የብረታ ብረት ኢንዱስትሪዎች ከአቅማቸው 20 በመቶ በታች እያመረቱ መሆናቸው ተነገረ
28 November 2021
አማኑኤል ይልቃል
በመሠረታዊ የብረታ ብረት ምርት ዘርፍ ላይ የተሰማሩ ኢንዱስትሪዎች፣ የአቅርቦት ፍላጎትን ተከትሎ አቅማቸውን ቢያሳድጉም እያመረቱ ያለው ምርት የአቅማቸውን 20 በመቶ እንኳን እንደማይደርስ ተገለጸ፡፡ የብረታ ብረት ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት የኮርፖሬት ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ፊጤ በቀለ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ በተለይ የኮንስትራክሽን ግብዓቶችን ከሚያመርቱ ኢንዱስትሪዎች ውስጥ ምርታቸው ከአቅማቸው ሦስት በመቶ ብቻ ነው፡፡
የኢንዱስትሪ ሚኒስቴር ሐሙስ ኅዳር 16 ቀን 2014 ዓ.ም. ባቀረበው የአራት ወራት አፈጻጸም ሪፖርት፣ በብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ዘርፍ የተመዘገበው አፈጻጸም ከሌሎች ዘርፎች ዝቅተኛው መሆኑን አስታውቋል፡፡ ሚኒስቴሩ የአራት ወራት አፈጻጸሙ 92 በመቶ እንደሆነ የገለጸ ሲሆን፣ የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ዘርፍ አፈጻጸም ደግሞ 16 በመቶ መሆኑ ታውቋል፡፡ ይኼም በዘርፉ ከተፈጠረው አቅም አንፃር ‹‹እጅግ ዝቅተኛ ነው›› ተብሏል፡፡
አቶ ፊጤ በዘርፉ ከ500 በላይ ከፍተኛና መካከለኛ ኢንዱስትሪዎች መኖራቸውን ገልጸው፣ በዓመት 11.3 ሚሊዮን ቶን ብረታ ብረት የማምረት አቅም እንዳላቸው አስረድተዋል፡፡ ይኼ አቅም አሁን ባለው የገበያ ዋጋ ወደ ገንዘብ ቢቀየር ከ381 ቢሊዮን ብር በላይ እንደሚሆንም አክለዋል፡፡
ባለፉት አራት ወራት የተመረተው ብረት 8.5 ቢሊዮን ብር ዋጋ ያለው መሆኑን፣ ከውጭ ለማስገባት ወጪ ይደረግ የነበረውን 44.6 ሚሊዮን ዶላር ማስቀረት እንደተቻለ ተጠቁሟል፡፡ ዘርፉ የአገር ውስጥ ፍላጎትን አሟልቶ ወደ ውጭ የሚላክ ብረት የማምረት አቅም ያለው ዘርፍ ከመሆኑ አኳያ፣ ምርቱ ዝቅተኛ መሆኑን አቶ ፊጤ አስረድተዋል፡፡
የብረታ ብረት ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት በውስጡ መሠረታዊ ብረታ ብረት፣ ተሽከርካሪና አውቶሞቲቭ፣ ማሽነሪና ኢኪዩፕመንት፣ እንዲሁም ኤሌክትሪካልና ኤሌክትሮኒክ የተባሉ ዋና ዋና ዘርፎችን ይይዛል፡፡ እንደ ዳይሬክተሩ አቶ ፊጤ ገለጻ፣ አሁን የተመዘገበው 16 በመቶ አፈጻጸም በራሱ የተመዘገበው ከመሠረታዊ ብረታ ብረት ውጪ ያሉት ዘርፎች አፈጻጸማቸው የተሻለ በመሆኑ ነው፡፡ በዚህ ዘርፍ የተሰማሩ አምራቾች በአጠቃላይ እያመረቱ ያሉት ከአቅማቸው ዝቅ ያለ መሆኑን፣ አንዳንዶቹ ኢንዱስትሪዎች የአቅማቸውን ሦስት በመቶ ብቻ እያመረቱ መሆኑንም ተናግረዋል፡፡
Continue reading https://www.ethiopianreporter.com/article/23896
-
- Senior Member
- Posts: 10186
- Joined: 23 Feb 2013, 20:08