ ይሄዳል። የኢትዮጵያ ሕዝብም የተቸገረው በሕይወት መኖርዎን በብዙ እየተጠራጠረና ሃሳቡም እየተከፋፈለ፣ ተጨንቆ ተጠቦዋልና ለፈጣሪዎ አስጨንቀው እንዲለምኑትና ጉዳዩው ሁሉ በፍጥነት እንዲፈጸም እንዲያደርጉለት ህዝብዎ በብዙ ተስፋ ይጠብቅዎታል። ገዳሪፍ መስከረም ፳፮ ቀን ፲፱፻፴፩ ዓ.ም። ፊርማ፣ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።” ገጽ 158

“ለግርማዊ ቀዳማዊ አጼ ኃይለ ሥላሴ። ሎንዶን። ሐዋርያት ያልቻሉት ረሐብና ችግር አስጨንቆኛልና ጊዜ ስለማይሰጥ የገንዘብ ርዳታ እንዲሰጠኝ ለግርማዊነትዎ ቸርነት አለምናለሁ። እኔም ከነ ባለቤቴና ከነ ልጆቼ ፭ት ራሴ ሆኜ ስደት ስሰደድ ጉዳቴ ከልኩ አልፎ የተረፈ መሆኑን ለማንም ሰው ያልተሰወረ ሆኖ ሳለ አንዳንድ ራሳቸው ለተሰደዱ ሰዎች ግን አስተዋሽና ዘመድም በማግኘታቸው ከግርማዊነትዎ በየጊዜው የገንዘብ ርዳታ ሲደርሳቸው እኔ ብቻ ተለይቼ በመቅረቴ በብዙ አዝናለሁ። ርዳታም እንዳይደርሰኝ ያስከለከሉኝ ትግሬ በመሆኔ ነው። ትግሬነቴም ምንም የሚያሳፍረኝ አይደለም። ገዳሪፍ፣ መስከረም ፳፮ ቀን ፲፱፻፴፩ ዓ.ም። ፊርማ፣ ታዛዥዎ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።” ገጽ 159

“ሞዓ አንበሳ ዘእም ነገደ ይሁዳ፣ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሥዩመ እግዚአብሔር ንጉሠ ነገሥት ዘ ኢትዮጵያ። ይድረስ ከአቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ። እንደምን ስንብተሃል? እኛ በእግዚአብሔር ቸርነት ደህና ነን። የላከው ደብዳቤ ደርሶናል። ድህንነታችሁን ስለሰማን ደስ የሚያሰኝ ነው። ምላሹም ተጽፎአል። በዚህ በፈተናችን ሰዓት በማናቸውም ጊዜ ሐይማኖታችንን ማጽናት ያስፈልገናል። በእርሱም ላይ የምናደርገው እምነት ከንቱ ሁኖ አይቀርም። ግንቦት ፲፱ ቀን ፲፱፻፴፩ዓ.ም ተጻፈ። ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሰ ነገስት ዘ ኢትዮጵያ።” ገጽ 159

“ይድረስ ለክቡር ወዳጄ አቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ። እጅጉን እንደምን አሉ፤ እኔ እግዚአብሔር ይመስገን ደህና ነኝ። የላኩልኝ ደብዳቤ ደረሰኝ፤ ምላሹን ከዚህ ጋር ያገኙታል። ምንም ችግርና የዚህ አለም የመከራ ኑሮ ቢታገለን የሰጠንን እድል በትዕግስት በመቀበልና ለማሸነፍም በመጣጣር መበረታት ይገባናል።” ገጽ 159

“ወሬዎን ሳልሰማ ብዙ ጊዜ አልፎ ነበር። ምንም ባይመችዎ እስከዚያው ድህንነትዎን በመስማቴ ደስ አለኝ። ደብዳቤዎ በመጥፎ አጋጣሚ ጊዜ ስለደረሰኝ ስለተመኙት ምንም ለማድረግ ባለመቻሌ ከልክ ያለፈ አዝናለሁ። ነገር ግን ተስፋ አልቆርጥም፤ የተሻለ ጊዜ እንዲገጥመኝ እለምናለሁ። የቤት አባት ጭንቅዎ ይሰማኛል፤ ሰው ለመርሳት ቢፈልግ ኢትዮጵያና ልጆቹን ታላቁ ጌታ አይረሳምና በቅርብ ብርሃን እንዲያሳየን እንለምን። ሎንዶን፡ ግንቦት ፩ ቀን ፲፱፻፴፩ ዓ.ም። የርስዎ፣ ፊርማ ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ።” ገጽ 159

“ካርቱም ነሐሴ ፲፬ ቀን ፲፱፻፴፪ ዓ.ም ይድረስ ለክቡር ወንድሜ አቶ ተስፋ ሚካኤል። ባቶ በርሄ አደራነት የላከልኝ ደብዳቤዎች ትላንትና ከ፮ ሰዓት በኋላ የደረሰኝ፤ ለባለቤቱ አድርሻለሁ። የኤርትራ ልጆች በመጡ ቁጥር ወደዚህ በቶሎ እንዲላኩ ለሚካኤል ኤፈንዲ እየነገርክ እንድታግዛቸው አደራ። ለዚሁ ስራ አንድ መንገድ እስቲበጅበት ድረስ ነው። አሥፈሐ ወደ ሥላሴ እዚህ መምጣቱን ያለመምጣቱን ለማወቅ አልቻልኩም፤ ለጊዜው አሁን ማለዳ ነውና ነገር ግን አስጠይቃለሁ። ለባለቤትና ልጆችህ የናፍቆት ሰላምታ አቅርብልኝ። ትናንሾቹን ባንዲራዎች ለመጀር ኖት አስረከብከው ወይ። ያንተ ። ፊርማ ፊታውራሪ መብራህቱ ታእዛዝ ሎረንሶ።” (በዚህ ደብዳቤ ዕለቱ በመጀመርያ ተጽፏል፣ የጸሐፊው ዘመናዊ ትምህርት መቅሰምን ሊያመላክት እንደሚችል አርታዒው ገልጿል)” ገጽ 160

ለወዳጀ አቶ ተስፋ ሚካኤል፤ ገዳሪፍ። እንደምን አሉ ከነቤተሰብዎ። እኔ ደህና ነኝ። የጻፉልኝ ደብዳቤዎች ደርሰውኛል። አቶ መንግሥቱም ተመልሰው ለስራቸው መጥተዋል። ለተባባልነውም ጉዳይ ወረቀቱን ተቀብለዋል። ሌላ የምንሰማው ሁሉ ደስ የሚያሰኝ ነው። የካሣ አብርሃ መምጣት ሳይሰሙ አልቀሩም፤ ከርስዎ ተርፎ የመጣ ነው። ይህንን የመሰለ ሰው በሕይወት ቆይቶ ወደዚህ ለመድረስ መቻሉ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር መሆኑን የሚያስረዳ ነው። የጠላታችን አይን ተቸፍኑዋል። ይህም የአምላክ ኃይል ነው። መልእክተኞቹ በቶሎ መነሳታችው ስለሆነ ይህን አጭር ቃል ጻፍኩልዎ። ባለቤትዎ ወይዘሮ ቀደስና ልጆችዎ ደህና ኣንዳሉ ተስፋ አለኝ። የማክበር ሰላምታ ይስጡልኝ፤ በቅርብ ያገናኘን። መስከረም ፲፭ ቀን ፲፱፻፴፫ ዓ.ም። ካርቱም። ፊርማ፣ ወልደ ጊዮርጊስ ወደ ዮሐንስ።” ገጽ 160

በቀጣዩ የምዕራፍ ሠላሳ ሦስት ትረካ “ስለ ኢትዮጵያ ጉዳይ እኔ ተስፋ ሚካኤልና አቶ መኰንን ተጻጽፈንባቸው ከጠፉት ውስጥ የቀሩት ደብዳቤዎች ለመታሰቢያ” በሚል ርእስ ስር ያካተቱን ታሪክ እናያለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 10 Dec 2019, 08:16

የአርበኛው የአቶ ተስፋሚካኤል ትኩእን ትረካ እየኮመኮምን ምዕራፍ ሠላሳ ሦስት ደርሰናል፤ አርበኛው ከአቶ መኮንን ጋር ከተጻጻፏቸው ደብዳቤዎች መካከል ከጠፉት ውስጥ የቀሩትን ለመታሰቢያነት ያህል ለዛሬ አጋርተውናል። መልካም ንባብ። :mrgreen:

“ለክቡር አቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ። የጥብቅና መጣበቅ ኮሚቴ ምክትል ፕረሲደንት። ካርቱም። ግንቦት ፳፰ ና ሰኔ ፩ ቀን የጻፉልኝ ደብዳቤዎች ደርሰውኛል፤ ለግርማዊ ከእኔ ማስታወሻ ጋር ልኬዋለሁ፤ ለማናቸውም ቢሆን ምላሹ እስኪመጣ ቢታገሡ ይሻላል፤ ባይሆን ለቤተ ዘመዶችዎ እዚያው እሱዳን ውስጥ ነፋሻ ቦታ ፈልገው (እነሱን እዚያ እሱዳን ውስጥ) እርስዎ ለቢሮዎ ወደ ተመቸዎት ከተማ ብትቀመጡ ይሻላል። ስደተኞቹ ወንድሞቻችን በታላቅ ብስጭት ላይ በመሆናቸው አለአግባብ በሚያባክንዎ ሁሉ እርስዎ የሀገር ፍቅር ስላለብዎ ይታገሡ።” ገጽ 161

“ገንዘብክ አልደረሰነም ስላሉኝ፤ ገንዘብ የተላከው ባቶ ገብርኤል ወልደ ማርያም በኩል ነው። ርስርስ ባንክ የለም፤ ለብላታ ዴሬሣ አንሰጥም ስላሉኝ፣ አቶ ገብርኤል ተቀብለው ለብላታ ዴሬሣ እንዲያደርሱ ስለላክንላቸው ገንዘቡ መጥቶልናል ለብላታ ዴሬሣ አስረክባለሁ ብለው ጽፈውልናልና በትህትና አቶ ገብርኤልን ይጠየቁአቸው።” ገጽ 161

“ዳግም እንግሊዝ ኰሚቴአችን አንድ ፻፶ ጊኒ በሱዳን ገቨርኔር በኩል ተልኮላቸው ሳይነግሩአችሁ አይቀሩም። ለማናቸውም ተመካክራችሁ በየጠረፉ ያሉትን ሰዎች ቁጥር ችግር ቢገጥማችሁ በትልቅ ትህትናና ብልሃት ለሀገር ገዥው ጸሐፊ ብታመለክቱአቸው መልካም ነው። አለዚያም እስኪያስታውቁዋችሁ ጥቂት ጠብቃችሁ ምላሹን አስታውቁን። ፓሪስ፣ ሰኔ ፲፪ ቀን ፲፱፻፳፱ ዓ.ም። ፊርማ መኰንን ሀብተ ወልድ።” ገጽ 161

“ይድረስ ለአቶ ተስፋ ሚካኤል፣ ጤናህን እንደምን ሰንብተሃል? ወንድሜ እኔ እግዚአብሔር ይመስገን ደህና ነኝ። በደህና ከነልጆችህ ካርቱም መድረስህን ብሰማ በጣም ደስ አለኝ። እንኳን አምላክ ከአደጋ ያተረፈህ። የአቶ መኰንን ሀብተ ወልድ ደብዳቤ ገና ዛሬ ከወረቀትህ ጋር ደረሰኝ። ሁሉንም በዝርዝር አድርጌ ቶሎ እሰዳለሁ። አስበህ ስለጻፍህልኝ እግዚአብሔር ይስጥልኝ። ባላምባራስ አሸብርም መጥቶ እዚህ ነው ያለው፤ እንዲጽፍላችሁ አድራሻችሁን እሰጠዋለሁ። የካቲት ፪ ቀን ፲፱፻፳፱ ዓ.ም. ርስሪስ፣ ፊርማ ብላታ ዴሬሣ አመንቴ።” ገጽ 162

“ይድረስ ለክቡር አቶ መኰንን ሀብተ ወልድ፣ ፓሪስ። እንደምን ሰንብተዋል? እግዚአብሔር ይመስገን እኔ ደህና ነኝ። ለጻፍሁለዎት መልስና ለሰጡኝ ብዙ ተስፋ እጠባበቃለሁ። ክቡር ሆይ የስደተኞች ቁጥርና ችግር በየቀኑ በዝትዋል፤ የግርማዊ ጃንሆይን ልክ ለማወቅ ብለው በበጌምድር አቋርጠው ጋላባት መጥተው የነበሩት ፊታውራሪ ኃይሉ ክብረት ተመልሰው ዳግም በጋላባት ገዳሪፍ ጠረፍ ለጠረፈ ከነጓዛቸው ከሀገራቸው ተነቅለው መጥተው መጉላላታቸውንና በብዙ መጨነቃቸውን ስለሰማሁ በሀገር ገዥው በኩል ተፈልገው እንዲረዱ ለግርማዊ ጃንሆይ እንዲያመለክቱላቸው አስታውሰዎታለሁ።” ገጽ 162

“፪ኛ ግራዝማች ፍስሐዬ ዘሚካኤል የሚባሉ አርበኛ ከሰሜን ራሳቸው መጥተው ኃደሊያ ካሉት ቀኛዝማች ዓምደማርያም ተስፋ ጽዮን ጋራ ተቀላቅለዋል፤ ሥዕላቸውን ግን ለማግኘት አልተቻለም።” ገጽ 162

“፫ኛ ግራዝማች ውብነህ ተሰማ የተባሉ በእውነተኛው ውብነታቸው በሀገር ፍቅር የተነደፉ አርበኛም ጓዛቸውን አስቀድመው በፊት ገዳሪፍ አስገብተው ራሳቸው ግን የአርማ ጭሆን ሰው ሁሉ አሳብረው ብርቱ የወንድ ሥራ ሠሩ፤ ጠላትን በብዙ ማረኩ። በማባረርም እጅግ አስቸገሩት። ያስቸግሩታልም። ስለዚህ ሞያቸው ለግራዝማች ውብነህ ተሰማ ደብዳቤ ቢጻፍላቸው እጅግ መልካም ነገር ነበር።” ገጽ 162

“፬ኛ ስዩ የፊታውራሪ ዮሐንስ ጆቴ አጋፋሪ የነበረው ቀኛዝማች ወልደ አማኑኤል ፲፫ ራሱ ሆኖ ሐምሌ ፲፱ ቀን ካርቱም ገባ። ከሞት የተረፈ ሰው ሁሉ እየበረረ ፈጽሞ መምጣቱ አልቀረምና ለባለቤቱ አስታውቀው አስቀድሞ እካርቱም ለኋላ የሚሆነውን ነገር ሁሉ አሁኑኑ ጀምረው እንዲያዘጋጁት አሳስበዎትለሁ። የኢትዮጵያ ሰው ሁሉ ዛሬ በግልጽ የሚያወጋው ጃንሆይ ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ ሱዳን ደርሰዋል፤ ጣሊያን ግን ቀኑ ስላለቀ አይኖርም፤ አልቆ ይቀራል እያለ ሌት ተቀን እግዚአብሔርን መለመን ይዞዋል ይሉናል። ልመናችንም እግዚአብሔር ፈጥኖ እንደሚሰማን የተረጋገጠ ነገር ነው እና እስከዚያው ድረስ ለስደተኛው ሁሉ መሠረት ያለው ተስፋ እንዲሠጡት።” ገጽ 162

“፭ኛ ላባ ገብረ ሥላሴ ተብሎ ወጥቶ ባቶ ገብረ መስቀል እጅ የተቀመጠውን ፲ ጊኒ እሳቸው ግብፅ ወርደው ስለጠፉ ሱዳን ካሉት ሰዎች ችግር ለበዛበት አይተው ቢሰጡት መልካም ይመስለኛልና ከባለቤቱ እንዲያስፈቅዱ።” ገጽ 162

ክቡር ሆይ፤ ክፉ ቀን ያልፋል፤ ስም ግን አያልፍምና ነዋሪ ሆኖ በታሪክ ለሚጻፈው ስምዎት እንዲጣጣሩ በብዙ አስታውስዎትአለሁ። ካርቱም፣ ሐምሌ ፳፫ ቀን ፲፱፻፳፱ ዓ.ምሕረት። ፊርማ፣ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።” ገጽ 163

በቀጣዩ የምዕራፍ ሠላሳ አራት ትረካ “ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኅበ እግዚአብሔር፤ በፓሪስ የቆመ ማኅበር” የሚል ርእስ የሰጡትን ትረካቸውን እንቃኛለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው። :mrgreen:

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 30 Dec 2019, 04:22

ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኅበ እግዚአብሔር፤ በፓሪስ የቆመ ማኅበር” በሚል በመጸሓፋቸው ሠላሳ አራተኛ ምእራፍ ውስጥ አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ ከኢትዮጵያ ማኅበር ፕሬዘዳንት ካቶ መኰንን ሀብተወልድ ጋር የተጻጻፏቸውን ቅልብጭብጭ ያለ ይዞታ ያላቸውን ደብዳቤዎች እንጋራለን። የአርበኛውን ሃሳብ የማፍለቅና ሃሳባቸውን በቅንነት የመግለጽ ባህሪም ይህ ደብዳቤያቸው አሁንም ፍንትው አድርጎ ያሳየናል። መልካም ንባብ። :mrgreen:

“ይድረስ ለክቡር ወዳጄ አቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ። የወዳጅነት ሰላምታዬን ለርስዎና ለተወደዱ ቤተ ዘመዶችዎ አቀርባለሁ። ወዳጄ ሆይ ለጤናዎ እንደምን ሰንብተዋል? ሐምሌ ፩ ቀን የጻፉልኝ ደብዳቤ ሐምሌ ፯ ቀን ደረሰኝ፤ አመሰግንዎታለሁ። ሌላ ፕሬሲደንት በመለወጡ ለርስዎ እረፍትና ጥቅም ነው፤ ቀድሞውንም ቢሆን የመረጥንዎ ለስደተኞቹ ወንድሞቻችን ጥቅም ነው እንጂ ለርስዎማ ድካም አይደለምን? አሁንም በሚቻለዎ ወንድሞቻችንን መርዳትዎን እንዳያቋርጡ እንለምንዎታለን፤ በሰላም ያገናኘን። ሐምሌ ፲፫ ቀን ፲፱፻፳፱ ዓ.ም ፓሪስ። የኢትዮጵያ ማኅበር ፕሬዘዳንት፤ ፌርማ፣ መኰንን ሀብተ ወልድ።” ገጽ 164

“ይድረስ ለክቡር መኰንን ሀብተ ወልድ፣ ፓሪስ። እንደምን ሰንብተዋል? ለጤናዎ ቸሩ እግዚአብሔር ይመስገን እኔ ደህና ነኝ፤ በሐምሌ ፲፫ ቀን የጻፉልኝ ክቡር ደብዳቤዎ ደረሰኝ፤ ስለ የሥራ መለዋወጥ ምክንያትም ደስ ብሎኛል፤ ወንድሞቻችንንም ለመርዳት አላቋርጥም፤ በዚሁ ነገር ተስፋ ሚካኤል ይከፋዋል ብለው ምንም እንዳያስቡ። ይልቁንስ የስደተኞቹ ጥቅም አብልጦ ደስ ይለኛል እንጂ አይከፋኝም።” ገጽ 164

“፪ኛ ራፓር በረኰማንዴ እንዳልጽፍለዎ የጊዜው ችግር አልፈቀደልኝም፤ ለጊዜው የሚያስፈልገውን በገዳሪፍና በከሰላ ለሰው እንዳይታዩ ፈርተው በድብቅ ገብተው በብዙ ችግር የተለወሱትን ስደተኞች በፍጥነት መርዳት ነው። ከሁሉ የበለጠ ነገር ለመጡና ለተቀመጡ በሌላ ሰው ስም አዙሮ ለመላክም የሰውዬውን ስም ይስጡን፤ አይስጉ።” ገጽ 164

“፫ኛ ክቡር ሆይ ከዚህ ቀደም የጻፍሁለዎትን ትንንሽ ኅሳቦቼን ከ፫ቱ አንዱን ተቀብለው ቢፈጽሙት ኑሮ እጅግ መልካም ነበር። አሁንም አለብርታት መፈጸም ምንም መዳኛ እንደሌለን ይወቁት፤ ለወደፊቱም ፲፱፻፴ ዓመተ ምሕረት ካለፈች በኋላ ተስፋችን በመቆረጡ ያለቀ የተፈጸመ ነው። ስለዚህ ዛሬውን መሥራት የመሰለ የለም። በሕይወት ያገናኘን እግዚአብሔር፤ አሜን። ሐምሌ ፳፬ ቀን ፲፱፻፳፱ ዓ.ም. ካርቱም። ፊርማ፣ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።” ገጽ 164

በቀጣዩ የምዕራፍ ሠላሳ አምስት ትረካ “እኔ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ በየጊዜው ለጻፍሁላቸው የማነቃቃት ደብዳቤዎች ሲመሰክሩ አርበኞች የሰጡኝ መልሶች” የሚል ርእስ የሰጡትን ትረካቸውን እንቃኛለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 13 Jan 2020, 10:26

ለዛሬ ኤርትራዊው አርበኛ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ‘የእውቁ የቦለቲካ ተንታኝ’ የታምራት አባት አያ ነገራም ሆኑ አያቱ አያ 'እንቶኔ' ንፍጣቸው ባፍንጫቸው ይዝረከረክባቸው በነበረ በዚያን ቀውጢ ሰዓት :mrgreen: ፡ እኒህ ኤርትራዊ አርበኛ ለኢትዮጵያውያን አርበኞች የጻፏቸውን የማነቃቃት ደብዳቤዎች፡ አርበኞቹም እማኝነታቸውን የሰጡባቸውን ደብዳቤዎች ለናሙናነት ጥቂቶቹን እናያለን፣ መልካም ንባብ። :mrgreen:

“ይድረስ ከአቶ ተስፋ ሚካኤል ጤናህን እንደምን ከርመሃል? እግዚአብሔር ይመስገን እኔ ደህና ነኝ፤ የጻፍህልኝ ደብዳቤ ደርሶኛል፤ ያንተንም ከጣሊያን አደጋ አምልጠህ ካርቱም መድረስህን ብሰማ በጣም ደስ አለኝ፤ ለወደፊቱም እንደዚሁ ብትጽፍልኝ መልካም ነው። የኢትዮጵያን ባንዲራ አቁም ፊት ለፊት ተገናኝተን ለመጨዋወት ያብቃን። ሐምሌ ፮ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ዝማኅተም፣ ደጃዝማች ኃይሉ ከበደ። መተማ ስለ አስሽከሮቻቸውና ባለቤታቸው እስከመጨረሻ ተዋጉ።” ገጽ 165

“ይድረስ ለአቶ ተስፋ ሚካኤል፣ ጤናኽን እንደምን ሰንብተሃል? እኔ አምላክ ይመስገን ደህና ነኝ፤ የላክህልንም ደብዳቤ ደረሰልኝ። እኛም በሥላሴ ቸርነት ከጠላታችን ከኢጣሊያን መዋጋት ከጀመርን እስካሁን ድል ከማድረግ በተቀር ድል ሆነን አናውቅም። ብዙ መትረየስና መድፍም ማርከናል፤ እስከ ዛሬ እንታገላለን። የኢትዮጵያ ልጅ የሆነ ሁሉ መርዳት ለዚህ ጊዜ ነው። ይኸው ለሁሉም ነገር ልጅ ታደሰን ልከነዋልና በየተቻላችሁ መርዳት ነው። የኢትዮጵያ አምላክ ለነፃነት አብቅቶ፣ ግርማዊ ጃንሆይንም አሰንብቶ፣ እኛንም አቆይቶ በሰላም ለመገናኘት ያብቃን። ሐምሌ ፴ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ተጻፈ። ፊርማ ደጃዝማች መንገሻ ጀመሬ(ጀምበሬ)።” ገጽ 165

“ይድረስ ለክቡር ወንድሜ አቶ ተስፋ ሚካኤል። በመክበር ሰላምታዬን አቀርባለሁ፤ እኔ ቤተሰዎቼም ደህና ነን፤ አምላክ ይመስገን። የላኩልኝ ደብዳቤ ደረሰኝ። ይኸውና በዚህ በኩል ባለፈው መስከረም የጀመርን እስከ ግንቦት ድረስ አልቦዘንንም፤ ብርታቱም ወደኛ ነበር። ባላባቶች በሀገር እየተቀያየሙ ከግንቦት ወዲህ ለጠላት ጉልበት ሰጡት። ፭ት ካምቦ የነበረው ፩ ተከለበት፤ ተከቦ በያለበት ተቀምጦዋል። በጌምድር ባሁኑ ጊዜ በጣም ጠንክሮዋል፤ እስከ መስከረም ድረስ ካለ ጎንደር ከተማው የሚቀረው አይመስልም።” ገጽ 166

“የጐጃም ሕዝብ ሳያውቁት አይቀሩም፤ ገንዘብ ወዳጅ ነውና ጠላታችን ጭካኔውን ትቶ በማታለል መስበክ ጀምሮዋል። ባላገርን በገበያ ሲሰቅል የነበረው ጣሊያን አሁን ግን እየገባችሁ ብረት አንሱ እያለ እርስ በርሳችን ሊያፋጀን አስቦዋል። እነ አቶ ገብረ መስቀል ሳይደርሱ መላላት ጀምሮ ነበር፤ አሁን ግን ዳር እስከ ዳር ተጽናንተዋል። አንድ ዋና ቢሆን ለወደፊቱ ደግ ነበር፤ በእውነት ለሀገራችው ነፃነት ብቻ አስበው የተነሱ ያለ ደጃች መንገሻ በጐጃም በኩል ያገኘ አይመስለንም። እኔ ቤቴን ለቅቄ ከርሳቸው ጋራ ነኝ ያለሁ። በሕይወት ያገናኘን ቤተሰዎቼ ለቤተሰዎችም ጭምር ሰላምታቸውን ያቀርባሉ። ሰኔ ፫ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ጐጃም ፊርማ፣ ጊላጊዮርጊስ (የዛሬው ፊታውራሪ)” ገጽ 166

“ይድረስ ለክቡር ወንድሜ፣ ወዳጄ ካቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ፤ ከተለያየን እስካሁን ጤናዎን እጅጉን እንደምን ሰንብተዋል። እኔ እግዚአብሔር ይመስገን ደህና ነኝ፤ የርስዎንና የልጆችዎን ደህንነት በሰማሁ ጊዜ እጅግ ደስ አለኝ። አሁንም የሚመጣ ሰው ሲገኝ እደጃዝማች ነጋሽ ድረስ ይጻፉልኝ፤ ይደርሰኛል። ይኸ መኰነን ደስታ የኔ ወንድም ነውና በማናቸው በሚቸገርበት ነገር ሁሉ እንዲረዱት ስል አጥብቄ እለምንዎታለሁ፤ በዚያ ሀገር ዘመድ የለውም። አደራ። ነሐሴ ፭ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ጐጃም። ፊርማ አለማየሁ ቦጋለ።” ገጽ 166

“ይድረስ ለክቡር አቶ ተስፋ ሚካኤል፣ እጅጉን ለጤናዎ እንደምን ከርመዋል? እኔ አምላክ ይመስገን ደህና ነኝ፤ እንኳን ዘመን ከዘመን አሸጋገረዎ፤ ይኸው ከዚህ ቀደም ፲፱፻፴፪ ዓ.ም. በሐምሌ በገዳሪፍ መኖርዎን ሰምቼ ጽፌለዎት ነበር። ይህም ደብዳቤ ሣይደርስዎት በመቅረቱ በጣም አዘንሁ። አሁንም ከዚህ ቀደም ከመጣው መሣሪያ ለአርበኛ አንድ አልደረሰልንም፤ እና ስለዚህ ኅሳብ እንዲያስታውቁልኝ። የኢትዮጵያ አምላክ ረድቶ በሕይወት ለመገናኘት ያብቃን። ፊታውራሪ ካሣ ኪዳነ ማርያም የጃንሆይን ድምጽ ስለሰሙ እኔም ስለላኩባቸው ፶ ራሳቸው ሆነው ከነ መሣሪያቸው ከጠላት ወደኔ መጥተው መግባታቸውን አስታውቀዎታለሁ። ጥቅምት ፳፩ ቀን ፲፱፻፴፫ ዓ.ም. ጸገደ። ፊርማ፣ ደጃዝማች አዳነ መኰነን።” ገጽ 167

“ገዳሪፍ፣ መስከረም ፲ ቀን ፲፱፻፴፩ ዓ.ም. ይድረስ ለክቡር ደጃዝማች ሕይወት መሸሻ፣ ትግሬ። እንደምን ከርመዋል ለጤናዎ? እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን እኔ ደህና ነኝ። የእርስዎ ብርታትና ትልቅ ጀግንነት በዓለም ሁሉ በመሰማቱ እድልዎ ከሁሉ ያማረና ታሪኩዎም የበለጠ መሆኑን አስቀድሜ አረጋግጥለዎታለሁ። ግርማዊ ጃንሆይም ብዙ ጊዜ ድህንነትዎን ጠይቀው ጽፈውልኛል፤ ስለዚህ በሕይወት የመኖርዎን ምልክት ደብዳቤ ይጠብቃሉና በቶሎ የሁሉን ነገር ገዳሪፍ ድረስ በኔው ስም ቢልኩት ይደርሳቸዋል።” ገጽ 167

በድፍን ኢትዮጵያ ያለውን ጣሊያን በያለበት መከበቡን፣ መሞቱን፣ በከንቱ ማለቁን የዓለም ሕዝብ በብዙ ያደንቃል። በአውሮጳም ታላላቆች መንግሥታት ጋራ በቅረብ ቀን ለጦርነት ውጊያ ለመግጠም ተፈራርሟል። አስቀድሞም በሀገሩ በረኃብና በእስፓኛም ጦርነት ብዙ ሺህ ሰው ሲሞትበት መሣሪያም አልቆበታል። ስለዚህ ጣሊያን ከኢትዮጵያ ፈጽሞ በፍጥነት መውጣቱንና የነፃነታችን ቀን በርግጥ መድረሱን አይጠረጠርምና ለሕዝባችን አስተካክለው ያስረዱት። በሞኝነቱ የጠላቱ ረዳትና ደም ከፋይ እንዳይሆን ያበረታቱት፤ ይምከሩትም።” ገጽ 167

“፪ኛ ጀርመንና ቺኮስሎቫኪያ ጦርነት ገጥመው ኤውሮጳ በነሱ ምክንያት ብርቱ ፍራትና መንቀጥቀጥ፣ ሞትና መደበላለቅ ተነስቶበታል። በበጌምድርና በጐጃም፣ በሸዋና በሐረር፣ በለቀምትና በጅማ፣ በሲዳማ፣ በወሎና በሰቆጣ፣ በሺረ፣ በአድያቦና በሰቲትም በያለበት ጣሊያን ተከቦዋል። ከብዙውም ቦታ ለቆዋል። የቀረው በምሽጉ ውስጥ ብቻ ነው ይባላል። ሁሉም ነገር አጣርተው በፍጥነት ደብዳቤዎን ይላኩልን። በሕይወት፣ በደስታ በእግዚአብሔር ያገናኘን፤ አሜን። ፊርማ፣ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ። ገዳሪፍ፣ መስከረም ፲ ቀን ፲፱፻፴፩ ዓ.ም.።” ገጽ 168

“ለክቡር ካህና ኣባ ጨርቆስ፤ ሐውሣ። ዛሬ የመጣልኝ ሐዲስ የምስራች። የጄኔራል ባዶሊዮ ወንድም የ፲፮ በጦሎኒ አለቃ ሆኖ የዘመተ በባህር ዳር ዘጌ ሲሄድ በጥይት ቆስሎ ሞተ፤ ሰዎቹም አለቁ፤ ሱዳኖች ግን አምልጠው ኣየበረሩ እብድ ሆነው አገራቸው ገብተዋል። እንግሊዝና ፈረንሣዊ፣ መስኮብና አመሪካን የኢትዮጵያን መንግሥት ረዳቶች ሆነዋል፤ የጉባኤው ስብሰባ መስከረም ፲፪ ቀን ነው- የኢትዮጵያ ጉዳይ ነገር የሚፈጸምበት።” ገጽ 168

ክቡር ሆይ፣ ባጭሩ ቃል ጠላታችን ጣሊያን አልቆዋል፤ ከሀገሩም ጦር መጨመር ምንም አይችልም። በኤውሮጳ ትልቅ የጦርነት ቃጠሎና ድብልቅልቅ ያለ ብርቱ ውጊያና ልቅሶ ደርሶበታል። የኛ የኢትዮጵያውያን ደስታ ግን ቀርቦዋልና ሕዝቡን ያጥናኑት፤ ይምከሩት። ፊርማ፣ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።” ገጽ 168

“ይድረስ ለክቡር አቶ ተስፋሚካኤል። እጅጉን እንደምን ሰንብተዋል? ባለቤትና ልጆችዎስ እንደምን ሰንብተዋል። እኔ እግዚአብሔር ይመስገን ደህና ነኝ። እስከ ዛሬ ድረስ እዚህ መኖርዎን ሳላውቅ ወደ ካርቱም ወረቀት ጽፌለዎ ነበር፤ መድረሱን አለመድረሱን አላውቅም። ኃጢያታችን ቢበዛ ለአረመኔ አሳልፎ ሰጠን፤ አሁን ግን ይቅር ሊለን ነውና ለሀገርዎ ምሕረት ያብቃዎት። ሰላመ እግዚአብሔር ከነቤተሰዎችዎ ይጠብቍዎት አውሳ ጥር ፲፩ ቀን ፲፱፻፴፩ ዓ.ም. ፊርማ፣ ኣባ ጨቆስ።” ገጽ 168

ይድረስ ለክቡር ርእሰ መኳንንት አቶ ተስፋ ሚካኤል እንደምን ሰንብተዋል ለጤናዎ? እግዚአብሄር ይመስገን እኔ ደህና ነኝ፤ ደብዳቤዎም ደረሰኝ፤ እግዚኣአብሔር ይስጥልኝ፤ ስለ የ፲፫ ት ሰዎች ነገር ስለጻፉልኝ። ሰው ለሃይማኖቱ ብሉ የደከመ እንደሆነ ከሰው ባያገኘው ከእግዚኣብሔር ያገኛል። አሁንም እርስዎ ለስደተኞች ብለው የለፉት፣ የደከሙ እንደሆነ ከእግዚአብሔር ዘንድ ያገኙታል። እኔም እንደ አቅሜ ስለ ሃይማኖትና ስለ ስደተኞች ብዬ የላኩኝን ሁሉ እፈጽማለሁ። በደህና ለመውጣቴ ለጃንሆይ ቢያመለክቱዋቸው ደግ ነው፤ ይቤ ታዛጅዎ። ኃደሊያ ሚያዝያ ፰ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ፊርማ፣ ቀኛዝማች ዓምደ ማርያም ተስፋ ጽዮን።” ገጽ 169

“ካርቱም መጋቢት ፳፩ ቀን ፲፱፻፴፩ ዓ.ም. ይድረስ ለክቡር አቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ። እጅጉን እንደምን ሰንብተዋል? እኔ እግዚአብሔር ይመስገን ደህና ነኝ። ባለቤትዎ በደህና ካርቱም ደርሰዋል። ያመጡትም ደብዳቤ ደርሷል፥፡ ወደ ባለቤቱ አስተላልፌ መላኬ ነው። ከወገራ የመጣው ደብዳቤ ደርሶኛል። ነገር ግን በፖስታ የማይላክ ዋና ፖስታ አለ ብለው በደብዳቤ ያስታወቁኝ ገና አልመጣልኝም። የታመነ ሰው ሲገኝ እልክልሀለሁ ብለውኝ ነበርና እጠብቃለሁ። ለባለቤትዎ ቢልኩልኝ ኖሮ ደግ ነበር። ለወደፊት ግን አቶ እሸቴ የመጣ እንደሆነ ለርሱ ይላኩልኝ። እርሱ ግን ካልመጣ እኔ ከዚህ ሰው መላኬ አይቀርም። ይህ ነገር በጣም ጥንቃቄ የሚያስፈልግ ነው። ላቶ አብርሃ ሰላምታዬን እንዲነግሩልኝ እለምነዎታለሁ። ጤና ይስጥዎ። ፊርማ ወዳጅዎ ዳባ ብሩ።” ገጽ 169

በቀጣዩ የምዕራፍ ሠላሳ ስድስተኛ ምዕራፍ ትረካቸው፡ አርበኛው ተስፋ ሚካኣኤል ትኩእ ኬኒያ ከነበሩ አርበኞችና ስደተኞች ጋር የተጻጻፏቸውን ደብዳቤዎች ለመታሰቢያነት እንቃኛቸዋለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 31 Jan 2020, 04:35

ከኬኒያ አርበኞችና ስደተኞች ለአርበኛው ለተስፋሚካኤል ትኩእ የተጻፉ ደብዳቤዎችን ለመታሰቢያ ከታተሙት ውስጥ ለዛሬ ይህችን መርጠናል። ይህችን ዘለግ ያለች ደብዳቤ የጻፈው “ተስፋም እንዳለን ከዚህ ሁሉ አንድ ጥቅም እንዲወጣበት ብዬ ነው ከሥሩ እስካናቱ የምወዝፍበዎት ያለሁ።” እያለ ያለ አንዳች መግደርገር ሃሳቡን ለአርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ የዘረገፈላቸው አርበኛ እንድርያስ አውዓሎም ነው። የዚያን ዘመን ቦለቲካ ለመገንዘብም እንችል ዘንድ ሳንሸራርፍ እንዳለ እዚህ አቅርበነዋል። መልካም ንባብ። :mrgreen:

“ኬኒያ ኢሲዮሎ፣ ነሐሴ ፲፭ ቀን ፲፱፻፳፱ ዓ.ም። ይድረስ ለክቡር አቶ ተስፋ ሚካኤል፣ አስቀድሜ ለክቡርት ባለቤትዎና ልጆችዎ፣ ለክቡራን የኢትዮጵያ ስደተኞች እጅ እየነሣሁ የማክበር ሰላምታዬን አቀርባለሁ፤ እገደድማለሁ። ወንድሜ ሆይ ስለሀገራችን ነፃነትና ስማችን ክብረት ምንም እንኳ ሕይወታችንን ሳንሳሳ፣ ገንዘባችንንም ሳንቆጥብ፣ ሌትና ቀን ሳንቦዝን ብንሠራ፣ የአምላክ ፈቃድ ሆኖ የጉልበታችንን መመንመንና የገንዘባችን መባከን፣ እንዲሁም የጥይቶቻችንና መሣሪያችን መጉደል፣ የአዛዦች ስምምነት ማጣት የጦርነቱ ዓቅድ እየፈረሰብን በመሔዱ፣ እኛ እንደ ትንኞች፣ ጠላት እንዳጥቂ ያላንዳች ጉልበት እየረገጠን ሲወዛወዝ እያየሁ ደም እያለቀስሁ ብዙ ቀን በማኸከሉ መጓዜን ሰምታችሁት ይሆናል። መጨረሻ ተስፋዬንም ለማስተካከልና የዓቅሜን ያህል ለመሥራትም ከጦር ጓደኞቼ ተለይቼ የቀረሁበት ምክንያትም ክቡር ፊታውራሪ ዘውዴ አየለን ምንም እንኳ ለመዋጋት ቢቆርጡም፣ በጣም አንቀላፍተው፣ ጠጅ ከመጉመጥመጥና ጮማ ከመቁረጥ የሚለዩ አይመሥሉም ነበርና በምክር እየረዳሁ ላንቀሳቅሳቸው በማለት ነበር።” ገጽ 170

እሺ ነገ ሣልስት ሲሉም አንድ ሥራ ሳንሠራ እከተማው እንደተቀመጥን በ፭ት ማዕዘን ሊከበን ሲሆን ጊዜ ሰልፍ በሳሳበት ጥሰን ለመውጣት ግድ ሆነብን። የገደልን ገድለንም አንድም ሰው ሳይቆስልና ሳይሞትብን እስከ ሰላሳ የሚሆን ብረት ማረክን። እግዚአብሔር እንደሚጠብቀን በዚህ ብቻ ያስረዳል። ዳሩ ግን ፊታውራሪ ዘውዴ ሥልጣናቸውን ሳያውቁ ኖሮ የሚገብርላቸውንና የሚያውቁትን ሀገር ጥለው ወደ ሌላ ሀገር ለመጓዝ ባሰቡ ጉዜ ጠላት ለማጥቃት የምንችልበት ሀገር ይህ ነው፤ በተቀረ እንደገና ሌላ ሀገር አቅንተን ጠላትን የምንወጋበት የምናገኝ አይመስለኝምና የእንግሊዝ ጠረፍ ተጠግተን በውኃ ብቻ እንዳምጠዋለን ብዬ ኅሳቤን ባካፍላቸው ማንስ ይቀበለኝ? ግዱን ቫኮን ታልተሻገርነ ሲሉ ጊዜ እኔ የዘንድሮ በሽታና መታረዝ አመንምኖኝ ልታከም ወደ ጠረፍ ለመጓዝ ግዜየ ሆነብኝ። ስመጣም ትንሽ ተስፋ ያደረግሁት ምናልባት የልጅ ኢያሱ ልጅ በፊታውራሪ ዘውዴ እጅ ታሥሮ የነበረ ያመለጠ እንደሆነ የኢትዮጵያ ወጣት ሳያብርለት አይቀርም፤ መጨረሻውንም ሳላይ የመጣሁትም በመታመሜ ነው እንጂ ብርቱ ልጅ ነውና መከተሉ እንደማይከፋ ተረድቸው ነበር። በተቀረ ፊታውራሪ ዘውዴ ከተራ ወታደር አፈጮሌነት በቀር ሕዝብና ወታደር በሚገባ ለማስተዳደር የሚያዛልቅ ልቦና የላቸውም፤ የዋህ ናቸው። ፯፻ ብረት ያህል ይዘው አንድም ሥራ ሳይሠሩት ይዘውት ሄዱ፤ በትኩሱ ያልሠራ ለወደፊት እንደማይሰራ ተረድቸው ተሰናበትሁ። እዚሁም በጠና ታምሜ ዳንኩ፤ ከሞት ተረፍኩ። ከ ፭፻ የሚበልጡ የሀገራችን ልጆች ኢትዮጵያን ፍለጋ ከሕዝቡ ጋራ ደባልቀውን በደኅና እንኖራለን፤ ዳሩ ግን ሲጋራ እንኳ ለመግዛት ስንወጣ በዘበኛ ነው የምንወጣው።” ገጽ 171

“ከአሁን በፊት ተስፋ ቆርጠው ከዚሁ መከራ ሞት ይሻለናል ብለው ቢሄዱ እመንገድ ደርሰውባቸው ገሚሱን ገደልዋቸው፣ የቆሰሉትን ደግሞ ይዞዋቸው መጡ፤ የበሽተኛ ምግብ እንኳ አይደረግላቸውም። ዳግም ወታደሩ የሚሠራው ሥራ ውኃ መቅዳትና የምጣድ እንጨት ሰበራ ነው፤ በየጊዜው ለሚበላሽ የሣር ቤታቸውንም ያሳድሳሉ። የሚበልጡት ዕድሜያቸው ከ፴ ዓመት በታች ነውና ለወደኋላ የሚረባ ጥበብና ሥራ ለመማር የሚችሉ ነበር፤ ዳሩ ግን አስተካክሎ የሚያስብለትና የሚያስታውስለት ጠፍቶ በከንቱ ጉልበቱን አእምሮው ተለውጦ በማንም ዘበኛ እየተደበደበ ለወደፊት እርባታ የለውም። ስለዚህ እኔ የምለምንዎ፣ ይኼንኑም የምጽፍልዎ ልመና በእንግሊዝ አስተርጉመው እንዲልኩልኝና እዚሁ ላለው የእንግሊዝ መንግሥት እንደራሴ አመልክተን እንኳ ተስፋ ብናገኝ ፩ድ ጥቅም ነው። በየጊዜው የምትጽፉትን እያየሁ በጣም እጽናናለሁ። ደግ ነው፤ ወሬ ብቻ አይበቃምና እዚሁ ላለው የኢትዮጵያ ሕዝብ እፃዕረሞት ድረስ ደርሶዋልና ከአሁን ኑሮው ትንሽ እንዲሻሻል የሚቻል እንደሆነ የሚያስረዳ ነገር ከእናንተ እጠባበቃለሁ። የወንድሞቼ ጥቃትና ውርደት በልቦናዬ ገብቶ እየሞረሞረኝ ሌትና ቀን እንቅልፍ ስለሚያሳጣኝ እርስዎንም እንቅልፍ እንዲያጡበት ብዬ ነው ማመልከቴ። ” ገጽ 171

“አቶ መኰንን ሀብተ ወልድ ያሉበትን አገርና አድራሻ እንዲጽፉልኝ አደራ። ታናሽ ወንድምዎ ልጅ ጳውለሥ በመስከረም ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. በጉራጌ ሀገር የጉምሩክ ጸሐፊነት ሊሠራ ተሰናብቶኝ እንደሄደ ከዚያ በኋላ አላየሁትም። ተገናኝታችሁ ይሆን? ብላታ ገብረዝጊ ከብላታ አየለ ስብሐት ጋር በዓጋሜ በኩል ዘምተው እንደሄዱ ወሬያቸው የለንም። ባለቤታቸውና ልጆቻቸው ግን አዲስ አበባ ላይ በደኅና ትቻቸው ነበር፤ ልጅ ገብረ መስቀል የመዋቹ ያቶ ወልደ ማርያም ታናሽ ወንድምም ከክብር ዘበኛ ጋራ እንደዘመተ ወሬው እንደጠፋብኝ ነው። ዳግሞ ትንሽ ልውቀስዎ እዚህ መግባቴን እያወቁ ብጣሽ ወረቀት እንኳ የነፈጉኝ በሥጋ ዝምድናችን ለመቁጣጠር ባልችል፣ በገር ልጅነት የአሁኑ አኳሆናችን ልንጠያየቅ የሟስገድደን አይደለምን?” ገጽ 172

እኔ ወንድምዎ ግን ውለታ የሚቆጥርልኝ ቢጠፋ ነው እንጂ የሠራሁት ሥራ ትንሽ አልነበረም፤ የሚመሰክሩልኝ የጦር ጓደኞቼም አብረዋችሁ ናቸውና ወዳጅነቴንና ዝምድናዬን የሚያስጠላ ዝና የለኝም። ከ፴፰ቱ የጥቁር አንበሳ ማኅበር አማካሪዎች እመጨረሻ ደረጃ እስቲደርስ የሠራና ብቻውን የቀረ ማለት እኔ ነኝ። ክቡር ራስ እምሩ እንደተያዙም ከሞትና ከመታሰር ማምለጤን ከተረዳሁ በኋላም ከሳቸው ጋራ ለመገናኘትና ትእዛዛቸውን ለመፈፀም ብዬ በጣሊያን ወታደር መካከል መግባቴን ግን ዕድሌ ከፍቶ አገስግሶዋቸው (አሸሽቷቸው) ቆየ፤ ለዚሁም ምስክሩ እነልጅ አማረ ፍስሐና ልጅ አምባዬ፣ አቶ ገብረ ትንሣኤ ዑቁበና አቶ ተክለ ዑቁበ አፈልባ ናቸው። እነሱም እጅግ ጀግኖች ናቸውና በሚቻላችሁ እንድትረዱዋቸው አደራ። እስካሁን ሳልጽፍ የቆየሁት ምክንያት ሥልጣናችሁ እስከ ወዴት እንደሚደርስ ለማወቅ ስል ነው። ይኸንኑም ከግርማዊ ተስፋ እንዳላችሁ ስለተረዳሁት እንድትቸገሩልን፣ መከራችንንም እንድትካፈሉ ብዬ ነው። ”ገጽ 172

ያገር ወሬ በኢትዮጵያ ውስጥ ያለመተማመንና ማጋለጥ እየበዛ፣ ወደረኛ የሌላቸው ግን ጀግኖችዋን ያለታሪክ ደማቸውን ከማፍሰስ አላቋረጡም። ይህም ርግጥ መሆኑን ከክቡር ራስ ደስታ ጋር የነበሩት የቀኛዝማች ሰለባና የቀኛዝማች ገብራይ፣ ከፊታውራሪ ጸጋይ ጋር አብሮዋቸው የነበሩ ጭፍሮቻቸው ፲፭ ሰዎች መጠተው የመሰከሩት ቃል ይስሙ። ”ገጽ 172

ክብር ራስ ደስታና ደጃዝማች ገብረ ማርያም በየቀኑ እየተዋጉ እስከ ከምባታ በደኅና መድረሳቸው ሲያረጋግጡ ከዚያ በኋላ ግን ትልቅ ጦርነት ስለገጠማቸው በየተሠለፉበት እንደተለያዩ ሳይገናኙ እዚህ ድረስ ስለመጡ አንድም ቁጥር እንደያዙ ዓሩሲ ድረስ መጥተው ካንድ ረጅማ (ሬጅሜንት) ሙሉ ገጥመው ፫ት ቀን ሙሉም ስፍራ ሳይለውጡ እዚያው እየተዋጉ ስማቸውን እንደተከሉ ሞቱ። ”ገጽ 172

ፊታውራሪ ኃይሌ አባ መርሣ የሚባሉ ዱሮ የአልጋ ወራሽ አሸበርም ጄነራል ማልታ አንድ ድቪሲዮን ጦር ይዞ እንደገጠማቸው ድል አድርገው ምርኮ እንደጀመሩ በእጅ ቦምብ ቆስለው በጐራዴ እንደቀነደቡት ደጄን አጥተው ማልታን ገድለው ሞቱ። የቀሩት ሰዎቻቸው ድል ሆነው በየጫካው ገቡ ይባላል።” ገጽ 173

“ባሻይ ይመኑ የአራዳ ዘበኛ ያንደኛ ኮማሳርያ የሺ አለቃም ከ፬፻ ወታደሮች አንድ ቀን ሙሉ እንደተዋጋ ሦስት ላይ ቆስሎ፣ ወታደሮቹን አደራርቦ፣ ምትርየሱኡን እንደተንተራሰ፣ ስሙን ለታሪክ ትቶ ከዚህች ዓለም ተሰናበተ። ሶስቱም በማረግ የተቀበሩ ናቸው።” ገጽ 173

በጅሮንድ ፍቅር ሥላሴ ከተማ ግን ለጠላት ለመገበር ሊገባ ባሰበ ጊዜ ጉዱ ተገልጦበት የኢትዮጵያ ወጣቶች እነ ጀግናው ቀኛዝማች ሰለባ ወደ ጠላት አትሄድም ሲሉ ጦርነት ገጥመውት ፭፻ ከሚሆን ወታደር ተጋድለው፣ ብጅሮንድ ፍቅረ ሥላሴን ወርሰውና በሕይወቱ ሳለም ማርከው ሊፋረዱት ሶስት ቀን በቁራኛ እንዳጓዙት አምልጦዋቸው እራቁቱን ወደ ጣሊያን ገባ። ቀኛዝማች ሰለባና ቀኛዝማች ገብራይ ፩ድ ክፍል፣ ፊታውራሪ ጸጋይና ቀኛዝማች አስፍሐ ፩ድ ክፍል ሆነው የክቡር ራስ ደስታን ትእዛዝ ኣየፈጸሙ ይሠራሉ ይባላል፤ መጨረሻውን እግዚአብሄር ያብጅላቸው። ጣሊያን ግን የጦርነት አቅድዋ ስለሚበላሽበት ያመኑዋትን ድሆችና ገበሬዎች፣ ሴቶችና ህፃኖች በየሣርቤታቸው በሩን እየዘጋች በእሳት ከማቃጠል ኣላቁረጠችምና የኢትዮጵያን ሕዝብ ለማውደም ያሰበች ይመስላል። ጀኔራል ግራሲኒን ለመግደል አንዱ ጀግና ቦምብ በተኰሰበት ጊዜ በአዲስ አበባ የነበረ ወንድ ልጅ ሁሉ ያለ ምሕረት እንዲገደል ስላዘዘ ለ፫ ሰዓት ወታደሮቹ ያገኙትን ያህል ገደሉ ይባላል። ዓለም ጥፋታችንን የፈቀደ ይመስለናል እንጂ ከቶ የምንድንበትን አይመክርም። ፊታውራሪ ዘውዴ ወታደሮቻቸውን ማዘዝ ቢያቅታቸው ይመስለኛል ለብቻቸው ከሌሎቹ የዓቅማቸውን ያህል ሥራ ሠርተው ከመጡት ጋር ተደባልቀው እኛ በመጣነበት መጥተዋል ይባላል። ርግጥም ነው፤ ጽፌላቸው አለሁና መልሱን እጠብቃለሁ።” ገጽ 173

“አሁንም በሞያሌ በኩል ብዙ ሰው ወደ ኬኒያ ገብተዋል፤ በቅርብ ቀን እዚሁ ድረስ ይገባሉና እንደገቡ ኣኳሆናቸውን አረጋግጩ ልጽፍልዎት እችላለሁ። የኣዛዥ ወርቅነህ ልጆች ልጅ ዮሴፍና ልጅ ቢንያምም ከብዙ ጄግኖችና ከክቡር ራስ እምሩ ጋር ማምለጫ በሌለበት ጠባብ ቦታ ላይ በጌራ እጃቸውን ሰጡ። ሎንዶን ካለው ከክቡር የኢትዮጵያ መንግሥት እንደራሴ ጋራ በማሕበራችን ስም ለመላላክ ሥልጣን የነበራቸው እነሱ ነበሩና የተቸገራችሁ እንደሆነ የገነት መኰንኖችና የኤርትራ ልጆች በኬኒያ ኮሎኒ እንድትገቡ ፈቃድ ሰጥናችኋል የሚል የክቡር ኣዛዥ ወርቅነህ ጽህፈት መኖሩን አውቅ ነበር። ይህንነም የፈቃድ ወረቀት በእነሱ እጅ ስላለ እኛ እዚሁ ስለአንዳች ቁም ነገር አልተቁጠርንም። ከዋና ማህበርተኛ ፫ት ሰዎች እዚሁ ደርሰናል። እኔ አቶ ተኩሉ ዘዋበና አቶ ሙሴ ብርሃን ነን። ከማህበሩ ወታደርቱም እስከ ፴ እንሆናለን። እስካሁን ድረስ ያመለከትነው ነገር የለም፤ ምክንያቱም ካገራችን መንግሥት ባለሥልጣኖች ባለማግኘታችን ነው። ተስፋም እንዳለን ከዚህ ሁሉ አንድ ጥቅም እንዲወጣበት ብዬ ነው ከሥሩ እስካናቱ የምወዝፍበዎት ያለሁ።” ገጽ 174

“ብላታ ወልደሚካኤል ተፈሪና ገብረእግዚአብሔር፣ ልጅ ሺፈራው ገብሩና ልጅ ገብረ ማርያም አብረውን አምልጠው ነበር። ዳሩ ግን የመንገዱን ችግርና መታረዝ ጠልተው ሞት ይሻለናል ሲሉ ተመልሰው ወደ ቦንጋ ከተማ ገቡ፤ ከዚያ ወዲህ ወሬአቸው የለኝም። ባሻይ ዑቁባ ሚካኤለ ገብረ አኩሩር ቦንጋ ቀሩ። በብዙ የሚናፍቅዎ ወንድምዎ፣ ዘመድዎ። ፊርማ፣ እንድርያስ አውዓሎም አሰጣህ መረታ ሰበነ።” ገጽ 174

በቀጣዩ ክፍል፡ ኬኒያ ከነበሩ አርበኞችና ስደተኞች ከነ ሙሴ ብርሃነና እንድርያስ ዘርኤ እንዲሁም ጠቅላይ ሹም ባሻይ ረዳ ተክለ፡ ለአርበኛው ተስፋ ሚካኤል ትኩእ የተጻፉ ደብዳቤዎችን ለመታሰቢያነት እንቃኛቸዋለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው። :mrgreen:

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 13 Feb 2020, 09:57

በዚያ ቀውጢ የፋሺስት ጣሊያን የወረራ ዘመን ኬንያን ምን ያህል ኤርትራዉያንና ኢትዮጵያዉያን ስደተኞች አጥለቅልቀዋት እንደነበር በዚህች አርበኛው አቶ ሙሴ ብርሃነ ከኬንያ ለአርበኛው አቶ ተስፋሚካኤል ትኩእ ካርቱም ከላኩዋት ደብዳቤ መገንዘብና የዚያን ዘመን የፖለቲካ ትኩሳት ለማጤን ይቻላል። የታሪክ ተመራማሪዎች ታሪክ እስኪጽፉልን ብንቆይ ኖሮ ይህን የመሰለ ብርቅ እውነታን ያካተቱ መጸሐፍትን ይህ ትውልዳችን ለማግኘት ባልቻለ ነበር ለማለትም ይቻላል፣ ለማንኛውም የአርበኛውን ደብዳቤ እነሆ ብለናል፡ ኩምኩሙ! :mrgreen:

“ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ፡ ከዘመነ ማቴዎስ ወደ ዘመነ ማርቆስ ከነ ባለቤትዎና ከነ ልጆችዎ እንኳን እግዚአብሔር አሻገረዎ። በፈረንጅ ቁጥር በ፳፰ ቀን ነሐሴ አቶ እንድርያስ ዘርኤም የጻፉልኝ መልእክት ደረሰኝ። ክቡር ደብዳቤዎን በመጀመሪያ ዓመት በቅዱስ ዮሐንስ ቀን ከምህልላ በኋላ ለስደተኞቹ ሁሉ አንብቤላቸው ልክ የሌለው ደስታና ተስፋ አድርገው ሀገራቸው የገቡ እንጂ በኬኒያ ስደት ተሰደው ያሉ አልመሰላቸውም ነበር። ችግራችን ሁሉ ወደ ጃንሆይ ስላመለከቱልን ምስጋናችንን እናቀርብለዎታለን።” ገጽ 174

“ያገራችንን ነገር፣ የሀገራችንንም አስተዳደግና አስተዳደር ከኔ ይልቅ እርስዎ ያውቁታልና እኔ ሁሉንም አንድ ላይ ከመሰብሰብና ስምምነትም እንዲያደርጉ ከመምከር እዚህ ከመጣሁ ጀምሬ አላቋረጥሁም። ከሁሉም የበለጠ የርስዎ መልእክትና ጃንሆይም በሕይወት መኖራቸው ስለተመሰከረ እኔ እነሱን ለማስማማት አንድነትም ለማድረግ ለመምከር የሚረዳኝ ስለሆነ የተገኘውን በወሬና የጃንሆይን ቃል ሲገኝ ወደኔ ቢጽፉልኝ መልካም ነበር። እነሱ ከዚህ በፊት እኛ ሳንመጣ ተስፋ በማጣትና በሚያገኙትም መከራና ጭንቅ ስምምነት ፈጽመው አጥተው፣ ተበላሽተው ነበር፤ አሁን ግን በእግዚአብሔር ፍቃድ ደህና ናቸው። ስምምነት አጥተው ነበር ያልኩትም በሌላ ነገር አይደለም፤ የኢትዩጵያ መንግሥት ጥፋትና ወዳሰቡትም ባለመድረሳቸው፣ ጥዋትና ማታም እዚህ ባለው የእንግሊዝ ጠባቂያቸው ጩኸት በመቅረባቸው እንዲህ ሆነን ከመኖር እንጥፋ፣ እንደምንም ብለንም ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰን ወደ ራስ ደስታ እንግባ ሲሉ ነው።” ገጽ 174

የራስ ደስታ ክፍለ ሀገር በጦርነት ተለይተው የነበሩ የሃማሴን ሰዎች ፻ ገብተዋል። ቀኛዝማች ገብራይም ኬኒያ ገብተዋል፤ ነገር ግን በብርቱ ታመው ገና ወደኛ አልደረሱም። ቀኛዝማች ጸጋይና ብዙ በራስ ደስታ የተሾሙ ቡሉቅባሾችና ሙንጣዞች ሞቱ፤ ቀኛዝማች ሰለባና አቶ ገብረ መድኅን ዘጉ ከነሚስቱ፣ አቶ ዮሐንስ አሊ ከነ ሚስቱና አፈወርቅ፣ የሐረር ቁንሱል አነጋጋሪ የነበሩ አቶ ተስፋ ማርያም ገደላ ከብዙ አማራ ወታደርና ፻፩ የኤርትራ ሰዎች ጋር ሆነው በረሃ ይጄ ገብቼ እዋጋለሁ ብሎ ቀረ፤ ያለበትን አናውቅም። ከራስ ደስታ ጋራ ከነበሩ ኤርትራዎች ውስጥ መሞታቸው የታወቀ ፻፫ ሰዎች መሆናቸውን ርግጠኛ ወሬ አግኝተናል። ሞታቸው ያልታወቀ ኤርትራዊያን ግን እጅግ ብዙ ናቸው። ቀኛዝማች አሰፋ ባህታ ግን ሞተዋል። አሁን በኬኒያ አገር የኢትዮጵያ ስደተኞች ሆነን የገባን ኤርትራዊያን ብቻ ድምር ፯፻፸፭ ሰዎች ደርሰናል።” ገጽ 175

የደጃዝማች ወልደማርያም፣ የፊታውራሪ ዘውዴ፣ የፊታውራሪ ታደመ፣ የልጅ ኢያሱ ልጅና የወይዘሮ ቀለመወርቅ ሰው፣ ልጅና ወንድ ሴትም የስደተኞች ድምር ፰ ሺ፪፻ ሰዎች ናቸው።” 175

እኒህ ከዚህ በላይ የተጠቀሱ ሰዎች የጣሊያንን ብረትና መድፍ ማርከው ብዙ ልፋት ከለፉ በኋላ በጋዝ መርዝ ሲያስቸግራቸው ጊዜ የገቡ ናቸው። የራስ ደስታ ወሬ ግን ምንም ርግጠኛ አጣን። ደጃዝማች ገብረማርያም ደጃዝማች በየነ ከራስ ደስታ ጋር ባንድ ላይ ናቸው ይሉናል፤ በጣሊያን እጅ እንዳልተያዙ እናውቃለን፤ የት ሀገር እንደሆኑ ግን አይታወቅም።” ገጽ 176

“ማርሻሎ ግራሲያኒ ሞተዋል የሚል ወሬ ሰምተናልና ርግጠኛውን እርስዎ ሳያውቁት አይቀሩምና ሞቱ ርግጥ መሆኑን እንዲያስታውቁን እለምንዎታለሁ። ልጅ ኃይለ በየነም ትንሽ ወረቀት ወደ አቶ ገብረ መስቀል ጽፎ ነበርና የሱን መሰል ሲመጣ በፍጥነት ይላኩልኝ ሲል ይለምንዎታል። ፊታውራሪ ዘውዴና ወይዘሮ ቀለመወርቅ ከነሰዎቻቸው በቅርብ ቀን ወደኛ አጠገብ ተዛውረዋል። ግን ለመገናኘት ገና እንግሊዙ አልፈቀደልንም። እነሱም ብንጽፍላቸው መልስ አላገኘንም። ወይዘሮ ቀለመወርቅ ግን ወደባላቸው ኢየሩሳሌም ሔደዋል ይሉናል፤ ርግጥ ሳይሆን አይቀርም።” ገጽ 176

“በመስከረም ፲፪ ቀን የተደረገውን ፍርድ በፍጥነት እንዲጽፉልን እንለምንዎታለን። እዚህ በኬኒያ ያሉት ፯፻፸፭ የኤርትራ ልጆች ሰላምታቸውን ያቀርባሉ። ለወይዘሮ ቀደስና ለአበባ፣ ለፀሐይ ሰላምታዬን ይንገሩልኝ። ነሐሴ ፪ ቀን ፲፱፻፳፱ ዓ.ም. ኬኒያ፣ ኢሲዮሌ። ፊርማ፣ ሙሴ ብርሃነ” ገጽ 176

በቀጣዩ ክፍል አርበኞቹ እንድርያስ ዘርኤና ጠቅላይ ሹም ባሻይ ረዳ ተክለ ከኬኒያ ወደ ተስፋሚካኣኤል ትኩእ ካርቱም የጻፉትን ደብዳቤ እንቃኛለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 26 Feb 2020, 07:58

ለዛሬ አርበኞቹ እንድርያስ ዘርኤና ጠቅላይ ሹም ባሻይ ረዳ ተክለ ከኬኒያ ወደ አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ ወደ ካርቱም የጻፉትን ደብዳቤ ይዘት እንቃኛለን። መልካም ንባብ! :mrgreen:

“ይድረስ ለክቡር አቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ፤ እጅግ ለጤናዎ እንደምን ሰንብተዋል? እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን እኛ ደህና ነን። በየጊዜው የሚጽፉልኝን የተስፋ ደብዳቤ እያየሁ፣ ወንድሞቼ ጭምር በጣም እናመሰግንዎታለን። እዚህ ከመጣንም አንዳች የተስፋና የርዳታ ነገር በማንም በኩል አልደረሰልንም፤ ለሁሉም ነገር እርስዎ እንዲበረቱልን በማለት ቀጥዬ ላመለክተዎ አሳሰበኝ። ከእሁን በፊት በነሐሴ ፲፭ ቀን በልጅ እንድርያስ በኩል የጥቃታችንና የጉልበታችንን ያለጥቅም ከንቱ ድካም መድከም ለእንግሊዝ መንግሥት ማመልከቻ (ማስገባታችንን)፣ ዳግም በመስከረም ፩ ቀን ግርማዊ ጃንሆይ ነገራቸው እንዲያልቅልንና እኛም በቅርብ ቀን ልናያቸው መጓጓት ቃሌና የወንድሞቼን ጥብቅ ኅሳብ መሆኑን እንገልጽልዎታለን። ለእንግዲሁም እዚሁ ላሉት ፭፻ የኤርትራ ተወላጆችና የኢትዮጵያ ልጆች ኃላፊነቱ በኔ ስለሆነ ለሚያስፈልገን ነገር ሁሉ ሳመለክት በልጅ እንድርያስ ዘርኤ ጸሐፊነትና በኔ ፌርማ ለመላክ ቆርጠናል።” ገጽ 176

“በግርማዊና በባለሥልጣኖች ለሚመጣልን ነገር ሁሉ እንዲተጉልንና እንዲጭርሱልን ስል እምነቴንና ልመናዬን አስቀድሜ አረጋግጥልዎታለሁ። ለዚህ ሁሉ ከአሁን በፊትም ሰብሳቢያቸው ሳልሆን፣ ሳላስበውም ቀርቼ አይደለም፤ ዳሩ ግን ኅሳቤንና እምነቴን ለብቻዬ ሳይሆን ለሞላው ሕዝብ ጥቅም ወይም ጥፋት እንደሚያመጣ እየተሰማኝ ከማንም ለመጻጻፍ አልፈቀድሁም ነበር። ምክንያቱም ከኔ ይበልጥ የዘንድሮን ነገር እርስዎ ያውቁታል፤ ለመጠንቀቂያ የሚያስፈልገኝን ሁሉ ባቶ ተኩሉ ዙዋበና በልጅ እንድርያስ፣ በልጅ ሙሴ ስለተረዳሁት ለማናቸውም ነገር በእርስዎ በኩል እንዲፈጸም እደፍራለሁ። ስለዚህ ፖለቲካችን እንዳይፈርስብን መጠንቀቅ ያስፈልጋል። ከብዙ ስንዴ አንድ እንክርዳድ የተገኘ እንደሆነ ዋጋ እንደሚያፋርስ፣ እንዲሁም በማይረባ ሰው ነገራችን እንዳይበላሽ ላስጠነቅቅዎ እገደዳለሁ። አንዳንድ ሰው ከዚህ ካለንበት ስፍራ ወደ ማንም እየተጻጻፉ እኛን ሁሉ የሚያውኩ ነገሮች እንዳይገኙብን በናንተ በኩልም መጠንቀቅ ያስፈልጋችኋል። ዳግም ለጦሩ የጋራ ጥቅምና ጉዳትም ቢሆን በእርስዎ በኩል በቀር በሌላ በኩል እንዳይተላለፍልን ስል አደራነቴን አስታውስዎታለሁ።” ገጽ 176

“የዘመድ ሰላምና ያገር ወሬ ቢሆን ግድ የለም ቢጻጻፉ፤ በተቀረ ፖለቲክ ከማያውቁ ሰዎች ጋር ተጻጽፈው ነገራችን እንዳይዘበራረቅብን፤ እኔም በዚሁ እጠነቀቃለሁ። አሁን ድረስ የሚደረግልን የእንግሊዝ መንግሥት ርዳታ አንድ ረጥል የበሬ ሥጋ ፩ ረጥል የበቆሎ ዱቄት ላንድ ሰው ላንድ ቀንና ፪ሺሊንግ ተኩል ለሲጋራ በየወሩ ላንድ ሰው፣ በ፮ ወርም ፮ ሜትር አቡጀዲ ነጠላ ሱሪና ኮት የሌለበት ይሰጠናል። እስከ ዛሬም ድረስ የቆየንበት የእጃችንን ቀለበቶችና ሰዓቶቻችንን እየሸጥን ነው።” ገጽ 176

ለወደፊቱ ግን”” ብዙ ልጆች እራቁታቸውን መሔድ ጀምረዋልና ሳንጋለጥ እንዲፋጠንልን፤ ዕድሜ ለንጉሠ ነገሥታችን እየተመኘን አምላካችን ፈጥኖ ይርዳን ስንል ነገራችንን ወስነናል፤ አሜን። ፭፻ ኤርትራዊያን ሰላምታ። መስከረም ፲ ቀን ፲፱፻፴ ዓም በኬኒያ ተጻፈ። ፊርማ፣ እንድርያስ ዘርኤ። ፌርማ ጠቅላይ ሽም ባሻይ ረዳ ተክለ” ገጽ 177

በቀጣዩ ክፍል ባሻይ ረዳ ተክሉ፣ እንድርያስና ሙሴ ብርሃኔ ከኬንያ ለአርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ ወደ ካርቱም የጻፏትን አንድ ደብዳቤ የግዜውን የቦለቲካ ትኩሳት ለመገንዘብ ይረዳን ዘንድ ተጋርተን ወደ ቀጣዩ የምእራፍ ሰላሳ ሰባት ይዘት እንሸጋገራለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 11 Mar 2020, 10:47

ለዛሬ፡ በኬኒያ የነበሩ አርበኞች ከአርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ ጋር የተጻጻፏቸውን ደብዳቤዎች አንዷን እንጋራለን። መልካም ንባብ።

ይድረስ ለክቡር አቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ፤ ካርቱም። አስቀድመን የናፍቆታችንንና የማክበር ሰላምታችንን ለርስዎና ለክብርት፣ ባለቤትዎ ለፍቁራን ልጆችዎም በኬኒያ ያለን የኢትዮጵያ ስደተኞች እናቀርባለን። መስከረም ፲፰ እና ፲፱ ቀን የጻፉልን ደብዳቤዎችዎ ልክ በ፳፰ መስከረም ደረሱን እና እጅግ ደስ አለኝ። ወንድሞቻችንም ደስታቸው ወሰን የለውም። በዚሁም ደስታ ብዛትም ሀገራችን ስለገባን ያህል አድርገን ቆጠርነው፤ የጣሊያንም በኢትዮጵያ አርበኞች በዬ ሀገሩ መከበቡንና መጨነቁን በሰሙ ጊዜ ዳር እስከ ዳር አጨበጨቡ።” ገጽ 178

“ከሀገራችን መኳንንቶች ጋር ግን ለመገናኘት አልቻልንም። ሠፈራችን ያንድ ሰዓት መንገድ ይራራቃልና እስካሁን ድረስ ለማንም ሰው ለመገናኘት አልተፈቀደም ነበር። ዛሬ ግን እዚሁ ላለው ጠባቂያችን እንድንገናኝ ብለን ሔደን ፈቃድ ጠየቅነው፤ እሱም የፊታውራሪ ዘውዴ ጠባቂ ሳይፈቅድ አይመችምና እሱን ጠይቄ መልሱን እሰጣችአለሁ አለን። እነኛ የዱሮ ናችውና ምናልባት በጽሕፈትና በወሬ እንዳይሰናከልብን ብዬ ቀኑ ለመመላለስ እንድችል በናንተው በኩል እዚሁ ላለው የእንግሊዝ መንግሥት እንዲፈቀድልን ብታመለክቱት ሥራውን ልናካሔደው እንችላለን፥፡ በተቀረ እስካሁን ድረስም አንዳችም ከመኳንንቶቹ ወደ እኛ ዘንድ የመጣ ወይም የተጻጻፈ የለም። ይልቁንስ ለሁሎቹም እንኳ ከመዓቱ አወጣችሁ እያልን ለመጣ ሁሉ ደጋግመን ጽፈንላቸዋል፤ ፊታውራሪ ታደመና ልጅ ግርማ ኢያሱ ብቻ መልስ ሰጡን። ምክንያቱን አናውቅም። ፈረንጆቹም የኤርትራ ተወላጆችና የኢትዮጵያ ተወላጆች ስምምነት እንዳያገኙ፣ ኣብረው አንድ ላይ አይቀመጡም ብለው ነው በተንኮላቸው ብዛት ለያይተውን ያሉ።” ገጽ 178

“ለታዘዝናቸው ሥራ በትጋትና በትሕትና ለመፈጸም የተዘጋጀን ነን፤ ዳሩ ግን ለተምብሩና ለወረቀት መግዣ የሚሆን ገንዘብ ስለሌለን በጣም በብዙ እናዝናለን። ዛሬ ድረስ ለምንልክበት እንኳ ወንድሞቻችን እየረጠቡን ነው፤ ለትክሻችን ልብስ እንደሌለንም ማወቅ ነው። ከአሁን በፊት ደጋግመን ጽፈነዋልና። ልጅ ኃይለ ማርያም ገዝሙ እዚሁ መኖራቸውን አናውቅም ነበር፤ በእውነት እንዳሉ ግን ሥራው በትክክል እንደሚካሄድልንየተረጋገጠ ነው። ምክንያቱም ድሮ የልጅ እንድርያስ ዘርኤ አለቃ የነብሩ ናቸውና መኳንንቶቹንም ያለጥርጥር እንዲሠሩ ያደፋፍሯቸው ነበር። ስለዚህ እንዲኖሩልን ተስፋ እናደርጋለን። ባሻይ ረዳ ተክለ ባለው ነገር ሁሉ ግን ሁሉም የአትሳካ ንው። እዚሁም ለፈረንጆቹ ተጠሪ ዋና ሻለቃ ባሻይ ረዳ ናቸው፤ በየክፍሉ አድርገን በሚመጣው ቡስታ እንጽፍልዎታለን።” ገጽ 179

“ኣሁንም ሳንጨርስ ከወዲያኛው ፈረንጂ እንዳንገናኝ የሚከለክለን መልስ መጣ፤ ስለዚህ በብዙ መጨቆናችንን እወቁትና እንድትጥሩበት መሠረት ይሁን። ዳግም ቀኛዝማች ገብራይ ከራስ ደስታ ጋራ የነበሩት ከጭፍሮቻቸው ጋራ ፸፭ ራሳቸውን ሆነው ከብዙ ጭንቅና መከረ ተርፈው እኛ ዘንድ ደረሱ። ሌሎቹም ከሞት የተረፉ እንደዚሁ እንዲደርሱልን ጸሎት እናደርጋለን፤ ስለ ታሪካቸውም በሌላ ጊዜ እንጽፍልዎታለን። ከራስ ደስታም የተለዩበት ለጦርነት በየክፍሉ ታዘው እንደሄዱ እየተቆረጡ ተለይተው የቀሩ ናቸውና ሞታቸውንና ሕይወታቸውን አያውቁም፡ ከተለያዩም ፱ ወር ሆኖአቸዋል። ፭፻፰፫ የኢትዮጵያ ስደተኞች ሰላምታና ምስጋና እያቀረብን ነገራችንን ወስነን አቅርበናል። መስከረም ፳፰ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ኪኒያ ተጻፈ። ፊርማ ባሻይ ረዳ ተክሉ፣ እንድርያስና ሙሴ ብርሃኔ።” ገጽ 179

በቀጣዩ ክፍል ወደ ምእራፍ ሰላሳ ሰባት ይዘት እንሸጋገራለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Degnet
Senior Member+
Posts: 25078
Joined: 16 Feb 2013, 11:48

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Degnet » 11 Mar 2020, 11:32

kerenite wrote:
07 Nov 2019, 13:52
Aite meleket wedajachin,

Your hero was an ethiophile same as zeray deres or aman andom or bereket simon. They were more ethiopians than the ethiopians themselves.
Don't include the name Bereket Semeon among these heroes.

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 19 Mar 2020, 03:17

ለዛሬ አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ፡ በኬኒያ ስለነበሩት አርበኞች በሚመለከት ጉዳይ ለንጉሠ ነገሥቱ የጣፉትን ምክርና ማሳሰቢያ ቢጤ እንኮምኩም። መልካም ንባብ። :mrgreen:

ለቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ንጉሠ ነገሥት ዘ ኢትዮጵያ ሎንዶን። ጃንሆይ፣ የኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞችዎ ከተጋደሉ በኋላ ከሞት የቀሩት ተሰደው በየቀኑ ኬኒያ የገቡት ቁጥራቸው ከ፩ ሺ ፫፻፹፭ ሰው ይበልጣሉ። በትግል መግባታቸውንና በብዙ መቸገራቸውን ስለሰማሁ፣ ከነሱ ጋርም ከብዙ ጊዜ በፊት ጀምሬ ስጻጻፍ ስለነበረ ችግራቸው ከልክ ያለፈ ስለ ሆነ ለግርማዊነትዎ እንዳደርስላቸው አጥብቀው አደራ ብለውኛልና አንድ ብልሃት እንዲደረግላቸው አሳስባለሁ።” ገጽ 180

“አዲስ አበባ ዋና የራዲዮ ሠራተኛ የነበረው አቶ ሙሴ ብርሃነ የጻፈልኝን መስል ከዚህ ጋራ ልኬልዎታለሁና አጥብቀው ቢመለከቱት እጅግ ጠቃሚና መልካም ይመስለኛል። ልጁንም ግርማዊነትዎ ያውቀዋል። ሊጻፍላቸው የሚገባቸው ሰዎች ዝርዝርም ለብቻው አድርጌ ልኬአለሁ።” ገጽ 180

“ግርማዊ ሆይ ለእነዚህ በብዙ ችግርና የጠበቀ እሥራት ተስፋ ቆርጠውና ተጨንቀው በኬኒያ በስደትና መሳይ በሌለው ጭቆና የሚገኙት የኢትዮጵያ አርበኞችዎ የሚያጥናናቸው በየስማቸው አንዳንድ ደብዳቤ በቶሎ ቢጻፍላቸው ከሁሉ የበለጠ ተስፋ ስለሆነ የግርማዊነትዎን የበጎነት ሥራ እንዲሠራላቸው በብዙ እለምናለሁ።” ገጽ 180

የራስ ደስታ አሽከር ፊታውራሪ ታደመ ዘለቀ የሚባሉ የሚገባቸውን ሠርተው ጋርዱላ ደርሰዋል ስለተባለ የደረሱበት ቦታ ድረስ ተላልኬ በፍጥነት አስጠይቃለሁ። ለሁሉም ግርማዊ ፊትዎን ከምዕራብ ወደ ምሥራቅ ፈጽመው እንዲያዞሩት እግዚአብሔር ፈቃድ ሆኖዋልና ለተጋዳዎች ጀግኖችዎ ሁሉ ቀን ከፍ ያለ ተስፋ እንዲሠጥዋቸው፤ በብዙም እምነትና ምስጋናም እንዲመግቡን እንለምንዎታለን። ነሐሴ ፲፩ ቀን ፲፱፻፳፱ ዓ.ም ካርቱም። ፊርማ፣ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።” ገጽ 180

በቀጣዩ ክፍል ከምዕራፍ 37 ይዘት፡ አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ ወደ ጃንሆይ ያስተላለፉትን የነ አርበኛው እንድርያስ ዘርኤ አባሪ ደብዳቤዎች ይዘት እንኮመኩማለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው። :mrgreen:

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 04 Jun 2020, 05:35

የምዕራፍ 37 ይዘት አንዱ ከሆነው፡ በኬንያ የነበሩት አርበኛው እንድርያስ ዘርኤ በኬንያ ያጋጥማቸው የነበረን ሁኔታ በተመለከተ ለአርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ የጣፉትን ደብዳቤ ይህን መስል ነበር! :mrgreen:

“ይድረስ ከአቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ፤ ጤና ይስጥልኝ ብዬ የማክበር ሰላምታዬን አቀርባለሁ፤ ለክብርት ወይዘሮ ቀደስና ለፍቁራን ልጆችዎ እዚያው ካሉትም የኢትዮጵያ ስደተኞች ጋራ ዓይን ለዓይን ለመገናኘት እየተመኘሁ የናፍቆት ሰላምታዬን አቀርባለሁ። በ፫ት መስከረም የተጻፈ ክቡር ደብዳቤዎ ደረሰልኝ፤ እዚያው ለነበሩ ብዙ ቁምነገርም ለወንድሞቼ የከፈልኩዋቸው፤ ለክቡር ፊታውራሪ ታደመም አሳለፍሁላቸው፤ መልሱ ግን አልመጣልኝም፤ እዚሁ ላሉት የኤርትራ ልጆች ግን ያአንድ ሚኒስትር ቃል መሆኑን አረጋገጥሁላቸው። እጅግም አድርጎ ደስ ስላላቸው በስማቸው ደብዳቤ እንድጽፍልዎ አስገደዱኝ። በዚሁ ሰሞ ከገነትዋ ኢትዮጵያ የመጣ ሰው አይተው ተስፋ ቆረጠው እህል መብላት ድረስ ለመተው በቅተው የነበሩትን ሰዎች በዚሁ ዓውደ ዓመት ነፃነታቸውን የሚያረጋግጥ ክቡር ቃልዎን በሰሙ ጊዜ ነፍሳቸው ተመለሰ። እኔም ምንም እንኳ ተስፋ ባልቆርጥ፣ እየተጠራጠርኩ ሌት ተቀን እንቅልፍ አጥቼ የነበርሁትን በጣም ስለተጽናናሁኝ፣ ኣእምሮየ እየተመለሰ ለመጻጻፍ እተጋለሁኝ። እድሜ ሰጡኝ። እግዚአብሄር ይስጥልኝ።” ገጽ 181

“ለወደፊትም እንዲሁ የመሳሰለ ተስፋ ቀርቶ ኅዘንም ቢሆን የምንካፋል ነንና ከሰማይ የወረደልን ይህል አድርገን ነው የምንጠባበቀው፤ ባ፲፪ መስከረም የሚደረገው የዓለም መንግሥታት ስብስባ በምን እንደተቆረጠ፣ ዳግም ግርማዊ ምን ዓይነት መልስ እንዳገኙ፣ የእንግሊዝስ መንግሥት በምን አኳሆን ሊረዳን እንዳሰበ (ይግለጹልን)።” ገጽ 181

እዚሁ የመጡት የኢትዮጵያ መሳፍንቶችና መኳንንቶች ቁጥራቸው ብዙ ናቸው። ከነሱም አንዱ ደጃዝማች ወልደ ማርያም፣ ፊታውራሪ ታደመ፣ ፊታውራሪ ዘውዴ እስከ ስድስት የሚሆኑ ሌሎች ፊታውራሪዎች በፊታውራሪ ታደመ ዘለቀ ውስጥ አሉ። ሕዝቡም እስከ ፭ ሺህ ነው፤ የሚበልጡት ሴትና ሕፃናት፣ ሽማግሌዎችና በሽተኞች ናቸው። ከኛ ያንድ ሰዓት መንገድ ይርቃሉ። ዳሩ ግን የእንግሊዝ መንግሥት እንዳንገናኝ ጨርሶ ከልክሎናል፤ ምክንያቱን አናውቅም። እነሱ ግን ነጋ ጠባ እንኳ ከመዓቱ ያወጣችሁ እያልን ደጋግመን ብንጽፍላቸው አንድም የጻፈልን የለም። በኅዘን ልባቸው መከበቡን ያስረዳል። ሠራዊቱም የተቅማጥና የሆድ ቁርጠት በሽታ አጥቅቶታል። ዳግም ችግር ጠንቶባቸዋል፤ የዱቄትና የሥጋው የቀን ስፍር ልክ እንደ የኛ ሳለ የሚሰጣቸው አስተካክሎ የሚያካፍላቸው ሰው ስለጠፋ ገሚሱ ሁለት ጊዜ ሲቀበሉ ገሚሶቹም አንድ እንኳ እያጡ ችጋሩ እየጠና፣ በሽታው እየበረታ ይሄዳል። ትንሽ ፊታውራሪ ታደመ ይሻላሉ እንጂ ከሌሎቹስ የሚንቀሳቀስ የላቸውም፤ ስለዚህ የሚያሳዝን ነው፤ ፈረንጆቹም እንዳይነቁባቸው እፈራለሁ፤ እስካሁን ግን አልደፈርዋቸውም ነበር።” ገጽ 182

“የልጅ ኢያሱ ልጅ፣ ልጅ ግርማው ፮ ዓመት ሙሉ ማጂ ላይ እግር ተወርች በብረት ታሥሮ የነበረ፣ ባኮ ላይ ጥቂት ወታደር አብሮለት እንደሌሎቹ ሐዲስ ምግብ በደስታ ሳይመገብ ለሀገሬ እሞትላት አለሁ ብሎ ፬ ቀን ሙሉ ጦርነት ተዋግቶ ገንዘብና ጥይት ስለሌለው ወታደሩ ተበተነበት። የቀሩትም ሃይማኖተኞች ወደ እንግሊዝ እንሂድ እንጂ አይሆንልንም ብለው ቢያስገድዱት እንግሊዝ ጎፈሬያችሁን ቆርጦ አፈር ከሚያሸክማችሁ ለኢትዮጵያ እናታችሁ መሞት ይሻላል ብሎ ቢለምናቸው እምቢ ብለው ገሚሱ ወደዚህ ገሚሱም ወደ ኬንያ ለመጓዝ ተገደደ፤ መጣም። እጠረፉ ድረስ የተሰበሰበለትም ሰው እስከ ፫ሺህ ይሆናል። እነሱም በሽታ እንደጠናባቸው ናቸው። ምክንያቱም የመንገዱ ችግርና የውኃው ጥም የሀገሩ ቆላነትና የቆየው የበቆሎ ዱቄት አልስማማ ብሎአቸው ነው።” ገጽ 182

“ክቡር ራስ ደስታና ደጃዝማች ገብረ ማርያም፣ ደጃዝማች በየነ መርዕድ እስከ ጉራጌ የደጃዝማች ገብረ ማርያም ሀገር ጠረፍ ድረስ እንደ ደረሱ ትልቅ ጦርነት ስለገጠማቸው ገሚሱ እስከ ከተማው ድረስ ገብተው የደጃዝማች ገብረ ማርያም ባለቤት ከሴት ልጃቸው ጋር እከተማው ገቡ። ዳሩ ግን እነኚህ ሦስት መኳንንቶች ከብዙ ሠራዊት ጋራ ተቋርጠው እንደቀሩ የገቡበትም ጠፍቶዋቸው ሕዝቡ ሲተራመስ፣ አንዳንዶቹ ለማመን፣ አንዳንዶቹም ለመዋጋት ሲሉ ከዚያው በረው የመጡ ሰዎች እንዳወሩልን ፫ቱ በሕይወታቸው እንደቀሩ ያረጋግጣሉ።” ገጽ 182

“ከክቡር ራስ ደስታ ጋር ዘምተው የነበሩ የሀገራችን የኤርትራ ልጆች ግን ጠላት በበረታበት በኩል እየታዘዙ በጥይት ሲነድፉት ከርመው በየጊዜው ከክቡር እየተቋረጡ በየሄዱበትም ቦታ ጠላት ሲገጥማቸው፣ ከክቡር ጋራ የሚያገናኛቸውን መንገድ ባለማወቅ አንድ ፻ የሚሆኑ መሞታቸው ተረጋግጦአል። ከእነዚህም አንዱ ፊታውራሪ ጸጋይ ንጉሤ ወላይታ ገብተው ከፊታውራሪ ዘሞ የደጃዝማች መኮንን ወሰኔ እንደራሴ ጋር ሆነው ብርቱ ጦርነት ገጥመው ካደረጉ በኋላ ጥይታቸውን ጨርሰው ፬ት ራሳችው ተማርከው ዕለቱን በስቅላት እንዲገደሉ ቢፈርድባቸው “ፊታውራሪ ጸጋይ እንደኔ ያለ ሰው ስለሀገሩ ነፃነት የተዋጋ ወታደር በጥይት ይሞታል እንጂ እንደሌባ አይሰቀልም” ብለው ፉከራ በፎከሩ ጊዜ፣ የጣሊያንም ወታደሮች “ወንድማችንን አንገድልም” ሲሉት ሁለት ቀን አውሎ በራሱ ሶልዳቶች አስገደላቸው ብለው በማረጋገጥ መሰከሩ። ገጽ 183

“ቀኛዝማች ሰለባ ፫፻ የሚሆን ደረቅ ጦር ይዘው በሲዳማ ማኸል ለማኸል ይወዛወዛሉ በሄዱበትም ሀገር የሸንፋሉ እንጂ ምንም አይሸነፉም ይላሉ። በኤውሮጳም በኩል ኢትዮጵያ በጣሊያን እንድትገዛ ፍርድ ተፈርዶ እንደሆነ፣ ወይም እኔ አካላቴ ሰንፎ እንደሆነ ነው እንጂ እንግሊዝ ሀገር የምሄደው የሚሉት ቃል ከልባቸው ፈጽመው አስወግደውታል፤ ለእንደዚህ ያለ ሰው አንድ ሰው መላክ ያስፈልግ ነበር፤ ዳሩ ግን በምን ዓቅማችን። የሚቻል በሆነ ግን ፩ብረት ባገኝ በስውር እነሱ ባሉበት ሀገር ለመግባት እኔ እችል ነበር፤ ለዚሁም አንደኛው ባለፍቃድ ሁኜ እኔ ለመሔድ እመኝ ነበር፤ ስለምን? መቶ ቀን እነ ፍቅየል ሆኖ ከመጠራት አንድ አን እንደ አንበሳ መጠራት እንደሚባለው ተረት፣ እዚሁ ታሥረን ከመሞት ሥራ እየሠራን በሀገራችን መሞት ይሻለን ነበር።” ገጽ 183

ቀኛዝማች ገብራይ ከሁሉም ተጣፍተው ፲፭ ራሳቸው ሆነው ከልጅ ኢያሱ ልጅ ጋራ ይመጣሉ፤ የሚመጡትም በጠና ስለታመሙ ነው፤ ግን አልጻፉልንም። እነሱ እንደመጡ የሁሉንም ነገረ ርግጠኛውን እጽፍለዋታለሁ። ልጅ ገብረ መድኅን ዘጎና አቶ ዮሐንስ አሊ ከነሚስቶቻቸው ከቀኛዝማች ሰላባ ጋራ ናቸው።” ገጽ 183

እዚሁ ላሉት የኢትዮጵያ መኳንንቶች በደምብና በወግ አድርገው ሰዎቻቸውን እንዲጠብቁ ብላችሁ ከወዲያ ብታስጠነቁቁዋቸው ይሻላል። እዚሁ ላሉት ሻንቅሎች መሣቂያ መሆናቸው ነው፤ ምክንያቱም ሴቶች ስለበዙ ይተነኩሱዋቸዋል፤ ይኸውም ጠባቂና አስተዳዳሪም በማጣታቸው ምክንያት ነው። እንኳን ከዘመነ ሉቃስ ወደ ዘመነ ማርቆስ አሸጋገረዎት ስል ነገሬን እወስናለሁ። ፌርማ፣ እንድርያስ ዘርኤ።

በቀጣዩ ክፍል የተመሳሳይ አባሪ የአርበኞች ደብዳቤዎች ይዘት እንኮመኩማለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው። :mrgreen:

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 15 Jun 2020, 03:48

ጎበዝ እንዴትናቹሳ ባያሌው! :mrgreen: ለዛሬ በምዕራፍ 37 የተካተቱትን በኬኒያ የነበሩ ስደተኛ አርበኞችን ሁኔታ የሚገልጹ በአርበኞቹ በነ ሙሴ ብርሃነና እንድርያስ ዘርኡ፡ ለአርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ የተጣፉ ደብዳቤዎችን እንገረምማለን። መልካም ንባብ። :mrgreen:

"ይድረስ ለክቡር አቶ ተስፋሚካኤል ትኩእ፤ እጅጉን ለጤናዎ እንደምን ሰንብተዋል? እግዚኣብሔር ይመስገን፤ እኛ ደህና ነን። በዓለም መንግሥታት ማህበርና በሱዳን ላሉት የኢትዮጵያ ስደተኞች የኅዘንና የናፍቆት ሰላምታችን እናቀርባለን።” ገጽ 184

“በመስከረም ፲፰ ቀን ለተላከልን ክቡር ደብዳቤዎ ቃል እንደትእዛኩ ልክ ትክክል ግልባጭ ለክቡራን መኳንንቶችና በተለይም አንድ ለፊታውራሪ ዘውዴ አየለ በራኮማንዴ ልከነላቸው ፈርመው ተቀብለውናል። ልጅ ኃይለማርያም ገዝሙ ግን በኬኒያ ቅኝ ክልል ስለሌሉ፣ ያለመግባታቸውም ስለተረጋገጠልን በሳቸው ምትክ መኳንንቶች መክረው እንዲያደርጉልን አመልክተናቸዋል፤ ለወደፊቱ እናስታውቀዎታለን። ስለየሰዎቻቸው ዝርዝር ሠርቶ ለመላክ ግን ብዙ ቀን ሳያስፈልጋቸው አይቀረምና ለወደፊቱ እንዲልኩልን እንጠብቃለን፤ እነሱም በጠባቂያቸው እንደኛው ልክ የተጨነቁ ይመስሉናልና ራሳችን እዚያው ሠፈራቸው ሄደን እንድንሠራ የኛም ጠባቂ ስለማይፈቅድልን ሥራውን ለጊዜው ለማፋጠን አልተቻለም። ስለዚህ ከአሁን በፊት በተለየ ፈቃድ እንደሚያስፈልገን ልከንልዎታልና የሚቻል ቢሆን ለሁለታችን ልዩ ፈቃድ ቢደረግልን በየቀኑ እየተገናኝን ሥራውን ከማፋጠን አናቋርጥም ነበር።” ገጽ 184

በክቡር ባሻ ረዳ ውስጥ ያሉትን ሹማምንቶችና ወታደሮች ግን እንደትእዛዙ ልክ አድርገን በየክፍሉ ሠርተን ከዚህች ደብዳቤ ጋር የተሸኙ አሥራ አራት ልዑክ (ሉክ) ወረቀት ከአንድ ቁጥር እስከ ፭፻፸፬ እዚህች ኢሲዮሎ ጣቢያ ላይ ገብተው ያሉና ስለ የሞቱ ድምር መሆኑ ነው። በሞላው ሁሉ እናታችን የሆነችዋን ኢትዮጵያ በዳነችልንና የእንግሊዝ መንግሥት ላደረገልን ውለታ ለመመልስ በበቃን እያሉ የሚመኙና የሚያደሉቱ የኢትዮጵያ ስደተኞች ኅሳብ መሆኑን እያረጋገጥን እንወስናለን። የኬኒያ ፣ ኢሲዮሎ ጥቅምት ፲ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ተጻፈ። ፊርማ፣ ሙሴ ብርሃነ፤ ፊርማ፣ እንድርያስ ዘርኡ።” ገጽ 185

“ይድረስ ለክቡር አቶ ተስፋሚካኤል ትኩእ። አስቀመን የማክበር ሰላምታችንን ለክቡርት ባለቤትዎና ለልጆችዎ፣ ለኢትዮጵያም ስደተኞች ሁሉ የማክበርና የፍቅር ሰላምታችንን እናቀርባለን። በጥቅምት ፳፩ ቀን ያጻፉልን ክቡር ደብዳቤዎ ደረሰን። ስለ ልዑል ራስ ሥዩም መንሻም ከእሥር መውጣትና ልባቸው ፈጽሞ ከኛ ጋራ በመሆኑ ደስታችን ወሰን የለውም። ሞላው የኢትዮጵያ ጀግናና ታሪካዊ ሕዝብም ለጣሊያን አልገዛም ብሎ ስለከዳው ጣሊያን ተጨንቆዋል ስላሉን የህን ደስታ እዚህ ያለውን ኢትዮጵያዊ ስደተኞች ሁሉ ዕለቱን ስለሰማነው በጣም ተጽናና፤ የምንሠራውም ሁሉ በምስጢር ነው እንጂ የተፈቀደልን ነገር የለም። ለመኳንንቶቹ በተቻለን መጠን አመልክተናቸዋል፤ እነሱም እሺ እንዳሉ ናቸው፤ ግን ስንሰማ በዚሁ ሳምንት ከባለቤቱ ተልኮላቸዋል፤ የሚያያችሁ ሰው እንልክላችሁ አለን የሚል ቃል፣ ዳግም ለጠላት አንገብርም ብለው የወጡ ሰዎች ዝርዝር እርስዎ እንዳሉት ላኩልን የሚል ማዘዣ ለደጃዝማች ወልደ ማርያም ተላልፎላቸዋል፤ ለኛ ግን አንድ መልስ አልሰጡነም።” ገጽ 185

“በጥቅምት ፲፪ ቀን ከሎንዶን የተላከለዎትን የደስታ ምልክት ለኛም እንደሚያካፍሉን አይጠረጠርምና ለጊዜው በዝና ደስ ብሎናል፤ ስለዚህ በፍጥነት እንዲደስልን እንጠባበቀዋለን። በእግዚአብሄር ኃይልና በቀዳማዊ ኃ.ሥ ድካም በስምምነትና መረዳዳት መኖራችንን እናረጋግጥልዎታለን። እኛ ግን በእርስዎ በኩል ካልሆነ አንድም ነገር የደረሰን የለም። አቶ ወልደጊዮርጊስ ተልኮላችኋል ያሉትንም ወደፊት እንጠብቃለን።” ገጽ 185

“ባለቤቱም ስለ ኢትዮጵያና ስለ እኛም ጉዳይ ምንም እንዳልዘነጉን እናምናለን፤ ቃላቸውንም እስኪፈጽሙልን እንጠብቃለን፤ እስኪዚያው ግን ጐልበታችን እንደጨው እየሙዋሸሸ በመሄዱ፣ አእምሮአችንም እየተደፈነ፣ ምናልባት ከሞት የቀረነ እንደሆነ ለምንም ሥራ እንድንድን እንጂ ለኛ ወይም ለእንግሊዝ መንግሥት ወይም ለሥጋችን ወይም ለነፍሳችን አንድም መሠረት ያለው ቀሪ ጥቅም ስለሌለው እጅግ ተጐድተናል። በቂ እውቀትና ጥበብም ባይኖረን ወደ እናንተ ስለተጠጋን ምናልባት ቀን ወጥቶልን ለወደፊት የእንግሊዝን መንግሥት ስም መጥሪያ እንዲሆነን በያይነቱ የእጅ ጥበብ ለመማር የምንችል ሰዎች እንድንሆን፣ አንድም ሳንማር እስከዛሬ ድረስ በከንቱ የቆየንበት እያሳዘነን፣ ለወደፊቱ በየመሥሪያ ቤቶቻችሁ ተበትነን እየተማርንና እየሰራን በየመንግሥት ቤቱ እንድንጠበቅ እንዲፈቀድልን። ይህነኑም የርኅራሔና የቸርነት በጐ ሥራ በቀላሉ ለመሠራት የሚችል (ሆኖ) ሳለ አንዳች ሥራ እንዳንሠራ ጨክናችሁ የከለከላችሁን እንደሆነ ግን ከፍ ያለ ኃዘንና ፀፀት ይሆንባችኃል ስንል አስቀድመንና አጥብቀንም እንለምናችሁአለን። የእንግሊዝን መንግሥት ተማምነን ኬኒያ የገባን የኢትዮጵያ ስደተኞች። ጥር ፩ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ኬኒያ። ፊርማ፣ የፀሐፊው እንድርያስ ዘርኤ” ገጽ 186

ለክቡራንና ለፍቁራን የኢትዮጵያ ስደተኞች ወንድሞቻችን መድኃኔዓለም ጤናና የገነነ እድል ቸሩ አምላክ ይስጥልን እያልን የማክበርና የናፍቆት ሰላምታችንን ከልብ እናቀርባለን።” 186

በታህሳስ ፬ ቀን የጻፉልን ክቡር ደብዳቤዎ ደረሰን፤ በውስጡም የነበረው የኢትዮጵያ ድምጽ ጋዜጣና የአቶ ወልደጊዮርጊስ አድራሻ ደረሰን፤ እግዚአብሄር ይስጥልን። በበለጠም ጋዜጣችን በዓለም በመታየቱ ተስፋችን እንደተረጋገጠ ሆኖ ተሰማን። ለጊዜው ወደ አቶ ወልደጊዮርጊስ ለመፃፍ አልቻልንም። ጠባቂያችን እስከዚያ ድርስ ለመጻጻፍ የሚፈቀድልን አይደለምና ለሚያስፈልገን ነገር ሁሉ ደጋግመን ላመለከትንዎ ነገሮች ራስዎ እንዲያስታውቁልንና እንዲጥሩልን እናምናለን። እስከአሁንም ድረስ ከርስዎ ደብዳቤዎች በቀር የደረሰን ነገር ምንም የለም። ስለ ልብስም ረገድ ለጌጥ ሳይሆን ለእርቃን ሥጋችን መሸፈኛ አጥተናል። ለደረሰብን ወሰን የሌለው አደጋም የጠየቀንና የቀበረን ያነጣጠረንም ዳኛ እስከ ዛሬ አላገኘንም። የቀረነውም ፈጽመው እስቲጨርሱን ድረስ “ግፍኦሙ እግዚኦ ለእለ ይገፍዑኒ፤ ጽብኦሙ እግዚኦ ለእለ ይጸብዑኒ” እያልን እንጠብቃለን።” ገጽ 186

በቀጣዩ የምዕራፍ ሠላሳ ስምንትን ይዘት ማለትም “የሞቱና የቆሰሉትንም የኢትዮጵያ ስደተኞች ዝርዝርን” እናቀርባለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው። :mrgreen:

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 01 Jul 2020, 04:28

ለዛሬ የአርበኛውን የተስፋሚካኤል ትኩእ መጽሐፍ የምዕራፍ ሠላሳ ስምንትን ይዘት ስንካፈል፣ በግፈኞችና ተስፋ በቆረጡ የጽልመት ኃይሎች ሕይወቱን ለተቀጠፈው ለኦሮሞ ሕዝብም የህልውናና የባህል ትንሣኤ ጉልሕ ድርሻ ለነበረው ለወጣቱ ፈርጥ አርቲስት ሀጫሉ ሁንዴሳ ክብር፡ በኤርትራ ህዝብና በሰላም ወዳድ ኃይሎች ስም ነፍሱ በአጸደ ገነት ትሰፍር ዘንድ እየተመኘን፣ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብና የተለያየ አመለካከት ያላቸውን ኃይሎች በትእግስትና በትህትና በጥበብና በፍቅር ለመምራት ያላሰለሰ ጥረት ለሚያደርገው ለሰላማዊው ወጣት ጠቅላይ ኣብዪና እሱ ለሚመራው መንግስት መጽናናቱን እየተመኘን ነው።

ወደ አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ ትረካ ምዕራፍ ሠላሳ ስምንት ስንመለስ “የሞቱና የቆሰሉትንም የኢትዮጵያ ስደተኞች ‘በኬኒያ’ ዝርዝር ቀጥሎ እንደተጻፈው ነው”

የሞቱ ወታደሮች አሥፍሐ ባህረ፣ ገብረ ስላሴ ገብራይ፣ ጸጋይ ወልደኪዳን፣ ሞገስ እምባዬ፣ ዘርእዝጊ ግርማ ጽዮን፣ በራኪ ሐጐስ፣ ክፍለየሱስ መልከየስ፣ ገብረ አብ ገብረ መድኅን፣ አስፍሐ መሐሪ፣ ገብረማርያም ረድኢ፣” ገጽ 187

ኣካላታቸው የጐደሉ መስፍን ገብረ መስቀል፣ ገብረ ጊዮርጊስ ሃብተሚካኤል፣ተክለ ወልደማርያም፣ ገብረትንሥኤ ተክለ፣ ፍሥሐጽዮን ብኢዱ፣ ገብረማርያም መንግሥቱ፣ በላይ አስገዶም፣ ገብረእንድርያስ ገብረጊዮርጊስ፣ ኪዳኔ ተስፋዝጊ፣ መንግሥቱ ተወልደ፣ ሃብተ ስላሴ አሥራት፣ ገብረ ስላሴ ባህታ፣ ተስፋይ ሥእሉ፣ ኣልፋይ በሪህ፣ ብርሃነ አይሙት፣ በርሄ ገብረ አምላክ፣ ተስፋ ሚካኤል አዳል፣ እንግዳ ተስፋጽዮን፣ ወልደ ገብርኤል ወልደጋብር፣ ተወልደብርሃን ግርማ ጽዮን፣ ወልደ ኣብ ክፍለ፣ ሞገስ ደሱ፣ ተስፋዝጊ ገብረስላሴ፣ ተስፋጋብር ስብሃት፣ ዮሴፍ ፍርዙን፣ ተክለ ኣብ ሐጐስ ናቸው።” ገጽ 187

“በየጊዜው የሚገኘው የዓለም ወሬ ምግባችን ነውና አስፍተው እንዲልኩልን እንጠባበቃለን። እስከ ዛሬ ድረስ ሳንጽፍለዎት የዘገየንበት ምክንያትም ከዚህ ቀደም እንዳመለከትንዎ ለቴምብር የሚከፈል ዋጋ እየቸገረን ነው እንጂ በቦዘን (በቸልታ) አይደለም። የባሻይ ረዳ ተክለንና የኣአቶ ተክሉ ዙዋቨን ከ፭፻፶፮ የኢትዮጵያ ስደተኞች ጋር ሰላምታ ይቀበሉ። ቸሩ አምላክ በሕይወት ለመገናኘት ያብቃን፤ ታማኞችዎ።ፊርማ፣ ሙሴ ብርሃነና እንድርያስ ዘርኤ ” ገጽ 187

በቀጣዩ የምዕራፍ ሠላሳ ዘጠኝ ይዘት ማለትም “የኢትዮጵያ ስደተኞች እንግሊዝ ለጠላት አሳልፎ መስጠት፣ የጸገዴን አርበኞች ለመረከብ ጣሊያን ፩ ኮሎኔል ገዳሪፍ መላክ፣ ደፋር የሴት አርበኛ ወ/ሮ ከበደች ሥዩም ሱዳን መሰደድ” በሚል ርእስ ስር፣ የእንግሊዝ መንግሥትን አድልዋዊ አካሄድ ፍንትው አድርጎ ከሚያሳየው ጥሑፍ እየጨለፍን እንቋደሳለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 07 Jul 2020, 10:22

ለዛሬ የአርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእን መጽሓፍ የምዕራፍ ሠላሳ ዘጠኝ ትረካ በከፊል እንቃኛለን፡ በዛሬው ትረካ የኢትዮጵያ ስደተኞችን እንግሊዝ ለጠላት አሳልፎ ስለመስጠቱና፣ የጸገዴን አርበኞችን ለመረከብ ጣሊያን ፩ ኮሎኔል ገዳሪፍ ድረስ ስለመላኩ የሚገልጸውን ክፍል እንቃኛለን። ይህን ስናደርግም የአዲስ አበባን ምክትል ከንቲባ ኢንጅነር ታከለ ኡማ የጀግናው አርበኛ የሃጫሉ ሁንዴሳን የአርበኝነት ገድል ለመተረክና ለመሰነድ የሚደረጉትን ጥረቶች ሁሉ ለማበረታታት የሚያደርጉትን ከልብ የመነጨ ቁጭት የሞላበት መነሳሳታቸውን ከልብ በማድነቅና ባለፉት የአፍሪካ ቀንድ የነጻነት አርበኞች ሁሉ ስም ከፍ ያለ ምስጋና እያቀረብንላቸው ነው። መልካም ንባብ!

“የኢትዮጵያ ስደተኞች እንግሊዝ ለጠላት አሳልፎ መስጠት፦ ከዓለም መንግሥታት ሕግ ውጭ በሆነው ሥራው ፲፫ የኢትዮጵያ ስደተኞች በተሰወረ አፈሳ ከከሰላ አሥሮ ጠላታቸው ለሆነው ጣሊያን ሌሊት በጨለማ ሰጣቸው። የኢትዮጵያ ስደተኞች የሱዳን ገዥ የሆነውን የእንግሊዝን መንግሥት ተማምነው ከሰላ ቢገቡለት ያለ አንዳች ርኅራሄና ያለ አንዳች ጥያቄ ወይም ፍርድ ወዳጁና ወገኑም ለሆነው ለጣሊያን መንግሥት በክዳትና በከሐዲነት አሳልፎ በመስጠቱ የኢትዮጵያ ሕዝብ እጅግ አድርጐ ኅዘን አዘነ። በእንግሊዝም ወላዋይ ፖለቲካ ተናደደ፤ ተሳደበ፤ በአስመሳይነቱና እንግሊዝ እምነቱን በመሰረዙ በኢትዮጵያውያኖች ዘንድ ፈጽሞ ተናቀ።” ገጽ 187

ከእነዚህም እንግሊዝ ለጣሊያን ካስረከብቸው ፲፫ ሰዎች ውስጥ ፲ሩን ወዲያው ሲገድላቸው መሐሪ ሐጎስና ገብረ መድኅን ወልደ ስላሴ፣ ገብረ ሚካኤል የሚባሉትን ግን በመደብደብና በርኃብና በውኃ ጥም ካሰቃያቸው በኋላ እነዚህ አርበኞች ከሻምበል ከአቶ ዓድሃኖም ክፍለዝጊ ጋራ ሆነው ማሓሪ ገብረ መድህን፣ ዘርዓ ሠናይና ዘርሐንስ በእንድርታ አደጋ ጥለው ፱ ዑፍሴሮችና ወታደሮች፣ በዓዲግራት ጐድጓዳ ፩ ካፒቴንና ፮ ወታደሮች፣ በሠንዓፈ ፩ድ የፖሊስ አሥር አለቃና ፬ ወታደሮች ሱዳን ከመግባታቸው በፊት እነዚህን ፳፩ ኢጣሊያኖች መግደላቸውን የጣሊያን መንግሥት ያውቅ ስለነረ አሥመራ አስጠርቶ ጠየቃቸው። መሐሪና ገብረ መድህንም ያለ አንዳች ምሕረት እንደሚገላቸው ስለተረዱትና መመታቱና (መደብደቡን) ረሃብና ጥማቱም ስላስመረራቸው መገደላቸውን መረጡ። ከእነዚህ ፳፩ ኢጣሊያኖች በላይም በየጊዜውና በየሃገሩ ሌሎች ኢጣሊያኖችንም መግደላቸውን ራሳቸው መሰከሩ።” ገጽ 188

“የኢጣሊያንም መንግሥት የእነዚህ ወጣቶች ነገር ከነከነው። ነገ ሳልስት እገድላቸዋለሁ ብሎ ቢያፈጥጥባቸውና ቢፎክርባቸውም ረቂቅ በሆነው የእግዚአብሔር ሥራ በሱ በራሱ በጣሊያን መንግሥት ሰራዊት ላይ መገደልንና ተዓምራታዊ መከራና እስራትም ዘነበበት። እነዚህን የአካለጉዛይ አርበኞች ለመግደል የጣሊያን ወራሪ መንግሥት ያለ ልክ ቢቸኩልበትም ያለ የእግዚኣብሔር ትዕዛዝ የሚፈጸም ነገር ስለሌለ እንግሊዝ አሥመራ መጣ፤ ለሞት የታሰሩትም አርበኞች ተርፈው ተፈቱ። ቸሩ እግዚአብሄርም በእነዚህ ፭ቱ ዓመታቶች ውስጥ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ጥቅም ብሎ ብዙ ተአምራትና መንክራትም ሠራ፤ ይሠራልም።” ገጽ 189

የዓድሐኖም ከነጓደኞቹ አርማጭሆ መግባት፦ የኦሮሞ ተወላጅ የሆኑ አቶ እሸቴ ዓለሙ የተባለ ሀገሩን አፍቃሪ የሆነ ወጣት ብርታትና ድፍረት አደገኛ ከሆነው ከሰላ ከእንግሊዝ እሥራት የቀሩት ዘርዕ ሠናይና ዘርሃንስ አብርሃንና ከዓጋሜ ያመጣቸውን ፭ት አልበኒ ብረትና ጥይት በራሱ ካሚዮን አስጭኖ ከከሰላ በገዳሪፍ ዶካ ድረስ በመሸኘቱ፣ አቶ ዓድሐኖም ከነጓደኞቹ በአቶ እሸቴ ዓለሙ ድፍረት በእንግሊዝ መንግሥት በጥብቅ የተከለከለውን ብረትና ጥይት ይዘው ከከሰላ በገዳሪፍ ከተማ ዶካ፣ ከዚያም አርማጭሆ በመግባታቸው እንደ አንድ ከፍ ያለ ጥበበኛው ዘዴ ታሰበ፤ እንኳንስ ብረትና ጥይት ባንድ ኢትዮጵያዊ አርበኛ መገኘቱ ይቅርና ባንድ ቀልሃ ፪ ዓመት ስለሚያሥር፣ በዚሁ የብረት መተላለፉ አደጋ እንዳይደርስብን በብዙ ፈራን፤ ተጨነቅን። በሱዳን መሬት ነዋሪዎች ሆነው የኢትዮጵያን አርበኞች በጉልበታቸውና በገንዘባቸው፣ በምክራቸውም ርዳታ ይረዱ የነበሩ የወላይታ ተወላጅ የዛሬው ፊታውራሪ አቶ ኃይሉ ተሰማና አቶ እሸቴ ዓለሙ፣ ኤርትራዊ አለቃ ክፍለ፣ እነዚህ ኢትዮጵያውያኖች ለተወደዱ ወገኖቻቸውና ለገነትዋ የተዋበች ሀገራቸው ንፁህ ለሆነ ልቦናቸው ስለ ከፍ ያለ ባለዋጋ አገልግሎታቸው ሕያው መታሰቢያ ታሪክ ለስማቸው ይገባቸዋል።” ገጽ 189

“የጸገዴን አርበኞች ለመረከብ ጣሊያን ፩ድ ኮሎኔል ገዳሪፍ ላከ፤ አርማጭሆ ጥሰው ሸቀጥ ለመግዛት ፸፭ አጋሰሶችና ፳፭ ሺህ ብር ይዘው ገዳሪፍ ስለገቡ፤ ለስሙ ብቻ የኢትዮጵያ ገዥ ነኝ የሚለው የጣሊያን መንግሥት እጃቸው እንዲሠጠው ፎከረበት። የእንግሊዝ ባለሥልጣኖች የጣሊያንን ፖለቲካ በመፍራት ኢትዮጵያኖቺን በመሰዋት ለመርዳት ተነሱና እጃቸውን ይዘው በስውር አሳልፈው ለመስጠት ስለ ተስማሙ፤ የጣሊያን መንግሥት ጸገዴዎችን የሚረከብለት ፩ድ ኮሎኔል በካሚየኖች ሊወስዳቸው ገዳሪፍ መጣ። የፖለቲካ ክፍል የሆነ የእንግሊዝ ሃገረ ገዥ ከብላክሊም ጋራ ተነጋገሩና ይህ የጣሊያን ኮሎኔል አስገድዶ እንዲወስዳቸው ፈቀደለት።” ገጽ 190

እኔም ዋና ሆነው ለመጡ አቶ ብርሃኑ “በሀገራችን በጸገዴ ጣሊያን የሚሉት ገብቶ አታውቅም፤ ለወደፊቱም አይገባም። እኛም የእንግሊዝን መንግሥት ወዳጅነት ተማምነን እቃ ለመግዛት መጣን እንጂ ጣሊያን ወንድ ከሆነ እመንገድ ይጠብቀን። እናንተስ ሀገራችሁ ብንመጣ እጃችንን ይዛችሁ ለጠላታችን ለጣሊያን አሳልፋችሁ ትሰጡናላችሁ። የዓለም ነገሥታትስ ምን ይሉናል ብላችሁ ለስማችሁ አታስቡም ወይ? ብለው በድፍረት ቃል በጣሊያን ፍቅር ለታወረው ብላክሊ ይንገሩት” ብዬ አስጠናሁዋቸውና ተናገሩ፤ ቢናገሩትም “በጣሊያን እጅ ገብታችሁ ትሄዳላችሁ፤ ገዥያችሁም የጣሊያን መንግሥት ነው” ሲል መሰከረ።” ገጽ 190

“በዚህ ጊዜ የገዳሪፍ ምክትል ሀገረ ገዥና ዋናው ጸሐፊ የኤርትራ ተወላጅ አፈንድ ሚካኤል በኪት “በእንግሊዝ የሱዳን ግዛት የገቡት የኢትዮጵያኖች እጃቸው ለጣሊያን አይሰጥም” ሲሉ አሉ። ከጸገዴዎቹም የሥልክ ዋጋ ከነመልሱ ፶ብር ተቀብለው ለሱዳን ጠቅላይ ገዥ ካርቱም የሥልክ ቃል አሳለፉላቸው። “የኢትዮጵያውያኖች ዕቃ ሳይገዙ ለጣሊያንም እጃቸው መስጠቱ ቀርቶ በመጡበት መንገድ መልሳችሁ ከግዛታችን ውጭ አስወጥታችሁ ነጻ ልቀቁዋቸው” የሚል መልስ ስለመጣላቸው በኅዘን ተቃጥሎ የነበረው የኢትዮጵያ ሕዝብ በረደ። በሱዳን ያለነው የኢትዮጵያ ስደተኞችም ጭምር እጃቸውን ስጡኝ እያለ እሳት ለብቦ እሳት ጐርሶ ሲፎክር የነበረው ጣሊያን እፍረትና ውርደት ተሸክሞ በሱዳኖች እየተሳቀበት መተማ ተመለሱ። በመንገድ ጠብቀን እያሉ በእንግሊዝ ወታደር ተገድደው የመጡትም ጸገዴዎች ጠረፍ እንደደረሱ ከቀበሩበት ብረት ብረታቸውን መዘዙ እንኳንስ ለጣሊያን ለእንግሊዝም አስፈሩትና ጣሊያን ድፍረት አጥቶ በመንገድ ሳይጠብቃቸው ፈርቶ ቀረ፤ እነሱም ሀገራቸው ገቡ።” ገጽ 191

እኔም በእነዚያ በግፍ ታሥረው ከከሰላ ለጣሊያን የተሰጡት ኢትዮጵያኖች መታሠር ምክንያት ነገሩን ለመመርመር ብዬ እየሰጋሁ ጥር ፪ ቀን ፲፱፻፴፪ ዓ.ም. ከገዳሪፍ ከሰላ ወርጄ በስውር ወሬአቸውን ብጠይቅ፣ ወኸኒ ቤት ገብተው መታሠራቸውንና የሞት ፍርድ የተፈረደባቸው መሆኑን አረጋገጡልኝና ተስፋ በመቁረጥ በመረረ በኅዘን ገዳሪፍ ተመለስሁ። ስመለስም ከባህር ዳር በአረዮፕላን አሥመራ የመጣ ወጣት አገኘሁና ጣሊያንን አመስጋገነልኝ፤ በትዕግስት ካዳመጥሁት በኋላም “አንተ የመጣኸው ለጣሊያን ስለላ ነው፥ እኔ ግን ፲፬ በጦሎኒ በባህር ዳር አጠገብ በኢልማና ደንሳ ድል ሆነው ማለቃቸውን፣ በቅርብ ቀን ከደጃዝማች መንገሻና ካቶ ጊላ ጊዮርጊስ ጣሊያን ሽባ መሆኑን ብዙ ደብዳቤዎች ደርሰውኛል። አንተም ከጐጃም ለስለላ መምጣትክን ለእንግሊዝ አመልክቼ ከማሳስርህ ይልቅ እውነቱን ብትናገር የተሻለ ነው” ስለው እውነት ለማስጠቃት እምችል መስሎት ደነገጠ።” ገጽ 191

“እውነት ነው፤ የጣሊያን ጦር ሠራዊት በያለበት በኢትዮጵያ አርበኞች መከበቡንና ድል መሆኑንም ርግጥ ነው። እየደከመ በመሄዱና ሰውን በመግደሉና ባለማመኑም የተነሳ ኃይሉ እየተቀነስ መኸዱን፣ መሸነፉም የማይቀር መሆኑንም ካረጋገጠልኝ በኋላ ወደ ካርቱም በዚያው ባቡር ወረደ። ይህ ልጅ በመጨረሻ በሶባ ኢትዮጵያዊ ወታደሮች ሠልፍ ውስጥ ገብቶ ሲማር ነበር፤ እኔንም ባዬ ቁጥር ሰላይነቱን እንዳልናገርበት በብዙ ፍራት ይሸሸኝ ነበር። እኔ ግን በዚያን ጊዜ ቸል ያልሁት አንድን ሰው በማጥቃት ኢትዮጵያ አለመመለስዋንና እንግሊዞችም ከኛ ይልቅ ጣሊያንን በመርዳታቸው ነው። ጸገዴዎቹም ገንዘባቸውንና ከብቶቻቸውን ይዘው ያለ ስጋት ሀገራቸው ገቡ። በዚያው ሀገር ረኃብ ሆኖ ጫብለ ሲበላ የነበረውም በረደ። በዚሁም ጊዜ በአርማጭሆ የነበረው አርበኛ አዝማች ፊታውራሪ ባህታ፣ አቶ ሕደጐ፣ ብዙ አርበኞችም ሲሞቱ ባለምባራስ አሸብር ገብረ ሕይወትና አቶ ዓድሐኖም፣ አቶ ወልዳይ ደህና ሆነው በቁል ሐወሣ ገቡ።” ገጽ 191

የዚሁ ምእራፍ ቀጣይ ክፍል ስለ ደፋሯ የሴት አርበኛ ወይዘሮ ከበደች ሥዩም መንገሻ ወደ ሱዳን መሰደድ፣ ስለ ሻለቃ መስፍን ስለሽና ብልሃተኛው ጋይንቴ ብላታ ታከለ ወልደ ሐዋርያት እንዲሁም ግራዝማች ዘውዴ አስፋውና ሌሎች የዚያን ግዜ ክስተቶች ገረፍ ገረፍ አድርገን እንመለከታለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 23 Jul 2020, 02:16

ለዛሬ ታርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ መጣህፍ የምዕራፍ ሰላሳ ዘጠኝ ክፍል የሆነውን ስለ የሴት አርበኛዋ ከበደች ሥዩምና “አጼ በጉልበቱ” ስላሉት ስለ አርበኛው በላይ ዘለቀና ስለ ብልሃተኛው ጋይንቴ ብላታ ታከለ ወልደሐዋርያትና ስለነ ኤርትራዉያኖቹ አርበኞች ሻለቃ መስፍንና ሻለቃ ኢሳይያስ እንዲሁም ሌሎች አርበኞችም ገድል የሚተርከውን ክፍል ከባህር በጭልፋ እንቃኛለን። መልካም ንባብ! :mrgreen:

“ደፋር የሴት አርበኛ ወይዘሮ ከበደች ሥዩም ሱዳን መሰደድ፦ ጀግናነት ከዘር፣ ከእውቀት ከትምሕርት ስለሆነ የባታቸውና የአያታቸው የሰማዕቱ አጼ ዮሐንስ ወደረኛ የሌለውን ጀግናነትና ቆራጥነት ሲመስክሩ፣ ወንዶቹ ወደ ጣሊያን ሲገቡ ወይዘሮ ከበደች ሥዩም መንገሻ የጠላት ዓይን አላይም ብለው አርበኛ በመሆናቸው፣ ደፋር የሴት አርበኛ የተባሉ እስከ መጨረሻ የአያቶቻቸውን ጠላት የሆነውን የጣሊያን መንግሥት ሳይዩ በአርበኝነት የኢትዮጵያ ትንሣኤ ድረስ ኅሳባቸውን ሳይለውጡ በሃይማኖታቸው በመርጋታቸው ለራሳቸው ተመስግነው ሀገራቸውንም አስመስገኑዋት። የዛሬው ደጃዝማች የሻለቃ መስፍን ስለሽና የዛሬው ደጃዝማች ብልሃተኛው የጋይንት ተወላጅ ብላታ ታከለ ወልደ ሐዋርያት፣ የዛሬው ደጃዝማች ግራዝማች ዘውዴ አስፋው ጋር ሆነው በሸዋ መሬት እየተዘዋወሩ ብዙ የጀግናነት ሥራ ከሠሩና ጠላትንም ለማጥቃት ከቻሉ በኋላ ሀገሩ-በሁለቱ ጦር ሠራዊቶች ስለተበላና ጠላትም በእሳት ስላቃጠለው ወደ ጐጃም ተሻገሩ።” ገጽ 192

“በጐጃምም ቢሆን ጣሊያን በአረዮፕላን ኃይልና በጄኔራል ጋሊያኖም ድፍረት ቁጥር በሌለው ሠራዊቱም በሰፊ ዙሪያቸውን እየከበበ ብዙ ወራት የጥይት በረዶ ቢያዘንብባቸውም ቀጥ ብለው በድፍረትና በበርታት ጣሊያንን አስጨንቀው ወጉት። አስጨንቀው ቢወጉትም የጣሊያን ብርና ፖለቲካም እንዳይስማሙ ሸዌ ጐጃሜ ተባብለው እንዲጣሉና አንድነትና ስምምነትም እንዳያገኙ አድርገው ለያዩዋቸው።” ገጽ 192

“በመጨረሻም ግን የጣሊያን ሠራዊት ሁሉ እየተሰበሰበ ሌት ተቀን የሻለቃ መስፍንንና ብላታ ታከለን ብቻ አደጋ በመጣል ስላሰቃያቸው፣ በማያውቁት ሀገርና በማያውቃቸው ሕዝብ በቂ ርዳታ ባለማግኘታቸው ምክንያት አርበኞቹን ሰብስበው ደፋር የሴት አርበኛ ወይዘሮ ከበደች ሥዩምን ከነ ሕፃኖቻቸው ወደ ሱዳን ጠረፍ አድርሰው ለመመለስ ምክር መክረው፣ ውሳኔ ወሰኑ። በወንበራ ዞረው በዱር በገደል በረሃ የሆነውን ወሰን የሌለው ምድረበዳ አቋርጠው በሱዳን ጠረፍ እስከ ደረሱ ድረስ የጣሊያን ጦርና አረዮፕላኖች ለመደብደብ፣ ለማጥቃት መፈለጋቸውን ምንም አላቋረጡም ነበር። ቢሆንም የእግዚአብሔር ጥበቃ ስላልተለያቸው አሰቡበት ሀገር ደረሱ። ከመድረሳቸውም በፊት በሬዲዩ ብበመነጋገር ጣሊያን እና እንግሊዝ ተመካከሩባቸው።” ገጽ 192

ተንኮለኛ የእንግሊዝም ማለቅያ የሌለው ፖለቲካ ሰላማዊ መሰሎ ንጉሣችሁ እኛ ዘንድ ናቸው፤ እናንተም ከነብረታችሁ ግቡና ተቀመጡ ብሎ በማባበሉ አምነው በግንቦት ወር ዓ.ም. ሪስሪስ ገቡ፤ እንደሰነበቱም የማታለል ዕድልና መሳይ የሌለው የፖለቲካ ስጦታ ያለው፣ የዓለምን ሩብ ግዛት በእጁ የጨበጠውን የእንግሊዝ መንግሥት በጦርነት፣ በችግር፣ በረኃብና በበሽታም የመነመኑትን የኢትዮጵያ አርበኞች ከፋፍሎ በተናቸው፣ በኋላም ዙሪያቸውን በጦር አስከብቦ ብረታቸውን በመጋዜን እንዲያስገቡ አዘዘ፤ አናገባም ሲሉትም የኔ ወታደር ብረት በመጋዜን ተሰብስቦ ሲቀመጥ የናንተ እምቢታ ስለምንድን ነው? ብሎ ሲከራከራቸው፣ ሰውም አናስረክብም በሚልና እናስረክብ በሚል በኅሳብ ተለያዬ። ከዚህ በኋላ የኢትዮጵያና የጣሊያን በያይነቱ መሣሪያ በጥበባዊ ዘዴ እንግሊዝ መጋዜኑን ሞላ፤ የፈቀዳችሁ ቦታ ዝለሉ ብሎ ሰውንም አሰናበተው። በሱዳን መሬት ለኢትዮጵያ ስደተኞች ሥራ እንዲሠጣቸው እንግሊዝ አልፈቀደም፤ ያልፈቀደበትም ምክንያት ኢጣሊያን እጃቸውን ስጠኝ፣ ያለዚያም ሥራ አትሥጣቸው፣ የምታሥወጋኝ ጠላቴም አንተነህ እያለውና ራሱም እንግሊዝ አልገዛም ለሚለው ሰው ደመኛው ስለሆነ የኢትዮጵያ ስደተኞች ሥራ እንዳይሰጣቸው በስውር አስከልክሎ ሰው ሁሉ በርኃብና በኅሳብ ራሱ ዞሮ እብድ እንዲሆን አድርጎ አሰረው። ቢሆንም ታሪከኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጥቃትን ስለማይችል በቅጽበት ተበተነ፤ እየተመለሰም ወደ ኢትዮጵያ ባዶ እጁ ገብቶ በዱላ ከጠላቱ ከጣሊያን ብረት እየቀማ ብዙ ምሽግ ያስለቅቀው ጀመር።” ገጽ 193

“የሸዋን ቤተ መንግሥት መስርተው ያቋቋሙ፣ በዓድዋም የኢትዮጵያ የጣሊያን ጦርነት እንዲነሳ ያደረጉና ድልም የመቱን እኒያ ደፋር በኃይለኛነታቸው የሚያንቀጠቀጡት ሴት እቴጌ ጣይቱ ናቸው” ብሎ ኮንተ አንቶኒሊ ራሱ ጠላታቸው መሰከረላቸው። እንደዚሁ የእቴጌ ጣይቱ ብጡልን ጀግናነት የወረሱ ደፋር የሴት አርበኛ ወይዘሮ ከበደች ሥዩም መንገሻ የካርቱም ሕዝብ በክብር ከተቀበላቸው በኋላ መንገዳቸውን ወደ ግብፅ ቀጠሉ።” ገጽ 193

“ምድረ ግብፅም እንደገቡ የግብፅ ጋዜጣም “ጀግናይቱ የሴት አርበኛ ልዕልት ከበደች ሥዩም መንገሻ እንኳን በደህና ገቡ” እያለ ሕያው ባለ ታሪክ አቀባበል ተቀብሎ ሰፊ ምስጋና ስላቀረበላቸው የጣሊያን መንግሥትና ሕዝብ አፈሩ፤ አዘኑ። ፖለቲካዊ ስብከታቸውም ሐሰት መሆኑን ተረጋገጠ።” ገጽ 193

የዛሬው ጄነራል የሻለቃ መስፍንና ደፋሩ ብላታ ታከለም ባልታወቀ ምክንያት ስምምነትና ያንድነትን ምከር አጡ። ቢያጡም ዝም ብለው አልቀሩም፤ ከብዙ የኢትዮጵያ አርበኞች ጋር ሆነው አንድ ባንድ የሻለቃ መስፍን ጐጃም፣ ብላታ ታከለና የሻለቃ ኢሳይያስ አርማጭሆና ስሜን ወጥተው አርበኝነታቸውን ከዱሮ የበለጠ አድርገው በማስፋፋት ጠላትን አጠቁት። ከብሸና(ብቸና) እስከ ደብረ ማርቆስ ድረስ በሕዝብ የተሾመው የኢትዮጵያ ደም መላሽ አጼ በጉልበቱ በላይ ዘለቀ የጣሊያንን ጦርነት ሽባ ሲያደርግ፣ ደጃዝማች ነጋሽ ከበደና ደጃዝማች መንገሻ ጀምበሬ በመጣላትና በግዛት በመቀያየማቸው ምክንያት ተሰረዞ የነበረው ጣሊያን ለመመለስ ቻለ።” ገጽ 194

“በአርእስቱም ደፋር የሴት አርበኛ ወይዘሮ ከበደች ሥዩም መንገሻ ሱዳን መሰደድ፤ የተባለበትም ምክንያት፤ ጉድለት በሌለበት ድፍረትና ቆራጥነት በአርበኝነት መዋጋታቸው ይቅርና፣ ስደት በመሰደዳቸውም ለሀገራቸው ክብርና መልካም አርአያ በመስጠታቸው ተደንቆላቸዋል። የተደነቀላቸውም የደፋርዋ የኢትየጌ ጣይቱን የጀግንነት ጋሻ አንግበው በመነሳታቸው ነው።” ገጽ 194

በቀጣዩ ትረካችን “ዓለም ሁሉጊዜ የምትገለባበጠው ፍርድን በማጓደልዋ ነው” የሚል ርእስ ያለውን የአርባኛውን ምዕራፍ ይዘት እንቃኛለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:


Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 10 Aug 2020, 09:19

አርባኛውን ምዕራፍ “ዓለም ሁሉጊዜ የምትገለባበጠው ፍርድን በማጓደልዋ ነው” የሚለውን የአርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእን ታሪክ እነሆ! :mrgreen:

“እግዚአብሄር ራሱ ያልጠበቀውን ሕዝብና መንግሥት ምንጊዜም ቢሆን በምድራዊ ኃይል ሊጠብቅ እንደማይችል ራሳቸው ሲያውቁት እውነት በሌለበት አድልዎ በታወረ ፍርዳቸው “የኢትዮጵያን ጥንታዊ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት በጣሊያን ፋሺስታዊ ንጉሥ ሥር ፣ በታች ሆኖ መገዛት ይገባዋል” ሲሉ በሐሰት ፍርድ ቢፈርዱ፣ ቢፈርሙም፣ ይግባኝ በሌለው እውነተኛው የእግዚአብሄር ፍርድ ዕለቱን በመገልበጡ ፈረሰባቸው። ዓለምም ሁሉ ጊዜ የሚገለባበጠው በፍርድ ጉድለት መሆኑን ለመሰወር ዛሬም የሚደክሙ መንግሥታትና ስዎችም ባለመጥፋታቸው እጅግ ይሳዝናሉ።” ገጽ 195

ባለ ብዙ ወገንና ሀብት፣ ባለብዙ ሠራዊትና መሣሪያ፣ ባለብዙ አረዮፕላንና መርዝ፣ ከሆነው የጣሊያን መንግሥት ጋር ኢትዮጵያ ያለ አንዳች መሣሪያና ረዳት እግዚአብሔርን ተማምኖ ጥይት በሌለበት ነፍጥና ዱላ ፯ ወር ሙሉ የጨበጣ ጦርነት ሲዋጋ፣ ያለ ልክ ያፌዙበት የነበሩት ኤውሮጶች የመንግሥቱን ሥልጣን ገፈው ሀገሩንም ተካፍለው ዙሪያዋን ከበው ሲያስጨንቁት፣ ታሥሮ የነበረው የጀርመን ሕዝብ በእግዝአብሄር ረቂቅ ፍርድ ዛሬ ተነስቶ በቅጽበት ፖላንድና ልቱዋኒያን፣ ዳንማርክንና ቸክስሎቫክያን በ፲፱፻፴ ዓ.ም. በጥቂት ቀን ውስጥ አከታትሎ በመያዙ፣ ኤውሮጳ በኢትዮጵያ ላይ በፈረደችው የፍራትና የአድልዎ ፍርድ በብዙ ተጸጸተች።” ገጽ 195

“ፋሺስታዊ ዱቼ ሲኞር ቨኒቶ ሙሶሊኒም ወራዳ በሆነው ፍራትና ድንጋጼም ተከቦ በመጨነቁ ወደ ድል አድራጊው ጀርመን በስውር ተስማማ። የጣሊያንም የዋህ ሕዝብ ሙሶሊኒን ከጠቅላይ ሚኒስትርነቱ ሽሮ ከእንግሊዝና ከፈረንሣይ መንግሥታት ጋር ለመሠለፍና ኢትዮጵያን እንደያዘ ለመቅረት ምኞት መመኘቱን ስለተረዳ፣ ወደ አዶልፎ ሂትለር ዘንድ ኸጄ በዓለም ሰላም እንዲሆን ለመስማማት እሔዳለሁ ብሎ መጋቢት ፲፬ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ሙሶሊኒ ሂትለር ዘንድ ሔደና ተጐንብሶ እጅ ነሳው፤ ታማኝ ወዳጁ መሆኑንም ከገለጸለት በኋላ። “የጣሊያን ሕዝብ ጀርመንን በመጥላት ከፈረንሣይ ጋር ለመሠለፍ እኔን በሽረት ከማዕረጌ ሊያወርደኝ ይመኛልና ራሴን የሚጠብቅ ወታደር ስጠኝ” ብሎ ስለለመነው በኩራት የተበላሸው ሂትለርም ያለ ችግር ፻፶ ሺህ የጀርመን ወታደር ልኮ የጣሊያንን ሀገር ያለጦርነት ይዞ ቂሙን ተወጣ። ሀገሪቱንም እለቱን ደምስሶና አስገብሮ፣ አብያተ ክርስቲያኖችዋን ሰባብሮ፣ ደናግሎችዋንም አስነውሮ በማበላሸት፣ የጥንት ሐውልቶችዋን በመንጠቅ ወሰዳቸው።” ገጽ 196

“በየኢትዮጵይ የሰማዕታትና የጀግኖች ንፁህ ደም በማፍሰስ የሰከረው ሙሶሊኒ ግን አስቀድሞ ለየዋሁ የጣሊያን መንጋ ህዝብ “እኛ ኢትዮጵያን ስናቀና የትሪፓሊ ዐረብ እንዳይነሳብን የሚጠብቅልን የጀርመን ወታደር ሂትለር ርዳታ ልኮልናልና በክብርና በደስታ ተቀበሉት” ብሎ ሰብኮ በዘዴ አስገባቸው። የሚያስወጣቸው ወንድ ምንም አልተገኘም።” ገጽ 196

“ይህም ጀርመን፣ በኢትዮጵያ ጥፋት ተደስተው ሲስቁ በነበሩት የምዕራብ አውሮጳ መንግሥታት ላይ እንደ ማዕበላዊ አውሎ ነፋስ ተነስቶ በሚያዝያ ፩ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ዳንማርክና ኖርቨጃን ባንድ ሌሊት ሁለቱን መንግሥታትና ሀገሮች ያዛቸው። በዚሁም ሌሊት እንደ አጋጣሚ የኢትዮጵያ አርበኞች በዑምሓጀርና በመተማ መሓከል ካለው አብደል ራፊዕ ላይ ገጥመው ጣሊያንን ድል መተው ገድሉ፤ ብዙ መሣሪያም ማረኩ፤ መንገዱንም ፈጽመው ዘግተው መተላለፊያ ነሱት።” ገጽ 196

“ግንቦት ፪ ቀን ከጠዋቱ በ፫ት ሰዓት በዚሁ ዓመት ጀርመን እንደልማዱ በልጀክንና ሆላንድን ያዘ። በግንቦት ፩ ቀንም የበልጂክ ንጉሥ ለዮፓልዶ ከ፬፻ ሺህ ወታደር ጋራ ሆኖ እጁን ለባለድሉ ለጀርመን ሠጠ። ቆራጥዋ የሆላንድ ንግሥት ግን ሎንዶን ተሰደደችና ኢትዮጵያዊውን ሊቅ ሎረንሶ ትእዛዝን መርጣ ጠበቃ፣ አማካሪም አደረገች። ጀርመን በብዙ ሚሊዮን ወርቅ የተሠራውን እማጅኖ የተባለውን አስደናቂ ምሽግ በ፫ት ቦታ በኩል ሰብሮ ጉዞውን ወደ ምታንጸባርቅ ወደ ፓሪስ ከተማ ግንቦት ፲፪ ቀን ቀጠለ። የባህር ንጉሥ፣ የመርከቦች ባለቤት በሆነው እንግሊዝ ባህር ላይም ገብቶ ራሱ ጐትቶ ካመጣው በኋላ አፈንድቶ የሚያሰጥም ጥበበኛ ዘዴው አበጅቶ ያለ ልክ አሸበራቸው። ከመጨነቃቸውም ብዛት ብዙውን ነገር ኑዛዜ ተናዘዙ፤ ብዙ ሰዎችም በሎንዶን የፈረሱት አዳራሾች አለበሱዋቸውና ተቀብረው ቀሩ። በዚህ ጊዜ የእንግሊዝ ንጉሥ “ጀርመን ዓለምን በሞላው በእጁ ጨብጦ ለመግዛት ስለፈለገ ብለን ነው እንጂ ለጦርነት የተነሳን ስለቅኝ ሀገሮቻችን ብለን ባልተዋጋን ነበር። አሁንም ጸሎት አድርጉልን” ብሎ ዲስኮር ተናግረ።” ገጽ 196

“በሰኔ ፴ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ጀርመን እጅግ በተዋበችዋ በፓሪስ ለስላሳይቱ ከተማ ላይ ፪፻ ቶን ማለት ፪ ሺህ ፪፻ ቦምብ በጭካኔ ጣለባት። በውበትዋ በብዙ የተመሰገነችዋ ፓሪስም ተቃጠለች፤ ፀሐይ የመስለች የምታንጸባርቀዋም ከተማ በመሰባበርዋ ዓለም ኅዘን አዘነላት፤ ቢያዝንላትም ከመደምሰስም የሚያስጥላት አልተገኘም። ጀርመኖችም በሮችዋን አጥብቀው ለመዝጋት ብለው በኃይል እየተወናጨፉ አልፈው በጥብቅ ከበው አስጨነቁዋት፤ ብድራቸውንም በተከፈልዋት ጊዜ ኢትዮጵያን አስታወሱ፤ ለጣሊያን አሳልፈው በመስጠታቸውንም ተጸጸቱ።” ገጽ 197

አሰቃቂ ከሆነው የጦርነት መዓት ለመሸሽ “ኢትዮጵያ በጣልያን መገዛት ይገባታል” ብሎ በሓሰተኛው ፍርድ የፈረደውን ኤውሮጳ፣ በበለጠም ፈረንሣይ ወሰን በሌለው አድሎአዊ በሆነው ስሕተትዋ፣ ለንስሐ ሳትደርስ በጥንታዊ ጠላትዋ በጀርመን ሠራዊት ዙሪያዋን ተከባ በመደምሰስዋ በትልቅ ፍራት ተሸብራ ያለልክ ተንቀጠቀጠች፤ ፈጽማም አበደች፤ እራቆትዋን ወጣች፤ እጅዋንም ሰጠች። የጣሊያን መሪ ሙሶሊኒም ከሃዲ በሆነው ክህደቱ ተሽቀዳድሞ ወንድሙ ከሆነው ከፈረንሣዊ ሕዝብና መንግሥት ከድቶ፣ በጐን ገብቶ በጩቤ ወጋው፤ ኢትዮጵያን ሲወጋ ሳለ ፈረንሣይ የዋለለትን ውለታና ርዳታም ሰርዘው። የእንግሊዝ መንግሥት ጣሊያን በሚፈልገው ዓይነት ውል ተዋውሎ የቃል ኪዳን ጓደኛው ማድረግ በብዙ ማባበል ቢለምነው የኢትዮጵያን ስደተኞች ለማስረከብ ከአፍሪካም ብዙ ሀገሮች ለጣሊያን መለቀቁን ጥያቄ ቢያቀርብለት። ጣሊያን የእንግሊዝን ጥያቄና ወዳጅነት የኢትዮጵያ ሕያው አምላክ ሁለቱን ጓደኞች ስምምነት አሳጥቶ ለያያቸው፤ ለጦርነትም አሳልፎ አዋጋቸው። የተሰወረ የወዳጅነት ምስጢራቸውንም ያለ አንዳች ድካም ለማግኘትና ለመረዳትም ቻልን። የኢትዮጵያ ምስጋና ለእግዚአብሔር ይድረሰው።” ገጽ 197

የዓለም መንግሥታት ማኅበር መሪዎች በጄኔቭ ተሰብስበው ሊጠገን ወይም ሊሻሻል በማይቻል ወሰን በሌለው ስሕተታቸው ብዛት “በጣሊያን ለተያዘው የኢትዮጵያ መንግሥት ብለን ጦርነት አንስተን ሞላዋን ዓለም እሳት አቃጥለን አናጠፋምና እንደተያዘ ሆኖ ይቅር፤ እኛም ለወደፊቱ የሚጠቅመንን መሠረታዊ ስምምነት አበጅተን በሰላም እንድንኖር እናድርግ” ብለው ወሰኑ። በዚሁ አድላዊ የሆነ ውሳኔአቸው ወደ መታረድ እንደሚነዳ መንጋ መስለው ዓለምን ወደ ጥፋት በሚወስደው መንገድ ነዱዋት። እንደ የፈረንሳይ ሚኒስትር፣ እንደ ከሀዲው የጣሊያን ወዳጅና ረዳት የሆነው ላቫል በግሉ የራሱን ጥቅም ብቻ በመፈለጉ እንኳንስ ኢትዮጵያን ይቅርና የገዛ ሀገሩን ፈረንሣይን ለጀርመን ሸጦ ተይዞ በፈረንሣይ ሕዝብ ፊት ቀረቦ ከተገደለ በኋላ በከሃዲዎች መቃብር ተቀበረ። ይህ ላቫል ነበር ኢትዮጵያ ለጣሊያን እንድትሆን ብዙ ሚሊዮን ሊሬ ከጣሊያን ተቀብሎ ቀዳሚሆኖ የመሰከረ። የኢትዮጵያ ዋጋ አልበቃም ብሎት የገዛ ሀገሩን የሸጠ፣ የለወጠ፣ ኸሓዲው የፈረንሳይ ሚኒስቴር ነው፤ ለማይበላው ገንዘብ የሸጠ የለወጠ፣ ደላላም ሆኖ ሃገሩን ለገዛ ጠላቱ ለጀርመናዊ ሂትለር ያስረከበ፤ ጓደኞቹም ሁሉ ከሱ ከንቱ ኅሳብና ፍርድ ካልተለዩ ከሌላው ነገር ሁሉ አለመለየታቸውን ያስረዳል።” ገጽ 198

“እነዚህም የጄኔቭ መማክርቶች የኢትዮጵያ መንግሥት ብቻ ጠፍቶ ለዓለም ሕዝብና መንግሥት መስዋእት እንዲሆን ብለው ፍርድ ሲፈርዱ ሳሉ “ትቤላ ነፍስ ለሥጋ ምድራዊት አንቲ ለምንተ ተሐንጺ አብያተ ኅበ ኢትነበሪ ለዓለም” ((ነፍስ ምድራዊቷን ሥጋን “አንቺ ለዘለዓለም የማትኖሪበትን ቤት ለምን ትሠሪያለሽ አለቻት”)የሚለውን ቃል ዘንግተውት ነበር። እኛ በኃይላችን ብርታት፣ በሃብታችንና በመሳሪያችን፣ በሰራዊታችንም ብዛት፣ በፖለቲካችን ርቀትና ጥልቀት፣ ሞላዋን ዓለም እንደሰም አቅልጠን፣ እንደኳስ በእጃችን ጨብጠን፣በእግራችን ረግጠን እንገዛታለን ብለው ሲመኩ የነበሩትም መሪዎች አስመሳይ በሆነ ፍርዳቸው ሕዝባቸውንና መንግሥታቸውን ሲያስደመስሱ፣ ክብራቸውን ሲያሰርዙ በማየታቸው፣ የሰማያዊ አምላክን ችሎታና ሕያው ሥራ አደነቁ፤ ይህም ማለት፣ ደምሳሾቹ ሲደመሰሱ፣ ገዳዎቹ ሲገደሉ፣ መዋቾቹ ሕያው ሆነው ሲነሱ በጉልህ ታዩ፤ ማለት ነው።” ገጽ 198

እምነቱን በሙሉ በእግዚአብሄር ላይ ከማድረግ ምን ጊዜም ያላቋረጠው ደፋር፣ ጀግና፣ ባለታሪክ የኢትዮጵያ ሕዝብ ያለ መሣሪያና ያለ ስንቅ ጣሊያንን ፯ ወር የጨበጣ ጦርነት ሲዋጋ ሳለ እስያዎች ከልብ ሲያዝኑ ኤውሮጶች በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ አጥበቀው ተሳለቁ፤ እነዚህ ደንቆሮች መገዛት ላይቀርላቸው የመድፍና የመትረየስ፣ የጠብመንጃ አፈሙዝ እንጨብጣለን ሲሉ በጥይት በረዶ ውስጥ ገብተው በከንቱ ያልቃሉ” እያሉ በትምክህትና በኩራት ኢትዮጵያውያኖቹን ሲሳደቡ የነበሩት ኤውሮጶች ፭ት ዓመት በአርበኝነት በመዋጋታቸውና በእግዚአብሄር ላይ ያደረጉትም የማይናወጥ እምነት ከንቱ ሆኖ ባለመቅረቱ በመጨረሻ አመስገኑት።” ገጽ 198

“በእርእስቱም ዓለም ሁልጊዜ የምትገለባበጠው ፍርድን በማጓደልዋ ነው፤ የተባለበትም ምክንያት እውነት የሌለበት በአድልዎ በታወረ ፍርዳቸው ኢትዮጵያ ትጥፋ፣ ትሰረዝ ብለው ሲፈርዱ ወዲያው ራሳቸውን በማጥፋታቸው ነው።” ገጽ 198

በቀጣዩ የምዕራፍ አርባ አንድ ክፍል “የኔ የተስፋ ሚካኤል ስንቅ ፈጽሞ ማለቅና መቸገር፣ የዶክቶር ሎረንሶ ታእዛዝ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥትን ይዞ ወደ ካርቱም መምጣት” የሚለውን ትረካ እንኮመኩማለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 02 Sep 2020, 08:20

የአበርኛው የተስፋሚካኤል ትኩእን ትረካ እንቀጥላለን ለዛሬ “የኔ የተስፋ ሚካኤል ስንቅ ፈጽሞ ማለቅና መቸገር፣ የዶክቶር ሎረንሶ ታእዛዝ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥትን ይዞ ወደ ካርቱም መምጣት” የሚለውን ትረካ እንኮመኩማለን። በተለይም የአበርኛውን የዶክተር ሎረንሶ (መብራህቱ) ታእዛዝን ገድልና አስተዋጽኦ ፍንትው አድርገው ያሳዩናልና ንባባችንን እንቀጥላ! :mrgreen:

“በዚሁ እጅግ የመረረ ስደት ከመጨነቃችን በላይ የሱዳን በረኃ ሙቀት አቃጠለን፤ ስለ ኢትዮጵያም ነፃነት በኢትዮጵያ ውስጥ ሆነው ከሚጋደሉና በኬኒያ ተሰደው በእንግሊዝ ብረታዊ ቀንበር ታስረው ከሚላቀሱ፣ በሌሎች ሃገሮች ተሰደው ካሉት የኢትዮጵያ ልጆች ጋር ለመጻጻፍ፣ ከኢትዮጵያ ተልከው የሚመጡትን ወደ ኢትዮጵያም የሚመለሱትን እንግዶች መቀበያና መሳፈሪያም የሚሆን የገንዘብ ርዳታ አስፈላጊ መሆኑን ለጃንሆይና ለመሥሪያ ቤታቸውም ገንዘብ እንዲላክ በሰፊው ባስረዳም ተስፋ አላገኘሁም።” ገጽ 199

ለዚህ ትክክለኛ ጥያቄ በቂ መልስ ሳይሰጠኝ፣ የዓለምም ሕዝብ ለርዳታ ብሎ ከሚሰጣቸው የገንዘብ ርዳታ ለቴምብር እንኳ የሚሆን ለስደተኞች ሳይሰጡ አቶ ወልደጊዮርጊስና አቶ መኮንን በየቀኑ የኔ ደብዳቤዎች በፍጥነት እንዲደርሱላችው መፃፋቸውን ከዚህ ቀደም በሰፊው አስረድቻለሁ፤ ለኔ፣ ለኔ፣ ለራሴ፣ ለብቻዬ ከማለት ይልቅ ከጓደኞቼ ማለት የተሻለና ከሁሉም የበለጠ ያንድነትንና የስምምነትን መልካም ዘዴ ባለመገንዘባቸውና አንዳች ገንዘብም ሥራ እንዲሰራበት ለመስጠት አለመፍቀዳቸውን ከማሳሰብና ከማዘንም ምንም አላቋረጥሁም ነበር።” ገጽ 199

“እኔም በዚህ የመከራና የስቃይ ጊዜ ለኢትዮጵያ እንግዶች መቀበያ የሚሆን ገንዘብ ይቅርና ለራሳችን፣ ለእኔና ለባለቤቴ ልጆቼም አበባና ፀሓይ ሆነን “ምን ታደርገን ይሆን አምላኬ” እያልን ሌት ተቀን እንቅልፍና እረፍት አጣን። በዚሁ ውኃ እንኳ በማይጠገብበት ገዳሪፍ ስንቅ ፈጽሞ ማለቅና መቸገራችንንም ቢታወቅም ሀገራችን ነገ ስንገባ ያልፍልናል የሚል እምነት ብቻ ምግብ አድርገን ስንጠባበቅ፣ በኢትዮጵያ ላይ እሳት አቀጣጥለው ሲቀልዱባት የነበሩትን ኤውሮጶች ላይ መጣላትንና ችግርን አዘነበባቸው።” ገጽ 199

ጣልያንም ሁል ጊዜ የምትሠራውና የምታየው በመሪዋ በእንግሊዝ መንግሥት ዓይን በኩል ስለሆነና በቀጥታ ለማየት ችሎታ ስላልነበራት በዚሁም መንግሥት ተረድታና ታዛ መልእክተኛውም ሆና በ፲፰፻፸፰ ዓ.ም. ምጽዋዕን ለመያዝ በቃች። ቀጥላም በእንግሊዝ መንግሥት ርዳታም በናድርንና ትሪፓሊን፣ ኢትዮጵያንም ለመያዝ ያበቃትን የእንግሊዝ መንግሥት ረቂቅ ፖለቲካና የገንዘብም ርዳታ መሆኑን ከድታ ወደ ጥንታዊ ጠላትዋና ገዥዋም ወደሆነው ጀርመን ዞረች።” ገጽ 199

“ይህም የቃል ኪዳን ጓደኛችዋን ፈረንሣይና እንግሊዝን ከድታ፣ ጣሊያን ወደ ጀርመን መንግሥት መዞርዋ እግዚአብሔር ራሱ ኢትዮጵያን ለመርዳት ያደረገው ሕያው ተአምራት ነው።” ገጽ 200

“በዚህም የፈረንሣዊና የእንግሊዝ፣ ያሜሪካን መንግሥታት የጣልያንን መክዳት ምክንያት በማድረግ የኢትዮጵያን ንጉሠ ነገሥት እንደራሴ ዶክቶር ሎረንሶ ታእዛዝን ዕለቱን በእንግሊዝና በፈረንሣይ፣ በአሜሪካን መንግሥታት ለምክር ተጠርቶ ብርቱ ውይይት ካደረገና ከተከራከረ በኋላ ጃንሆይን ይዞ ካርቱም እንዲሄድና የኢትዮጵያ መንግሥት ጽሕፈት ቤት እንዲያቋቁም፣ የኢትዮጵያም መንግሥት የጦር ጓደኛው መሆኑን አውቀው ውሳኔ ወስነው ፊርማቸውን ሰጡት።” ገጽ 200

“ጀግናው፣ ደፋሩ አርበኛ፣ ሊቁ ፊታውራሪ መብራህቱ (ሎረንሶ) ታእዛዝም በማያወላውል ቆራጥነቱ ወዲያው ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ኃይለ ሥላሴን ይዞ በስውር ከሎንዶን በአረዮፕላን በሰኔ ወር ፲፱፻፴፪ ዓ.ም. ካርቱም ገቡ። የጃንሆይም ካርቱም መግባት ድርጅቱ እስኪከናወን ድረስ ለጊዜው ምስጢር ቢሆንም፣ ለሐማሴኔው ለፊታውራሪ መስፍን ረዳና ለኔ በፊታውራሪ መብራህቱ ስም ከገደሪፍ ተጠርተን በመጀመሪያ ግርማዊነታቸውን ተገናኘን።” ገጽ 200

ፊተውራሪ መስፍን አርማጭሆ ወጥተው ማሕተምና ጓንዴ ጠበንጃ ከነ ጥይቱ የተቀበሉትን እያሳዩ ለአርበኞች የምስራች እንዲነግሩ፣ እኔም ከአሥመራና ከጎንደር፣ ከጎጃም እስከ ሰቆጣ ጃንሆይን ፍለጋ የሚመጣውን የኢትዮጵያዊ እየተቀበልሁ ወደ ካርቱም በመንግሥት ኪሳራ እንድልክ ታዘዝሁ።” ገጽ 200

“ፊታውራሪ መብራህቱ ታእዛዝም በፍጥነት የኢትዮጵያ መንግሥት ጽሕፈት ቤት ካርቱም አቆመ። በኤውሮጳና በኢየሩሳሌም፣ በግብፅና በሱዳንም ተበታትነው የነበሩት የኢትዮጵያ ስደተኞችን ጠራ፥ አርበኞቹንም ከያሉበት በአዋጅ ሰበሰበ።” ገጽ 200

ፕሮፌሰር ተአምራት አማኑኤልም በተዋበ አማርኛቸው በአረዮፕላን የሚጣለውን ቃል አሰናድተው ማተሚያ ቤት እንዲታተም አደረጉ። የኢትዮጵያ ሕዝብ ከጣልያን እየከዳ ንጉሠ ነገሥቱን ፍለጋ ባንድ ጊዜ እንደ አውሎ ነፋስ ግልብጥ ብሎ መጣ፤ ኅዘኑም ወደ ደስታ ተለወጠ። ሊቁ ኢትዮጵያዊ ፊታውራሪ መብራህቱ ታእዛዝም ወዲያው ባለታሪክ በሆነው የኢትዮጵያ ንግሥት ሳባ ሜዳ ስደተኞችና አርበኞቹን ሰብስቦ የኢትዮጵያ መንግሥት አልጋ ወራሽ አስፋ ወሰንና ልዑል መኰንን ሳይቀሩ የጦር ሠልፍ በደንብ እንዲማሩ ተማሪ ቤትና እንግሊዞች አስተማሪዎችም አድርጎ ከካርቱም ውጭ አቆመ።” ገጽ 201

“ማታም ጡዋትም ዶክቶር ሎረንዞ ታእዛዝ ያለ ማቋረጥ ሶባ እየተመላለሰ “ከዚህ ቀደም ገነትዋ ኢትዮጵያ ሀገራችንን በጠላታችን በጣሊያን ያስነጠቅናት ካለ መማራችና ካለ መስማማታችን ነው። ዛሬም ለመመለስዋ በእውቀት ጎልምስና ልዩ ልዩ የጦርነት ሰልፍ ተምረን ጠንቅቀን ማወቅና መስማማትም አስፈላጊያችን ስለሆነ ሁላችን ትምህርት እንማር። ከጥሩ የባእድ ገዢም የወገን ገዢ መብለጡን አትዘንጉ እያለ ከማስጠናቱም በላይ ግርማዊነታቸው ይህን የጦር ተማሪ ቤት እንዲጎበኙለት ለመናቸው።” ገጽ 201

“ግርማዊነታቸውም የዶክቶር ሎረንሶን ኅሳብ ለኢትዮጵያ ኃይልና ብርታት፣ አንድነትም የሚሰጥ መሆኑን በመገንዘባቸው ከልዑል አልጋ ወራሽና ከልዑል መኮንን ጀምሮ እስከ ተራ ወርታደር ሰብስበው “በትጋትና በብርታት ተማሩ፤ የዶክቶር ሎረንሶ ታእዛዝንም ትእዛዝ ፈጽሙ” ሲሉ ኅሳቡን በመደገፍ አጥብቀው አስጠነቀቁአቸው።” ገጽ 201

ከዚህ መካከል አንዳንድ ምቀኛ ሰው ተነስቶ በዚሁ ሙቀትና አሸዋ ተውጠን ባፈር ላይ እየተንከባለልን አስገድደው የጦርነት ትምህርት እንድንማር ያደረጉን ፊታውራሪ መብራህቱ (ሎረንሶ) ታእዛዝ ናቸው። ልዑል አልጋ ወራሽና ልዑል መኮንን ሳይቀሩ የንጉሠ ነገሥቱን ልጆች ከማንም ሰው ጋር እኩል ሆነው ሰልፍ እንዲሰለፉ ማድረጋቸው ምን ቀራቸው - አልጋውን ወደ ሀገራቸው ወደ ኤርትራ ከማዞራቸው በቀር እያሉ በዲያብሎሳዊ ቅናታቸውና ምቀኝነታቸው ብዛት ለመስማት የሚቀፍ ወሬ አውርተው አስወሩ።” ገጽ 201

“ገና እኛ ካርቱም ሳለን ጣሊያንም ከኢትዮጵያ ፈጽሞ ለቆ ሳይወጣ የአርበኞቹን ልብ አሻከሩት። ይህ ሀገር ለኔ፣ ያን ሀገር ላንተ፣ ያኛውንም ለወንድሜ እየተባባሉ በተሰወረ ምስጢርና መሀላም ተስማሙ። መሠረትም መሠረቱ። በዚህም የራሳቸው ጥቅም ፈላጊዎች ከሆኑት የሸዋ ሰዎች ዘንድ በቀር እንደዚህ ያለው የመለያየት መጥፎ ሀሳብ ወይም አፄ ኃይለሥላሴን መጥላት በዚህ ጊዜ የነበረው የሌላ አካባቢ ኢትዮጵያዊ አልነበረም።” ገጽ 201

“ይልቁንስ ኢትዮጵያዊ የተባለ ሰው ሁሉ ሕይወቱን ሊገብርላቸው ባልጠላ ነበር። ዶክቶር ሎረንሶ ታእዛዝ ግን የእነዚህን በምቀኝነት አይናቸውን የታወሩ ኢትዮጵያውያንን በሞኖፖል ለመግዛት የሚሹ ሰዎች ኅሳብ ሁሉ ፈጽሞ በመሰረዝ ኢትዮጵያን ነጻ ለማውጣት ሌት ተቀን በድፍረትና በእውቀት ታገለ። ከካርቱም በአረዮፕላን ኬንያ ስደተኞቹን በሰልፍ ከጎበኘ በኋላ ለሥራና ለሰልፍ የሚሆኑትን የኢትዮጵያ ጎልማሶች ወደ ካርቱም በምድር ሲልክ ስደተኞቹ በቦረናና በማጂ እንዲዘምቱ አዘዘ።” ገጽ 201

“የኢትዮጵያ ስደተኞች ዘመቻ አንዘምትም አሉ ብሎ በሐሰት የጻፈውን የእንግሊዝ ዑፍሴር ወደ ኢትዮጵያ ለወደፊቱ እንዳይገባ ከከለከለው በኋላ ተመልሶ ከመጀር አንድሩስ ጋር ካርቱም መጣ።” ገጽ 202

ወጣቱ ለጋው የአከለጉዛይ ሊቅ ፊታውራሪ መብራህቱ (ሎረንሶ) ትእዛዝ ስም ያለ ልክ በዓለም መንግሥታት ዘንድ ታወቀ፤ ተወደደ፤ ተመሰገነ። በፍጥነትም ድርጅቱን አከናወነ። እንግሊዞችም በጣሊያን ተሸብረው የበርበራ ግዛታቸውን ለቀው አደራ ተሻገሩ። በሱዳንም መሬት ገብቶ የእንግሊዞችን ይዞታ ቃሮራና ከሰላን፣ ጋላባትንም ለጣሊያን ለቀቀለት። ይህም መለቀቅ ለየዋሁ የጣሊያን ሕዝብና ወታደር እውነት መሰለው፤ እንግሊዝ ግን ይህን ሁሉ መልቀቁ ሰነፍ ለመምሰልና ኃይሉንም በመሰወር ለመቆጠብ፣ የህንድም የ፺፭ ሺህ ጦር እስኪደርስለትና እሱም እስኪሰናዳ ድረስ ነው። ስለዚህም የእንግሊዝ መንግሥት ጠቅላይ ሚኒስትር ቻምበርሊን ሂትለርን ደስ ለማሰኘት በካናዳ የነበረውን መሣሪያ የሚሆን ብረታ ብረት ጦርነት የለም ብሎ ለጀርመን ሸጦ እጃቸውን ለማስያዝ የተሰወረውን ሥራ ስለሰራ፤ የእንግሊዝም የስለላ ክፍል ስለደረሰበት ሳይበቀሉት አልቀሩም። በዚሁም የጭንቃቸው ሰዓት እንግሊዞች ለኢትዮጵያ ሰው ያለ ልክ አከበሩት፤ ለወጣቱ ሊቅ ለአርበኛው ፊት አውራሪ መብራህቱ ሎረንሶ ታእዛዝም በአዋቂነትቱ ስለ የእንግሊዝና የኢትዮጵያ የጋራ ጥቅም ምክሩን በመቀበል፣ ቃሉንም ሊያከብሩና ሊቀበሉም የተገደዱ ሆኑ። ስለዚህ ፊታውራሪ መብራህቱ ታእዛዝ እንዳለ ይሁን ብለው አሉ። የፈቀደውን ብረትና ጥይትም ለኢትዮጵያ ሰው መሸከም እስኪያቅተው ድረስ ሰጡት። መልሰውም ለመውሰድ እንዳይችሉ ተጠነቀቀባቸው።” ገጽ 202

"በአርእስቱም የዶክቶር ሎረንሶ ታእዛዝ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ይዞ ካርቱም መምጣት የተባለበት ምክንያት ለኢትዮጵያ ነፃነት የደከመና ከዓለምም መንግሥታት በእውቀት ተከራክሮ ያስረዳ፣ በእግዚአብሔር ኃይልም ታግሎ ኢትዮጵያን ለነፃነት ያበቃ ዶክቶር ሎረንሶ ታእዛዝ መሆኑ የማይካድ ነው። ለዚሁም ጠላቱ ጣሊያን ሳይቀር መስክሮለታል፤ ይመሰክርለታልም።" ገጽ 202

በቀጣዩ የምዕራፍ አርባ ሁለት “የኔ የተስፋ ሚካኤልና የሻለቃ መስፍን መከራከር፣ የግርማዊ ጃንሆይ ከካርቱም በአየር ገዳሪፍ መምጣት” በሚል ርእስ ስር ያለውን ትረካ እንኮመኩማለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Meleket
Member
Posts: 3044
Joined: 16 Feb 2018, 05:08

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Post by Meleket » 25 Sep 2020, 04:51

በዛሬው የአርበኛው የተስፋሚካኤል ትኩእ ትረካ፡ ምዕራፍ አርባ ሁለት “የኔ የተስፋ ሚካኤልና የሻለቃ መስፍን መከራከር፣ የግርማዊ ጃንሆይ ከካርቱም በአየር ገዳሪፍ መምጣት” በሚል ርእስ ስር ያለውን ይዘት እንኮመኩማለን። አርበኛው በተጨማሪም ስለ ሐማሴኔው ሙንጣዝ፣ ስለ የዛናው ትግሬና ስለ ወልቃይቴው ተስፋይ አኩሪ ገድል ይተርኩልናል። የኢትዮጵያውያኖች በሽታ ብለው ለሰየሙት በላይ ኣሉላ ስለተባለው የአገው ምድር ተወላጅ የጣሊያን ሰላይም መሰሪ ተልዕኾውንና አመሻሽ ላይ ያጋጠምውን ጉዳይ ይዘከዝኩልናል። መጨረሻም በሳቸው አመለካከት የኢትዮጵያ ሕዝብን ባህርይም ለመግለጽ ሞክረዋል፡ እስቲ እናንብባቸው! መልካም ንባብ! :mrgreen:

“የዛሬው መጀር ጀነራል የሻለቃ መስፍን ስለሺ ከካርቱም ጎጃም ተመልሰው የጃንሆይ በእውነት መምጣን ስለሰሙ ፯፻፶ የሚሆኑ አርበኞችና በቅሎችና አጋሰሶችም ይዘው ገዳሪፍ ገቡ። እኛም የምናስተናግድበት የበቃ ውኃ እንኳ ባይኖረን በብዙ ደስታ ተቀበልናቸው። አርበኞቹም የደጋ ሰዎች በመሆናቸው ከዚህ የቆላ ሙቀት ጋር አልተስማሙም። የሻለቃ መስፍን የካርቱምን ሙቀትና ችግር የማያውቁ መስለው ያመጡዋቸውን አርበኞች ይዘው ሰልፋቸውን ለማሳየት ተፋጠኑና ካርቱም እንወርዳለን ሲሉኝ፣ ሐምሌ ፳፩ ቀን ፲፱፻፴፪ ዓ.ም. ግርማዊነታቸው በሰጡኝ ትእዛዝ መሠረት ይህን ያህል ጦር ይዘው ይህነኑ የጦርነት ልብስ እንደለበሰ የመውረጃውና የመመለሻው የባቡር ክሳራ፣ የቤቱ ክራይና የምግቡ ወጭ ስናመዛዝነው በባቡር ካርቱም ለመውረድ አይፈቀድለዎትም ስላቸው የሻለቃ መስፍን ስለሺ ተቆጡ፤ ከኔ ጋራም ከፍያለውን ክርክር አምጥተው ከአከራከሩ፤ በኋላ “የናንተን በከንቱ ካርቱም መውረድ ከሚያመጣብን ወሰን የሌለው ጉዳትና ኪሳራ በላይ ብዙ ጊዜ የሚፈጅብን ስለሆነ ሥራችን መልካም ርምጃና ፍጥነትም እንዲያገኝ ግርማዊ ን.ነ.አጼ ኃይለሥላሴ በአየር ገዳሪፍ ቢመጡ ከሁሉ የበለጠና የተቻለም ነው” ስላቸው የሻለቃ መስፍን ኃሳቤን በደስታ ተቀበሉትና ጃንሆይ ኣንዲመጡ ስለተስማማን ለግርማዊነታቸው ቴሌግራም ተላለፈ።” ገጽ 203

ግርማዊ ጃንሆይ በኢትዮጵያ መሳፍንትና መኳንንት በእንግሊዝም ኮሎኔሎች ታጅበው በአዳኝ አረዮፕላኖች ተከበው ወዲያው ገዳሪፍ መጡና የሻለቃ መስፍንን አርበኞች ሰልፍ በብዙ ደስታና ሳቅ ካዩ በኋላ በገዳሪፍ ነዋሪዎች የሆኑ የኢትዮጵያን ሰዎች እንዳቀርብላቸው አዘዙኝና አንድ ባንድ አቅርቤ አነጋገሩዋቸው። እንደዚሁም የገዳሪፍ አውራጃ አገረ ገዢዎች በአጼ ዮሐንስ ጊዜ በሹም ደህና ፈንታ በታች ሆኖ ገዳሪፍን ሲገዛ የነበረው ወዛያድ ሲቀር ምስለኔዎቹ በገዳሪፍ የተገኙት ከግርማዊነታቸ ዘንድ ቀርበው እጅ ነሱ፤ ከነሱም መካከል የኤል ፋሽር ተወላጅ የዶካ ገዥ የሆነ ናዝር አብዱላሂ “ግርማዊነትዎን እጅ ለመንሳት ካርቱም ወርጄ ሳለሁ የናተን እክል ስለሰማሁ ሳላገኝዎት በመመለሴ አዘንሁ” አላቸው። ግርማዊነታቸውም “ለኢትዮጵያ በብዙ መርዳትህን ሰምተናል” ሲሉት “እኔ የኢትዮጵያ ጎረቤት ነኝ፤ እና ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያውያኖቹን የመርዳት ግዴታ አለብኝ” ሲል መለሰላቸው።” ገጽ 203

“እኔም ሰዎቹን ሁሉ ካሰናበትሁ በኋላ ሀገራቸውን አፍቃሪዎች የሆኑትንና ጣሊያንን ከድተው በየበኩላቸው የመጡትን ፫ት የኢትዮጵያ ወጣቶች ከፍ ያለ የሚያስቸኩል ጉዳይ የያዙ መሆናቸውን ተረድቼ አነጋገርሁዋቸው።” ገጽ 204

፩ኛ የሐማሴን ተወላጅ የሆነ ሙንጣዝ የሰቲትን የጣሊያን ፈረሰኛ ጦር የተሸሸገበትን ዱር አሳያለሁና ያለ ድካም በአረዮፕላን መትረየስ ተመተው እንዲረግፉ፣ ”ገጽ 204

፪ኛ የዛና ትግሬ ሰው ነኝ፣ ጣሊያንም አስገድዶ ለዘመቻ አመጣኝ፤ ከጦር ግንባርም ከድቼ መጣሁ፤ ጠላታችንም ኩዶ ፈላሲ ከሚባል ሀገር የተሸሸጉትን አረዮፕላኖች አሳያለሁ አለ፤” ገጽ 204

፫ኛ ተስፋይ የሚባል የወልቃይት ሰው እኔ መተማ ከመጣው በጠላት ጦር ሰራዊት ተገድጄ ወታደር ነበርሁ:: አሁን ግን እግዚአብሔር ከታረቀንና ንጉሠ ነገሥታትንም ከመጡልን ለሀገሬ እረዳለሁ ብዬ መጥቻለሁና የጠላት ጠቅላይ ጦር ኣዛዥ ዋናው ኮሎኔል ከተሸሸገበት ጉድጓድ በ፮ ሰዓት ሲወጣ ላስገድላችሁ እችላለሁ አለ።” ገጽ 204

“ግርማዊ ሆይ እነዚህ ሰዎች ገና ወደኔ በዚህ ሰሞን እንደ ደረሱ አስፈላጊውን ጥያቄ ጠይቄ ራፕራቸውን ጽፌ በፍጥነት በዶክቶር ሎረንሶ ታእዛዝ በኩል የሁለቱንም ልኬለዎታለሁ። ከመተማ የመጣው ግን ገና ሁለት ቀኑ ስለሆነ ተጽፎ በመላክ ላይ ነው ያለው” ስላቸው ጃንሆይም ለዚህ ሁሉ ኃላፊና እንደራሳቸውም የሆነውን ፊታውራሪ መብራህቱ ታእዛዝን ሲጠይቁት፡ “ ስለነሱ የተፃፈ የአቶ ተስፋሚካኤል ትኩእ ራፖር ደርሶን ከእንግሊዞች ጋር በሰፊው ተነጋግረንበታል” አላቸው፤ ግርማዊ ጃንሆይም እነዚህን ፫ት የኢትዮጵያ ወጣቶች በብዙ ካመሰገኑዋቸው በኋላ ወደ እንግሊዞች ተላልፈው በአረዮፕላን በረው እንዲያሳዩን መልካም የጀግናነት ሥራ እንዲፈጽሙ አድርገው ላኩዋቸው።” ገጽ 204

ሐማሴነው ሙንጣዝ በማግስቱ የሰቲት የጠላት ፈረሰኛ ጦር እንዳለ በሙሉ ለእንግሊዙ አረዩፕላን አዛዥ አሳየውና ወዲያው በመትረየስ አስፈጃቸው፤ በዚህም የፈረሰኛ ጦር ማለቅ ምክንያት ከሰላ ገብቶ የነበረወ የጄኔራል ፍሩሺ ጦር ሰራዊት ወግ የሌለው ሽሽቱን ጀመረ፤ በዚሁም ቀን የዛናው ጠንካራ ልጅም እንደሰጠን ቃል ኩዶ ፈላሲ የተሸሸጉትን ፴፮ የጠላት አረዮፕላኖች አሳይቶ በማስቃጠሉ (እንዲቃጠሉ በማድረጉ) ገዳሪፍን ሌት ተቀን በቦምብ አቃጠሉ። ብዙ ሰውና ቤት በ፯ አረዮፕላኖችም ስላቃጠሉት መድረሻ አጡ፤ የወልቃይት ተስፋይም የመተማ የጠላት ጦር ኣዛዥ ኮሎኔል ልክ ፮ት ሰዓት ከ፭ ደቂቃ ከተሸሸገበት ጉድጓድ እንደወጣ ሰውዬውን አሳዬና የአረዮፕላኑ ኣዛዥ እንግሊዝ በቦንብ ቆራርጠው። አርበኛው ጀግና ብላታ ታከለ ወልደ ሐዋርያትን ከቦ ለመማረክ አድርሶዋቸው የነበረው የጠላት ጦር በዚሁ ጦር ኣዛዥ መሞት ምክንያት ድል ሆነ። የዛሬው ደጃዝማች የጋይንቴው የብላታ ታከለን እውቀትና ድፍረት፣ ጅግነትም ለታሪክ ፀሐፊ ትተነዋል።” ገጽ 205

ክፉ ሥራ የሰራ ሰው ምንጊዜም ቢሆን የጁን አያጣምና ልክ በዚሁ ቀንና በዚሁም ሰዓት ሰማያዊ (አምላክ) ጉልህ በሆነው ቅጽበተኛው ምስክርነቱን ኣሳየ፤ በላይ አሉላ የተባለ የአገው ምድር ተወላጅ ለግል የእለት ጥቅሙ ብሎ ወገኖቹንና ሀገሩን ለጠላቱ ለጣሊያን እየሸጠ የስለላ ሥራ ይሰራ የነበረ፣ የእንግሊዝ አረዮፕላን ቦምብ ክንዱን ቆርጦ እፊቱ በጣለበት ጊዜ፣ ይህ በላይ “እኔን ያየህ ተቀጣ፤ በሀገርህና በወገንህ ክፉ ሥራ አትሥራ” እያለ ፫ት ቀንና ፫ ሌሊት በሞት ጣር ተሰቃይቶ ሞተ።” ገጽ 205

“ይህነኑ የሰማያዊ አምላክ ሕያው ተዓምራታዊ ፍርድ ያየ ሰው ሁሉ አመሰግነ፤ በብዙም አደነቀው። ያደንቀዋልም። ግርማዊ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት በመጡበት መንገድ ማታ ወደ ካርቱም ሲመለሱ እጨጌ ገብረ ጊዮርጊስ የመንፈሳዊ ሥራ ለመሥራት፣ ዶክቶር ፊታውራሪ መብራህቱ ሎረንሶ ታእዛዝና አቶ ወልደአ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ ብረትንና ስንቅ ለሚመላለሱ አርበኞች እየሰጡ ለማሰናበት በገዳሪፍ ሰነበቱ፤ ብረትና ጥይት እንደልባቸው እየተቀበሉ ወደየ ሀገራቸውም በግስገሳ ሲገቡ ጠላት በብዙ ደነገጠ።” ገጽ 205

የእንግሊዝም ዘዴኛው መንግሥት ተላላኪውና ጠቃሚው ከሆነው የጣሊያን መንግሥት ጋር ለኢትዮጵያውያኖች ብሎ ለመጣላት ስለጨነቀው በ፲፱፻፴ ዓ.ም. ጀግኖች የኢትዮጵያ አርበኖች በህመም ወይም በመልአክተኛነት ወደ ሱዳን እንዳይገቡ፣ ወደ ሀገራቸውም እንዳይመለሱ፣ የገቡትም እንዲጠበቁ በወኽኒ ቤት እንዲታሰሩ አድርጐ እየተቆጣጠረ አስጨንቆ አስጠብቦ ስለጠበቀን ከልብ ረዳው፤ ሠራለትም። እንደዚህም አድርጎ እንግሊዝ እኛ ኢትዮጵያውያኖችን አስጨንቆ የጠበቀን ነገ ከወዳጁ ከጣሊያን መንግሥት ጋር እታረቃለሁ የሚል ሙሉ ተስፋ ስለነበረው ነው። በዚሁም ውስጣዊ የሁለቱ ስምምነት ጣሊያን ቁጥር የሌላቸው ሴቶች ሰላዮች ሱዳን ላከ፤ በላይ አሉላ የተባለ እንደሲቶቹ ወገኖቹን ለመሰለል ለጣሊያን ተቀጥሮ ሰላማዊ ሰው መስሎ በገበሬነት ዶካ ተቀመጠ፤ በነጋዴ ስም ካርቱምና መተማ ወደ ጠላት እየተመላለሰ በኢትዮጵያ ስደተኞችና አርበኞች ላይ በየጊዜው ብርቱ ጉዳትና ጥቃት አመጣብን፤ አደረሰብን።” ገጽ 205

በሌብነት የተወለደ የወንድ አሞት የሌለው የአገው ምድር በላይ አሉላ የያዘውን ሃብት ላይበላ፣ የማይበላውን ሀብት ፈለገ። ከዚህ ቀደም በሕዝብ ዘንድ ራስ ተብለው የሚዋጉት የጀግናው የአሞራው ውብነህ ተሰማ ባለቤት ወይዘሮ ዘነበችና ልጆቻቸው አርማጭሆ ለመሄድ ከገዳሪፍ በዶካ መንገድ ሲሄዱ ለጣሊያን መነሳታቸውን ነግሮት ተቃጠለ፤ ጉልበትና ድፍረትም ስላጣ ጣሊያን አስመሳይ በሆነ አታላይ ሐሰተኛነቱ ብዛት የአሞራው ውብነህ ተሰማን ባለቤትና ልጆች ማረክሁዋቸው እያለ እውነት አስመስሎ ስላስወራ እኔ እኒህን ሴት ከነልጆቻቸው በመላኬ በኃዘን ተከበብሁ፤ ሰዎቻችንም ሁሉ እውነት መሰላቸውና በያሉበት ተጨነቁ።” ገጽ 206

“ቀጥሎም ከካርቱም ጠፍተው የዛሬ ፊታውራሪዎች ካፒቴን ወርቁ አየለና የመቶ አለቃ ከበደ ይርዳው ፭ ራሳቸውን ሆነው በሌሊት እኔ ዘንድ ገዳሪፍ መጡ፤ ሽሽጌ ካሰነበትሁዋቸው በኋላ በስውር ወደ ዶካ ከማሳፈሬ በፊት “በላይ አሉላ የሚባል የጠላት መሣሪያ” መጥፎ ሰው አለና ዶካ ስትደርሱ እንዳትታዩት አደራችሁን ብዬ እየደጋገምሁ በብዙ አስጠነቀቅሁዋቸው። የኢትዮጵያኖች በሽታ የሆነው በላይ አሉላ ግን ዶካ እንደደረሱ አርበኞች መሆናቸውን ስላወቀ በጐን ሰው ልኮ እኔ መንገድ መርቼ አርማጭሆ አደርሳችኋለሁ ሲላቸው በ፴ብር ገዙትና ሲመራቸው በላይ ቀድሞ መተማ ገብቶ ለጠላት ነግሮ ቆዬ፤ መሪያቸውም ሰተት አድርጎ በመተማ ምሽግ ሥር አስቀምጦዋቸው በሽሽት አመለጣቸውና ተመለሰ፤ የበላይ አሉላ ሰው መሆኑን ተረዱት፤ በላይ አሉላ ባስላከውም ጦር ካሚዮን ድምጽ ነቅተው በወንዙ ጉድጓድ ሥር ተሸሽገው በታምራት ሳይታዩ ቀሩን የሚፈልጋቸው የጣሊያን ጦር እንዳለፋቸው፣ በብዙ ረኃብና የውሃ ጥም መከራን ከተቀበሉ በኋላ ወደ የሻለቃ መስፍን ጐጃም ደረሱ።” ገጽ 206

ጣሊያንም እንደልማዱ እነ ካፒቴን ወርቁ አየለን በመንገድ ያዝሁዋቸው፣ ያለ ምሕረትም ቅጣታችውን ይቀበላሉ ብሎ ሲያወራ ሰው ሁሉ ትልቅ ኅዘን አዘነ። እኔ ግን የጣሊያንን ወሬ ባላምነውም በላይ አሉላ ተቀብሎ መሸኘቱ ስለተነገረኝ ቃሌን ባለመጠበቃቸውና እኔው ሸኝቼ በመላኬም በካፒቴን ወርቁ አየለ ተናደድሁ፤ ይህንንም ነገር ዛሬ በነሱ ፊት ሳነሳው እጅግ ይመረኛል።” ገጽ 206

“ክፉ ሥራ የሚሠራ ሰው ሁሉ ምንጊዜም ቢሆን የጁን አለማጣቱን በላይ አሉላን ራሱን በቃሉ አናግሬው፤ ክንዱን ቆርጦ ጥሎም ስቃይ አሰቃይቶ፣ የሰው ደም የገበየበትን ገንዘብ ሳይበላ፣ ይሁዳ ሆኖ ሞተ። እንደዚህን ያለውን መከራ ከመስማት እግዚአብሄር ይሰውረን። ጀግናው፣ ደፋር፣ ሃይማኖተኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ ሰው አክባሪ፣ እግዚአብሄርን ፈሪ፣ እንግዳ ተቀባይ፣ ስለ ሀገሩ አፈር አጥብቆ ተጋዳይ፣ ጥንታዊ ባለታሪክ መሆኑ የተመሰከረለት ስለሆነ፣ ዛሬ ባንዳንድ የራሳቸውን የእለት ጥቅም ፈላጊዎችና ሐሰተኞች ሰዎች ምክንያት ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያኖች ምንም ሊታሙ ወይም ሊሰደቡ ከቶ አይቻልም፤ ስለምን ይህ የዛሬው መንፈስ ከውጭ ሀገር ሰዎች የወረሱት ስለሆነ።” ገጽ 207

“በአርእስቱ የኔ የተስፋሚካኤልና የሻለቃ መስፍን መከራከር፣ የግርማዊ ጃንሆይ ከካርቱም በአየር ገዳሪፍ መምጣት፣ የተባለበት ስለዚህ የኢትዮጵያ ስደትና ትንሳኤ ነው።” ገጽ 207

በቀጣዩ ክፍል ምዕራፍ አርባ ሦስት “የተስፋ ሚካኤል ትኩእ ከነባለቤቱና ከነልጆቹ ተጠርቶ ካርቱም መውረድ፣ የመጀር ኖት በኔ ማዘን” የሚለውን ትረካቸውን እንጋራለን። ቸር እንሰንብት!

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ ቅንነትን የተላበሰ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Post Reply