28 July 2019
ነአምን አሸናፊ
በ2010 ዓ.ም. ወርኃ መጋቢት በአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች ሲከናወኑ የነበሩ ሕዝባዊ ተቃውሞዎችን ባስከተለው ግፊት በገዥው ግንባር የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢሕአዴግ) የአመራር ለውጥ ተደርጎ ወደ ሥልጣን የመጡት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ካከናወኗቸው ዓበይት ተግባራት መካከል፣ ለሁለት አሥርት ዓመታት ያህል ተቋርጦ የነበረውን የኢትዮጵያና የኤርትራ ግንኙነት እንደገና ማስጀመራቸው አንዱ ነው፡፡
ኢትዮጵያና ኤርትራ ካካሄዱት ደም አፋሳሽ የድንበር ጦርነት ምንም እንኳን በኢትዮጵያ አሸናፊነት ተጠናቅቆ የአልጀርስ ስምምነት ቢፈረምም፣ ስምምነቱን ተፈጻሚ ማድረግ ላይ በተፈጠረ አለመግባባት ሁለቱ አገሮች ጦርነትም ሰላምም በሌለበት መፋጠጥ ሁኔታ ውስጥ ነበሩ፡፡
ይህ ፍጥጫ በኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ውሳኔ መሠረት የዛሬ ዓመት ገደማ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ ባቀረቡት የሰላም ጥሪ አማካይነት የተቋጨ ሲሆን፣ የሰላሙን ጥሪን ተከትሎ የፕሬዚዳንት ኢሳያስ ምላሽ ታክሎበት ሁለቱ አገሮች ግንኙነታቸውን ዳግም ማደሳቸው እንደ ስኬት ተቆጥሮ የበርካታ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙኃን፣ እንዲሁም የተለያዩ መንግሥታት መሪዎች አድናቆታቸውን ቸረውት ነበር፡፡
ይህ የግንኙነት ማደስ፣ እንዲሁም ጠላትነትን የማስወገድ ስምምነት በርካታ ተቋርጠው የነበሩ እንቅስቃሴዎች ዳግም እንዲጀመሩ ያደረገ ሲሆን፣ ከዚህም ውስጥ የስልክ አገልግሎት መጀመር፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በቀን ሁለቴ በረራ ማድረግ፣ የድንበር መከፈትና ድንበር አካባቢ ከተሞች በሚኖሩ የሁለቱም አገሮች ዜጎች ገበያ መጀመር ዋነኛዎቹ ናቸው፡፡
Reporter: https://www.ethiopianreporter.com/article/16312