Ethiopian News, Current Affairs and Opinion Forum
eden
Member+
Posts: 9251
Joined: 15 Jan 2009, 14:09

Ethiopian Human Rights Commission Press Release

Post by eden » 07 Dec 2022, 21:22

Ethiopian Human Rights Commission – EHRC


በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በየጊዜው በሲቪል ሰዎች ላይ በሚፈጸሙ ጥቃቶች ምክንያት የተከሰቱ መጠነ ሰፊ ሰብአዊ ቀውሶችን በተመለከተ
December 7, 2022
Press Release

በክልሉ በሲቪል ሰዎች ላይ እየደረሰ ያለው ግድያ፣ አካል ጉዳት እና መፈናቀል መጠነ ሰፊ ምርመራን ጨምሮ እየደረሰ ካለው ከፍተኛ የሰብአዊ መብቶች ጥሰት ጋር የሚመጣጠን የፌዴራል መንግሥቱን አፋጣኝ እርምጃ እና ተጨባጭ ዘላቂ መፍትሔ የሚሻ ነው
የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ሐምሌ 1 ቀን 2014 ዓ.ም. ባወጣው ዓመታዊ የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ሪፖርት፣ ሰነዱ በሸፈነው የ12 ወራት ጊዜያት ውስጥ በሀገር አቀፍ ደረጃ በሕይወት የመኖር መብት እጅግ የከፋ አደጋ ውስጥ እንደወደቀ መቀጠሉንና በተለይም በኦሮሚያ ክልል በሚንቀሳቀሱ የታጣቂ ኃይሎች እና በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በሚፈጸሙ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ሲቪል ሰዎች ለሞት፣ ለአካል ጉዳት፣ ለመፈናቀል፣ ለዘረፋ እና ለንብረት ውድመት መዳረጋቸውን መግለጹ የሚታወስ ነው። በዚሁ ሪፖርት በተለይም በክልሉ ያለው አለመረጋጋትና የፀጥታ ችግር መንግሥት የሚጠበቅበትን የሰብአዊ መብቶች ግዴታ እንዳይወጣ እንዳደረገው፣ ኢሰመኮም በክልሉ ሁሉም ክፍሎች ተንቀሳቅሶ የሰብአዊ መብቶች ምርመራ እና ክትትል ሥራ እንዳይሠራ እንቅፋት እንደሆነበት ማስታወቁም የሚታወስ ነው፡፡

በወቅቱ ኮሚሽኑ ባቀረባቸው ምክረ ሃሳቦች በተለይም በአጥፊዎች ላይ ምርመራ በማድረግ ተጠያቂነት እንዲረጋገጥ፣ የፌዴራልና የክልሉ ኃላፊዎች በቅንጅት እንዲሠሩ እና ለተጎጂ ቤተሰቦች ተገቢ የሆነ ማካካሻ እንዲከፈላቸው፣ እንዲሁም በተለይ በወለጋ አካባቢ በየጊዜው ተመሳሳይ ግድያዎች የሚከሰቱበት በመሆኑ፤ መንግሥት ለችግሩ ዘላቂ መፍትሔ ማፈላለግ እንደሚያስፈልግና ተጨማሪ ጥቃት እንዳይፈጸም አስፈላጊ የሆኑ የቅድመ መከላከል እርምጃዎችን መውሰድ እንደሚገባው ማሳሰቡ የሚታወቅ ነው።

ዓመታዊ የሰብአዊ መብቶች ሪፖርቱ ይፋ ከተደረገበት ከሐምሌ ወር 2014 ዓ.ም. እስከ ኅዳር ወር 2015 ዓ.ም. ድረስ በኦሮሚያ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች የሚከሰቱ ግጭቶችና የሚደርሱ ጥቃቶችን፣ በእነዚህም ሳቢያ የሚደርሱ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶችን ኢሰመኮ ሲከታተል ቆይቷል። ኮሚሽኑ በአካል ተገኝቶ ምርመራ ለማካሄድ ባልቻለባቸው አካባቢዎች ደግሞ ተጎጂዎችን፣ የተጎጂ ቤተሰቦችን፣ ከእነዚህ አካባቢዎች የተፈናቀሉ ነዋሪዎችን፣ የዐይን እማኞችንና የመንግሥት ኃላፊዎችን ጨምሮ የተለያዩ ምንጮችን በማነጋገር የቃል እና የጽሑፍ መረጃና ማስረጃዎችን በማሰባሰብ ክትትል ያደርጋል።

በዚህም መሰረት በተለይም በሆሮ ጉድሩ ወለጋ፣ በምሥራቅ ወለጋ ዞን፣ በምዕራብ ወለጋ ዞን፣ በሰሜን ሸዋ፣ በቄለም ወለጋ ዞን፣ ኢሉ አባቦራ ዞን፣ በቡኖ በደሌ ዞን፣ በምሥራቅ ሸዋ፣ በምዕራብ ሸዋ፣ በደቡብ ምዕራብ ሸዋ፣ በአርሲ ዞን እና በሁለቱ የጉጂ ዞኖች ውስጥ በሚገኙ የተለያዩ ወረዳዎች በተለይም በኪረሙ፣ ጊዳ አያና፣ አልጌ፣ ሁሩሙ፣ በአሙሩ፣ ሆሮ ቡሉቅ፣ ጃርደጋ ጃርቴ፣ ቦሰት፣ ግንደበረት፣ ጮቢ፣ ደራ፣ ኩዩ፣ መርቲ ጀጁ እና የአርሲ ዞን አጎራባች ወረዳዎችን የሚደርሱ ግጭቶችና ጥቃቶችን በመከታተል ላይ ይገኛል።

ግጭቶቹና ጥቃቶቹ የሚከሰቱባቸው አካባቢዎች ስፋት ከጊዜ ወደ ጊዜ መጨመር እንዲሁም ያስከተሉት የሰብአዊ መብቶች ቀውስ ደረጃ አስከፊነት አንዱ አመላካች ነጥብ ነው። ይህ መግለጫ ይፋ እስከተደረገበት ጊዜ ድረስ በኮሚሽኑ ክትትል ከዚህ ቀደም ግጭት የተከሰተባቸው ወይም እየተከሰተባቸው ያሉ ተብለው የተመዘገቡ አካባቢዎች በምዕራብ ወለጋ ዞን ውስጥ ጊምቢ ወረዳ ቶሌ ቀበሌ፣ መነ ሲቡ ወረዳ (ነጆ መንዲ ከተማ)፣ ለታ ሲቡ፣ ቦጂ ድርመጂ (ቢላ ከተማ)፣ ነጆ ከተማ፣ ቆንዳላ ወረዳ፣ ቤጊ ወረዳ፣ ቅልጡ ካራ ወረዳ፤
በምሥራቅ ወለጋ ዞን ውስጥ ዴጋ ወረዳ፣ ሳሲጋ ወረዳ፣ ጊዳ አያና ወረዳ፣ ኪረሙ ወረዳ፣ ጉትን ወረዳ፣ ሊሙ ወረዳ፣ ጅማ አርጆ፤
በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን ውስጥ ጃርደጋ ጃርቴ ወረዳ (አሊቦ፣ ጃርደጋ እና ጃርቴ ከተሞች)፣ አሙሩ ወረዳ (አሙሩ ከተማ፣ አገምሳ ከተማ እና ከ10 በላይ ቀበሌዎች)፣ ሆሮ ቡልቅ ወረዳ፣ ጉዱሩ ወረዳ፤
በቄለም ወለጋ ዞን ውስጥ ሀዋ ገላን ወረዳ (መንደር 20 እና 21)፤
በምዕራብ ሸዋ ዞን ውስጥ ሜታ ወልቂጤ ወረዳ፣ አደዓ በርጋ ወረዳ፣ ጮቢ ወረዳ፣ ጀልዱ ወረዳ፣ አቡና ግንደበረት ወረዳ፣ ግንደበረት ወረዳ፣
በምሥራቅ ሸዋ ዞን ውስጥ ቦሰት ወረዳ፣ ዱግዳ ወረዳ፣ ፈንታሌ ወረዳ፤
በአርሲ ዞን ውስጥ ጀጁ ወረዳ፣ መርቲ ወረዳ፤
በሰሜን ሸዋ ዞን ውስጥ ኩዩ ወረዳ ወረጃርሶ ወረዳ፣ ደራ ወረዳ፤
በኢሉ አባ ቦር ዞን ውስጥ ደርሙ ወረዳ፣ አሊጌ ሰቺ ወረዳ፤
በቡኖ በደሌ ዞን ውስጥ ጨዋቃ ወረዳ፣ ዳቦ ሃና ወረዳ፣ መኮ ወረዳ፣ ዴጋ ወረዳን ያጠቃልላሉ።

በእነዚህ አካባቢዎች የሚንቀሳቀሱ የታጠቁ ቡድኖች በአይነታቸውና በቁጥራቸው የመጨመር ወይም የመወሳሰብ አዝማምያ ማሳየታቸው እንዲሁም በተለያዩ ወቅቶች የተለያዩ ቡድኖች ሙሉ ቀበሌዎችን ወይም ወረዳዎችን ጭምር ተቆጣጥረው የቆዩ መሆናቸው የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶቹን ከማባባሱም ባሻገር ተመጣጣኝና የተጎዱ ሰዎችን ብዛትና አካባቢዎችንም የሚመጥን ምርመራ ማድረግ አልተቻለም፡፡ ይህ ደግሞ የደረሰውን ጥሰት በተገቢው የሕግና የሰብአዊ መብቶች መርሆችና ድንጋጌዎች መሰረት ለመመደብ አስቸጋሪ አድርጎታል፡፡
ይህ ውስንነት እንደተጠበቀ ሆኖ በኮሚሽኑ ክትትል መሰረት በተለያዩ ወቅቶች በእነዚህ በተዘረዘሩት አካባቢዎች የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች፣ እንዲሁም በመንግሥት እራሳቸውን እንዲከላከሉ በሚል የታጠቁ የአካባቢው ነዋሪዎች፣ ከሌሎች ክልሎች ጭምር እንደመጡና በተለምዶ በአካባቢው የአማራ ታጣቂዎች መሆናቸውን የሚነገሩ የታጠቁ ቡድኖች እና የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት (በተለምዶ “ኦነግ ሸኔ”) እንደሚንቀሳቀሱ ታውቋል። እነዚህ የታጠቁ ቡድኖችና የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች በተለያዩ ወቅቶች እርስ በእርሳቸው በሚያደርጓቸው ውጊያዎች፣ በሌላ ወቅት በተናጠል በሚያደርሷቸው ጥቃቶች ሳቢያ በርካታ ሲቪል ሰዎች ለሞት፣ የአካል ጉዳት፣ መፈናቀል እና የንብረት ውድመት ተዳርገዋል፣ አንዳንድ ቀበሌዎች ወይም የገጠር ከተሞች ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል ደረጃ ወይም በከፊል ወድመዋል።

በግጭት አውድ ውስጥ እና በግጭቶቹ ሳቢያ ከሚደርሱ ግድያዎች፣ መፈናቀል፣ አካል ጉዳት፣ ዘረፋዎች፣ የአካባቢ ውድመቶችና የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች በተጨማሪ በአንድ በኩል ታጣቂዎቹ ወይም የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች አካባቢዎቹን በተቆጣጠሩበት ወቅት፣ በሌላ በኩል ግጭት ባልተካሄደባቸው አካባቢዎች የሚደርሱ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶችም በእኩል ደረጃ ሊያሳስቡ የሚገባ ነው።
በታጣቂ ቡድኖች ቁጥጥር ስር በዋሉ አካባቢዎች ደግሞ አፈናዎች፣ “መንግሥትን ወይም ሌላኛውን የታጣቂ ቡድን ትደግፋላችሁ ወይም የመንግሥት ኃላፊ ናችሁ ወይም መረጃ አቀብላችኋል” በሚል የሚደርሱ ግድያዎች፣ ዝርፊያዎች፣ ሌሎች ጥሰቶች፣ በግዳጅ የሚጠየቁ የገንዘብ ክፍያዎች የአካባቢዎችን ነዋሪዎችና ማኅበረሰብ ከግጭቶቹና ከጥቃቶቹ ባልተናነሰ ለስቃይ የዳረጉ መሆናቸውን ኮሚሽኑ በተለይም ከተጎጂዎችና ከተጎጂ ማኅበረሰብ በየጊዜው የሚደርሱት መረጃዎችና አቤቱታዎች ያሳያሉ።

ኮሚሽኑ ባሰባሰባቸው መረጃዎች እና ማስረጃዎች መሰረትም በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች የሚፈጸሙና አንዱን ወይም ሌላኛውን “ታጣቂ ቡድን ትደግፋላችሁ” በሚል ከፍርድ ውጪ የሚፈጸሙ ግድያዎች፣ ተገቢ የሆነ ማጣራት ሳይደረግ ታጣቂ ቡድኖችን ኢላማ በማድረግ በሲቪል ሰዎች የመኖርያ ሰፈሮች አቅራቢያ የተፈጸሙ የአየር ጥቃቶች፣ ሕገ ወጥና የዘፈቀደ እስሮች፣ ተጠርጠሪዎችን የማሰቃየት ተግባራት በሲቪል ሰዎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት በማድረስ ላይ ይገኛሉ፡፡
በተጨማሪም የሰብአዊ እርዳታና የመሰረታዊ አገልግሎቶች አቅርቦት መዘግየት ወይም አለመኖር፣ እንዲሁም በግጭቱ ሳቢያ የሚቋረጡ መንገዶች፣ የምርት ሥራዎች፣ የትምህርት፣ የጤና እና ሌሎች አገልግሎቶች በአካባቢው የሚገኙ ነዋሪዎችን ለከፍተኛ ችግርና እንግልት የዳረጉ ናቸው።

በእነዚህ በተዘረዘሩ አካባቢዎች የሚደርሱና ሆን ተብሎ ሲቪል ሰዎችን ኢላማ ያደረጉ ጥቃቶች በተለይም ብሔርን መሰረት ያደረጉ መሆናቸው፣ እንዲሁም በተወሰኑ ሁኔታዎች የፖለቲካ አመለካከትን (ለአንዱ ወይም ለሌላው ቡድን ድጋፍ ያደርጋሉ በሚል) መሰረት ያደረጉ መሆናቸው በአካባቢው ነዋሪዎች ላይ ከሚደርሰው የሰብአዊ መብቶች ጥሰት ላይ ተደራቢ ጫና/ሥጋት የሚያሳድር፣ እንዲሁም በሕግ ሥርዓቱ፣ በፍትሕና በፀጥታ አስተዳደሮች ላይ ያለውን እምነት የሚሸረሽር በመሆኑ ዘላቂ መፍትሔ በማፈላለግ ጥረቱ ላይ ከፍተኛ አሉታዊ ተጽዕኖ የሚያሳድር ነው። በአብዛኛው የግጭትና የጥቃት ሁነቶች ብሔርን መሰረት ባደረጉ ጥቃቶች መነሻ ወይም መንስዔ ሲሆኑ፤ ይህንን ተከትሎ ወይም በዚህ ሳቢያ መጠነ ሰፊ ግጭቶችና ተያያዥ ውድመቶች መከተላቸውን መገንዘብ ተችሏል። ይህም የግጭቶቹና የጥቃቶቹን ለተጎጂዎች ምሉዕ የሆነ ፍትሕ ለማስገኘትና ሁነቶቹ ያደረሱትን የጥፋት መጠን ለመገምገም፣ እንዲሁም ዘላቂ የሆነ መፍትሔ በማፈላለጉ ሂደት የተሟላና ፍትሐዊ እንዲሆን ስለ እያንዳንዱ የግጭትና የጥቃት ሁነት የተሟላ መረጃ የማግኘት አስፈላጊነትን የሚያስረዳ ተጨማሪ ነጥብ ነው።

ከሐምሌ ወር 2014 ዓ.ም. እስከ ኅዳር ወር 2015 ዓ.ም. ከላይ በተጠቀሱት አካባቢዎች ኮሚሽኑ ለማሰባሰብ በቻለው መረጃዎች መሰረት በታጣቂ ቡድኖቹ በተፈጸሙ ጥቃቶች በብዙ መቶዎች የሚገመቱ ሰዎች በአሰቃቂ ሁኔታ ተገድለዋል፣ ብዛታቸው የማይታወቅ ሰዎች ለአካል ጉዳት ተዳርገዋል፣ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ከሚኖሩበት ቀዬ ተፈናቅለዋል። የመንግሥት የፀጥታና የአስተዳደር አባላት ተገድለዋል፣ የመንግሥት እና የሲቪል ሰዎች ንብረቶች ተዘርፈዋል፣ ወድመዋል፣ መሰረተ ልማቶችና አገልግሎቶች ወድመዋል ወይም ተቋርጠዋል። በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ተፈናቃዮች ያለ ሰብአዊ እርዳታ አቅርቦት ወይም በቂ ባልሆነ አቅርቦት ምክንያት በከፍተኛ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ይገኛሉ።

ከዚህ በላይ በተዘረዘሩ አካባቢዎች ባለፉት ስድስት ወራት ብቻ የደረሱ ግጭቶችና ጥቃቶች ያስከተሉት የሰብአዊ መብቶች ጥሰት በሰብአዊ መብቶች መርሆችና ድንጋጌዎች መሰረት እጅግ ከፍተኛ የሰብአዊ መብቶች ጥሰት (grave violation of human rights) ተብሎ ሊመደብ የሚችል ስለመሆኑ በርካታ አመላካቾች በመኖራቸው፤ የክልሉ እና የፌዴራል መንግሥቱ ተቀናጅተው በአፋጣኝና በሙሉ ትኩረት በመሥራት ዘላቂ ምላሽ መስጠት የሚሻ ነው።
በእነዚህ ቦታዎች የሚገኙ ሲቪል ሰዎች፣ እንዲሁም በአካባቢዎቹ ባለው ሁኔታ ሳቢያ ወደሌሎች አካባቢዎች ተፈናቅለው የሚገኙ ሰዎችን ደኅንነት ለማስጠበቅና አፋጣኝ የሰብአዊ እርዳታ እንዲቀርብ ሁሉንም ባለድርሻዎች ከማስተባበር ጀምሮ በቂ የፀጥታ ኃይል ማሰማራትና አስፈላጊውን ሁሉ ጥረት በአፋጣኝ ማድረግ ይገባል።
ይህንንም ለማድረግ የሚያስችለውን የፀጥታና የደኅንነት ሁኔታ የመፍጠሩን ኃላፊነት ጨምሮ በአካባቢዎቹ መድረስ የሚገባውን የሰብአዊ እርዳታ አቅርቦት ማስተባበር የሚችልና ከፍተኛ የክልሉንና የፌዴራል መንግሥት የፀጥታ ኃላፊዎችንና የሚመለከታቸውን መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችን እንዲሁም የተጎጂዎች ተወካዮችን ያካተተ የአፋጣኝ ሁኔታዎች/የልዩ ሁኔታ ጊዜያዊ መዋቅር በአፋጣኝ ሊቋቋም ያስፈልጋል።

“እነዚህ ሁሉ ተያያዥ፣ በተወሰነ ደረጃም ተመጋጋቢ ሁኔታዎች በተለይም ደግሞ በእነዚህ ዞኖች ውስጥ በአሁኑ ወቅት የሚገኙ ነዋሪዎች ያሉበት በተዋጊ ቡድኖች መካከል መውጫ የሌለው አጣብቂኝ ውስጥ መጠለፋቸው ቢያንስ በተሟላ መልኩ ለመግለጽ/ለማስተጋባት የሚያስችል ሁኔታ እንኳን አለመኖሩ ከደረሰው የሰብአዊ መብቶች ጥሰት ተነጥሎ ሊታይ የማይገባ ሲሆን አጠቃላይ ሰቆቃው ከዚህ የበለጠ ሊቀጥል ስለማይችል ሳይውል ሳያድር ሰላማዊና ዘላቂ መፍትሔ ሊደረግለት ይገባል” በማለት የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ ገልጸዋል።

አክለውም “ከሰላማዊና ዘላቂ መፍትሔ ጎን ለጎን በተለይም በሲቪል ሰዎች ላይ የደረሰውንና እየደረሰ ያለውን የመብቶች ጥሰት ተጠያቂነትና ፍትሕ የማስገኘት ጥረትም ሊዘነጋ አይገባም” በማለት በከፍተኛ አጽንዖት አሳስበዋል።

https://ehrc.org