Ethiopian News, Current Affairs and Opinion Forum
Right
Member
Posts: 2801
Joined: 09 Jan 2022, 13:05

Command Post - Gurage Zone,Ethio insider

Post by Right » 26 Nov 2022, 09:08

የጉራጌ ዞን ከዛሬ ጀምሮ በኮማንድ ፖስት እንዲመራ ውሳኔ ተላለፈ – ኢትዮጵያ ኢንሳይደር
November 25, 2022


በተስፋለም ወልደየስ

በደቡብ ክልል የሚገኘው የጉራጌ ዞን ከዛሬ አርብ ህዳር 16፤ 2015 ጀምሮ በኮማንድ ፖስት እንዲመራ መወሰኑን የክልሉ ሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ አለማየሁ ባውዲ አስታወቁ። የጉራጌ ዞን በኮማንድ ፖስት ስር እንዲሆን የተደረገው፤ ከክልል አደረጃጀት ጥያቄ ጋር በተያያዘ በአካባቢው የተፈጠረውን የጸጥታ ችግር “በመደበኛ አሰራር ለማስተዳደር” ባለመቻሉ መሆኑን የቢሮ ኃላፊው ገልጸዋል።

የደቡብ ክልል ሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ኃላፊ ይህን ያስታወቁት፤ የጉራጌ ዞን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ ትላንት ሐሙስ በሰጡት መግለጫ ነው። የጉራጌ ዞን በተደራጀ ኮማንድ ፖስት እንደሚመራ ትላንት ምሽት በደቡብ ክልል ቴሌቪዥን በተላለፈው መግለጫቸው ይፋ ያደረጉት አቶ አለማየሁ፤ “የኦፕሬሽኑን ስራ” የፌደራል ፖሊስ እና የክልሉ ልዩ ኃይል በቅንጅት እንደሚመሩ ተናግረዋል።

ሁለቱ አካላት ሌሎች የጸጥታ ኃይሎችን ይዘው፤ በተደራጀ መንገድ በአካባቢው ውስጥ እየተፈጠረ ያለውን የጸጥታ ችግር እንደሚያስተዳድሩ የቢሮ ኃላፊው ገልጸዋል። በደቡብ ክልል በማዕከል ደረጃ ይህንን የሚያስተባብር አካል መቋቋሙንም አክለዋል።