ይድረስ ለአማራ ህዝብ !!
"አላማህንና የትግል ፍኖትህን በጥላቻ ፖለቲካ ላይ ሳይሆን በህዝብ ለህዝብ አጋርነትና በዘላቂ ጥቅምህ ላይ ተመስርተህ፣ በተጨባጭ የሃይል አሰላለፍ ላይ ተመርኩዘህ ብታቅድ ይበጅሃል።"
እነሆ ከዚያ በፊት ከነበሩት መከራን ከቆጠርክባቸው አመታት ይልቅ “ለውጥ መጣ” ፣ “ተስፋ ፈነጠቀ” ካልክበት ከዛሬ አራት አመት ጀምሮ ለውጥ ባልሆነ ለውጥ፤ ተስፋ ባልሆነ ተስፋ የአሳር ገፈት እየገፈገፍክ ትገኛለህ። ገና ከጠዋቱ አማራ መገፋቱ ይብቃ፤ ከእንግዲህ ደረታችንን ለአንተ ስንል እንሰጣለን እንጂ ለበላተኛ አሳልፈን አንሰጥህም ብለው ማጣፊያቸውን ጥለው በትራቸውን ወዝውዘው የተነሱትን ልጆችህን እነ አምባቸውን የትናንት ኢሃዴጎች የዛሬ ብልጽግናዎች ከእጅህ ላይ ነጠቁህ። ጎበዝ ተሰናዳ፣ የአምስት መቶ አመቱ ታሪክ ሊደገምብህ ነው ያሉትን ፊታውራሪዎችህን እነ ጄኔራል አሳምነውን ከአይንህ ስር ወሰዱብህ። ለውጥ ካመጣችሁማ ከማንነታችሁ እኔ ምን አለኝ ብለህ፣ የጥይት አረር ተጋፍጠህ፣ ቤተ መንግስት ያስገባሃቸው እነዚሁ ባለጊዜዎች ገና ከማለዳው ጀምሮ እርም ለአማራ ዘር ብለው፣ ማንነትህን ተጸይፈው፣ ሴት ከወንድ፣ ህጻን ከሽማግሌ፣ ነፍሰ-ጡርን ከአራስ፣ በሽተኛን ከጤነኛ ሳይለዩ በጅምላ እየጨፈጨፉህ፣ የተረፍከውንም ከገዛ አገርህ ከኢትዮጵያ ምድር እየነቀሉ፣ ጥሪትህን እየዘረፉ አሳደዱህ።
የወለጋው፣ የቤንሻንጉሉና የከሚሴው በማንነትህ ላይ የፈጸሙብህ አሁንም የሚፈጽሙብህ ጭፍጨፋ ሳይበቃቸው በሺዎችና በአስር ሺዎች የምታልቅበትን ጦርነት ቆስቁሰው፣ የመጥፊያህን ሴራ ዶልተው፣ ያመንከውን አሳምነው፣ ያላመንከውን አጃጅለው ከገዛ ወንድምህ ከትግራዩ ወገንህ ጋር የሚያቆራርጥህ ጦርነት ውስጥ ከተቱህ፤ ከአገርህ ልጅ ጋር አዳሙህ። በቤተሰብህና በባህልህ፣ በታሪክህና በሃይማኖቶችህ ተጋምደህ ከኖርከው ከቁርጥ ቀን ወዳጅህ ጋር አፋቱህ። የጀግና ደምህን ከጀግና ደሙ ጋር በየሸለቆው ቀላቅለህ፣ ትከሻ ለትከሻ ገጥመህ ስንቱን የባእድ ወራሪ አብረህ ከመከትከው ከጦር ጓድህ፣ በኢትዮጵያዊነትህ ከተማማልከው ቃል-ኪዳነኛህ ጋር አቀያየሙህ። እነሆ አባቶችህ “ትሻልን ገፍቼ ትብስን አገባሁ” እያሉ እንደሚቀኙት ካለፈው አገዛዝ በከፋ መልኩ መፈናፈኛ አሳጥተው፣ የግፍ መአት፣ የአሳር-የፍዳ መአልት ለሚያስቆጥሩህ ገዥዎች፣ እነሱ ለሚነግሱበት ስልጣን የደምና የህይወት ግብር እየገበርክ፣ የገዛ መጥፊያህ በሆነው ጦርነት ውስጥ እጅህን በእጅህ እየቆረጥክ ትገኛለህ።
የአማራ ህዝብ ሆይ ! እስቲ ለአፍታ ቆም ብለህ አስበውና ይህ ጦርነት ከቶ ለአንተ ምንህ ነው? ምን አግኝተህ ምንስ አሳክተህበታል? ይህን አግኝቼበታለሁ እንዳትል ካለፈው ይልቅ አሁን ሁለ-መናህን አጥተህ ቆመሃል። እንደ አይንህ ብሌን የምትሳሳላቸው ብርቅ ልጆችህ እንደወጡ ቀርተዋል። መርዶአቸውን እንኳ በቅጡ ሳትሰማ፣ እንደ ወግ-ማእረጉ የመቅበር እድል ሳይገጥምህ ከጎንህ እንደተለዩ የምታውቃቸው እነ ወንድም-ጋሼ፣ እነ አይወይና እነ ወንድም-ጥላ ወዴት የወደቁ ይመስልሃል?! ገሚሶቹ ልጆችህ ያለ አባት ሌሎቹም ያለ ወላጅ፣ ሚስትህም ያለ አባ ወራ፣ እህትህም ያለ ወንድም ተንከራተው ቀርተዋል፤ እነሱም ቢሆን በቤታቸው አልተረፉልህም። አሁን ደግሞ በቀበሌ ኮታ እየሰጡ ልጆችህን ለጦርነት እየገፈፉብህ ነው። ይሄ ጦርነት በየቀኑ በሺዎች እንድትሞት፣ በአስር ሺዎች እንድትሳደድና ከመኖሪያህ ተፈናቅለህ በረሃብ አለንጋ እንድትገረፍ ቸነፈርና ሰቆቃን አተረፈልህ እንጂ አልጠቀመህም። ከቶውንም ይሄ ጦርነት በመኖርና በመጥፋት መካከል በሰቀቀን የምትኖርበትን ጊዜ አወረደብህ። በንብረትህስ ቢሆን ምን አተረፍክ?? በዚህ ጦርነት ከ300 ቢሊዮን ብር በላይ የሚገመት ሃብትና ንብረትህ ወድሞብሃል፣ እንደ ሰቆጣና አካባቢው ባሉ ቦታዎች የሚኖሩት ወገኖችህ በኤሌክትሪክ፣ በመገናኛና መሰል መሰረተ ልማቶች መዘጋት የተነሳ እየተሰቃዩ ነው። አንተም እንደ ትግራዩ ወንድምህ የበሻሻ እጣ-ፈንታ ሊደርስህ አንድ ጋት ብቻ ቀርቶሃል። የእርሻ ማሳህ ጦም አድሮ ጎተራህ ተሟጥጧል፤ ቸሩና ለጋሱን፣ ባለ ሰፊው ማእዱን ሰው ተመጽዋች አድርገውሃል። በተፈናቃይ ብዛት ተጨናንቀሃል። እንደዚህ ያለ እጅጉን የከፋ የምጥ ጨለማ፣ የጭንቅ ዳፍንት፣ የመከራ አውድማ ውስጥ የሆንክበት ዘመን ከቶ ገጥሞህ ያውቃልን ??
በዚህ ጦርነት ኢትዮጵያን አዳንኩ እንዳትል የምትወዳትንና የሞትክላትን አገርህን ኢትዮጵያን ልታጣት ጫፍ ደርሰሃል። አገርን የማዳን ጦርነት ብለው እየሰበኩ ነድተውህ አገርህን እያሳጡህ ነው። በክፉም በደጉም ዘመን ተፋቅረህ የኖርከውን ኢትዮጵያዊውንና ትግራዋዩን ወንድምህን እንደ ባእድ ወራሪ አስመስለው የጠላትነት ግንብ ገንብተው ጦርህን እንድትሰብቅበት ቀሰቀሱህ። እንዲያውም የታሪክ አግራሞት ይሁንብህና ኢትዮጵያን የወረረውን የሻቢያን ሰራዊት እየተፋለሙ የሚገኙት የትግራይ ህዝብና ሀይሎች መሆናቸውን ከቶ ልብ ብለሃል?! የአማራ ክልል መንግስትን፣ የአማራ ልሂቃን የተባሉትን፣ የስመ-ክርስትና ሰባኪዎችንና የስመ-ነቢያት ጠንቋዮችን በቤተ መንግስት ፍርፋሪ አልከስክሰው፣ በብርና በስልጣን ዳረጎት አሳውረው ትግሬ ላይ ዝመት፣ በአረመኔያዊ ጭፍጨፋ ጨፍጭፍ፣ ዝርያቸው እንዳይተርፍ፣ በታሪክ እንዳይታወሱ ከምድረ-ገጽ አጥፋቸው እያሉ ቀስቅሰው ነዱህ። ከጨቅላ ህጻናት እስከ መበለቶችና መነኩሲቶች ባረከሱበት እርኩሰት ውስጥ ነከሩህ፤ ከሚጠቡ ህጻናት መቆም እስከማይችሉ አረጋውያን ባረዱበት፣ ባቃጠሉበትና፣ ገደል በጣሉበት አረመኔያዊ ጭካኔ ውስጥ ማገዱህ ፤ ከብረት ምጣድ እስከ ፋብሪካ በዘረፉበት ዝርፊያ ውስጥ ከተቱህ። በኢህአዴግ ዘመን የተበደልከውን በደል እየቆሰቆሱ፣ በህወሃት ላይ ያለህን የቅሬታህን ደም-ስር እየጎረጎሩ ጥቅምህን ሳይሆን ጥቅማቸውን እንድትጠብቅ፣ የራስህንና የምትወዳትን ኢትዮጵያን ህልም ሳይሆን “የሰበሩንን ሰበርናቸው” የሚሉበትን ህልማቸውን እውን ሊያደርጉ አሰለፉህ። ዛሬም ያንኑ የህወሃት ጥላቻ ሽፋን አድርገው “እንዴት ይረሳል” ያሉትን መርዘኛ እንጉርጉሮ ዶኩመንታሪ ሰርተው ከወንድምህ ከትግራይ ህዝብ ጋር ማጋደላቸውን ቀጥለዋል።
መቼም ታሪክ ምጸቷን አንዴ በትራጀዲ ሌላ ጊዜ በቧልት ትከትባለችና ብለው ብለው ደግሞ “የኦሮሞ” ና “የአማራ” ብልጽግና በማለት፣ ባልተወከሉበት ተወክለው የተሰደሩብህ ገዢዎች ከደመኛ ጠላትህ፣ አገርህን ለመበተን ሲያልም ከኖረ ሴረኛ፣ የበቀል ጥሙን ሊያዝረበርብ ቀን ሲጠብቅ ከባጀ አረመኔ የሻቢያ ወራሪ ሰራዊት ጋር አጎዳኙህ። አገርህን ከደፈረ፣ ሉአላዊነትህን ከገሰሰ ወንጀለኛ ጋር አብረህ የገዛ ህዝብህን እንድትወጋ አሰለፉህ። ለመሆኑ ኢሳይያስና ሰራዊቱ፣ የሻቢያ ወራሪ መንጋ ለአንተ ምንህ ነው? የጠላታችን ኢትዮጵያ ዋነኛ መስራችና ወኪል፣ ከሃይለስላሴ እስከ ደርግ ኤርትራን በቅኝ አገዛዝ ሲጨቁን የኖረው ዋነኛ ጠላታችን አማራ ነው እያለ፤ የኢትዮጵያን ሰራዊት “አህያው የአማራ ሰራዊት” በማለት እያዋረደ ከኖረው የኢሳይያስ ሰራዊት ጋር ምን ውሎ አለህ? እንደ ህልሙ ቢሆንለት ዛሬ ከብልጽግና ቡድን ጋር ሆኖ የትግራይን ጉዳይ ፈጸምኩ ካለ በኋላ እንደገና ከብልጽግና ጋር ሆኖ ጎራዴውን ወደ አንተ እንደሚያዞር፣ ኢትዮጵያን የእድሜ ልክ ገባሪው አድርጎ ለመኖር “ዛሬ ነው እድሌ” ብሎ እንደ ፎከረ አልገባህምን? ዛሬ ኢሳይያስንና ሻቢያን ወዳጅህ ነው እያሉ የሚሰብኩህ የብልጽግና ቤተመንግስት ድርጎኞች ትናንትና ኤርትራ ላይ በሻቢያ ቤተመንግስት ውስጥ ከኢሳይያስ ጋር ቁጭ ብለው ኢትዮጵያን እንዴት እንደሚያፈርሱ ሲያሴሩ፣ ለዛሬዎቹ የብልጽግና መሪዎች የሰጧቸውን ኢትዮጵያን የሚያፈርሱበትን ፍኖተ ካርታ ሲዶልቱ የኖሩ ተስፈኞች መሆናቸውን አታውቅምን? ከሻቢያ ጋር መወዳጀት ማለት የእርድህን ስለት ማዘጋጀት ማለት መሆኑን ተገንዝበህ በእነዚህ ሴረኞችና የሻቢያን ወዳጅነት በሚነግሩህ ለአንተ ቆመናል በሚሉህ ልሂቃኖች ወጥመድ አትጠመድ።
የብልጽግና ገዥዎች የትግራዩን ወንድምህን ዙሪያ-ገባውን ዘግተው፣ ከመዋጋት በስተቀር ምርጫ እንዳይኖረው መፈናፈኛ ካሳጡት እነሆ ሁለት አመት ሊሞላቸው ነው። አርሶ እንዳይበላ ማሳውን ጦር ሜዳ አድርገው፤ የህክምና ተቋሞቹን በሙሉ አፈራርሰውና አቃጥለው፤ አለም አቀፍ የምግብና የመድሃኒት እርዳታ እንዳይገባለት አራቱንም ማእዘናት ዘግተው፤ በገዛ ገንዘቡ እንኳ እንዳይጠቀም የባንክ አገልግሎት እንዳያገኝ ከልክለው፤ የኤሌክትሪክ፣ የስልክ፣ የውሃ፣ የህክምና፣ ሌሎችም ማናቸውም አይነት አገልግሎቶች እንዳያገኝ አድርገው ከሰብአዊነት ውጭ በረሃብና በበሽታ እንዲረግፍ ፈርደውበታል። በዚህም ምክንያት የትግራይ ህጻናት፣ እናቶችና አባቶች በጣእረ-ሞት እየሞቱ ናቸው። አላማቸውን ራሳቸው በአንደበታቸው እንደነገሩን፣ በተግባራቸውም እንደመሰከሩት የትግራይን ህዝብ ከምድረ ገጽ ማጥፋት ነው። አንተ የእዚህ እኩይ አላማ፣ የእዚህ ሰይጣናዊ ክፋትና ሴራ አካልና ተባባሪ ልትሆን አይገባህም። የእዚህ ክህደት ተባባሪ ሆነህ ብትገኝ ግን የህሊናህ ዘላለማዊ ሰለባ፣ የታሪክና የትውልድ ተጠያቂ ትሆናለህ።
የአማራ ህዝብ ሆይ ! የብልጽግና ገዥዎች ዛሬ በትግራይ ወገንህ ላይ የሚፈጽሙትን ይህን ሁሉ ወንጀል አንድም ሳይቀር እንዲያውም በባሰ ሁኔታ ነገ በአንተ ላይ እንደሚፈጽሙት አትጠራጠር። ዛሬ አጋርህ እንደሆነ እየተደረገ በልሂቃንህ የሚሰበክልህን ሻቢያን ይዘው በአንተ ላይ እንደሚዞሩብህ እርግጠኛ ነገር መሆኑን በተግባርም እያሳዩህ አይደለምን?? በአንድ በኩል ትግራይ ላይ እያዘመቱህ ከኋላህ ደግሞ ወለጋ ላይ በየቀኑ እየጨፈጨፉህ ነው። ራስህን አደራጅተህና አጠናክረህ ህልውናህን እንዳትጠብቅ መሪዎችህንና ታጋዮችህን እየገደሉ፣ እያሰሩና እያሳደዱህ ነው። ዛሬ ትግራይን ከምድረ-ገጽ ማጥፋት የተባለው ዘመቻ ነገ አማራን ከምድረ-ገጽ ማጥፋት ተብሎ በይፋ እንደሚታወጅብህ አትጠራጠር፤ ዛሬም ቢሆን ጦርነቱን ተከልለው በአማራነትህ ምክንያት እየፈጁህ አይደለምን?? ። ዛሬ ትግራይን ዙሪያውን ከበው መፈናፈኛ እንዳሳጡት ነገ ደግሞ አንተን መውጫ መግቢያ እንዳይኖርህ ከበው፣ የምትበላው አሳጥተው፣ አገልግሎት እንዳታገኝ አድርገው በረሃብና በበሽታ እንደሚፈጁህ አትጠራጠር። እነሆ ወለጋ ላይ ከበባ ውስጥ አይደለህምን?? አዲስ አበባ እንዳትገባ ከልክለው፣ ከቤንሻንጉልና ከሰሜን ሸዋ አቅጣጫዎች አፍነው ክልሉን ከበባ ውስጥ እንዳስገቡት አልታየህምን?? ቁማሩን በልተነዋል ብለው ካወጁብህ ቆይተዋልና ይልቁንስ ነግ-በእኔ ብለህ ራስህን ከእዚህ ከንቱ ጦርነት አውጣ። በትግራይ ወንድሜ ላይ አልዘምትም፤ ብልጽግና ለተባሉ ገዥዎች ስልጣንና ለሻቢያ ሴራ ደሜን አልገብርም ብለህ እምቢ በል። እምቢ ያልክ እለት እምቢታ መች ጠፍቶህ ያውቃል?!
የወቅቱ አንገብጋቢ ጉዳይህ በዚህ ጦርነት ውስጥ እየገባህ መማገድ አይደለም፤ ይልቁንስ የወቅቱ አንገብጋቢ ጉዳይህ አደጋ ውስጥ የገባውን ህልውናህን ለማዳንና የአገርህንም ህልውና ለመጠበቅ አስተዋጽኦ የምታደርግበትን ዘዴ ማበጀት ነው። ለዚህም ስትል፦
1) ጦርነት ይብቃ! ሰላም ይውረድ! ብለህ ተነስ። ወጣት ልጆችህ በሃይል እየተገፈፉም ሆነ ባለማስተዋል ወይም መስሏቸው የእዚህ ከንቱ ጦርነት እሳት እራት እንዳይሆኑ ከልክላቸው፤ እነዚህ ሳተና ልጆችህ ለዋነኛው ጉዳይህ ያስፈልጉሃልና ትውልድን ከሚበላው ከዚህ ጦርነት ጠብቀህ አቆያቸው፤
2) ከትግራይ ወንድምህ ጋር እርቅ ፍጠር፣ በመካከላችሁ ሰላምን ለማውረድ ስትል ቀድሞም በምታውቀው ዘዴህ አማካይነት ውስጥ ለውስጥ እየተገናኘህ በሽማግሌዎችህ አማካይነት ምክክር አድርግ፤ የጋራችሁ የሆኑትን ጋራ ሸንተርሮቹን የጦር ሜዳችሁ ሳይሆን የሸንጎ መዋያችሁ፣ የምስጢር ታዛችሁ፣ የቃል-ኪዳን ማደሻችሁ እንዲሆኑ የበኩልህን ለማድረግ በሚመችህ መንገድ ሁሉ ተጠቀምበት። ጣሊያንን ድል የመታችሁበትን፣ የደርጉን አረመኔ የተፋለማችሁበትን የጋራ ጥበባችሁን አስታውስ፤
3) ወቅታዊ የሆኑ ሁለት ቁም-ነገሮችን ልብ-በል፦ አንደኛ፣ በውስጥህ ያሉትን ያለፉትንም ሆነ አዳዲስ ቁርሾዎችህንና ልዩነቶችህን ወደ ጎን አድርገህ፣ በውስጥም በውጪም ያለህን የሰው ሃይል ሁሉ አሰባስበህ በጠንካራ አንድነት ቁም። ሁለተኛ፣ መሰረታዊ አላማህን ለይተህ ለጥቅምህ ሳያወላውል በሚከላከልልህ ድርጅት ተደራጅ፤ በእጅህ የሚገኙትን ህዝባዊ አደረጃጀቶች ሁሉ አጥርተህና አጠናክረህ፣ በአውራጃና በጎጥ ሳይሆን በአንድነት እንዲቆሙ መልክ አስይዘህ፣ ከብልጽግና አፈናና ግድያ እየጠበቅህ ለመሰረታዊ አላማህ በሚሰለፉበት መንገድ አዘጋጃቸው እንጂ በእዚህ ከንቱ ጦርነት ውስጥ እንዲማገዱ አትተዋቸው፤
4) የአማራ ብልጽግና ብሎ በስምህ የሚነግደውን፣ ነገር ግን በጦርነት የሚያስጨርስህን ፓርቲና የክልል አስተዳደር በየደረጃው ያንተ በሆኑ ሃቀኛ ልጆችህ እየተካህ እውነተኛ የአማራ ተሟጋቾችና ታጋዮች እንዲመሩት፣ በክልሉ ፓርቲና መንግስት ውስጥ ያሉትም አባላት የህዝብ ወገኖች ሆነው ከአንተ ጋር እንዲቆሙ ለያቸው። የክልሉን አስተዳደር ህልውናህን የምታስጠብቅበት የአንተ የራስህ ክልላዊ መንግስታዊ መሳሪያ እንዲሆን አድርገው፤
5) የወልቃይትና የራያ አካባቢዎች ላይ ያለህን ተገቢ የማንነት ጥያቄ በሚመለከት በጦርነት ልትፈታው እንደማትችል ትገነዘባለህ። ይህን ጉዳይ ያለማንም ጣልቃገብነት ከትግራይ ወንድምህ ጋር በመወያየትና በመመካከር በሰላማዊ መንገድ ብቻ መፍታት እንደምትፈልግ አቋም ይዘህ የትግራይ ህዝብ እንዲያውቀው አድርግ። ከዚሁ ጋር በተጓዳኝ የትግራይ ህዝብም ተመሳሳይ አቋም አንዲይዝ ወንድማዊ ጥሪህን አቅርብለት። በሁለታችሁም በኩል የሚገኙት የፖለቲካ ሃይሎች ደግሞ ይህንኑ ተከትለው ይታገሉ ዘንድ እናንተ ፋና ሁኑላቸው። አንተም ሆንክ የትግራይ ህዝብ ይህን ጉዳይ በጦርነት መንገድ እንደማትፈቱት ግልጽ ሆኖላችኋል። ለሁለታችሁም በሚበጅ ሁኔታ ችግሩን ለመፍታት የሚያስችል ጥበብ፣ ትእግስትና ትህትና ግን በእጃችሁ መኖሩ አያጠራጥርም።
6) ወንድምህ ለሆነው ለትግራይ ህዝብ ድምጽህን ከፍ አድርገህ ጩህለት። ሞቱን-ሞትህ፣ ስቃዩን-ስቃይህ፣ ግፉን-ግፍህ፣ በደሉን-በደልህ አድርገህ ቁጠርለት። ጦርነቱ ይቁም ብቻ ሳይሆን ዙሪያውን የተከበበው ከበባ ይሰበር፣ በረሃብና በበሽታ እንዲያልቅ አይፈረድበት፣ የተዘጋበት አገልግሎት በሙሉ ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታ ይከፈትለት፣ የሻቢያ ወራሪ ከትግራይ ይውጣ፣ የኤርትራ መንግስት ከአራት ኪሎና ከሌሎችም የአገራችን ክፍሎች ሁሉ ለቆ ይውጣ እያልክ ድምጽህን አሰማ። ይህን ስታደርግ የትግርዩ ወንድምህም ስለአንተ አብሮህ ይቆም ዘንድ በር ትከፍታለህ።
አላማህንና የትግል ፍኖትህን በጥላቻ ፖለቲካ ላይ ሳይሆን በህዝብ ለህዝብ አጋርነትና በዘላቂ ጥቅምህ ላይ ተመስርተህ፣ በተጨባጭ የሃይል አሰላለፍ ላይ ተመርኩዘህ ብታቅድ ይበጅሃል። ህወሃትን በሚመለከት ያለህን የቅርብም ሆነ የሩቅ ማንኛውንም ጉዳይና ጥያቄ በቅድሚያ ሰላም እንዲሰፍን ከታገልክ በኋላ፣ በቅድሚያ ህልውናህን የምታስጠብቅበትን የቤት ስራህን ከሰራህ በኋላ፤ በአገር አቀፍና በአለም አቀፍ ደረጃ በሚኖሩ የፍትህ አደባባዮች አማካይነት ሰላማዊ ትግልህን ትቀጥላለህ። ከትግራይ ህዝብና ከሌሎችም ኢትዮጵያውያን ጋር በመሆን በመላ አገሪቱ ላይ የፍትህና የተጠያቂነት ስርአት ይዘረጋ ዘንድ በጽናት ትቆማለህ።
ታምራት ላይኔ (የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር)
መስከረም 25 ቀን 2015 ዓ.ም.