Page 1 of 1

ኦነግ ነባር አባላቱ እንዲመለሱ ጥሪ አቅረበ!!!!

Posted: 14 Sep 2020, 12:34
by Ejersa

የኦሮሞ ነፃ አውጪ ግንባር ከምስረታው ጀምሮ ደርጅቱን ደግፈው ሲታገሉ የነበሩ፤ ነገር ግን የተገፉ እና በግል ምክንያትከድርጅቱ የወጡ የቀድሞ አባላት እንዲሰበሰቡ ጥሪ አቅርቧል፡፡ ለስሙ የሚመጥኑ አመራሮችን በመምረጥ ራሱን እንደሚያጠናክርም ገልጿል፡፡

በኦሮሞ ነፃ አውጪ ግንባር ፅህፈት ቤት ዛሬ መግለጫ የተሰጠ ሲሆን፤ በወቅቱ የድርጅቱ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል እና ቃል አቀባይ አቶ ቶሌራ አዳባ እንደተናገሩት፤ ድርጅቱ ለተወሰነው የኦሮሞ ህዝብ ብቻ ሳይሆን፤ ለመላው የኦሮሞ ህዝብ የቆመ በመሆኑ በዚሁ መልክ የሚሰራ መሆኑን በማመልከት፤ የሚመራው በጋራ በመሆኑ ቀድመው የተገፉ ነባር አባላት በተመሳሳይ ዓላማ በሰላማዊ መንገድ በትግሉ ላይ መሳተፍ የሚፈልጉት መሳተፍ ይችላሉ ብለዋል፡፡

የኦሮሞ ነጻነት ግንባር የህዝብ ግንኙነት ሃላፊው አቶ ቀጄላ መርዳሳ በበኩላቸው፤ በተለያየ መልኩ በኦነግ ስም የሚንቀሳቀሱ እና ሌሎችም ለኦሮሞ ህዝብ የቆሙ ፓርቲዎች ከኦነግ ጋር የዓላማ ልዩነት ከሌላቸው ከእነርሱ ጋር አብሮ መስራት እንደሚፈልግ የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው መግባባት ላይ ደርሶ በአብላጫ ድምፅ መወሰኑን ገልፀዋል፡፡

ይሁን አንጂ በስራ አስፈፃሚው የታገቱት የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ ዳዉድ ኢብሳ የሥራ አስፈፃሚውን ውሳኔ ከማስተግበር ይልቅ ከ8 የሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴዎች 2ቱ የታሰሩ ሲሆን የድርጅቱን ህገ ደንብም ሆነ አሰራር በመጣስ 5ቱን አባላት ‹‹ከስራ አባርሪያለሁ›› በማለት የግል ፍላጎታቸውን ማራመዳቸውን ተናግረዋል፡፡

የድርጅቱ ሥራ አስፈፃሚ ደግሞ ህጉን ተከትሎ ሊቀመንበሩን አግዶ፤ ለጠቅላላ ጉባኤው የማቅረብ መብቱን በመጠቀም በዚህ መልኩ በጋራ ሃላፊነቱን እየተወጣ መሆኑን ተናግረው፤ ጠቅላላ ጉባኤም በመጪው ታህሳስ 2013 ዓ.ም ይካሄዳል የሚል ዕቅድ መያዙን ጠቁመዋል፡፡

ምህረት ሞገስ