Page 2 of 4

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 26 Jun 2019, 10:48
by Meleket
እኒህ ቆፍጣናና ከዓላማቸው ዝንፍ የማይሉት አርበኛ ለዛሬ፣ አልፋረዶ ካርሎ ሲቪል ለብሶ የመጣው ኮሎኔሉ የጣሊያን ሰላይ ማን ነው? እንዴትስ በጎንደር መንገድ ዘጌ ባህር ሲሰልል ህይወቱ አለፈች? ማንስ ገደለው? ለምን? ጣልያን ምን ዓይነት ሴራ ጎነጎነች? የሱን ወይንስ የባንዳዎችን ሞት እንደ ሰበብ ቆጥራ ነውን በኢትዮጵያ ላይ ጦርነቱን ያፋፋመችው? የጎንደሩ ከንቲባ ደስታ ምትኬ ጣሊያንን ለማብረድ ከአዲስ አበባ ምን እንዲያደርግ ታዘዘ? "ረቂቁ ዲፕሎማት" የተባሉት ባሻይ ዑቁባ ሚካኤል ገብረ ምን ሚና ነበራቸው? ለቀምት ላይስ ከኮሎኔል በላይ ኃይለኣብና ከአጋሮቹ ጋር ሆነው ፫ የጣሊያን አውሮፕላኖችን ምን አደረጓቸው? “ነፃነት ከሌለበት ሀገር ሚኒስትርነት ከመሾም ነፃነት ባለበት ሀገር ገበሬ መሆኔን እመርጣለሁ” እያሉ የነ አቶ መኮንን ሃብተወልድንና ቀኛዝማች ተኽለ ማርቆስን ድርጊት ለምን አብጠለጠሉት? እነዚህንና ተያያዥ ጉዳዮቹን ታሪከኛዉ አርበኛ ያስኮመኩሙናል። መልካም ንባብ።

“የጣሊያን መንግሥት ካለፉት ዓመታቶች ሁሉ የበለጠ ስለላ፣ በኢትዮጵያ በ፲፱፻፳፮ ዓ.ም. በቆንሱሎቹ ስለላውን ፈጸመ፤ ለጦርነት ተዘጋጀ። ለ፫ቱ መንግሥታት ለመካፈል ሲመኙዋት የነበሩትን ገነትዋ ኢትዮጵያ በጣሊያን ስም ብቻ እንድትያዝ፣ መብታቸው እንዲጠበቅ በፖለቲካና በገንዘብ፣ በመብልና በዕቃም እንዲረዱዋት ተስማሙ። በጣሊያን ስም ብቻ ኢትዮጵያ እንድትያዝ ወደው አልነበረም የተስማሙ። ሙሶሊኒ ከሂትለራዊ ጀርመን ጋር እንዳይስማማባቸውና ጣሊያንና ኢትዮጵያም መንግሥት በጦርነት ሲዳከሙ ከሁለቱ ጥቅም እናገኛለን ብለው ነው እንጂ ጣሊያን ኢትዮጵያን ድል መታ ትይዛለች አላሉም ነበር። ጣሊያንም ከፈረንሣይና ከእንግሊዝ ባገኙቹ ተስፋ የዶጋሊና የኣድዋን ድልና በቀል ለመመለስ፣ ኢትዮጵያንም አንድ ቀን እንኳ ይሁን ለመያዝዋ፤ የምታፈሰው ደምና የምታጠፋውም ገንዘብ ሳትቆጥብ መነሳትዋን ያልፈቀዱ ልጆችዋ ሰሚ አጥተው ስደት ተሰደዱ።” ገጽ77

“ስለዚሁም አስጨናቂ የሆነውን የኢትዮጵያ ወታደር ጦርነትና ወሰንና መሳይ የሌለውን ድፍረት ምንም እንኳ ጣሊያን ሓዳዲስ መሣሪያና አረዩጵላን ቦምብና የጋዝ መርዝ ጢስና ኢፕሪት በያይነቱ ፋሺስቶች በአረማዊነታቸው በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ቢጥሉበትም፣ ምን ጊዜም ደሙ አለመቀዝቀዙን ስለሚያውቁት በትንሹ አልተገመተም። ስለዚህ ሁሉ የጣሊያን መንግሥት የስለላና የፖለቲካ ክፍል ሰዎቹን “በየጊዜው ወደ ኢትዮጵያ በየስሙ ሲልክ በትሪፓሊ በ፲፱፻፫ ዓ.ም. ብዙ ጥቅም ያስገኘውን ካርሎ የተባለ ባለ ታሪክ ኮሎኔል፣ ሲቪል ለብሶ ተራ ነጋዴ መስሎ፣ በጎንደር መንገድ ዘጌ ባህር ገብቶ ሲሰልል ሳለ ኮሎኔል ካርሎ በጣሊያን አሽከር በአየለ ተገደለ። አየለም ሰላማዊ ሰው መስሎ ካርሎን ገደለና የኢትዮጵያ ሺፍቶች እድንዃኑ ውስጥ ገብተው ሌሊት ገደሉት ብሎም አስወራና ጎንደር እንደገባ በጣሊያን ቆንሱል ግቢ ታሠረ። የጣሊያንም መንግሥት ለኢትዮጵያ መንግሥት አስጨንቆ ከፍ ያለውን የገንዘብ ካሣ ወይም ዘጌ እንዲሠጠው ጠየቀ። የኢትዮጵያ መንግሥት የኮሎኔል ካርሎ መሞትና የጣሊያን መንግሥት ኢትዮጵያን ካሣ መጠየቅ እንግዳ ነገር ስለሆነበት ገንዘብ የተበደሩትንና ከሱ ጋር ግንኙነት የነበራቸውን እነ ቀኛዝማች በላይ መሸሻን ለማሳለፍ በጥብቅ አሰራቸው። የሚያደርገውም ጠፋው። እነሱም መግደላቸውን ፈጽመው ካዱ።” ገጽ 78

“በዚሁ መካከል ከሁለቱ መንግሥታት መልእክተኞች ተልከው ነገሩ ሲመረመር ፪ቱ ሐማሴኖች (የዛሬው አርበኛ ፊታውራሪ) አቶ ጊላጊዮርጊስና ባሻይ ዑቁባሚካኤል ገብረ የጣሊያን አነጋጋሪ አቶ ጊላጊዮርጊስ በኢትዮጵያ በኩል አባሎች ሆነው ስለተገኙ፣ ኢትዮጵያን በተሰወረ ፖለቲካ በመደገፋቸው የጣሊያን መንግሥት ኢትዮጵያን ካሣ ከመጠየቅ አስጣሉት። የሠገነይቲ ባሻይ ዑቁባሚካኤል ገብረ ለአቶ ጊላጊዮርጊስ ኮሎኔል ካርሎን ያስገደለው ኮመንዳቶረ ፖለራ ነው፤ ያስገደለውም የጎንደር ቆንሱል አሽከር የሆነ አየለ የተባለ ልኮ በራሱ በግል ቂሙና የዘጌንም መሬት ወይም ካሣ ለመንግሥቱ ለማሰጠት፣ ኢትዮጵያንም ለመጕዳት ባሰበው ኅሳብ መሠረት ነው፤ እና ተጠንቀቁ፣ ይህም የጎንደር ቆንሱል የካርሎ ገዳይ ነህ ብሎ አየለን አስሮ ሰንብቶ መልሶ ኢትዮጵያን ለመክሰስ ፈትቶ ለቀቀው ብለው ሲያስጠነቅቁዋቸው፣ አቶ ጊላጊዮርጊስም ለጐጃም ሕዝብ አስጠነቀቁትና የራሱ አሽከር አየለ የተባለ ካርሎን መግደሉን ድምፁን ከፍ አድርጎ መሰከረ። የኢትዮጵያ መንግሥት ከዚሁ ጥልቀኛው ፖለቲካ በባሻይ ዑቁባሚካኤል ገብረና በአቶ ጊላጊዮርጊስ ትጋትና ብርታት ከመጠየቅ ሲድኑ፣ በድፍን ኢትዮጵያ ጣሊያን መርዝ በተነ፤ ኤውሮጳም አረዮፕላኖች በኢትዮጵያ ጀግኖች ሲቃጠሉና ፲፪ የጦር መሪዎች ጄኔራሎችና ነጂዎች ሲገደሉ ባሻይ ዑቁባ ሚካኤል ገብረም ከገዳዎች ጋር አብረው ነበሩ።” ገጽ 78

“በጌራም በ፲፱፻፳፱ ዓ.ም. በታህሣሥ ወር በሆነው ጦርነት ከክቡር ራስ እምሩ ጋር ስለነበሩ በጄኔራል ማልታ ተማረኩ፤ በወላሞ ሶዶም ሲታሠሩና ሲፈቱ ቆይተው ባሻይ ዑቁባ ሚካኤል ገብረ በአሥመራና በጎንደር፣ ባዲስ አበባም በስውር የምስጢር ፖለቲካ ለኢትዮጵያ መንግሥት ከመሥራታቸው በላይ፣ በኢትዮጵያ ቀርተው ሥራ በመያዛቸውና በጦር ሜዳም በመገኘታቸው ቂመኛው የፋሽት መንግሥት ያለ አንዳች ኅዘኔታና ሰብአዊ ርህራሔ ጂማ ላይ መጋቢት ፬ት ቀን ፲፱፻፴፫ ዓ.ም. ባሻይ ዑቁባ ሚካኤል ገብረን ገደላቸው።” ገጽ 79

“በፓለራ ቆንሱልነት ጊዜ የተነሳው የካርሎ መገደል በዮሴፍ ዲ ላውሮ ጊዜ ተፋለሰ፤ ዬሴፍም የአጼ ቴዎድሮስ ስም ዓለማየሁ ልጅ ነኝ ብሎ ሰበከ፤ የኢትዮጵያ ልብስ ለበሰ። የራስ ካሣን እና የልጅ ደጃዝማች ካሣ መሸሻን ወዳጆች አደረገ፤ ግብርም ያበላና መሣሪያና ጥይት፣ ብርም መስጠቱን አዘወተረ። የሀገሩ ገዢዎች ደጃዝማች ወንድወሰን ካሣና ደጃዝማች ካሣ መሸሻም የሱን ግብር በመብላታቸው የጣሊያን ተገዢዎች መሰሉ።” ገጽ 79

“በጎንደር ቆንሱል ተሹሞ የመጣው ፋሽስታዊ ሻምበል ዮሴፍ ዲ ላውር መንግሥቱ ያዘዘውን አንባጓሮ በማንሳት በሰላማዊ የኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ባንዶቹ ተኩስ እንዲተኩሱበት የጠበቀ ትእዛዝ ሠጠ። የሱ ባንዶችም ሲተኩሱ የኢትዮጵያ ሰዎች ለተኩሱ መልስ ሰጡትና አንድ ሰው ስለገደሉበት ”የኢትዮጵያ መንግሥት ወታደሮች የቆንሱል ቤታችንን ዙሪያ ከበው ተኮሱብን የሞተና የቆሰለም ሆነናል” ብሎ ለሮማ ሙሲሉኒ በራዲዮ ዕለቱን አስታወቀ። የጣሊያንም መንግሥት ክብራችንን የኢትዮጵያ መንግሥት በወረራ ገፈፈን፤ ዘረፈን፤ ተገፋልን ሲል አስመስሎ በሐሰት ለማሳጣት ለዓለም መንግሥታት አስታወቀ። ለኢትዮጵያ መንግሥትም “ባንዳ በመግደላችሁ ለጣሊያን ባንዴራ ስገዱላት፤ ይቅርታም ጠይቁን ያለዚያ ጦርነት አነሳባችሁ አለሁ” ሲል ጊዜ ኢትዮጵያ ከጠብ ለመዳን ብሎ ከጎንደር ከንቲባ ደስታ ምትኬ ሰዎቹን አሠልፎ ለጣሊያን ባንደራ ይቅርታ ጠይቅ፣ ሰላምታም ስጣት ተብሎ ታዘዘ። የጎንደርም ከንቲባ ደስታ በአዲስ አበባ ትእዛዝ መሠረት ሊያደርገው የማይገባው በውርደት የተሞላ ሰላምታ ለጠላት ባንዴራ ሰጠ። በዚህ ጊዜ ኤርትራዊ የተባለ ወጣት ሁሉ ተስፋ ቆረጠ፤ ሞቱን መረጠ፤ ሰሚ ሰው ጠፋ እንጂ ብዙም ተናገረ። የጣሊያንም ሙሶሊኒ በዚህ በቃኝ አላለምና በየቀኑ መጣሁ እያለ ያስፈራራ ጀመር። ይህነኑም ጨካኝ፣ የጣሊያን መንግሥት ጭከና መጻፌ ለመጭው ኢትዮጵያዊ ትውልድ ጠቃሚና ሕያው ታሪክ ሆኖ እንዲያገለግለው ብዬ ነው።” ገጽ 79

ኢትዮጵያኖች ሆይ! ነፃነት ከሌለበት ሀገር ሚኒስትርነት ከመሾም ነፃነት ባለበት ሀገር ገበሬ መሆኔን እመርጣለሁ። ነፃነት ከሌለ ክብርና ጽድቅም የለም። ለጋ ለስላሳው የአኩሩር ከንቲባ አንዱ የልጅ ልጅ ባሻይ ዑቀባ ሚካኤል ገብረ የተሰወሩ የኢትዮጵያ ዲፕሎማሲ ረቂቅ ፖለቲካ መሪ መሆናቸውን ሳይገነዘብ የጣሊያን መንግሥት ከጎንደር አነጋጋሪነታቸው ወደ አዲስ አበባ ለጋሲዮን አዞራቸውና በ ፲፱፻፳፭ ዓ.ም. መጨረሻ መጥተው እንኳ የጎንደርና የአዲስ አበባ ፓለቲካቸው፣ የሮማም ሳይቀር አካፍለው በሰፊዉ የነ ኮሎኔል ካርሎን ምስጢራዊ የጠበቀ ስለላና መገደሉንም ከባሻይ ዑቁባ ሚካኤል ለማጥናት ቻልን።” ገጽ 80

“የጣሊያንም መንግሥት ከኢትዮጵያ ጥንታዊ ንጕሠ ነገሥት መንግሥት ጋር ጦርንት ለማድረግ ተሰናድቶ ሚኒስትሩን አዲስ አበባ ሲያስወጣ የሚኒስትሩ ዋና አነጋጋሪ ባሻይ ዕቁባ ሚካኤል ገብረ ከድተው ቀሩና የኢትዮጵያ መንግሥት ሥራ በውጭ ጕዳይ ሚኒስቴር ያዙ። ባሻይ ዑቁባ ሚካኤል ገብረ አዲስ አበባ በሚያዝያ ፳፯ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ጠላት እንደገባ በደፋሩ ያንበሳ ግልገል በኤርትራዊው ኮሎኔል በላይ ኃይልኣብ ከሚታዘዙት የሁለታ (አበባዎችን) ተማሪዎች ጋር ሆነው በለቀምት ያረፉትን ፫ት የጣሊያን አረዮፕላኖች አቃጥለዋል።” ገጽ 80

“በዚሁም፣ የኔው ከጃንሆይ የጐጃም ጕምሩክ ዲረክተር መሾሜ ከጽሕፈት ሚኒስቴር ለንግድ ሚኒስቴር ትእዛዝ እንደ ደረሰ የንግድ ሚኒስቴር ዋና ዲረክቴር አቶ መኮንን ሀብተ ወልድ ወደ ጃንሆይ ቀርበው “እኛ ሳንሰማው እንዴት አቶ ተስፋ ሚካኤል የጐጃም ጕምሩክ ይሾማሉ” ብለው ለማስቀረት ሲከራከሩ “ወይድ” ብለው መለሱዋቸው። ቢመልሱዋቸውም በጣሊያን ሚኒስቴር በጥብቅ አደራ ተብለው ኤርትራዊያኖችን ለማጕላላት ራስ ራሳችውን የተሳሙ አቶ መኰንን ሀብተ ወልድና የጽሕፈት ሚኒስቴር ዋና ዲራክቴር ቀኛዝማች ተክለ ማርቆስ የሀገራቸው በጠላት መከበብ ሳያሳዝናቸው የደመወዜ ፻፮ ብር ከጃንሆይ ለተቆረጠልኝ ማዘዣና ስንቅም ከልክለው ለማሰንበቴና አልሄደም ብለው፤ ነጋሪና መስካሪም ሆነው ንጕሠ ነገሥት ዘንድ ለማሳጣት ያለልክ መቅበዝበዛቸውንና ለማስቀረት መስማማታቸውን በንግግራቸው ስለተረዳሁት በቅጽበት ተነስቼ ደብረ ማርቆስ በ፮ ቀን ገባሁ።” ገጽ 80

እነዚህ ሁለት የኢትዮጵያ መንግሥት ዲረክተሮች ከመባላቸው ይልቅ የኢትዮጵያ እናታቸው ጠላቶችና ባለጋሮች ተብለው መጠራት የሚገባቸው ከነፃነት ባርነት፣ ከመግዛት መገዛትን የመረጡ፣ የጣሊያን ሚኒስቴር አደራና ፍቅርን የጠበቁ ውሸትና ማታለልን የታጠቁ (እንጂ) እፍረት የሌላቸው ዲረክተሮች ተብለው መጠራታቸው ኢትዮጵያን ኣያስመሰግናትም። ይህም የሆነበት ምክንያት ከአጼ ምኒልክ ጀምሮ በዚህ ቦታ የቆመው የአስተዳደር የታወረውን ደንብ “ፈረንጆቹን አክብሩ ታዘዙ” የሚል ስለሆነ ለፈረንጅ ያላከበረና ያልታዘዝ ሰው የሚሻርና የሚታሠር ብቻ እየመሠላቸውና ሆድ አምላኩ ሆነው፣ የራሳቸውን የግል ጥቅማቸውን እንዳይቀርባችው ሲሉ ነው እንጂ ከነሱ ጋር ጥልና በቀል እኛ ኤርትራዊያኖች ምንም የለነም ነበር።” ገጽ 81

"ዱሮም ከወሎ ጕምሩክ ዲረክተርነቴ አዲስ አበባ የተዛወርሁበትም ምክንያቱ የጣሊያን ቆንሱል አቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ ዕቃችንን በድፍረት ፈተሸብን፣ ጨቆነን፣ በዲስኩር ሰደበን እያሉ ሲሉኝ የነበሩትን የጣሊያን የፖለቲካ ሰዎች ዛሬም ደብረ ማርቆስ ቢሾም የጣሊያንን ቆንሱል አያሠራዉም ብለው ነው አቶ መኰንንና ቀኛዝማች ተክለ ማርቆስ የተጨነቁት። ከእንደዚህ የመሰለው ስሕተትና ውርደት ይሠውረን፤ ኣሜን። ገጽ 81

በቀጣዩ ክፍል አርበኛው ጎጃም ደብረማርቆስ እንደገቡና ሥራቸውን እንደተረከቡ ያጋጠማቸውን ጉዳይ፣ የአቶ መኰንን በሠራተኞች መጫወትና የጣሊያን ቆንሱል ባሮነ ሙዝ በዘበናይነቱ ማበጥ መጀመር በሚሉ ሃሳቦች ዙሪያ የጊዚያቸውን ቦለቲካ እየተነተኑ ታሪካቸውን ይቀጥሉልናል።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 02 Jul 2019, 09:07
by Meleket
የዛሬው ትርክት አሁን ያለው ትውልድ የመንግሥት አካሄድና ቢሮክራሲን ከዛሬ 100 ዓመት በፊት ከነበሩት ወላጆቹ መማር እንደሚገባው ይገልጽልናል። ያኔ ማንኛውም መንግሥታዊ ሥራና ትእዛዝ በጽሑፍ ይተላለፍ ነበር፡ አሁን በሰለጠነው ዓለም ደግሞ በቃል ብቻ ምስክርየለሽ ሥራ ለመሥራት የሚያነፈንፉትን መሰሪዎች እያየን እንገኛለን። በአሥተዳደር ረገድም ይህኛው ትውልድ ከቅድመ አያቶቹ ምን ያህል ወደ ኋላ እንደቀረ እንገነዘባለን። ባለታሪኩ አርበኛ በደብረማርቆስ ከጣልያን ቆንስሉ ጋር ያደረጉትን እሰጥ አገባም በዛሬው ትረካ አካተነዋል። መልካም ንባብ።

"ባለታሪኩ ከታላላቅ ባለሥልጣኖችና ግለሰቦች ጋር የተጻጻፉዋቸውን ደብዳቤዎች ናሙናዎች ከዚህ መጽሐፍ ገጾች ላይ በአባሪነት አስገብተናቸዋል። የተገኙትን ሁሉ ብናስገባቸው እጅግ ጠቃሚ በሆኑ ነበር፤ ነገር ግን ገጹ ስለሚባዛና የኅትመት ዋጋውን ከአቅም በላይ ስለሚያደርገው ተውናቸው።" ገጽ82

“ስለ የኔ የጐጃም ጕምሩክ ዳረክተር መሾም የተጻፉት ደብዳቤዎች - ራስ እምሩ -ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል - እንደምን ሰንብተሃል እግዚአብሄር ይመስገን እኛ ደህና ነን። የጻፍከው ደብዳቤ ደረሰኝ። እስካሁን የበቃ ሥራ ባለመያዝህ እደነቃለሁ። አሁንም ወደዚሁ መጥተህ ሥራ እንድትይዝ ማሰቤ አልቀረም፤ የሁሉንም እንድትጽፍልኝ። ጥቅምት ፳፱ ቀን ፲፱፻፳፮ ዓ.ም. ደብረ ማርቆስ ፌርማ እምሩ ኃ. ሥ.” ገጽ 82

“የኢትዮጵያ መንግሥት - የጽሕፈት ሚኒስቶር - ለክቡር የንግድ ሚኒስቴር - ነጋድራስ ሠርፀ ወልድና አቶ መሸሻ ገብረ ማርያም ስላልተስማሙ አቶ መሸሻ ወደዚህ እንዲመጣ። አቶ ተስፋሚካኤል ትኩእ የጐጃምን ጕምሩክ ዲረክተርነት ሥራ ተረክቦ እንዲሠራ ይሁን ብለዋል፤ የኢት.ን.ነ. መንግሥት ማህተም - ፊርማ ጸ፡ት ወልደ መስቀል (ገጽ 82)

“የኢት. ን ነገሥት መንግሥት - የንግድ ሚኒስቴር - ቁጥር ፫ሺ ፮፻፶፰ -ይድረስ ካቶ ተስፋሚካኤል - የጐጃም ጕምሩክ ዲረክተርነት ስለተሾምክ ለነጋ ድራስ ሠርፀ ወልድና ላቶ መሸሻ ገብረ ማርያም የጻፍነውን ማዘዣ ከዚህ ደብዳቤ ጋር ልከንልሃልና እዚህ ትሰራ የነበረውን ሥራ አስረክበህ በቶሎ ወደ ሥራህ እንድትሄድ ይሁን። ይህንኑም ላቶ ኃይለ ፀጋዬ አስታውቀነዋል። መጋቢት ፳፯ ቀን ፲፱፻፳፮ - የኢትዮጵያ ን.ነ.መን. ንግድ ሚኒስቴር ማህተም - ፊርማ መኰንን ሀብተ ወልድ (ገጽ 83)

“በቂ ሠራተኞች እንዲሠጡኝ ደመወዝ እንዲወሰንልኝ ብጽፍ የተሰጠኝ የክርክር የደነቆረ መልስ። የኢትዮጵያ ን.ነገሥት መንግሥት የንግድ ሚኒስቴር - ቁጥር ፫ሺህ ፯፻፵ - ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል - ስለሠራተኞችና ስለቀለብህ ሚያዝያ ፮ ቀን የጻፍክልን ደብዳቤ ደረሰን፤ የጐጃም ጕምሩክ አሁን አዲስ የቆመ ጕምሩክ ስላልሆነ ከዚህ ቀደም ጕምሩክ ሲቆም የሚያስፈልጕትን ሠራተኞች ልከናልና እዚያው ሄደህ ሥራውን መርምረህ በጐደለ ስትጽፍልን የሚያስፈልገውን እናደርጋለን። ቀለብህም እንዲቆረጥልህ እናመለክትልሃለን፤ እስከዚያ ድረስ ግን ወደ ሥራህ እንድትሄድ የሚያስፈልግ ስለሆነ በ፫ሺ፮፻፶፰ ቁጥር እንደጻፍንልህ ትእዛዝ በቶሎ ወደ ሥራህ እንድትሄድ ይሁን። ሚያዝያ ፲ ቀን ፲፱፻፳፮ ዓ.ም. ። ቀዳማዊ ኃ.ሥ.ን.ነ. ዘኢትዮጵያ የንግድ ሚኒስቴር - ፊርማ መኰንን ሀብተ ወልድ ” ገጽ 83

“በሚያዝያ ፲፮ ቀን ፲፱፻፳፮ ዓ.ም. በበቅሎ ኪራይ ከነ ቤተ ሰዎቼ ደብረ ማርቆስ ገና እንደገባሁ የደጕ ክቡር ራስ እምሩ ኃይለሥላሴ አባይነህ ያጌጠ በያይነቱ መስተንግዶ የተሸከሙ የግቢ አሽከሮችና ገረዶች ከመግባታችን አለበሱን። ወደ ግቢ ገብቼም አዋቂው ራስ እምሩን እጅ ለመንሳት መጣሁና እጅ ስነሳቸው “ስንቅ ተቀብለሐል?” ጃንሆይ ፻፮ ብር ደመወዝ ቆርጠውልህ ነበር፣ ሲቆርጡልህም ቀኛዝማች ተክለ ማርቆስ ቃላቸውን ሰምቶዋል፤ ማዘዣ ተቀብለሐልን” ብለው ጠየቁኝ። “ስንቅ ከለከሉኝ፤ ስለ ደመወዝህም ለወደፊቱ እንዲቆረጥልህ እናመለክትልሃለን። እስከዚያ ድረስ ግን ወደሥራህ እንድትሄድ” ብለው እንዳልሄድና እንዳልቀርም ስላደረጕኝ ዝም ብዬ መጣሁ” ስላቸው በብዙ አዘኑ። ወዲያውኑ ግምጃ ቤት ቀኛዝማች ከበደ ብሩን ሠፈሬ ድረስ መጥቶ ፻ ብር እንዲሠጠኝ አስይዘው ላኩልኝ።” ገጽ 83

አማካሪዎቾ እኛ ነን” ብለው በመመካት ለደመወዜ ማዘዣና እንደ የመንግሥት ሠራተኞችም ሁሉ ስንቅ ከልክለው፣ ስውል ሳድር ነጋሪና መስካሪ ሆነው “ተስፋ ሚካኤል ግርማዊነትዎ መልካም ሰው መስሎት የጐጃም ዲረክቴርነት ቢሾመውና ወደ ሥራህ እንድትሄድ ብለን ብናዘው ከተማ ተቀምጦዋል” ብለው በማሳጣት ለማስቀረት የተሰናዱትን ቀኛዝማች ተክለ ማርቆስና አቶ መኮንን ሀብተወልድ በግስገሳ ደብረማርቆስ (መንቆረር) መግባቴን በራስ እምሩ በኔም ስም ቴሌግራም በመቀበላቸው ወሰን በሌለው ኅዘን ተቃጠሉ፤ ሥራው በደንብ እንዳይካሔድም በብዙ ደከሙ፤ ድካማቸውም ሁሉ የጣሊያን ቆንሱል ተቆጣጣሪ ሰው ሳይኖረው በነፃነት በጐጃም እንዲሠራ ብለው ነው።” ገጽ 84

“በማግስቱም የጐጃም ሠራተኞች ወደኔ መጥተው “በየጊዜው አዲስ አበባ ሔደን ለንግድ ሚኒስቴር ዲረክተር ላቶ መኰንን ብናመለክታቸው ነጋድራሱና ዲረክተሩ ቀለባችሁን ይወስኑላችሁላ ብለዉን ነበር። ያለ ደመወዝም ካንድ ዓመት በላይ ሠራን፤ ደመወዝም የማይሠጠን ከሆነ አሰናብቱን” ብለው ሲሉኝ ደመወዝ ለመስጠታቸው ባለመቻሌ እያዘንሁ ባቶ መኰንን ሀብተ ወልድ ከእውነት መንገድ የራቀ ንግግራቸው ተደነቅሁ። እማደርገውም ጠፋኝ። ስለዚህ እኔም ለክቡር ራስ እምሩ በግልጽ “የሠራተኞች ደመወዝ ተወስኖ ካልተሰጣቸው በቀር ሥራ መሥራት ችግር ስለሆነ ከሁሉም ሥራ በፊት የሠራተኞቹን ደመወዝ ይወስኑልኝ” ስላቸው፣ አዋቂው ኢትዮጵያዊም “ደልድለህ አምጣልኝ፤ እሽ” አሉን። እኔም የሰዎቹን ዝርዝርና የገንዘቡንም ልክ ሰንጠረጅ አሰናድቼ ፈርሜና ነጋድ ራሥ ሠርፀ ወልድን አስፈርሜ ሳቀርብላቸው በደቂቅ ፈርመው በየወሩ ሠራተኞች ደመወዝ፣ ደመወዛቸውን እንዲቀበሉ ማዘዣ ሰጡን። ሠራተኛም ራስ እምሩን አመሰገነ፤ ለኔ ከኅሊና የማይስማማውን መጥፎ ክርክርና አድልዎም ከመጨነቅ አሳረፉኝ።” ገጽ 84

“እኔም ከመድረሴ በፊት ላንድ የደብረ ማርቆስ የመደብ ሠራተኛ ልጅ ፩ዲት ቤሣ ከገቢው የቀን ሂሳብ ቢጐድልበት በጅራፍ እንዲገረፍ ሲሉ ነጋድ ራስ ሠርፀወልድ በራስ እምሩ ችሎት ቢያቀርቡት በብዙ ተቆጥተው ነፃ ለቀቁት። ይህና ከዚህም የባሰው የባለሥልጣኖቹ መጥፎ ሥራ ከዚህ የመረረውን የጣሊያንን ግፍ ጐተተ። አመጣም።” ገጽ 84

“በጐጃም አገው ምድር በዳንግላ ተቀምጦ የጻና ባህር ሀብትና የዳንግላን የባሮች መሸጫ ገበያ መርምሮ የተረዳና ለመንግሥቱም በሰፊው ያስረዳ የእንግሊዝ መንግሥት ቆንሱል ሥራውን ፈጽሞ ለጣሊያን መንግሥት ቁንሱል ስብከቱን ለቆለት ሔደ። በራስ ኃይሉ ተክለ ሃይማኖት መሻርና መታሠር ብቻ ሳይሆን በጣሊያንም የማያቋርጥ ብርቱ የፕሮፓጋንድ መጥፎ ስብከት በጐጃም ሕዝብ ልዩ ሃሳብ ተወለደ። ምንም እንኳ ቢገፉትና ቢበድሉት የጐጃም ሕዝብ በመታሠራቸው አዘነ እንጂ በደላቸውን አላስታወሰም። የኢትዮጵያ መንግሥት ልዑል ራስ ኃይሉን ልጅ ኢያሱን አቀፉ ከጣሊያን ጋራም ተስማሙ ብሎ አሠራቸው እንጂ ሕዝብን በድለዋል፣ በሳቸውም መጥፎ አገዛዝ ጐበዝ ወደ ትራፓሊ ለገንዘብ ብሎ እየሔደ አልቆዋል፣ ብሎ መንግሥት አላሠራቸው ነበርና ወጣት የተባሉ ሁሉ በሕዝብ ጉዳት አጥብቆ አዘነ።” ገጽ 85

የጣሊያን ቆንሱል ባሮነ ሙዝ በዘበናይነቱ ማበጥ ጀመረ። ይህ ባሮነ ሙዝ የተባለ ወጣት በአዲስ አበባ የሚቀመጥ የእንግሊዝ ሚኒስተር ልጅ አግብቶ ስለነበረ፣ በማበጡ ላይ የበለጠ ማበጥን መበጥበጥም ጨመረበት፤ ኢትዮጵያንም በእጁ የጨበጠ መሰለው። ኤርትራዊያን ከሆኑት አነጋጋሪው ብላት ወልደ ሚካኤልና ጸሐፊው ከአቶ ሰሎሞን ወልደ ኪዳን፣ ከአቶ ተክሌ ኃይሉ የራዲዮ ሠራተኛው ጋር ስምምነት ፈጽሞ አጣ። እነሱም ከዱትና መልካም አድርገው ራስ እምሩ ስላስቀመጡዋቸው ሙዝ በእግርና በፈረስ እስከ ዓባይ ድረስ ቢፍልግና ቢያስፈልጋቸውም ሳያገኛቸው ስለቀረ በጐጃም ብጥብጥ ተነሳ። በኔ ወደ ጐጃም መምጣትም በበለጠ ኅዘን አዘነ። ስለምን? በደሴ የነበሩትን የጣሊያን ቆንሱሎች ብሪዬሊና ካርሎ እናራቶነ በሰፊው ለአዲስ አበባ ሚኒስትራቸው አቶ ተስፋ ሚካኤል በመቃወምና በዲስኩር፣ በስድብም አላሠራም አለን ብለው በየጊዜው ስላመለከቱት የጣሊያን ጠላት መሆኔን ስለሚያውቅ ነው።” ገጽ 85

“ እንዲሁም በ ፲፱፻፳፭ ዓ.ም. የሐረር ቆንሱል አነጋጋሪዎች ባሻይ ተስፋ ማርያም ገደላና ባሻይ ገብረ እግዚአብሄር ወልደ ሚካኤልም የምስጢር ደብዳቤዎቹን ሰብስበው ስለከዱት የኤርትራዊያንና የጣሊያንን መንግሥት ጠብና ጥል እየገነነ ሲሄድ፣ በዚያን ጊዜ አታሽ ሚሊተሪ ተብሎ ተሹሞ የመጣው ኮሎኔል ሩጀሮ ለብዙ ባለሥልጣኖች በብዙ ሽህ የሚቆጠር ብር ሲያድላቸው እነ አቶ “በልተን እንሞት” መሸከም እስክያቅታቸው ድረስ ብር በሣጥን፣ በሣጥን ሞልቶ ሲሰጣቸው ያልተቀበለ አልነበረም። ከመቀበላቸውም የበለጠ “ጣሊያንን እናደኸየዋለን ዝም ብለህ ተቀበልልኝ Aየተባባሉ” ማለታቸውን ነበር የሚያናድደን። ስለምን ብራቸው ጨምሮ መወሰዱንና ዘውዳቸውና ሀገራቸውን መቀማቱ፣ ርስታቸውና ምሽቶቻቸውን መወሰዱን፣ ያለ ብር መቀበላቸው በቀር መታሠራቸውና በዶማና በአካፋ Aንደ እባብ Aየተቀጠቀጡ መገደላቸውን ባለማሰባቸውን ነው - ለኤርትራ ልጆች የበለጠ ኅዘንና ስቃይ ሲሰማን የነበረ።” ገጽ 86

“እንደዚሁም በጐጃም ለማንም ሰው ሳይቀር እንደየማዕረጕ ብር እየሰጠ “የጣሊያን መንግሥት በሸዋ ላይ ጦርነት ያነሳል፤ ጐጃምም ለሸዋ ኣይረዳም” እያለ ስብከት አሰበከ። ከሰባክዮቹና ከብር አቀባዎቹም ስዎች ተያዙ። በክቡር ራስ እምሩም ጥበባዊ የእውቀት ሥራ ብዛት ተይዘውና ብር ለየሰዎቹ ሌት እየሄዱ መሥጠታቸውንና በየገበያው ስብከት መስበካቸውን አምነው እንደየጥፋታቸው መጠን እሥራትና ግርፋት በችሎት ተፈረደባቸው። በዚህ ጊዘ ባሮነ ሙዝ አበደ፤ የሚያደርገውም ጠፋው። የኢትዮጵያም የውጭ ጕዳይ ሚኒስቴር በጐጃም የጣሊያን ቆንሱል ራዲዮ እንዲያቆም በመፍቀዱ እየወቀስሁ፣ ባንዴራውን በመኖሪያ ቤቱ ይሥቀለው እንጂ ያለ ደንቡ በመሬት ላይ ስለምን ይተክላል ብዬ ለራስ ብጠይቅ፣ ራስም በተቆርቋሪው ኢትዮጵያዊ ስም እንዲከለከል ጥያቄ ቢያሳልፉ በገንዘብ የተገዛው ሚኒስትር ከክብሩ እንዳይወርድ፣ ከሹመቱም እንዳይሻር የጣሊያን መንግሥት ወዳጅነትና በሚሊዮን የሚሰጠውም ብር እንዳይቀርበት ብሎ “ጠብ ያነሳብናልና የፈቀደውን ሥራም ቢሠራ ኣንዳትቃወሙት” የሚል መልስ ልኮ አሳፈረን። እኔም በበለጠ ኅዘን አዘንኩ፤ ተስፋም ቆረጥሁ፤ ያለ ልክ ጣሊያንን መፍራታቸውንና መገዛታቸውንም ተረዳሁት። በዚሁም መሳይ የሌለው ኅዘንና ስቃይ ታምሜ ወደቅሁ። ኅዘን እማዝነውና እምሰቃየው ስለሀገሬ ብቻ ሳይሆን ከኤርትራ ስላስመጣሁዋቸው ልጆቼና ባለቤትም ነበር። ” ገጽ 86

“እንግሊዛዊት የሙዝ ባለቤትም በጽሞና በጐጃም መኖርን አጥብቃ ጠላችና አዲስ አበባ ለመሔድ ስላስቸገረች፣ በመጨነቅ ተጠበበ፤ በሥራውም አልተደሰተም ነበር። ስለምን አዋቂው ራስ እምሩ በጥበባዊ ሥራቸው ዙሪያውን አስከብበው በቤቱ ውስጥ የሚሠራውን ሥራ ሳይቀር ዕለቱን ስለሚያውቁበት ኅሳቡን ሁሉ በመሠረዙ እሥረኛቸው መሆኑን ስለተረድው ተጨነቀ። እንዳይሠራ በራስ እምሩ እውቀት በመታሠሩና ባንድ በኩልም በምሽቱ በጽሞና መኖርን በመጥላትዋም በመታወኩ ምክንያት ባሮነ ሙዝ ባለቤቱን ይዞ ከጐጃም ወደ አዲስ አበባ ለመሔድ ተነሳ። የደብረ ማርቆስ ጕምሩክ ሠራተኞች በበር ከልክለው በባለቤቴ ላይ ሳቁባት፣ ሰደቡዋትም፣ እያለ አምባጓሮ ለማንሳት በ፲፱፻፳፯ ዓ.ም. በግንቦት ወር ባሮነ ሙዝ እንደ አንድ ዕብድ መለሎ በቢሮዬ ተንደርድሮ ገባ። ከገባም በኋላ እነዚህ በባለቤቴ ሳቅ የሳቁና ስድብም የተሣደቡ ሠራተኞች ቀጥተህ ከሥራቸው ማስወገድ አለብህ፣ አለዚያም ባለቤቴን ያሰደብካትና ያሳቅባት አንተነህ አለኝ፤ እኔም ትነጣጠራቸው እንደሆነ ሥራቱን ልይልህ፣ ካለዚያ ባንተው ቃል የኢትዮጵያ መንግሥት ሠራተኞች ማንም ሰው ሊቀጣቸው ዓይችልም፤ ስለው በበለጠ ተናደደና በቁጣ እየጋለበ ወደ ግቢ ወደ ክቡር ራስ እምሩ ሔዶ ከሰሰኝ። እኔንም ከልካይ በፍጥነት መጥቶ ራስ ይጠሩዎታል ይድረሱ አለኝና በበቅሎ ወደ ግቢ ወጣሁ፤ ባሮነ ሙዝም በብላታ ንግሩ አነጋጋሪነት አቶ ተስፋ ሚካኤል የጕምሩክ ሠራጠኞች አዞ ባለቤቴን አሰደባት፣ መሳቅያም አስደረጋት እያለ ሲናገር ደረስሁበትና ከዚህ በላይ እንደተመለከተው ቃል ለክቡር ራስ እምሩ አስረዳሁዋቸው።” ገጽ 87

ባሮነ ሙዝ ግን ላመጣው የሐሰት አስመሳይ የማታለል ቃሉ በክርክር ስላቸነፍሁት ራስ ፊት የማስፈራራትና የፉከራ ቃል ሲያነሳ በደንብ ሆነህ ተናገር ብዬ ባባቱ ቋንቋ ልኩን ብነግረው፣” አቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ የኤርትራ ተወላጅ ስለሆነ ከኔ ጋራ ተቋቁሞ እኩል ሊነጋገር ዓይችልምና፤ የሚገባውን ቅጣት ባለቤቴን ስላሰደባትና ስላሳቀባት ቅጣት ይቅጡልኝ፤ የተሰደብነውም እኔና እግሊዛዊት ባለቤቴ ነን” ሲል ነገሩን ለማነካካት ብሎ መነሳቱን ማስረጃ ተገኘለት። እኔም እንደዚህ መለስሁለት “ባሮነ ሙዝ እጅግ ተሳስተሀል፤ ሕጋችሁም ሕግ ለሁሉ እኩል ነው ሲል አንተው መፋቅህ። እኔም እውነተኛው ኤርትራዊ ኢትዮጵያዊ ነኝ፤ ኤርትራዊ የሆነው ሰው ሁሉ በኤርትራና በሶማሊያ ከሕግ ውጭ በሆነው በአድልዎ የተሞላ ደንባችሁ በሚገዛው ቅኝ ሀገራችሁ በቀር በማንም መንግሥት ዘንድ የታወቀና ለመነጋገርም የሚችል ነፃ ሕዝብ ነውና አንተ ተሰውረህ እንደምትሠራውና እንደምታስበው ዓይምሠልህ፤ ተሳስተሐል። የኔም ኤርትራዊነቴ እጅግ አድርጎ የሚያኮራኝ ነው እንጂ የሚያሳፍረኝ ዓይምሰልህ” ስለው የሚያደርገው ጠፋው። “እናንተ ኤርትራዊያኖች ብትከዱና ብትሸፍቱም የጣሊያን ተገዥዎች ናችሁ፤” እያለ ጠቡን በብዙ አከረረውና እኔንም እፊትዎ ሰደበኝ ሲላቸው፣ ክቡር ራስ እምሩም “በቂ መርቻ ያለበት ነገር አንጣ፤ ካለዚያ ባንተ ቃል ማንንም ሰው ለማሰርና ለመቅጣትም አልችልም” ሲሉት ጊዜ ባሮነ ሙዝ በትልቅ ቁጣ ተነስቶ እየፎከረ መንገዱን ቀጠለ።” ገጽ 87

ብቀጣዩ ክፍል “የባሮነ ሙዝ አዲስ አበባ መግባትና ጎሐ ጽዮን ደርሶ በፍራት መመለስ፣ ሙስ በግዴታ እንዲመልስ ቢታዘዝ በፊቼ ራሱን መምታቱና ኢትዮጵያኖች ገደሉኝ ብሎ በሐሰት መመስከሩ” የሚለውን ክፍል እንቃኛለን ቀጥለንም ወደ አይቀሬው የኢትዮጵያና ጣልያን ጦርነት ታሪክ እንዲህ እንዲህ የታሪከኛውን አርበኛ ታሪክ እየኮመኮምን እናዘግማለን።  

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 05 Jul 2019, 11:02
by Meleket
አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ ዛሬ ስለ በደብረ ማርቆስ የጣሊያኑ ቆንሱል ባሮነ ሙዝ፣ ስለሸረበው ሸፍጥ፣ ስለ ቅሌቱ መዋረዱና ማፈሩ እንዲሁም ጣልያን በምን መላ የኢትዮጵያውያንን ምስጢር ታገኝ እንደነበረችም ሆድ አደሮችን እየወረፉ ይገልጹልናል። መልካም ንባብ።

“የጣሊያን ቆንሱል ባሮነ ሙዝ በጐጃም ሕዝብ ላይ የጣሊያንን የስብከት መንፈስ ለማስፋፋት በሚያስበው ኅሳብ ሁሉ አስተዋይ የራስ እምሩ እውቀት በቅጽበት በማፍረስ ስለሚሰርዝበትና ያለ ፍቃዳቸውም እንዳይወጣ፣ ቢወጣም ፍቃድ ጠይቆ አብሮት የሚሄድ ሰው ስለሚሰጡት መሥራቱ ቀርቶ ኅሳቡን በመመርመር ቤቱ ዘግቶ እንዲቀመጥም አደረጉት። ባለቤቱም ያዲስ አበባ ፍቅር ስለያዛት ከደብረ ማርቆስ ተነስቶ አዲስ አበባ ደረሰ፤ ከመግባቱም የጣሊያን ሚኒስትር ተቆጣውና ባለቤቱ ጐጃም አልመለስም ብላ ስላለችው፣ በፍቅርዋ እያለቀሰ ጎሐ ጽዮን ብቅ ብሎ ዓባይን ሲመለከት፣ “የባሮነ ሙዝ አዲስ አበባ መግባትና ጎሐ ጽዮን ደርሶ በፍራት መመለስ” እንደተባለው፣ በመመለሱ ዓለም ሳቀበት። የጣሊያ ሚኒስትርም ሰድቦና ተቆጥቶ ተመልሶ ወደ ጐጃም እንዲመለስ ቢያዘው “ኣለ ባለቤቴ አልሄድም” ቢል፣ ባለቤቱም ካዲስ አበባ ፈረስ ግልብያ አልወጣም ብትል፣ በግድ ከባለቤትዋ ጋር እንድትሔድ ተደረገና አብረው እያጕረመረሙ ፊቼ ሲደርሱ የጣሊያንም ሚኒስትር ወዳጅ ስለነበረች በመለየትዋ ኅዘን ገብቶባት “ባልሽ ከዓባይ ሓፋፍ የተመለሰ ፈርቶ ነው ብሎ የጣሊያን ሚኒስትር ነገረኝ። እውነትም ፈሪ ነህ፤ አላንቺ ጐጃም ብቻዬን አልሔድም ብለህ አብርዬህ እንድሔድ አድርገህ ያስገደድኸኝ ብላ ስትለው፣ “ሞኝ የነገሩትን አይረሳም” እንደተባለው ተረት ከባለቤቱ ጋር “እኔ ፈሪ አይደለሁም” እያለ ፎከረ። ተጣላት፤ ለብቻውም ተለየ።” ገጽ 88

“ብርቱና ጀግና ወንድ የመሰለውን የጣሊያን ቆንሱል ባሮነ ሙዝ እንግሊዛዊት ባለቤቱ ከወዳጅዋ ለይቶ በግድ ስላመጣትና አዲስ አበባም ለመመለስ ስለተመኘች። “ባልሽ ከዓባይ ሐፋፍ የተመለሰ ፈርቶ ነው ብሎ የጣሊያን ሚኒስትር ነገረኝ” ብላ ስትለው ወንድ መስሎ ሽጉጡን መዞ በራሱ ላይ እንደማይገድለው አድርጎ ተኮሰ። ሽጕጡንም ለማስመሰል ወርውሮ ጣለው። በዚህ ጊዜ አሽከሮቹ ረዱ፤ ባለቤቱም ደንግጣ ካኮረፈችበት በሩጫ መጣችና ስትጠይቀው “የኢትዮጵያ ሽፍቶች ገደሉኝ፤ ያስገደለንም ራሱ መንግስታቸው ነው” ብሎ አላት። በዚሁም መካከል ከአሽከሮቹ አንዱ ከበደ ቸኮል የተባለና ሀገሩን የሚያፈቅር፣ ትሮፓሊ የኖረ የቡሬ ዳሞት ሰው ሙዝ የጣላትን ሽጕጥ በስውር አንስቶ አዲስ አበባ ሙዝን ተሸክመውት ሲገቡ ሆስፒታል ገባ። የደብረ ማርቆስ ቆንሱላችን ባሮነ ሙዝ በየኢትዮጵያ መንግሥት ሰዎች ስለቆሰለ ለመሞት ያጣጥራል፤ የጣሊያንም መንግሥት ክብር ተዋረደ፤ የሚል ያዲስ አበባ ሚኒስትሩ ቃል የደረሰለትን ሙሶሊኒ በሞላው የዓለም መንግሥታት ፊት ኢትዮጵያን ኃጢያተኛ ናት ብሎ ለመውጋትም የሚመኘውን ሙሶሊኒ ደስ ብሎት አፉን ከፍቶ አሰማ፤ በሐሰትም ለመውጋትዋ ተነሳ።” ገጽ 89

“ባሮነ ሙዝና ባለቤቱም በጕባዔ ተመርምረው የኢትዮጵያ ሰዎች ናቸው ያቆሰሉኝ ብሎ በሐሰት የሰጠውን ቃሉንና የባለቤቱም ቃል አንድ ሆነ፤ በጕባዔው የተሰበሰቡትም ሰዎች አመኑ፤ የኢትዮጵያ መንግሥትም በነገሩ እጅግ ተጨንቆበት ሳለ ከበደ ቸኮል በሀገሩ በኢትዮጵያ አንዳች ጕዳት እንዳይደርስባት በማሰቡ ሙዝ ራሱን የመታበትን ሽጕጥ በስውር አንስቶ ከጣሊያንም ለጋሲዮን ባጥር ተሾልኮ ወጥቶ ሌሊት ላይ ለዶክቶር ሎረንሶ መብራህቱ ታእዛዝ ለየኢትዮጵያ መንግሥት አማካሪ አስረከበ። ዶክቶር ሎረንስ መብራህቱ ታእዛዝም አቶ ከበደንና ሽጕጢቱን ይዘው ወዲያውን ወደ ግርማዊ ንጕሠ ነገሥት ፊት አቅርበው ካሳዩ በኋላ ሽጕጢቱ ከነ ቀልሀዋ ለዚሁ ኮሚሲዮን ለተሰበሰቡቱ ሰዎች አሳይተው፣ ይህ ሽጕጥ ሙዝ ራሱን የመታበት መሆኑን በቀለሁ ታወቀና ተመሰከረበት። በዚሁ ጊዜም የሙዝ ቃል ብቻ ሳይሆን የሙሶሊኒና የጣሊያን ቃል በመረታቱ አፈረ፤ ተዋረደ። በዓለም ሕዝብ ፊትም ዋጋ አጣ። አታላይ፣ የሐሰት ፖለቲካ ስብከት መስበኩን በማንም ዘንድ ግልጽ ሆኖ ተነገረ፤ ተሳቀባቸውም።” ገጽ 89

በአርእስቱም ባሮነ ሙዝ በግዴታ ወደ ጐጃም እንዲመልስ ዚታዘዝ በፍቼ ራሱ መምታቱንና ኢትዮጵያውያኖች ገደሉኝ ብሎ በሐሰት መመስከሩን የተባለበት ምክንያት በዚሁ ወሰንና መሳይ የሌለው የጣሊያን መንግሥት ወራሪነት በኢትዮጵያ ላይ ለማስከተል የታሰበ መሠረትና እውነት የሌለበት በኅሰት የታወረ ምኞት ብቻ መሆኑን ተመሰከረባቸው። አሥር ጊዜ በሐሰተኛነታቸው ቢመሰከርባቸውና በሐማሴነው የአከለጕዛይ ቡቺላ ወይ ታማኝ ጠባቂ በዶክቶር ሎረንሶ ታእዛዝ ቢረቱም፣ ሙሶሊኒና ወገኖቹ የሆኑት የጣሊያን ፋሺስቶች መረታታቸውን ቢያምኑትም የኢትዮጵያ መንግሥት በሰቲትና በጎንደር፣ በዘጌና በወልወል ከ፲፱፻፳፭ ጀምሮ እስከ ፲፱፻፳፯ ዓ.ም. ድረስ እውነተኞች ለመምሰል አቤቱታቸውን ከፍ ባለው ድምፅ ለዓለም መንግሥታት አሰሙ።” ገጽ 89

“ሙሶሊኒ በየጊዜው በኢትዮጵያ ላይ ያስነሳውን የሌብነት ልዩ ልዩ ልምድ ስራ ያላቸውን ሰዎች እየመረጠ በተሸከመው ነውር አለማፈሩ እጅግ የሚያሳዝንም ቢሆን፣ እንደ ካፒታኖ ቺማሩታ የመሰለ በወልወል፣ እንደ ግራሲያኒ የመሰለውን የቸረናይካን ሕዝብ የጨረሰውን ለመቃድሾ ጦር ኣዛዥ አድርጎ መላኩን ቀጠለ። ባሮነ ሙዝም ከሆስፒታል ወጥቶ በመረታቱ ወርደቱንና ሐሰቱን ለብሶ ወደ ሀገሩ ተሣፈረ። ጨክኖ ባለመሞቱም ለኢትዮጵያ መልካም ሆነ፤ በዘመዶቹ ዘንድ ግን ፈሪነቱ ተመስክሮበት አንዳች ምስጋና ሳያገኝ ቀረ።” ገጽ 90

“በጣሊያንም ፖለቲካዊ ዘዴ ከኣስያ የምሥራቅ ሰዎች በስተቀር፣ በኤውሮጳ ሰዎች በልዩ ልዩ የሥራ ስም አድርጎ ለሰለላና ለምርመራም ያለ ማቋረጥ ወደ ኢትዮጵያ እየቀጠረ ላከ። ራሳቸው በዚያን ጊዜ የኢትዮጵያን መንግሥት ከፍተኛው ሥልጣን በእጃቸው ጨብጠው የነበሩት ሰዎችም ወደ ጠላት በመሆናቸው ምክንያት በቀላሉ የኢትዮጵያ ምስጢር ሊያገኝ ቻለ። የኢትዮጵያ አፍቃሪዎች እንደ ጠላቶች፣ ጠላቶችም እንደ ወዳጆችዋ አድርገው እየደለደሉና መጥፎ ቦታና መጥፎ ግምትም ለጀግኖችዋ እየሰጡቱ፣ ኢትዮጵያ ድል እንድትሆን ያስደረጕዋት አንዳንድ የተረገሙ፣ ህሊና ቢሶች የሆኑት ሐሞት የሌላቸው ሰዎች በነገሩ ተጨምረው የጣሊያን ወገን በመሆናቸውና ሥራው ሁሉ እንዳይሠራ በመቃወማቸው፣ ምስጢርን ሁሉ ለጠላት በማቀበላቸው ነው።” ገጽ 90

በቀጣይ ክፍል መንግሥትን መሰሪ ምክር ስለሚመክሩ የመንግሥት አማካሪዎች ከአጤዉና ለራስ እምሩ ከራስ ካሳም ከራስ ሥዩምና ከፊተውራሪ ብሩ የዝውውር ሃሳብ አኳያ የጣሊያንን መሰሪ አላማ ለማሳካት የተሸረበውን ሴራ ያብጠለጥሉታል፣ ሆድ አደሮችንም ይወርዱባቸዋል። አርበኛው ከራስ እምሩ ጋር ከጎጃም ወዴት እንዳቀኑም ይገልጹልናል። በቡሬና በገነትዋ የአንጃባራ አበቤ ዳንግላ አድርገው ደንገል በር እንደደረሱ ከዚያም ከአቶ ዮሐንስ ዓብዱ ጋር ፊታውራሪዎች ሆነው ወደ ጎንደር አርማጭሆን አቋርጠው ጸገደ ወልቃይት ወደ ደጃዝማች አያለው ብሩ ታዘው እንደተላኩ በመግለጽ እዛ ያጋጣማቸውን የግዜውን ፖለቲካዊ ትኩሳትም በብስለት እየተነተኑ ያስኮመኩሙናል፣ ስለ ደፋሩ ጋይንቴው ፊተውራሪ ሺፈራዉም ያወጉናል አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ!

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 11 Jul 2019, 10:37
by Meleket
ለፋሺስት ጣሊያን ያደሩ ባንዳዎችን የሚጠየፉት አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ ትረካቸው 20ኛ ምእራፍ ላይ ደርሷል፣ ለዛሬም እንደወረደ አቅርበነዋል። ታሪክ መስታውትም አይደል በጥንቃቄ ስናነበው ብዙ ነገሮችን እናስተውልበታለን እናይበታለን! እንዳባጉና የዛሬ ምናምን ዓመት ጋይንቴው ፊተውራሪ ሺፈራው ፋሺስት ጣልያንን ያርበደበዱበት ቦታ መሆኑንም እንረዳለን።

ከአዋቂው ነጋድራስ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ ጀምሮ በአቶ ገብረ እግዚአብሔር ደስታም ጊዜ የንግድ ሚኒስቴር ሥራ እየተቻቻለ በመሔዱ በበርና በገበያ፣ በየ ሀገሩም ውስጥ የአዛዥነቱን ሥልጣን በማሳየቱም ስሙ ተነሳ፤ አስተዳደሩም ከሁሎቹ ሚኒስቴሮች የበለጠ ስለነበረ ተመሰገነ። በየ ጠቅላይ ግዛትም ነጋድራስ እያለ ሹም ሲልክ የሥራ ርምጃ መራመዱን ሲጀምር ከፍ ያለ የወገንና የአድልዎ ሰዎች ተነስተው ራሳቸውን ንጹሕ ለማድረግ ሲሉ የንግድ ሚኒስቴርን ሥራና ሥልጣን ዕለቱን እንዲደመስስ በስውር አስፈረዱበት።” ገጽ 91

ከልብ ሣይሆን በአፋዊ ስብከት ለጦርነት መሰናዳ ተጀመረ፤ መጀመሩንም የወደዱት ሰዎች ለራሳቸው ክብርና ጥቅም ለማግኘት የሚሹ፣ ዛሬ ክብርና ደረጃ ሀብትና ጥቅም ያልተለያቸው ሰዎች፣ ክብር ላይ ክብር፣ ሀብት ላይ የበለጠውን ሀብትና ጥቅም እንጨምራለን የሚሉ ሰዎች ነበሩ። ታማኞች መስለው በደላላነታቸው ያባትና የናት ሀገራቸውን ለጠላታቸው ለጣሊያን አሳልፈው ለመስጠት ተጣደፉ፤ በፉከራቸውም ብዛት የሰውን ጆሮ አደነቆሩ። የሰውን ስም አጠፉት፤ በሰው ትከሻና በሰው ሀብትም ጋለቡ፤ ሲናገሩም እውነተኞች መሰሉ፤ ምስጢርን ሰብሰቡት፤ ይሁዳ በከሐድነቱ ጌታውን እንደሸጠም ሆኑ።” ገጽ 91

“ከ፲፱፻፳፭ ዓ.ም. እስከ ፲፱፻፳፮ ድረስ ከጣሊያን ለጋሲዮን ቆንሱሎች፣ ከኤርትራ ሀገረ ገዥና ከመቃድሾም ሀገረ ገዥ እየከዱ በየጊዜው ወደ ኢትዮጵያ የገቡት ሰዎች፣ ከጣሊያን ፊት ለመሰወር ስንደክም፣ ስንከራከርም ያዩን ሰዎች ኢትዮጵያ ለኛ ለኤርትራዊያን የግላችን የሚመስላቸው ሰዎች ነበሩ። ይህም ለመሆን የተቻለበት ሌላ አልነበረም፤ ሕዝብ ከሕዝብ፣ ወገን ከወገኑ፣ በቋንቋና በወንዝ እየለያዩ የተጠቀሙት ኢጣሊያኖችና ጓደኞቻቸው የኢትዮጵያን አንድነት ለመደምሰስ በሚያደርጕት ሐሰተኛው የማታለል ስብከታቸው ያመኑ ሰዎች ናቸው። ያስገቡዋቸው ኣንጂ፣ ጣሊያኖች እስከ ዛሬ ድረስ አዋቂዉ አጼ ዮሐንስና ደፋሩ ራስ አሉላ በህይወታቸው እንዳሉ አድርገው በሽብር ሲባንኑ ይታዩ ነበር።” ገጽ 92

“እነዚ የራሳቸው የግል ጥቅማቸውን ፈላጊዎች የሆኑትም፣ ለኢትዮጵያ መንግሥት እድገትና ስፋት ማሰባቸው ትተው፣ በጠላት ፕላን ተመርተው በ፲፱፻፳፮ ዓ.ም. በህዳር ወር የኢትዮጵያ ራሶች እንዲዛወሩ አድርገው፣ ለሹም ሺር መክረው የወሰኑትን ውሳኔ ራስ እምሩና እኔ ከጐጃም ወደ ጎንደር፣ ራስ ሥዩም ዳር ሀገር፣ ራስ ካሣ ከጎንደር ወደ ጐጃም፣ ፊታውራሪ ብሩ ወደ ትግሬ ሹምሽር እንዲደረግ ብለው መክረው የወሰኑ ሰዎች ተሳስተዋል። ዛሬ በያለንበት ለወረራ ለመጣብን ጥንታዊ ጠላታችን ጣሊያንን ተሠልፈንና ጦራችንን አደርጅተን መዝመትን ነው እንጂ ሹም ሺር ማድረግ ፈጽሞ የማይገባ ነው ብለው ራስ ኣምሩ ኃይለሥላሴ ባያሰርዙት ኑሮ፤ የኢትዮጵያ ራሶች በሹም ሺር ሲዘዋወሩ የጠላታችን ጦር በመካከሉ ሰተት ብሎ ገብቶ ጥይት ሳይተኩስ ለመግባቱ ያሰቡለት ረዳቶቹ የኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት ወዳጆችና ኅሳቢዎች መስለው ያልሆነውን ምክር የሚመክሩት ሰዎች ስለነበሩት ሥራው ሁሉ ምንም ሊቃና አልተቻለም።” ገጽ 92

“የኢትዮጵያ ጥንታዊ ብርቱ፣ ደፋርና ጀግናው ባለ ታሪክ ሕዝብ በዚህ ጊዜ በነበሩ ባለ ሥልጣኖች ስሕተተኛው ጕድለትና በጠላታቸውም ንዋይ በመታወራቸው ምክንያት ጨዋው የኢትዮጵያ ወጣትና አዋቂ፣ ጀግኖችና ሊቃውንት ሁሉ በእነዚህ የጣሊያን ረዳቶችና ደላሎች በሆኑ ሰዎች ላይ በብዙ ዓዘን አዘንን። ሰሚም አጣን፤ ሐሰተኞች እውነተኞች ፣ እውነተኖች እንደ ሐሰተኖች ተቆጠሩ፤ በየጊዜው ከደረጃ ወደ በለጠው ደረጃና ክብር በቅጽበት ሲተላለፉ የነበሩትም መኰንኖች ሀገራቸውን ለመክዳት እረፍትና ኣንቅልፍ አጡ።” ገጽ 92

“ኢትዮጵያም ለ፫ይ መከፈልዋ ቀርቶ ለፋሺስታዊ ጣሊያን ብቻ ሆነች። ስለምን በስውር የጀርመናዊ ሂትለር ጓደኞች ስለሆነች በጣሊያን ስም ብቻ ኢትዮጵያ ተወራ እንድትያዝ ውስጣዊ ፖለቲካዊ ውሳኔ ተወሰነባት። በዤኔብ ጉባኤ ግን ለይምሰለው “የኢትዮጵያ ጥንታዊ ንጕሠ ነገሥት መንግሥት በጣሊያን መንግሥት ሊወረር ዓይገባዉም” ተባለ። ሲወረር ግን “በጣሊያን ለተወረረው ኢትዮጵያ ብለን ወደ እሳታዊ ጦርነት አንገባም” ብለው አመካኙ። የእስያ ሀገሮች ግን ስለ ኢትዮጵያ በጣሊያን ቦምብና የጢስ መርዝ በጭካኔ መደብደብና መወረር በብዙ ኅዘን አዘኑ። ራሩ፥፡ ስለ ኢትዮጵያም በብዙ ተጨነቁ።” ገጽ 93

አዋቂው ራስ እምሩ ኃይለ ሥላሴ አባይነህም አያታቸው ቀኛዝማች አባይነህና አጐታቸው ቀኛዝማች ታደሰ አባይነህ በታሪካዊ ጀግናነት የሞቱበትን የዓድዋን መድኃኔ ዓለም ለማየት በደስታ ተነሱ። ከመነሳታቸውም በፌት የጐጃምን ሕዝብ በመስከረም ወር ለምክር ሰበሰቡት፤ ገልጸውም “ለምለምዋ ኢትዮጵያ ሀገራችንን በአጭበርባሪነት ለመንጠቃችን ጥንታዊ ጠላታችን ጣሊያን ፵ ዓመት ተሰናድቶ ለጦርነት መጥቶብናልና ለሀገራችንና ለክብራችን ብለን ትግሬ ዘምተን ጦርነት እንዋጋለንና በወንድነትና በድፍረት በርትተን እንነሳ” ሲሉ አማከሩት። የጐጃምም ሕዝብ በብዙ ነገር ደስ ባይለውም በራስ እምሩ አንድነት መውደድና ፍቅር ብሎ ከሽማግሎቹ እስከ ሕፃናት የጭብጦ ስንቅ ሰንቆ በመዝመቱ በብዙ አስደነቀ፤ በዚሁም ጊዜ ራስ እምሩ “ዘመቻ ዘምተህ ከምትሠራው ሥራ ቀርተህ የምትሠራው ሥራና የምትሰጠው ምክር ይበልጣልና ከዘመቻ ቀሪ አድርገንሀል” ስላሉኝ በብዙ አዘንሁ፤ ፈጽሜ ዘመቻ ከመዝመት ለመቅረት አለመቻሌን ገልጨ ስነግራቸው ፈቀዱልኝና ተሰናድቼ ተነሳሁ።” ገጽ 93

“ክቡር ራስ እምሩ ኃይለ ሥላሴም በጥቅምት ፭ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ከደብረ ማርቆስ ወደ ትግሬ ዘመቻ መዝመታቸውን አዋጅ አወጁ። ታዛዥና ታማኝ የሆነውም የኢትዮጵያ ሕዝብ በደስታ በገዛ ብረቱ፣ በገዛ ስንቁም ሰንቆ፣ ስንቅና ከብት የሌለው ጭብጦ ብቻ ስንቅ ሰንቆ፣ እግዚአብሄርን አምኖ በመዝመቱ ደፋርና ጀግና ሕዝብ አሰኘው። የጥንት የጐጃም ከተማ ደምበጫም ስንደርስ የባሮነ ሙዝን ሽጕጥ በዶክቶር ሎረንሶ መብራህቱ ታእዛዝ በኩል ገብቶ ሽጕጡን ለግርማዊነታቸው ያስረከበ አቶ ከበደ ቸኮል ከጃንሆይ ወደ ራስ እምሩ የተላከው ደረሰብንና ባልደረባነቱን ለኔ ሰጡኝ። የቀረውም የሙዝ እፍረተኛው ታሪክ ሁሉ ከሥሩ ነገረን፤ ራስም ከዘመቻ እንዲቀር አድርገው መለሱትና ዘመቻችንን ቀጠልን፤ በቡሬና በገነትዋ የአንጃባራ አበቤ ዳንግላን አድርገን ደንገል በር ስንደርስ እኔና አቶ ዮሐንስ ዓብዱ ፊታውራሪዎች ሆነን በጎንደር አርማጭሆን አቋርጠን ወልቃይት ወደ ደጃዝማች አያለው ብሩ ታዘን ተልከን ሔድን።” ገጽ 94

“ጎንደር ስንደርስ በጎንደር ከንቲባ በኩል በደብረ ታቦር ሥልክ አዲስ አበባ ለጃንሆይ ስለ የኛ ወደ ወልቃይት መሔድና ስለ ራስ እምሩ መድረስ አሥታወቅንና በቅጽበትም ገስግሰን ጸገዴ ሐፋፍ ስንደርስ በቅሎዬ ደነበረና ቁልቁል ወደ ገደል ወርውሮ ስለጣለኝ የግራ ጐኔ ሁለት አጥንቴ ተሰበሩ። የሽጕጤ ማደርያ ተበሳ። እኔም ለመነሳት ስላልቻልኩ ሽጕጤን ስተኩስ በፊትና በኋላም ያሉት ሰዎች ደርሰው ከወደቅሁበት አደገኛና መጥፎ አወዳደቅ አንስተው ሠፈር አደረሱን። በማግስቱም እኔና አቶ ዮሐንስ ወደ ደጃዝማች አያሌው ብሩ ዘንድ በደጋፊ ሕጄ ስንገናኛቸው ደጃዝማች አያሌው ብሩ ደነገጡ፤ የደነገጡበትም በኔ ጐን መሰባበር ብቻ አልነበረምና ወዲያው ሐኪም ሠፈሬ እየተመላለሰ እንዲያክመኝ አዘዙልኝ፤ ፍሪዳና መስተንግዶም ላኩልን። የወደቅሁትም ህዳር ፯ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ስለሆነ በጸገዴ ሥልክ ቤት እንድታመም ከክቡር ራስ እምሩ ትእዛዝ መጣ፤ ቢመጣም ከዘመቻ ለመቅረት ሕልናዬ ምንም እረፍት ሊሰጠኝ ስላልቻለ በብዙ ታወክሁ፤ ሞት መሞቴ ላይቀር በጦር ሜዳ ደርሼ መሞቴን ተመኘሁ።” ገጽ 94

“የጠላትም ፴፪ አረዮፕላኖች በህዳር ወር በራስ እምሩ ሠፈር ዳባት የቦምብ በሮዶ ስላፈሰሱበት ደጃዝማች ገሰሰ በለውና የሞጣው ፊታውራሪ ታምራት በየበኩላቸው እየከዱ ተመለሱ ማለትን ሰማን፤ በብዙም ኅዘን አዘንን። ራስ ኣምሩም እግዚአብሄርን አማኝ ስለሆኑ “ሀገሬን እረዳለሁ የሚል ሰው ይዝመት፤ ፍቃድ የሌለው ሰው አስገድዶ ማዘመት ጉዳትን ያስከትላል እንጂ ጥቅም ኣይሰጥምና ሰው ከዳን ብላችሁ ማስገደድና ማሠር መታኮስም የለባችሁም ብለው “ ከለከሉ። እኔም ከጸገዴ በጠልእሎ ማርያም በህዳር ፳፭ ቀን ተንስቼ በ፴ ጠለምት ደጃዝማች አያሌው ሠፈር ስደርስ በበለጠ ደነገጡ፤ ወድቀዋል ብለው የተዉኝን ተነስቼ ስደርስባቸው በብዙ ጠየቁኝ።” ገጽ 94

“ “ዛሬ እነ ክቡር ራስ አሉላ በነበሩ ጣሊያን በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት ለማንሳት ባላሰበ ነበር” ስላቸው፤ “እኛን ራስ ቢሉን የበለጠ አድርገን በሠራን ነበር” አሉኝ። “የራስ አሉላን ሩብ ሥራ ቢሠሩም መልካም ነበር፤ ዳሩ ግን አይችሉም” ስላቸው በብዙ ተናደዱ። “የሁለት ራስ ሀገር እየገዙም ዓነሰኝ ማለት ዓይገባዎትም፤” ስላቸው ደጃዝማች አያሌው ብሩም እንዲህ ብለው አሉን። “ራስ ተብለው የበጌምድርን ጠቅላይ ገዢነት ማዕረግ ተሰጥተዎታል ተብዬ የግርማዊ ንጕሠ ነገሥት ኃይለ ሥላሴን ጫማ ከሳምሁ በኋላ ራስ መባሌ ቀርቶ ሀገሩንም ለራስ ካሣ ኃይሉ ስለተሰጠብኝ፣ አጐቴ ራስ ጕግሣ ወሌን ገድዬ መንግሥትን ብረዳ ራስነቱና ሀገርነቱንም ሳላገኝ ከንቱ ሁኜ ቀረሁ። እንደኔስ ለመንግሥት ያገለገለና የተሞኘ የተጐዳስ ማን አለ?” እያሉ እንደ አንድ ዕብድ ሂነው ምስጢራቸውን ገልጸው ነገሩኝ።” ገጽ 95

“እኔም ወሰን የሌለው ኅዘን ማዘናቸውን በመመልከት ከድንኳናቸው ወጥቼ ወደ የጠላትም ማይ አንበሳ ስሔድ የሺሬ ባላባትና ገዥ የሆኑትን ደጃዝማች ገብረ መድኅንን አገኘሁና ሰላምታ ከሰጠሁዋቸው በኋላ “ትግሮችም ከጦርነት ይሻሻሉ ወይ ስላቸው” በብዙ ሳቁ። ስለ የጦርነቱም እቅድና ሁናቴም በለማልሞ በኩል ለሚመጡ ራስ እምሩ እንዲጽፉ ምክር ረጠብሁዋቸው። እኔም ማይ አንበሳ ላይ ጋይንትየው ፊታውራሪ ሺፈራው ሠፈር ሠፍረው አገኘሁዋቸውና አብሬ ሠፈርሁ በህዳር ፴ ቀ። ደጃዝማች ገብረ መድኅን ባይርዑ ማለትም በመጀመሪያ ሐመዶ ላይ ጣሊያን መረብ ተሻግሮ ሲመጣ ወግተው ብዙ ገድለው መሳሪያ የማረኩ ጀግና የጀግናው ራስ ባይርዑ ቱርክን በጕራዕ ያረዱ ልጅ ናቸው።” ገጽ 95

“ታህሣሥ ፩ ቀን የጋይንት ደፋር ፊታውራሪ ሺፈራው ከሠፈርንበት ማይ አንበሳ ተነስተው በታህሣሥ ፭ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. በዳባ ጕና ጣሊያንን በወንድነት ድል መተው ከፈጁት በኋላ ማታ በአረዮጵላን መትረየስ በጀግናነት ሞቱ። ሀገራቸውን አስከበሩ። በዚህ በላይ ለተነገሩት ምስክርነት፤ ከራስ እምሩ ለኔ ተጽፈው በጸገዴና በጸለምት የደረሱኝ ሁለት ደብዳቤዎች ከዚህ በታ እጽፋቸዋለሁ።” ገጽ 95

“ራስ እምሩ - ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል - ለጤናህ እንደምን ሰንብተሃል፤ እግዚአብሔር ይመስገን እኛ ደህና ነን፤ ወድቀህ ጐንህን አሞሃል ማለትን ሰምተን አስበናል፤ አሁንሳ በጣም አልተሻለህም ወይ። እኛም ወደዚያው መቃረባችን ነውና ስለእህል ነገር በጣም የሚያሳስበን ስለሆነ በርትታችሁ እንድታስቡበት ይሁን። ህዳር ፲፪ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ፌርማ፣ እምሩ ኃይለ ሥላሴ” ገጽ 96

“ራስ እምሩ- ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል - ለጤናህ እንደምን ሰንብተሃል፤ እግዚአብሄር ይመስገን እኛ ደህና ነን በ ፯ ታህሣሥ የጻፍከው ደብዳቤ ደርሰኝ። ሕመምህንስ በጣም አልተሻለህም ወይ? እኛም ሰው እስኪሰበሰብልን አንድ ነገን ብቻ እንውላለን እንጂ ወደዚያው በፍጥነት መምጣታችን ነው፤ አንተም እዚያው እንድትቆየን። ታህሣሥ ፯ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ቦያ ፊርማ፣ እምሩ ኃይለ ሥላሴ” ገጽ 96

በቀጣይ ክፍል በምዕራፍ 21 ስለ የራስ እምሩ በሺሬ በጀግንነት ጦርነት መዋጋት በሚል ርእስ ከቀረበው ታሪኽ እንየዀመኾምን፤ በእንዳባጉናዉ ጦርነት የጣሊያን ኪሳራ ዝርዝርን እንዲሁም ጣሊያን በራስ እምሩ ሰራዊት ተከዜ ላይ በአውሮፕላን የጣለዉን በዓለም መንግሥታት ሕግ የተከለከለዉን “የጢስ መርዝ ጋዝ የብረት ጋን” ማስረጃ ይሆን ዘንድ ከተጣልበት ከተከዜ ዳባት ከዳባትም አዲስ አበባ አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ እንዴት እንደላኩት እንኰመኩማለን። አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእም ልብ ለልብ ከሚናበቧቸው ከራስ እምሩ ጋር የተጻጻፏዋቸውን መልእክቶችም አለፍ አለፍ ብለን እናያቸዋለን፣ የወቅቱን ወታደራዊ ሁኔታም ለመረዳት ያስችሉናል።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 19 Jul 2019, 01:30
by Meleket
አርበኛዉ ተስፋሚካኤል ትኩእ ለዛሬ ስለ የእንዳባጉናዉ ጦርነት፣ ጣሊያን በዚህ ጦርነት ስለተከናነበችው ኪሳራ በከፊል፣ ስለ በተመድ የተከለከለው የመርዝ ጋዙ የብረት ጋን በተከዜ፣ ስለ የራስ እምሩ ቀጭን ትእዛዝ፣ ለራስ እምሩ ስለጻፉላቸው ዘለግ ያለ የምክር ደብዳቤ ወዘተ ይተርኩልናል። በምክሩ በሽሬው የጦርነት ቀጠና የሽቦ አልቦ የንፋስ ሥልክ ቴሌፎን አስፈላጊነት፣ የደጀን ሰራዊት አስፈላጊነት፣ በጦርነቱ ወደፊት ብቻ መጋለብ መዘዝ እንዳያስከትል ወዘተ ምክር ቢጤ የቸሩበት ደብዳቤያቸውን አርበኛው በዛሬው ትረካቸው አካተውልናል። መልካም ንባብ።

“ስለ የራስ እምሩ በሺሬ በጀግንነት ጦርነት መዋጋት በኢትዮጵያ ታሪክ በሚል ፬ኛው መጻፌ ስለተጻፈ መድገም አያስፈልግም። ስለዚሁም የሺሬ የሚያሰቅቅ የጀግንነት፣ የድፍረት ሥራ መሠራቱን የሚያመለክቱ በየቀኑ የጻፍሁዋቸውን ደብዳቤዎች ውስጥ ረቂቆች በአርበኝነቱ ጊዜ ቢጠፉም ለማስረጃ የሚሆኑ ከክቡር ራስ እምሩ የተጻፉልኝ ደብዳቤዎችና ለኢትዮጵያም የንጕሠ ነገሥት አጼ ኃይለ ሥላሴ ላሳለፍሁዋቸው ቴሌግራሞች የተሰጠኝ መልስ ቀትሎ የተጻፉት ናቸው። “ ገጽ 97

“ለክቡር ራስ እምሩ - የተከዘን ወንዝ በግስገሳ ካልታለፈ በቀን አረዮፕላን አለማሳለፉን ቦታውም እጅግ ጠባብ መሆኑን ከተከዘ ሓፋፍ ከማይ ዓይኒ ወደ ኋላ ማይተክሊት ተመልሸ አስረድቻቸው ራስም የጠበቀ ትእዛዝ ለፊታውራሪ ክንፌ ሰጥተው ተመልሼ ከተከዘ ታህሣሥ ፲፪ ቀን በዳባ ጕና የወደቀው የጠላት ሬሣና ምርኮኞች ፲፱ ታንኮች እየዞርኩ ስቆጥር፣ በዓለም መንግሥታት ሕግ የተከለከለዉን የጢስ ጋዝ መርዝ በታህሣሥ ፲፪ እና ፲፫ ቀን በራስ እምሩ ሠራዊት ላይ በተከዜ ጥሎ ፲፭ ሰዎች ስለሞቱና ብዙዎቹም ስለቆሰሉ የኢትዮጵያ መንግሥት አቤቱታውን ቢያቀርብ ከእውነት የራቀ የጣሊያን ፋሺስታዊ መንግሥት በአረማዊነቱ የሠራዉን ሥራ ፈጽሞ ስለካደ የጢስ መርዝ ጋዝ የጣለበትን የብረት ጋን ከተከዘ በክራይ አጋሰስ አስጭኜ ዳባት እንዳደርስና ከዳባትም በአረዮፕላን አዲስ አበባ እንድልክ፣ ለዚሁ ሥራ ከራስ ኣምሩ ተመርጨ ስለታዘዝሁ ከሺሬ የጦር ግንባር ተከዜ ተመልሴ “የጢስ መርዝ የብረት ጋን” ሊየው ለሚባለው ነጋዴ አስጭኜ ስገሰግሥ ፫ ቀን በማይ ዓይኒና በጓልድባ በለማልሞም ነጣቂዎች ተሠልፈው ቢጣሉንም እግዚአብሔር አወጣኝና ጥር ፮ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ዳባት ገብቼ በብዙ ቺኮላ የተፈለገውን ዕቃ በአረዩፕላን ለማሳፈር ቻልሁ።” ገጽ 97

“ራስ እምሩ - ቁጥር ፵፫ ይድረስ በየበሩ ካላችሁ ሹማምንቶች። አቶ ተስፋ ሚካኤልና አቶ ይትባርክ ተግኘ ለሥራ ወደ ዳባት ልከናቸው ይሄዳሉና ጓዛቸውን እንደያዙ ሲያልፉ እንዳይከለከሉ ይሁን። ሼሬ ታህሣሥ ፲፰ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ፊርማ፡ እምሩ ኃይለ ሥላሴ። “ ገጽ 98

“ራስ እምሩ - ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል እንደምን ሰንብተሃል! እግዚአብሔር ይመስገን እኛ ደህና ነን፤ ከመንገድስ በደህና ዘለቃችሁ ወይ። ዳባጕና በሆነው ጦርነት ከዘረፋው የተገኘ የኢጣሊያኖች የቁጥር መጽሐፍ ወደ ግርማዊ ጃንሆይ እንዲላክ አንተ ድረስ ሰደነዋልና በፍጥነት ዳባት አድርሰኸው በሚመጣው አውሮፕላን እንዲላክ አድርግ። ለሥራ የሚረዳ ሳይሆን አይቀርምና በቶሎ እንዲደርስ አድርገው ። አደራህን። ስለዚህ ነገር ወደ ጃንሆይ በቁጥር የሚተላለፈዉንም ቃል ከዚህ ጋር ልከንልሃልና በቶሎ እንዲያልፍ አድርግ። ጥር፫ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ሺሬ።” ገጽ 98

“ራስ እምሩ - ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል - እንደምን ሰንብተሃል፤ እግዚአብሄር ይመስገን እኛ ደህና ነን፤ ይኸው ወደ ግርማዊ ጃንሆይና ለውጭ ጕዳይ ሚኒስትር የሚላክ ሁለት አምቮሎፕ ልከንልሃልና አውሮፕላን እንደመጣ እንድትሰደው። ዳግም አንተ ዘንድ ተቀማጭ እንዲሆን አንድ ቲኒሽ ሳጥን እንደተቆለፈ የጽሕፈት መሳሪያ ልከንልሃልና ተቀብለህ መድረሱን እንድትጽፍልን፤ ካዲስ አበባም የሚመጣልንን ቃል ሁሉ በፍጥነት እንዲደርሰን እያደረግህ እንድትልክ ይሁን። ለግርማዊ ጃንሆይ የሚያልፈውም የቁጥር ቃል ከዚህ ጋር ልከናል፤ በፍጥነት ይለፍ ጥር ፲፫ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ፊርማ፣ እምሩ ኃይለ ሥላሴ።” ገጽ 98

“ይድረስ ለክቡር ጌታዬ ራስ እምሩ። ዛሬ ጥር ፲፫ ቀን ቃል ለቃል ከቀኛዝማች ተክለ ማርቆስ ጋር ተገናኘተን ሥልክና ፖስታ እጅግ አድርጎ ስለራቀን ቸግሮናልና ሥልኩ እስከ ድበባህር ድረስ በፍጥነት እንዲዘረጋ፣ ለፖስታም ሥራ ሠራተኞች ልከው በቀጥታ ሥራው እንዲሠራ እንዲያደርጕት ብዬ አስታውቂያቸው መልካም ነው እናስብበታለን። ለክቡር ራስ እምሩ እጅ ንሣልኝ፤ ደብዳቤአቸውም ተቀብያለሁ ብለው መልስ ሰጡኝ።” ገጽ 98

“ ፪ኛ የመንገድ ያለሺቦ የንፋስ ሥልክና ሠራተኛው ለክቡር ራስ እምሩ በፍጥነት ቢላክላቸው እጅግ ከፍ ያለ የመንግሥት ጥቅምና ብርታት ይሠሩበታልና በቶሎ እንዲላክላቸው እለምነዎታለሁ ብዬ ብጠይቃቸው ደግ ነው አሁን ከኤውሮጳ በዚህ ሰሙን አዲስ አበባ የሚደርስ አለንና እንደደረሰን እልክላቸዋለሁ። የብርታቸውም ነገር እጅግ ደስ ብሎኛል ብለው መልስ ሰጥተውኛልና ጌታዬም በርትተው በየቀኑ ቢጠይቁ ራዲዮና ሠራተኛ ሣይመጣለዎት ዓይቀርም ነበር።” ገጽ 99

“፫ኛ ስለ ደጀን የሚሆን ጦር ወደ ጌታዬ የታዘዘ እንዳለ በስውር ብጠይቅና ባስጠይቅ የተነሣ ሰው የለም ብለውኛልና ከመቀሌ ጦር ወደ ጌታዬ እንዲዛወርለዎ ከጃንሆይ በቶሎ እንዲያስፈቅዱ፣ ካለዚያ የኅሳብዎን ለመሥራት እንቅፋት ይሆንቦዎታል። የመቀለም ጦር ዝም ማለቱ ሰውና ከብቱ በከንቱ በረሐብና በበሺታ እስክደናገጥ ድረስ ነው እንጂ ጃንሆይ እስክመጢልን ድረስ ለጠላት አትንኩት ብለው እነ ራስ ካሣና ራስ ሙሉጌታ ዝም ብለው የጦር ድግሥ አያቆይዋቸውም ነበር።” ገጽ 99

“፬ኛ ክቡር ሆይ ዓይዳቦና (ዓዲያቦና) መረብ ሠራዊትዎ መውረዱንና አኵሱም በርትቶ መጠጋቱን፣ ሐማሴኖች ጠላትን ከድተው ወደ ጌታዬ መግባታቸውን፣ አረዩፕላን በየቀኑ መሰበሩን፣ በሺሬ መንገድ ጣሊያን ወገቡ መያዙንና በብዙ መጨነቁን፣ የተማመነው ታንክ ከቁጥር መውጣቱን ለይተው ለጃንሆይ ያመልክቱዋቸውና ጦር በፍጥነት እንዲመጣልዎ ያድርጕ። ካላደረጕ ለወደፊቱ በየቀኑ ወደፊት መግፋትዎ በዝቷል። እንደሐሳብዎ ብዙ ጦር ከመጣለዎ ግን አሥመራም ቢሆን ባዶናት ይባላል። ለሁሉም ነገር ከጌታዬ የተሰወረ ነገር የለም፤ እግዚአብሄር ብርታቱን ይስጥዎት።” ገጽ 99

“፭ኛ ኢጣሊያኖች የመሸነፋችውን ልክ ካገኙትና ከተረዱት በኋላ ለኤርትራ ጦር ሠራዊታቸው አለቃ የሙሶሊኒ ዋና ጠላትና ተካራካሪ ባላጋራው የሆነው ማረሻሎ ባዶ ሊዮ መሾማቸውን እጅግ ያስደንቃል። ያስደስታልም። ጥር ፲፫ ቀን ፲፱፻፳፰ዓ.ም. ዳባት። ፊርማ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።” ” ገጽ 99

በቀጣዩ ክፍል “ስለ ሀገር ነፃነት በደንብ መሥራትና መሞት የተገባ ከመሆኑ በላይ ጽድቅና ርትዕም ነው” በሚል ርእስ ታሪካቸውን ያስኮመኩሙናል አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:lol:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 25 Jul 2019, 10:07
by Meleket
ኣርበኛው ዛሬ የቆረጣ የውጊያ ስልትን ለኃይለስላሴ ሲመክሩ፣ ንጉሠ ነገሥቱንም ኣገልጋይዎ ባርያዎ እያሉ በጊዜው የኣነጋገር ዘይቤ ትህትናቸውን ይገልጻል። የጣሊያንን ጭንቀት ምክንያት፣ በኣዅሱም ስለነበሩት ፳ የጣሊያን ኣውሮፕላኖችና የኃይለሥላሴ ደብተሮች ምን ኣደረጉ ተብሎ እንደተወራም ይገልጻሉ! :mrgreen: :lol: :mrgreen:

“ለግርማዊ ጃንሆይ - ለመንግሥታችን ጕዳት ሆኖ የታየኝን ለማመልከትዎ ኅሊናዬ ስለአስገደደኝ ሰውና ከብቱ በረሐብና በበሺታ ሳይደናገጥ መቀለ ፫፻ ሺህ ያህል ያለው ሠራዊታችን እስከ ዛሬ ድረስ ተሠልፎ ባለምግጠሙና መቀለን ባለማስለቀቁ ብርቱ ስንፍና የሚያመጣብን ሆኗል። ክቡር ራስ እምሩም ኅሳባቸው ሁሉ እንዳይፈጽሙ እንቅፋት ሆኖባቸዋል፤ አሁንም ምንስ ጐጃም ቢከዳቸውና ደጄን የሚሆን ሠራዊት ባይታዘዝላቸው ነው እንጂ ሌላ ቀርቶ ኣዅሱምንና ዓድዋን እለቱን እጅ ለማድረግ በጣም የተዘጋጁ ነበሩ፤ ጊዜውም እጅግ መልካም ነው። ይህም ሁሉ ሆኖ ራስ እምሩ ሠራዊታቸውን በዓይዳቦ(ዓድያቦ) መረብን ተቻግሮ የጣሊያንን ግዛት ትኩል እንዲመታ አፋጥነው ልከዋል። የሐማሴንም ሰው እየከዳ መግባት ጀምሮላቸዋል። የሁሉም ማሰሪያ በፍጥነት ረዳት የሚሆናቸው ጦር ታዞላቸው፣ መገናኛም ለሥልኩና ለፖስታ ብልሐት እንዲደረግበት መሬት ወድቄ ለግርማዊነትዎ አመለክታለሁ። ጥር ፲ቀን ፲፱፻፰ዓ.ም. ዳባት በሥልከኛው ባቶ በዛብህ የተላለፈ የሥልክ ቃል። ፊርማ፣ ባርያዎ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ ”ገጽ 100

“ለግርማዊ ጃንሆይ - ትንሹ ኅሳቤን እንድገልጽለዎ እንዲፈቀድልኝ መሬት ወድቄ እለምናለሁ። በእግዚአብሄር ሰፊ ቸርነት፣ በንጕሠ ነገሥታችን ጸሎትና ብርታት፣ በሠራዊትዎ ድፍረት የጠላታችን አረዮጵላኖች በየጫካውና በየተራራው በየቀኑ መውደቅ በዝተዋል። በአዅሱምም ያሉት ፳ው ከመሬት አልነሣም አሉት። እሱም አጼ ኃይለ ሥላሴ ደብተሮች ልከው አረዮፕላኖቻችንን ከመሬት እንዳይነሱ አደረጕ። ጥይት የማይገድለው ተንኮለኛው ጅብ ልከው ወታደራችንን አስነክሰው ጨረሱት እያሉ ጣሊያኖች ያለቅሳሉ ይባላል። ይህም የእመቤታችን የማርያም ጽዮን ሥራ ነው የሰው ሥራ መሠላቸው እንጂ። በሰዎች ዘንድ ታንክም ፈጽሞ ተንቆዋል።” ገጽ 101

“አሁንም የግርማዊነትዎ ፈቅድ ሆኖ በሺሬና በኣይዳቦ (ዓድያቦ) በኩል ጣሊያንን በጐኑ እርድ በሌለበት ገብተን ወገቡን ለመቁረጥ ብዙ ጦር በፍጥነት መላክ ማስፈለጕን ለግርማዊነትዎ አሳስባለሁ። እኔም ከሺሬ ለሥራ ዳባት መጥቻለሁ። ጥር ፲፬ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም ። ፊርማ፣ ባርያዎ ተስፋ ሚካኣኤል ትኩእ። ”ገጽ101

“ለግርማዊ ጃንሆይ- ግርማዊ ጃንሆይ ጦርነቱ ይቆይ ብሏል እያሉ የሚሰብኩ ፈሪዎች የሆኑት ሰዎች ጀግኖቹን እያሳነፉ በመሔዳቸውና በመስበካቸው እጅግ ያሳዝናል። ለንጕሥም ፈጽሞ የጦርነት ድግሥ ማቆየት አያስፈልግም ነበር። አሁንም ሣሩ ሣያልቅ፣ ምንጩ ሣይደርቅ ሰውም በሐዲስ ጕልበት እንደ እውቀቱ አድርጎ እንዲዋጋው ማድረግ መልካም ነበር፤ ጣሊያንም በኛው ብርቱ ጦርነት፣ በሀገሩ ሕውከት በዓለም ነገሥታት ቁጣና ብድር መከልከል ምክንያት መጨነቁን ዓይጠረጠርም። ጥር ፲፬ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ዳባት። ፊርማ፣ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።”ገጽ 101

“ይድረስ ለክቡር ጌታዬ ራስ እምሩ ኃይለ ሥላሴ እንደምን ሰንብተዋል፤ ለጤናዬ እግዚአብሄር ይመስገን ደህና ነኝ፤ ከዚህ ቀደም እንደጻፍሁለዎት የአገው ምድር ቀኛዝማች በላይ ዘለቀና ቀኛዝማች ረታ፣ ቀኛዝማች መድፉ ከነተከታዎቻቸው ጋር ሆነው መዘጋ ለመዘጋ ኣቋርጠው ከጌታዬ ከድተው አርማ ጭሆ ማዝኞ ከሚባለው ቦታ በባላገር ተከበው ሰንብተው ፶ ሰው ሞተባቸው፣ ፲፭ቱ ተማረኩ፤ ቀኛዝማች መድፉም ቆሰለ ብለው የጎንደር ሥልከኛ አረጋግጠዉልኛልና ለወደፊቱ ቢሆን መጠንቀቅ ነው። . . .”ገጽ 104

“ቁጥር ፭ - ራስ እምሩ - ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል . . . በዚያለ በኩል የምትሰማውን አንዳንድ ነገር ለምን አትጽፍልንም? ተምቤን ራስ ካሣና ራስ ሥዩም ከኣኢጣሊያኖች ተዋግተው ድል አደረጕ ማለትን ፊታውራሪ መርሶ ላባቱ ጽፎ ሰማነው፤ የዚህን አንተስ የማሰኸውን ለምን ሳትጽፍልን ቀረህ? አሁን እንድትጽፍልን። ዳግም ጠላቶቻችን ሕዝቡን በሀሰት ወሬ ለመስበር ለየሀገሩ ወረቀት ስለሚበትኑ በዚህ ሰሞን ከበተኑት ተገኝቶ ዛሬ የመጣልንን ከዚህ ጋር ልከንልሃልና ወደ ግርማዊ ጃንሆይ በቶሎ እንድትሰደው ይሁን። የነ ወይዘሮ ጽጌ ማርያምንም ድህንነት ኣንደዚሁ በየጊዜው ኣየጠየቅህ እንድትልክብን። ለጃንሆይም የሚያልፍ ቃል ልከንልሃልና እንዲያልፍ። በዚያም በኩል የምትሰማውን ጻፍልን፤ ጤናዉን ይስጥህ። ጥር ፳፱ ቀን ፲፱፳፰ዓ.ም. ሺሬ። ፊርማ እምሩ ኃይለ ሥላሴ” ገጽ 106

በቀጣዩ ክፍል ኣርበኛው ከራስ እምሩ ጋር የተጻጻፏቸውን ኣንዳንድ ቀጣይ ሃሳቦችንም እንቃኛለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 31 Jul 2019, 04:10
by Meleket
ለዛሬም ኣርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ ከራስ እምሩና ከጃንሆይ ጋር የተጻጻፏቸውን ደብዳቤዎች ይዘት እየቃኘን የወቅቱ የፖለቲካና ወታደራዊ ትኩሳት ምን ይመስል እንደነበረ እንመለከታለን። ሞሶሎኒም ወታደራዊ መሪዎችን ከኣሥመራ ሮማ የቀያየረብትን ምክንያት ለምን እንደነበረ በአርበኛው አገላለጥ እንቃኛለን። መልካም ንባብ።

“ይድረስ ለክቡር ጌታዬ ራስ እምሩ ኃይለ ሥላሴ፤ እንደምን ሰንብተዋል ለጤናዎ እግዚአብሄር ይመስገን ደህና ነኝ። --- -- “፪ኛ ለክቡር ጌታየ ሠራዊት ብርና ስንቅ በብዙ አስፈላጊው መሆኑን ስለተረዳሁት ጐጃም ለፊታውራሪ አላምረው ከማርቆስ የተገኘውን ገቢ ብርና የሠራዊቱንም ስንቅ በብዙ ብርታትና ጥንቃቄ በዘበኛ አድርገው በፍጥነት ጌታዬ ካሉበት ቦታ ድረስ እንዲልኩ ብዬ በክቡርነትዎ ስም አሳልፌላቸዋለሁ፤ እነሱ እስኪሰናዱ ድረስ ብዙ ቀን ያስፈልጋቸዋልና ኅሳብዎን ያስተውቁኝ። ”ገጽ 107

“፫ኛ በሺሬ ሳለሁ በወጨፎ ጠበንጃ ጥይት ተመቶ በሺሬ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ሁለጠው ቃብቲያ በነ ቀኛዝማች መንግሥቱ ፫ኛ በሠራዊቱ የጥይት በረዶ ተመቶ በኃይል ሄዶ ጠላት ሠፈር አቁርደት መውደቁን በሰቲት በኩል ከወደቀው ሌላ፣ ዛሬም በአረዮፕላን መጣያ ራስ እምሩ አረዮፕላን ጣሉ ማለትን ስለሰማን ደስ ብሎናልና በጽሁፍ ብናውቀው መልካም ነበር፤ በየጫካዉም የወደቁትስ የጠላት አረዮፕላኖች ይገኛሉ ወይ?” ገጽ 107

“በዚህ ሰሞን እንግሊዝ ግዛት ቶከር ላይ የጣሊያን አረዮፕላን ወድቃ ፫ ሰዎች በውስጥዋ ተገኝተው ተይዘው ቢጠየቁ ብዙ ነገር ቀበጠሩ፤ የኢትዮጵያ ሰውና መሬት የማይቻል ብርቱ መሆኑንና በባህርም የጣሊያን መንግሥት መንገድ አጥቶ መጨነቁን ገልጸው ተናገሩ ብለው የመተማ ኢትዮጵያዊ ሥልከኛ አሳለፉልን። . . . ”ገጽ 107

“ ---፮ኛ ግርማዊ ጃንሆይ ከደሴ ወደ መቀለ ዘመቱ ይባላል፤ መሄዳቸው ግን የማይቀር ነው። የሁሉም ነገር የካቲት ፳፩ ጀምሮ እስከ ፳፬ ቀን ድረስ በብርታትና በአንድነት ጦር ሁሉ በያለበት እንዲገጥም ማሰባቸው አይቀርም ይመስለኛልና ዱሮውም ጥንቃቄ ገንዘብዎ ነው።” ገጽ 107

“---- ፯ኛ በአርማይጭሆ ሕዝብ በጭንቅ ተከበው የነበሩት ቀኛዝማች ረታና ቀኛዝማች በላይ መያዛቸውን ደጃዝማች አስፋው ወሰን ካሣ ለጃንሆይ አስታውቀው ነበር። ኣገሬው ግን ተባብሎ በመልቀቁ ብርቱ ፍለጋ ተይዞዋል ብለው የደንቀዝ ሥልከኞች አሳለፉልኝ።”ገጽ 108

“ --- ፰ኛ ከሶስት ቀን ወዲህ ብርቱ የመድፍ ተኩስ ስለሰማን በብዙ ሰግተናልና የሁሉም ነገር ይግለጹልን፤ በህይወት ጫማዎን ለመሳም ያብቃኝ፤ ታማኝዎ። የካቲት ፫ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ዳባት/ ፌርማ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።” ገጽ 108

“በደሴ ከተማ ዙሪያ ባለው ጫካና ገደል ተሸሸው ፬ት የምንገድ ራዲዮ ማርኮኒ ተክለው ፲፰ ሰዎች የጣሊያን ሰላዎች ተያዙ። በኢትዮጵያ ውስጥ ከእነዚህ የበለጡ ሰዎች እስከ ፫፻ መኖራቸውን ስለተሰማ ባጠገብዎ ያለው ዱርና ገደል በብዙ ጥንቃቄ እንዲያስመረምሩት አጥብቄ እለምነዎታለሁ። የማሸነፍ እድልና ረጅም እድሜ እግዚአብሄር ይስጠዎት። የካቲት ፲ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ዳባት። ፌርማ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።” ገጽ 109

“ይድረስ ለክቡር ጌታዬ ራስ እምሩ --- --ጕረኛው የጣሊያን ወታደር ሞቱ የተባሉት ራስ ኣምሩ መጡብን፣ ሠራዊታቸውም ጨካኝ ነው ብሎ በሰቲት በኩል ከነበሩት ወታደሮች ውስጥ ሸሽተው ወደ እንግሊዝ ግዛት ሱዳን ፣ እንደዚሁም በበረና ሞያለም ወደ እንግሊዝ ግዛት በሽሽት መግባታቸውን በመተማ ሥልከኛ ተነገረ።” ገጽ 110

“የቀይ መስቀል ሐኪሞች የእንግሊዝና ሆላንድ የሱደንና የግብጽ፣ የዓለምም መንግሥታት ማኅበር ሹሞች ሆነው ካምዮኖቻቸውን ይዘው በድምሩ ፬ሺ ሰዎች ለርዳታና ለስለላም መጥተዋል። ደሴና ወጋዴንም ይመላለሳሉ። ለሌሎቹ ጣሊያን በአረዮፕላን ጥይት ሲተኩስባቸው፣ የእንግሊዝ ባንዴራ ባለው ድንኳንና ካሚዮን እስከ ዛሬ ተተኩሶበት አያውቅም። የመጡትም ኤውሮጶች ደሴና ወጋዴን ይመላለሳሉ፤ በሌሎቹ ሲተኮስባቸው በእንግሊዝ ድንኳንና ባንዴራ አረዮፕላንና ካሚዮን ያልተተኮሰበት ምን ይሆን?”ገጽ 110

“ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል - ቁ፵፫ - እንደምን ሰንብተሃል፤ እግዚአብሄር ይመስገን እኛ ደህና ነን። የጻፍከው ደብዳቤ ደረሰን፤ በጠላት ጦር ላይ አደጋ እንዲጣል በቀኝና በግራም በኩል አደጋ ጣዮች ልከን ነበርና፣ በግራ በኩል የሄዱት መረብ አጠገብ ራማ ከሚባለው ቦታ ባለው የጠላት ጦር አደጋ ጥለው በ ፭ የካቲት ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ፬፻፩፪ ያህል ነጭ ገድለው፣ የቻሉትን ዕቃ ማርከው፣ የተረፈውን አጥፍተው ብዙ ጉዳት ሳያገኛቸው በደህና ተመለሱ። ” ገጽ 111

በቀኝ በኩልም የሄዱት ዓድዋ ኣጠገብ ድረስ ሔደው ብዙ ሰው ገድለው፣ ያገኙትን መሣሪያም ገፈው በደህና ተመልሰዋል። ይኸንን ትሰማው ብለን ነው። እግዚአብሔር በቸርነቱ በየጊዜው እርዳታውን አላጓደለብንም። ስለ አውሮፕላኑም ብዙ ጊዜ እየተተኮሰበት ለጊዜው እንኳን እፊታችን ባይወድቅ እየራቀ በየበረሃው እየወደቀ መገኘቱን እንሰማለን። - - የካቲት ፲ ቀን ፲፱፻፳፰- ሺሬ ፌርማ፡ እምሩ ኃይለ ሥላሴ”ገጽ 111

“ይድረስ ለክቡር ጌታዬ ራስ እምሩ ኃይለ ሥላሴ - ወሎ ሣይንት ላይ አንድ ትልቅ የጣሊያን አረዮፕላን ፮ ሰዎች ፮ ምትረየስና ፮ ጠበንጃ እንደያዘ በእግዚአብሄር ኃይል ወድቆ መቃጠሉን ሰው ሁሉ እጅግ ተደነቀ፤ ፈጣሪውንም አመሰገነ የሚል ከደብረ ታቦር ሥልክ የካቲት ፱ ቀን ተሰማ። -- -- -- በዓድዋም ያለው የጠላት ጦር የተቅማጥ በሽታ ገብቶበታል በየቀኑ ያልቃል፤ ወታደሩም ተስፋ ቆርጦ በፍራት ተንቀጥቅጦዋል፤ ተከቦዋልም ይባላል።” ገጽ 111

“ጥር ፲፩ና ፲፪ ቀን በራስ ካሣና በራስ ሥዩም ዘንድ በሆነው ጦርነት ስ ካሣ ወደኋላ ፊታቸውን ስላዞሩ ጠላት ገፍቶ ሲመጣ መክተው የመለሱትና ፭፶ ምትርየስ ፮ መድፍ የማረኩ እነ ደጃዝማች አድማሱ ብሩ ናቸው ተብሎ ትላንት ዳባት ፈንጠዝያ ተደረገ፤ የምድፉም ስም አንዱ ፈጣሪ፣ አንዱ መላክ ይባላል። ክብደቱም ከልክ ያለፈ ነው፤ ራስ ካሣ ግን አልተመሰገኑም። በጦርነት ተመረዋል እንጂ፤ የዳውንት ሰውም እምቢ ከራስ ካሣ ጋር ሆነን ተሠልፈን አንዋጋም ቢል ጃንሆይ ብጅሮንድ ለጢበሉን ባልደረባ ሰጡዋቸው ይባላል። ዛሬም ቢሆን በተንቤን በኩል ተኩስ በብዙ ሲተኮስ አረፈደ።”ገጽ 111

“ይድረስ ለክቡር ጌታዬ ራስ እምሩ። - - - በዑምሐጀር ያለው የጣሊያን የጦር ሠፈር በፍራት ከተማውን ትቶ የካቲት ፲ ቀን ባጠገቡ ካለው ተራራው ላይ ብዙ ቤቶችንና ምሽጎችም አሠርቶ ከተማውን ለቆ ገብቶበት የነበረውን ባልታወቀ ምክንያት የእሳት አደጋ እግዚአብሄር ጥሎባቸው ፪ ሰዎች ሲሞቱ ብዙ ገንዘብና መሣሪያም በመቃጠሉ ኢጣሊያኖች ኅዘን አዘነዋል። ያቃጠለውም ኢትዮጵያው ሰው ነው ብለው አምተዋል። የካቲት ፲፬ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ዳባት። ተስፋሚካኤል ትኩእ” ገጽ 112

“ራስ እምሩ - ቁጥር ፩ - ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል እንደም ንሰንብተሃል”” እግዚአብሄር ይመስገን እኛ ደህና ነን። የጻክው ደብዳቤ ደረሰን፤ ተንቤን በሆነው ጦርነት በልዑል ራስ ካሣ ዋናውንም ጦርነት ያደረገ ልጃቸው ደጃች ወንድ ወሰን መሆኑን በርግጥ ሰምተናል። - - - እናም ወደነሱ እንድንጠጋ ትእዛዝ ስለተላለፈልን ወደ ተንቤን ጉዞ ጀምረናል። ወደዚያ ማለፋችንን እንድታውቀው። ወደፊት የሚመጣለንንም ፖስታ ታቹን በዛና መንገድ እንዲመጣልን ማድረግ ነው።በዚያም በኩል የምትሰማውን ሁሉ በየጊዜው እንድትጽፍንል። እግዚአብሄር በሰላም ያገናኘን። የካቲት ፲፱ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ሺሬ - ፊርማ፡ እምሩ ኃይለ ሥላሴ።”ገጽ 114

“ለግርማዊ ጃንሆይ። - ከሠቲት አንስቶ ሺሬ ድረስ ያለው የኛው የጦር ግንባር እጅግ ሰፊና ረጅም ስለሆነ ለወልቃልትና ለሺሬ ተጠባባቂ ብርቱ ጦር በፍጥነት ማዘዝ ግዴታችን መሆኑን ለግርማዊነትዎ አሳስባለሁ። የካቲት ፲፪ ቀን ፲፱፻፳፰” ገጽ 114

“ይድረስ ለክቡር ጌታየ ራስ እምሩ ኃይለሥላሴ። - - - - የካቲት ፲፫ቀን የመጣ የሥልክ ቃል ይህ ነው። “የጣሊያን ወታደር ኤርትራዊያን ፮ ሺ፯፻፶ ሰው ከወጋዴን ወደ ኢትዮጵያ ዙረው ጣሊያንን ወጉት፤ አለቆቹም በአረዮፕላን አዲስ አበባ ስለገቡ በደስተኛው ሠልፍ ውለናል የሚል ቃል” ብሰማ እንደገና አዲስ አበባን ብተይቅ እውነት ነው ብለው መልስ ስለሰጡኝ እጅግ ከፍ ያለ መልልካም ደስታ ሆኖዋል። -- -- የካቲት ፲ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ፊርማ፡ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።”ገጽ 115

“ይድረስ ለክቡር ጌታየ ራስ እምሩ ኃይለሥላሴ። - - - -በ፩ ቁጥር የካቲት ፲፱ቀን ወደ ተንቤን ጉዞ ጀምረናል የሚል ደብዳቤዎን በመቀበሌ እጅግ አድርጌ አዘንሁኝ። ስለምን? በጐኑ ገብተው አስጨንቀውት የነበረውን ጣሊያን ወደ ተንቤን መሄድዎን አሰልሎ ዓዲያቦንና ሺሬን እይዛለሁ ብሎ መጓዙ አይቀርም። ስለዚህ ክብርነትዎ ለግርማዊ ጃንሆይ የሚገባ መልስ ሰጥተው ባሉበት ሺሬ ሆነው ጠላትን ቢገጥሙት እጅግ መልካም ሠልፍ መሠላለፍያ ይመስለናል። -- -- የካቲት ፲ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ፊርማ፡ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።”ገጽ 115

“ -- -- ፫ቱ የጣሊያን ምርከኞችም ደርሰዋል። ባደረጉላቸው ቸርነትዎ በብዙ ክብርነትዎን አመስግነው ነገሩን። ያመሰግናሉም። ኣኔም ስመረምራችው የራማ ምርከኖች የጣሊያን ሠራዊት ፈጽሞ በችጋረኛው ረሐብ ተጠቅቶዋል፤ የተስቦ በሽታም ታመው መሞታቸውን በግልጽ ነገሩን። የሮማ ሊቀ ጳጵእሳትም ለስሙ እርቅ ላስታርቅ ብሎ ይደክማል። የሙሶሊኒ ወገኖችም በፈቃዳቸው ወደ ጦርነቱ እንሄዳለን እያሉ ሲሉ የነበሩት እንኳንስ በፈቃዳቸው ሊሄዱ ታዘውም ለመሄድ ብርቱ ችግር ሆኖባቸዋል። ከአሥመራ እስከ ዓድዋም በክፍል በክፍል ለባለ ኮንቲራት ሰጥቶ መንገዱን ያሠራል። በሀገራችን ግን ሕዝብ ራብ በዝቶበት ተጠቦዋል። ለወደፊቱም ረጅም ጦርነት ለማድረግ አይችልም። ሙሶሊኒም የጣሊያንን ሕዝብ ጠብ ፈርቶ ጀነራል ደ ቦኖን ከአሥመራ ወስዶ ባጠገቡ አደረገው። ጠላቱ የነበረውን ማረሻሎ ባዶሊዮን አድማ እንዳያነሳበት አሥመራ ሰደደው። በመጨረሻም ጣሊያን በእዳ ተይዛ ሀገርዋን ለውጭ መንግስታት አለጥርጥር ታስይዛለች ብለው ገልጸው ነገሩኝ። ነገሩም የሚመስል ነውና አጥብቀው ይመርምሩት። ቸሩ እግዚአብሄር ይጠብቍኦች አሜን፤ የካቲት ፳፭ ቀን ፲፱፻፳፷ ዓ.ም. ጋባት ፊርማ፣ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።” ገጽ 115

ብቀጣዩ ክፍል አርበኛው “የጎጃም ሺሬ ዘመቻ፣ ከሺሬ ድል ሆነን ጎጃም መመለስ፣ ከጎጃም ጎሬ ድረስ በአርበኝነት መከላከላችን” በሚል አርእስት ስር ያሰፈሯቸውን አንዳንድ ሓቆች እንኮመኩማለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው። :mrgreen:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 31 Jul 2019, 05:02
by Degnet
Meleket wrote:
25 Jul 2019, 10:07
ኣርበኛው ዛሬ የቆረጣ የውጊያ ስልትን ለኃይለስላሴ ሲመክሩ፣ ንጉሠ ነገሥቱንም ኣገልጋይዎ ባርያዎ እያሉ በጊዜው የኣነጋገር ዘይቤ ትህትናቸውን ይገልጻል። የጣሊያንን ጭንቀት ምክንያት፣ በኣዅሱም ስለነበሩት ፳ የጣሊያን ኣውሮፕላኖችና የኃይለሥላሴ ደብተሮች ምን ኣደረጉ ተብሎ እንደተወራም ይገልጻሉ! :mrgreen: :lol: :mrgreen:

“ለግርማዊ ጃንሆይ - ለመንግሥታችን ጕዳት ሆኖ የታየኝን ለማመልከትዎ ኅሊናዬ ስለአስገደደኝ ሰውና ከብቱ በረሐብና በበሺታ ሳይደናገጥ መቀለ ፫፻ ሺህ ያህል ያለው ሠራዊታችን እስከ ዛሬ ድረስ ተሠልፎ ባለምግጠሙና መቀለን ባለማስለቀቁ ብርቱ ስንፍና የሚያመጣብን ሆኗል። ክቡር ራስ እምሩም ኅሳባቸው ሁሉ እንዳይፈጽሙ እንቅፋት ሆኖባቸዋል፤ አሁንም ምንስ ጐጃም ቢከዳቸውና ደጄን የሚሆን ሠራዊት ባይታዘዝላቸው ነው እንጂ ሌላ ቀርቶ ኣዅሱምንና ዓድዋን እለቱን እጅ ለማድረግ በጣም የተዘጋጁ ነበሩ፤ ጊዜውም እጅግ መልካም ነው። ይህም ሁሉ ሆኖ ራስ እምሩ ሠራዊታቸውን በዓይዳቦ(ዓድያቦ) መረብን ተቻግሮ የጣሊያንን ግዛት ትኩል እንዲመታ አፋጥነው ልከዋል። የሐማሴንም ሰው እየከዳ መግባት ጀምሮላቸዋል። የሁሉም ማሰሪያ በፍጥነት ረዳት የሚሆናቸው ጦር ታዞላቸው፣ መገናኛም ለሥልኩና ለፖስታ ብልሐት እንዲደረግበት መሬት ወድቄ ለግርማዊነትዎ አመለክታለሁ። ጥር ፲ቀን ፲፱፻፰ዓ.ም. ዳባት በሥልከኛው ባቶ በዛብህ የተላለፈ የሥልክ ቃል። ፊርማ፣ ባርያዎ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ ”ገጽ 100

“ለግርማዊ ጃንሆይ - ትንሹ ኅሳቤን እንድገልጽለዎ እንዲፈቀድልኝ መሬት ወድቄ እለምናለሁ። በእግዚአብሄር ሰፊ ቸርነት፣ በንጕሠ ነገሥታችን ጸሎትና ብርታት፣ በሠራዊትዎ ድፍረት የጠላታችን አረዮጵላኖች በየጫካውና በየተራራው በየቀኑ መውደቅ በዝተዋል። በአዅሱምም ያሉት ፳ው ከመሬት አልነሣም አሉት። እሱም አጼ ኃይለ ሥላሴ ደብተሮች ልከው አረዮፕላኖቻችንን ከመሬት እንዳይነሱ አደረጕ። ጥይት የማይገድለው ተንኮለኛው ጅብ ልከው ወታደራችንን አስነክሰው ጨረሱት እያሉ ጣሊያኖች ያለቅሳሉ ይባላል። ይህም የእመቤታችን የማርያም ጽዮን ሥራ ነው የሰው ሥራ መሠላቸው እንጂ። በሰዎች ዘንድ ታንክም ፈጽሞ ተንቆዋል።” ገጽ 101

“አሁንም የግርማዊነትዎ ፈቅድ ሆኖ በሺሬና በኣይዳቦ (ዓድያቦ) በኩል ጣሊያንን በጐኑ እርድ በሌለበት ገብተን ወገቡን ለመቁረጥ ብዙ ጦር በፍጥነት መላክ ማስፈለጕን ለግርማዊነትዎ አሳስባለሁ። እኔም ከሺሬ ለሥራ ዳባት መጥቻለሁ። ጥር ፲፬ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም ። ፊርማ፣ ባርያዎ ተስፋ ሚካኣኤል ትኩእ። ”ገጽ101

“ለግርማዊ ጃንሆይ- ግርማዊ ጃንሆይ ጦርነቱ ይቆይ ብሏል እያሉ የሚሰብኩ ፈሪዎች የሆኑት ሰዎች ጀግኖቹን እያሳነፉ በመሔዳቸውና በመስበካቸው እጅግ ያሳዝናል። ለንጕሥም ፈጽሞ የጦርነት ድግሥ ማቆየት አያስፈልግም ነበር። አሁንም ሣሩ ሣያልቅ፣ ምንጩ ሣይደርቅ ሰውም በሐዲስ ጕልበት እንደ እውቀቱ አድርጎ እንዲዋጋው ማድረግ መልካም ነበር፤ ጣሊያንም በኛው ብርቱ ጦርነት፣ በሀገሩ ሕውከት በዓለም ነገሥታት ቁጣና ብድር መከልከል ምክንያት መጨነቁን ዓይጠረጠርም። ጥር ፲፬ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ዳባት። ፊርማ፣ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።”ገጽ 101

“ይድረስ ለክቡር ጌታዬ ራስ እምሩ ኃይለ ሥላሴ እንደምን ሰንብተዋል፤ ለጤናዬ እግዚአብሄር ይመስገን ደህና ነኝ፤ ከዚህ ቀደም እንደጻፍሁለዎት የአገው ምድር ቀኛዝማች በላይ ዘለቀና ቀኛዝማች ረታ፣ ቀኛዝማች መድፉ ከነተከታዎቻቸው ጋር ሆነው መዘጋ ለመዘጋ ኣቋርጠው ከጌታዬ ከድተው አርማ ጭሆ ማዝኞ ከሚባለው ቦታ በባላገር ተከበው ሰንብተው ፶ ሰው ሞተባቸው፣ ፲፭ቱ ተማረኩ፤ ቀኛዝማች መድፉም ቆሰለ ብለው የጎንደር ሥልከኛ አረጋግጠዉልኛልና ለወደፊቱ ቢሆን መጠንቀቅ ነው። . . .”ገጽ 104

“ቁጥር ፭ - ራስ እምሩ - ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል . . . በዚያለ በኩል የምትሰማውን አንዳንድ ነገር ለምን አትጽፍልንም? ተምቤን ራስ ካሣና ራስ ሥዩም ከኣኢጣሊያኖች ተዋግተው ድል አደረጕ ማለትን ፊታውራሪ መርሶ ላባቱ ጽፎ ሰማነው፤ የዚህን አንተስ የማሰኸውን ለምን ሳትጽፍልን ቀረህ? አሁን እንድትጽፍልን። ዳግም ጠላቶቻችን ሕዝቡን በሀሰት ወሬ ለመስበር ለየሀገሩ ወረቀት ስለሚበትኑ በዚህ ሰሞን ከበተኑት ተገኝቶ ዛሬ የመጣልንን ከዚህ ጋር ልከንልሃልና ወደ ግርማዊ ጃንሆይ በቶሎ እንድትሰደው ይሁን። የነ ወይዘሮ ጽጌ ማርያምንም ድህንነት ኣንደዚሁ በየጊዜው ኣየጠየቅህ እንድትልክብን። ለጃንሆይም የሚያልፍ ቃል ልከንልሃልና እንዲያልፍ። በዚያም በኩል የምትሰማውን ጻፍልን፤ ጤናዉን ይስጥህ። ጥር ፳፱ ቀን ፲፱፳፰ዓ.ም. ሺሬ። ፊርማ እምሩ ኃይለ ሥላሴ” ገጽ 106

በቀጣዩ ክፍል ኣርበኛው ከራስ እምሩ ጋር የተጻጻፏቸውን ኣንዳንድ ቀጣይ ሃሳቦችንም እንቃኛለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:
Thank you again and again,wend yemiadergeh tarik new.

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 19 Aug 2019, 09:15
by Meleket
የአርበኛው የተስፋ ሚካኤል ትኩእን ትረካ እንቀጥል እስኪ! :mrgreen:

“ከዚህ በላይ እንዳመለከትኩት ሁሉ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት በጠቅላላው የጦርነት ሠልፍ ድርጅት ለመደራጀት ካለመቻሉ በላይ፣ የአንድነት ስምምነት ፈጽሞ ስላልነበረና ከኢውሮጳም ያስመጣውን መሣሪያ ተስማምተው በጅቡቲና በበርበራም ከልክለው በማስቀረታቸው፡ ቀደም ብሎም አዲስ አበባ የገባውንም የጦር መሣሪያ ከየሣጥኑ ሳይወጣና ለሰውም ሳይሰጥ ጠላት ገብቶ ከፍቶ እስኪወስደው ደረስ ዝም ብለው ያስቀመጡት ባለሥልጣኖች በጣሊያን ተገዝተው ነው ወይስ ራሳቸው ባዶ ሆኖ ነው? የሁለታ ልጆች ጣርማበር ሄደን እንዋጋለንና መሣሪያ ስጡን ሲሉዋቸው አንሰጥም ብለው ከልክለው ለጠላታቸው ለጣሊያን ሳይከፈት እንደተዘጋ በጥንቃቄ ያቆዩት?” ገጽ 117

“በክቡር ራስ እምሩ ኣዛዥነት በታህሳስ ፲፪ ቀን ሺሬ እንደገባን ለራስ እምሩ መሣሪያና ገንዘብ ቢሰጣቸው ኑሮ ሰውን በገንዘብና በመሣሪያ፣ በስንቅም ደስ አሰኝተው በዓይዳቦና(ዓዲያቦና) በትኩል ወደ ዓረዛና ሠራዬ፣ ወደ ሐማሴን በመረብም አቋርጠው በመረታ ወደ አከለጉዛይ ደረቅ ጦር ልከው የሽፍታነት ጦርነት ለማንሳት ዋና ኅሳባቸው ነበር። እንደዚሁም ጎጃም ሆነው በአሰብ በኩል ባለግመል ጦር እንዲላክ በሰፊው ለመንግሥት በጥብቅ አሳስበው መሣሪያም እንዲላክላቸው፣ ለወታደሩም ስንቅ እንዲሰጠው ከማሳሰብ አላቋረጡም፤ ከሁሉም የተሰጣቸው ነገር ምንም አልነበረም። በዓጋሜ ምሥራቅ ዞሮ በአሳኦርታ ወደ አከለጉዛይ ዕውቀት ያላቸው የጦር መሪዎች ተልከው የጠላት አረዮፕላንና መድፍ ሊደርስበት በማይችል ቦታ ገብተው ለመሥራት መቻላቸውንም አስታውሰው ነበር፤ ያለ መስማማት ሳለ ግን አንዳች የወንድነት ሥራ ለመሥራት ወይም ለማሠራት አልተቻለም።” ገጽ 117

“ይህም የራስ እምሩና የአማካሪዎቻቸው እውነተኛው ሥራ አጥቂ በሆነው የሺፍትነት ወራሪነት አካለጉዛይ ጦር ቢገባ ኑሮ ተይዞ በግዴታ ዘመቻ ዘምቶ በመቀለ ያለው የኤርትራ ሕዝብ ሀገራችን ተወረረ፣ ቤታችንና ንብረታችን ተዘረፈ ሲል ያለ ጥርጥር እለቱን ጣሊያንን ከድቶ ወደ ቤቱ በተመለሰና በወጋውም ነበር። የኤርትራ ሕዝብ ከጣሊያን ከድቶ ይወጋው ይሆናል ብሎ ከንቱ በሆነው ተስፋ ዝም ብሎ ከመጠበቅ ይልቅ ድሮ ኤርትራን አለመሸጥ ይቀርብ ነበር። ከዚህም ሁሉ በላይ በማይጨው ጦርነት ቀን “አለ መሪዎች በተፈጥሮው ጦረኛና ጀግናም በሆነው ኢትዮጵያዊ ደፋር ወታደር ጦርነት ፈፅመን ሽሽት ለመሸሽ ውሳኔ ወሰነን ተነሳን ሳለን ንጉሣዊ ሠራዊት መሸሹን በአረዮፕላን ታይቶ ስለተነገረን ነው እንጂ የተከተልነው። ድል ሆነን ሸሽተን በመጨነቅ ላይ ነበርን።” ሲል ራሱ የጣሊያን ማረሻሎ ባዶሊዮ በጻፈው መጻፍ ለኢትዮጵያ ወታደር መሰከረለት።” ገጽ 119

የጣሊያንን ሠራዊት በስለታም ጐራዴአችን እንደዱባ አንገት አንገቱን እንቀረድደዋለን፤ ድል አድራጊዎቹም እኛ ኢትዮጵያኖች ነን እያለ ሲል የነበረው ድል ሆኖ ሲመለስ ተስፋ ያላደረገበትም ጣሊያን ድል ማድረጉን በማግኘቱ የዓለም መንግሥታትና ሕዝብ ሁሉ በብዛት ተደነቁ። ታሪክ አዋቂዎቹ የሆኑትም ሰዎች ሁሉ የጣሊያንን ኢትዮጵያን ድል ማድረግ ፈጽመው አላመኑም ነበር። ከሁሉም በላይ ዐረቦች ካለማመናቸው በላይ ስለ ኢትዮጵያ ኅዘን አዘኑ፤ ጣሊያንን አጥብቀው ጠሉት፤ ሰደቡትም። ይህንኑ እጅግ ከፍ ያለውን መለዋወጥና መከራን ጐትቶ ያመጣ የሀገረ ገዢዎችና የወታደር ወገን የሆኑት ፣ ያለ ማቋረጥ በደሀው ገበሬ ላይ እውነተኛውን ፍርድ ነስተው መከራና ስቃይ ስላዘነቡበት፣ የደካሞች ብድር ከፋይ የሆነው እግዚአብሔር ይህንን መጥፎ አገዛዝ ለመሠረዝ፣ ለአጥፊዎቹም ፍርዳቸውን በጣሊያን እንዲቀበሉ ያደረገው ራሱ እግዚአብሔር ነው። ምንም እንኳ የኢትዮጵያ ሠራዊት ስንቅና ውሃ፣ ገንዘብና ጥይትም ቢቸግረው፣ መሣሪያና አረዮፕላንም እንደ ጠላቱ ባይኖረው በጣሊያን ሠራዊት ድል ባልሆነ ነበር፤ በእኒያ ኢትዮጵያውያኖች ላይ በየዓይነቱ ስቃይ መሰቃየት፣ እሥራት መታሠር፣ ግፈኛው ሞት በጣሊያን ፈርዖናዊ አገዛዝ ባላዘነበባቸውም ነበር። በኢትዮጵያም ላይ እግዚአብሄር ያደረገው ተአምራትና መንክራት ለወደፊቱም የሚያደርገው ማንም ሰው ሊደረስበት አለመቻሉንና የግል ንጉሥዋ መሆኑን አለመዘንጋት ነው።” ገጽ 119

“ኢትዮጵያን ድል መታሁ ብሎ ካለልክ ተደስቶ የነበረውን የሙሶሊኒ ፋሺስታዊ አረመኔው ሠራዊት፣ በጦርነትና በህመም አለቀ፤ ሕይወቱን ገበረ፤ ገንዘብንም በሚሊዮን አወጣ። የእንግሊዝም መንግሥት በተሰወረው ውሉ መሠረት የጻና ባህርና ጂማን እንዲሠጠው ቢጠይቀው፣ ጣሊያንም የእንግሊዝን መንግሥት በመጥላት ወዳጅነቱን ጥንታዊ ጠላቱ ወደሆነው ጀርመናዊ ሂትለር አዞረ፤ ከኢትዮጵያም መሬት ስንዝር አልሠጥህም፣ ይልቁንስ ያለ ምክንያት በየጊዜው ከኢትዮጵያ የወሰድከውን ቃሮራና ከሰላ፣ ርስርስና በሮና፣ ሐርጌሳንም ልቀቅልኝ ብሎ ስላለው ተጨነቀ፤ በማናቸውም ዋጋ ስምምነት ለማድረግ ቢያቆላምጠውም ሳይሰማው ቀረ። የእንግሊዝም አዋቂ መንግስት የባህር የጦር መርከቦቹን ልኮ በሀገሩ ሆነ፣ በአፍሪካም ሆነ፣ ዕለቱን እንዳይደመስሰው ስለፈራ፣ የጣሊያን ሕዝብ ከእንግሊዝ መንግሥት ጋር ሆኖ ከሥልጣኔ ሊያበርረኝ ተነስቶዋልና ሠራዊት ስጠኝ ብሎ ፪፻፶ ሺህ ወታደር ተቀበለ። ለጣሊያን ሕዝብም “ትርፓሊን የሚጠብቅልን ረዳት ጦር ጀርመን ሰጥቶናልና በሀገራችን ሲያልፍ በደስታና በክብር ተቀብላችሁ ሸኙት” ብሎ ሕዝቡን አታለለው፤ የጣሊያንም መንጋ ዝምብሎ የጀርመንን ጦር ተቀብሎ ወደ ሀገሩ አስገባ።” ገጽ 119

“ገናም የኢትዮጵያ ጦርነት ሳይፈጸም በስስታምነቱ የታወረው የጣሊያን ፋሺስታዊ መንግሥት ለእስፓኛ ጄኔራል ፍራንኮ ለመርዳት ጦሩን ስለላከ ቁጥር የሌለው ወታደሩንና ገንዘቡን ጨረሰ። ውዳሴ ከንቱ ወዳድ የሆነውም የጣሊያን መንግሥት ትልቅ መንግስት ለመምሰል በ፲፱፻፴፪ ዓ.ም. ሰተት ብሎ ገብቶ የአልባንያን ንጉሣዊ መንግሥት ያዘ። ጉራውንም ያለልክ አዘነበ። ሀገሩን በጀርመን ወታደር አስነጠቀ፤ አስነወረ። ውርደትና እፍረትም አስለበሰው። ይህም ለስሙ የንጉሰ ነገስት መንግሥት የተባለው የጣሊያን ንጉሥ መንግስት ራሱ ጠርቶ ባመጣው ቂመኛው ጀርመናዊ፣ ጀግናው ወታደር ሙሰሎኒን ከሥልጣኑ ወርውሮ ለመጣል ሲያስብ ለነበረው ለጣሊያን ተታላይ ሕዝብ ሰላማዊ መስሎም አለበሰው፤ የጥንቱንም ባለታሪክ ዕቃና የቤተክርስቲያንም ንዋየ ቅድሳት ገፈፈው። ባለቤት ባለቤቱን ተቀማ፣ ደናግሎቹንም እያስገደዱ ሕጋቸውን በማፍረስ አበላሹዋቸው። ግፍና መከራ በጀርመኖች ተሠራበት።” ገጽ 119

“በሚያዝያ ፳፯ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. የገባው ጣሊያን በሚያዝያ ፳፯ ቀን ፲፱፻፴፫ዓ.ም. ከኢትዮጵያ በተአምራዊ የእግዚአብሔር ኃይል ወጣ። ዕፍረትና ውርደትም ለበሰ፤ ወደ ኬንያም ተነዳና በዚያም በካርቱምም መንገድ እየሰራ በችግርና በህመም አለቀ።” ገጽ 120

“እንግሊዝና አሜርካን፣ ኢትዮጵያኖችና ግሪኮች፣ የፈረንሳዊ ጄኔራል ደጐልም ወገኖች በትሪፓሊና በቸረናይካ በብዙ ተዋጉት - ለጀርመኑ ጄኔራል ሮመል። ሮመል በጀግንነት ሲሞት የጣሊያን መንጋ ተፈታ፤ እስከ ሀገሩም እየተከተሉ ወግተው ያዙት፤ መንግሥቱም ፈረሰ። እሥር ነገራችን እንግባ።” ገጽ 120

“በመጨረሻም ሺሬ ዘመቻ ድል ሆኖ ጐጃም መመለስ በየሀገሩ ገብቶ ሰው ለነፃነቱ የሚከላከል መስሎን ነበር። ዳሩ ግን ከድተው ከብዙ ጦር ጋር ከዳባት ከተመለሱት ደጃዝማች ገሰሰ በለው ተክለሃይማኖት ደብረ ማርቆስ ገብቼ አልጋን እይዛለሁ በሚል የታወረ ከንቱ በሆነው ሃሳብ ተነስተው፣ ከአበቤ እንጅባራ ደምሬው በቡሬና በማርቆስ፣ በብቸናና በቆለላ ጦርነት ከሸዋ ጦር ጋር ገጥመው ሰው ፈጁ። ጣልያንም ዕለቱን ሰምቶ በቆለላ ጦርነት ቀን ለደጃች ገሰሰ መትረየስና ጥይት፣ ብርና መብልን ዝቅ ብሎ በአረዮፕላን አወረደላቸው። ስለዚህ ጐጃምና ሸዋ ወገን ለይቶ ብዙ ደም በከንቱ ተፋሰሰ። አዋቂው ራስ እምሩ ለባላባቱ ለፊታውራሪ ነጋሽ ከበደ ደጃዝማች ብለው ሀገሩን እንዲጠብቅ ሹመው በትልቅ ጥበበኛው ፖለቲካዊ ዘዴ በፍቅርና በስምምነት ሰዋቸውን ሰብስበው በሰላም ግንቦት ፩ ቀን ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ከደብረ ማርቆስ ዓባይን በዘሜ ተሻግረን በግንደበረት አምቦ ገባን። የአምቦም አዳራሽ ለጠላት እንዳያገለግል ብሎ ልጅ በላይ ኃይለአብ አቃጥሎ፣ የሆለታ ልጆችና ማይጨው የዋሉትን ሐማሲኖችና በአዲስ አበባም የነበሩትን ሰብስቦ ፊት ፊታችን አለፈ፤ በዚህ ግዜ እኛ የጉደርን ድልድይ ተሻግረን መሠላለፊያ ቦታ ይዘን ወይዘሮ የመስራች እምሩን ስንጠብቅ። እኛን ፍለጋ ፴፪ አረዮፕላን ላከና ያለንበት ቦታ ሳያየው የለቀምትን መንገድ ይዞ ወደ ሔደው ልጅ በላይ ኃይለአብ ነጎደ፤ ሳያገኘውም ቀርቶ በላያችን ላይ ወደ አዲስ አበባ ሲመለስ አየነውና የለቀምትን መንገድ ትተን በኖኖ በሊሙ ድደሣን ተሻግረን ቡኖ ገባን።” ገጽ 120

በቡኖም ዘመቻ ያልዘመተ ሰው አገኘንና ሰባስበን በገባ ወደ ጐሬ ተጉዘን አረዮፕላን ያልደረሰበት የሰላም ሀገር ጎሬ በሐምሌ ወር ገባን፤ ብዙ ወታደርም አገኘን። ከጎጃም ዓባይን ተሻግረን ግንደበረት እንደደረስን ክቡር ራስ እምሩ ኃይለ ሥላሴ ዓባይነህ ሰውን ሁሉ ሰበሰቡትና አስተዋይ በሆነው፣ እውነተኛው ጉድለት በሌለበት መልካም ዐዋቂ ህሊናቸው ተመርተው “እኛ እስከ መጨረሻው ጠላትን እየተከላከልን ጠረፍ ድረስ እንሔዳለንና ስለ ሀገሬ ነፃነት እከላከላለሁ የሚል ሰው ይከተለን፤ አልሄድም ለሚለው ግን የሰጠነው ብረቱንና ጥይቱን እንደያዘ በየሀገሩ እንዲገባ ብለው በቃላቸው ነገሩት”የጣሊያንን ዓይን አላይም ብለው በሐመዶና በራማም ጦርነት በጀግናነት ጣልያንን በድፍረት የወጉት ደጃዝማች ገብረመድኅን ባይርዑ እስከ ልጅ ልጆቻቸው ከሺሬ ከኛ ጋር መጥተው ነበርና ጣሊያንን ሳያዩ ወደ ዐረፉበት ደብረ ሊባኖስ እሄዳለሁ ስላሉ ከክቡር ራስ እምሩ ጋር በሃዘን ተለያዩ፤ የጠላትን ዓይን ሳያዩ በደብረ ሊባኖስ ሳይገቡ ቆይተው፣ ቢልክባቸውም አልገባም ብለው ዐርፈው ተቀበሩ ማለትን ሰማን። የተቀሩት መኰንንቶች እነ እቴጌ ጦር እንደራሴ ደጃዝማች ተስፉ ትኩእና አፈ ንጉሥ አረጋይ ሌሎቹም ወደየ ሀገራቸው ተበተኑ።” ገጽ 121

በዚህም ትልቅ የመከራና የችግር ሰዓት ክቡር ራስ እምሩ እኛን ኤርትራዊያኖችንና የመንግስት ሠራተኞችን ሁሉ ወደ ድንኳናቸው ሰብስበው አንድ ባንድ እስከ ጠረፍ ከኛ ጋር ትሔዳላችሁ ወይስ ትቀራላችሁ ሲሉ ጠየቁና እኔ ላይ ሲደርሱ” ተስፋ ሚካኣኤል የጣሊያን ጠላት መሆንክን እናውቃለን፤ አንተ ከኛ ጋር ትሔዳለህ፤ ጓዝህ ግን ርዳታ ተደርጎለት በዱላ መሬታን እንዲቀመጥ ለቀኛዝማ ሥዩም ደብዳቤ እንጽፍላቸዋአ ውለን” ሲሉ አሉኝ። እኔም “ክቡር ሆይ እስከ ደከሙበት ቦታ ድረስ ይዜ እሔዳለሁ፤ ሲደክሙም በሽጉጤ እገድላቸዋአለሁ እንጂ ባለቤቴንና ልጆቼን ለጣሊያን ወታደር መጫወቻ እንዲሆኑ ትቻቸው አልሔድም” ስላቸው። ሴትና ሕፃናት ይዞ ወደ ጦርነት መሔድ አስቸጋሪ ስለሆነ አደራ ብለን በርስቴ ላይ ብንተዋቸው የተቻለ ነው፤ አይሆንም ይሆናል በማለት ስንከራከር ከነበሩ ሰዎች ውስጥ በኋላ በጐሬ ከብፁዕ አቡነ ሚካኤል ጋር ጣሊያን የገደላቸው ቀኛዝማች ይነሱ የተባሉ የራስ እምሩ አጐት ብቻ እውነቱ ነው አቶ ተስፋ ሚካኤል ሲሉ በቀር የተቀረ ሰው ሁሉ ባለቤቴንና ልጆቼን ይዜ እሔዳለሁ ቢዘልቁ ዘለቁ ባይዘልቁ በደከሙበት ቦታ ገድያቸው እሔዳለሁ እንጂ ትቼ አልሔድም ማለቱ “አብዶ ነው” አሉኝ።” ገጽ 121

“እነዚህ አብዶ ነው ሲሉኝ የነበሩት ሰዎች ይቅርና ነገሩን የሰሙት ያለ ምሕረት በጠላት እጅ የተገደሉትና በየእሥር ቤቱም በኢትዮጵያና በጣሊያን ሀገር በመቃድሾም የታሠሩት ሰዎች ሁሉ “ባለቤቴንና ልጆቼን ለጣሊያን ትቼ ከመሔድ ይቅል በደከሙበት ገድያቸው መሔድን እመርጣለሁ” ያለው ሰውዬ እውነቱ ነው እያሉ የጣሊያንን ክፋት ያዩ ሰዎች በማድነቅ ማመስገናቸውን እነ ዶክተር ሚካኤል ተሰማ መሰከሩ። ይመሰክራሉም።” ገጽ 122

“ . . . ይህም ሲሆን ፈርተን በየ ርስታችን ተቀምጠን እርሻ አርሰን እንኖራለን ያሉትን ሰዎች በእሥራትና በስቅላትም ሲገድላቸው፣ ከክቡር ራስ እምሩ ጋር በጦርነት ጌራ ላይ የተማረኩትን ሲምራቸው በመታየቱ ሕዝብ በብዙ ተደነቀ።” ገጽ 122

በቀጣዩ ክፍል ፦ በሺሬ የተማረኩት ኢጣሊያኖች “ኢትዮጵያን እንይዛታለን አሉ እንጅ እንገዛታለን” አላሉንም ነበር በማለት የጀመሩትን ታሪክ አርበኛው ተስፋ ሚካኤል ትኩእ፣ ዶክተር የደሐርቲ የተባለ የአመሪካን ሚሲዮን ሰው ለነ ራስ እምሩ ሰዎች ያሰማውን ስብከት አስታከው አርበኛው ተስፋሚካኤል፡ ደሐርቲ እስኪ ከፋው ድረስ የሰጡት ምላሽ፡ ነቀምት ላይ ፫ት የጣሊያን አረዮፕላኖችን “የአንበሳ ቡቺላ” ሐማሴኔው ልጅ በላይ ኃይለ አብ ምን እንዳደረጋቸው፣ ግራዝማች መስፍን ቀለመወርቅ ከጐሬና ከጋምቤላ የሰበሰበውን ፴፭ ሺህ ብር በአጋሰስ በአሽከሮቹ አስጭኖ እንደላከ፣ እሱም ለሊት ገስግሶ ወደ ጋምቤላ ወርዶ በካርቱም በጂቡቲ ወደ ወዳጁ ወደ ጣሊያን ለመግባት ሲሰናዳ ምን እንዳጋጠመው አርበኛው ተስፋ ሚካኤል ትኩእ ያስኮመኩሙናል።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው። :mrgreen:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 27 Aug 2019, 03:07
by Meleket
የራስ እምሩን ሠራዊት በጐሬ ያደረገው ክርክር፣ የጣሊያን ከጦርነት ይልቅ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ፣ የሐማሴኑ ቡቺላ ልጅ በላይ ኃይለአብ ከነ ተከታዮቹ በነቀምት ያሳየው ድፍረትና ጀብድ (የጣልያን ፫ት አረዮፕላኖች ማጋየት ኦፊሰሮችና አንድ ጄነራል መግደል)፣ ፊተውራሪ ሙሣ ለጣልያን ኮሎኔል ከለላ በመሆናቸው ደጃዝማች እንደተባሉ፣ በነቀምት የቁስለኛው ጣልያን ወታደር ጥልቅ የሃገርና የባንዴራ ፍቅር ስሜት፣ ‘ያልታደለው’ ግራዝማች መስፍን ቀለመወርቅ ፴፭ ሺህ ብር በአጋሰስ በአሽከሮቹ አስጭኖ ምን እንዳደረገና ፍጻሜው ወዘተ በዛሬው ትረካቸው አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ ይገልጹልናል። መልካም ንባብ። :mrgreen:

“ቅጣት ለመቅጣትም ነው እንጂ የጣሊያን መንግሥት ኢትዮጵያን ፈጽሞ ለመግዛት አለመቻሉን በቅዱሳት መጻሕፍትና በኢትዮጵያ ሊቃውንት ተረድተው ነበር። በሺሬም የተማረኩት ኢጣሊያኖች “ኢትዮጵያን እንይዛታለን አሉ እንጂ እንገዛታለን” አላሉንም ነበር። ብዙዎቹም እስከ መያዛቸውም ተጠራጥረው ነበር። ሞላው ዓለምም አላመነም። ሙሶሊኒም ራሱ “ከቢጫና ከጥቁር ሕዝብ አደጋ ተጠንቀቁ” ሲል ኤውሮጳን አስጠነቀቀ፤ በዶጋሊና በሠሐቲ፣ በሠገነይቲና በኃላይ፣ በኮዓቲትና በዓድዋ ጦርነት ያለቁትን የጣሊያን ወታደሮች በቀል ለመበቀል ተነሱ እንጂ ኢትዮጵያ በጣሊያን መገዛትዋ ይቅርና ለመያዝዋም ብዙ ችግርና በብዙ ተጨነቆ ነበር።” ገጽ 123

“ሙሶሊኒን እኛ ኢትዮጵያን እንጥላው እንጅ የጣሊያን ሕዝብና መንግሥት እንኳንስ እንደ እባብ ቀጥቅጦ መግደሉ ይቀርና ሊጠላውም ባልተገባው ነበር። ከጐረቤቶቻቸው ባርነት ነፃ አውጥቶ፣ እዳቸውን ከፍሎ፣ ከድህነት ወደ ማግኘት፣ ከደካማነት ወደ ብርታት፣ ከድንቁርና ወደ ሥልጣኔ፣ ከስንፍና ወደ ኃይለኛነት፣ ከፍተኛው ደረጃ ያደረሳቸውን ሙሶሊኒን መግደል ለኢጣሊያኖች ያሰድባቸዋል እንጅ አያስመሰግናቸውም። የጣሊያን መንግሥት ኢትዮጵያን አለመግዛት በብዙ የኢትዮጵያ ሊቆች ዘንድ ከብዙ ጊዜ ጀምሮ ተረጋርጦ ነበር።” ገጽ 123

“የደሐርቲ ስብከት፦ ጐሬ እንደገባን ምን ዓይነት ሰው መሆኑን ምንም ሳናውቀው ዶክተር ደሐርቲ የተባለ የአመሪካን ሚሲዮን ሰው ለራስ እምሩ ሰዎችና ለመንግሥት ሠራተኞች፣ ለነ አቶ አብርሃምና ዮሐንስ ዓብዱ፣ አቶ ገብረ መስቀል ሃብተማርያም፣ አቶ ተክለ ብርሃን፣ አቶ ስብሃቱና እኔንም ለሻሂ ግብዣ ጠርቶን በተሰበሰብንበት “ዓለም ጐባጣ ናት” ሲል ደሐርቲ ተናገረ። እኔም “አዎ ዓለም ጐባጣ ባትሆን እኛ ኢትዮጵያኖቹን ድል ያደረገ ማረሻሎ ባዶሊዮን ሺሮ በትምህርት ቤት የዑፍሴር ማዕረግ ምስክርነት የሌለው፣ በክፋቱ የታወቀውን ማርሻሎ ግራሲያኒን ሙሶሊኒ መሾሙን ብቻ ያስረዳል። ለኛም ከአዋቂው ባዶሊዮ ግራሲያኒ ይሻለናል። የሙሶሊኒም ሃሳብ ሰማይ ያልነካ፣ ምድር ያልያዘ፣ በንፋስ ላይ የሚወዛወዝ ነው፤ ኢጣሊያንም ኢትዮጵያን አትገዛም።” የሚል ረጂሙን ዲስኩር ስናገር እንኳንስ ደሐርቲ ይቅርና የኢትዮጵያ ወጣቶችም በንቀት ዓይን ትኩር ብለው ተመለከቱን። በኋላም ውጭ ስንወጣ አቶ ገብረ ሕይወት ደስታ የተባለ የሐረር ሰው “የሙሶሊኒ ሃሳብ ሰማይ ያልነካ ምድር ያልያዘ በንፋስ ላይ የሚወዛወዝ” በማለቴ አጥብቆ ተቆጣኝ።” ገጽ 124

“ጣሊያንም ኢትዮጵያን ለመግዛት የማይችልበት ምክንያት ካስረዳሁት በኋላ “ኢትዮጵያን መሬት ለእንግሊዝና ለፈረንሳይ መንግስታት ሳታካፍል ጣሊያን ለብቻዋ ኢትዮጵያን ይዛ እንድትገዛ አይፈቀድላትም። በኤውሮጳም አሁን በቅርብ ጦርነት ይነሳል።” ብዬ ስለው ዶክቶር ደሐርቲ እጅግ ከፋውና ከወንበሩ ተነስቶ ወደ ሌሎቹ ዘንድ ሔደ። ጣሊያን የጦር ጓደኞችዋን ትታ በክዳት ወደ ጀርመን እንዳትከዳቸው በገንዘብና በስንቅ በመሣሪያና በሰውም ቢረዱዋትም ጣሊያን ኅይል እንድታበጅና ከነሱም ጋር እኩልነት እንድታገኝ የሚወድ መንግሥት የለም ስላቸው ሁሎቹም የጠላትነት መሰላቸው እንጅ እውነት አልመስል አላቸው። ገጽ 124

“በራስ እምሩ እውነተኛው ኢትዮጵያዊነታቸው፣ መልካም ስምና ጥበባዊ መሪነታቸው፣ በሺሬ እስከ ጐሬ ከሕዝብ ጋር ያለ አንድ ጠብና ክርክር ኦሮሞ ካማራ በደስታ እየተቀበለና በፈቃዱም መስተንግዶም አምጥቶ እያበረከተ፣ ክቡር ራስ እምሩም ለየመኳንንቱና ለየደሐው የብርና የከብት ርዳታ እየሰጡ፣ ጠበንጃና ጥይትም ለሚገባቸው እየሸለሙ፣ ሠራዊታቸው በደንብ ሆኖ ጐሬ ከተማ በመግባቱ በብዙ ተደነቀላቸው።” ገጽ 125

“የጐሬም ሕዝብ ራስ እምሩ በመምጣታቸው ያልተደሰተ ሰው ምንም አልነበረበትምና ስለ ጦርነቱ ድርጅት ረጅም ክርክር ተደረገ። ክርክርሩም ደጀን አበጅተን፣ ለዘማቹም ስንቅ ሰንቀን ወደፊት እንላክና ስለ ነፃነታችን እንከላከል፣ ካልሆነም ብረትና ጥይታችንን ቀብረን ወደ ካርቱምና ወደ ኦጋንዳ እንሰደድ፣ የቻለው ወጣት በዱር በገደል ይከላከል፣ ጣሊያንም እስከ ሁለት ዓመት ድረስ ምሽቱንና ርስቱን፣ ልጁም ሲነጥቀው ሕዝቡ ጣሊያንን ይከዳል፤ ዛሬ ግን በመጥፎው አገዛዛችን ምክንያት ሐዲሱን መንግስት ፈቅዶዋል፤ የሚል እና በዚያን ጊዜ የተሰደደውንና በዱር በገደል ያለውም አንድላይ ተሰብስበን ስንወጋው ኃይልና ብርታት እናገኛለን፤ ድል ለማድረግም እንችላለን፤ የሚሉትንና ወደ ርስታቸው በሰላም ለመግባት የተመኙና ወደ ጠላታቸው ወደ ጣሊያን ለመግባት ለባርነት የናፈቁትን ወደ አዲስ አበባ ዘመቻ እንዝመት እያሉ አፋዊ በሆነው ውዳሴ ከንቱ ቃላቸው ተከራከሩ።” ገጽ 125

“በዚሁም ጊዜ ሁሉ ጣሊያን ከነ ረዳቶቹ ከጦርነት በበለጠ አታላይ ሐሰተኛ፣ የውሸት ስብከቱና ሰፊ በሆነው የገንዘብ ስጦታው ብዛት፣ በሥልክና በራዲዮ፣ በደብዳቤና በአየርም ስብከቱን በአረዮፕላን ያለ ማቋረጥ እየበተነ ከበበን። ነቀምትም ፫ት አረዮፕላኖችን አረፉ፤ የአንበሳ ቡቺላ ሐማሴኔው ልጅ በላይ ኃይለአብ አደጋ እንጣልባቸው ብሎ ለደጃዝማች ሃብተ ማርያም ገብረ እግዚአብሔር ቢጠይቃቸው አደጋ እንዲጣልባቸው ሳይፈቅዱ ቀርተው። ፫ቱ አረዮፕላኖች በትልቅ ድፍረትና ጀግንነት ሰዎቹን ይዞ ሔዶ ልጅ በላይ ካቃጠላቸው በኋላ ደጃች ሃብተ ማርያማ ለልጅ በላይ መልካም ሥራ ሠርተሃል እንኳን ደስ አለህ የሚል ወረቀት ጻፉለት። ልጅ በላይም ሕይወታቸውን የማይቆጥቡ ሐማሴኖችና የሁለታም ልጆች ይዞ ሔደ ለሊቱን ከቦዋቸው አደረና ሳይነጋ አረዮፕላኖች ሲያቃጥላቸው በውስጡ የነበሩትን ዑፍሴሮችና አንድ ጄኔራል ተኩስ ለመተኮስ ሳይችሉ ቀርተው ሲወጡ እየተቀበሉ ገደሉዋቸው። “ቄስ ነኝ” እያለ ነቀምትን መርምሮ ያወቀና ከነቀምቶችም ጋር በብዙ እምነት የተጻጻፈ ኮሎኔል ቦረሎ የተባለ በሚያውቀው መንገድ ሸሽቶ ፊታውራሪ ሙሣ ቤት ገብቶ ቢከታተሉት እጁን አንሰጥም ብሎ ስለተከላከለለት ብዙ ሰዎችን ፊታውራሪ ሙሣ አስገደለ። በዚሁም ውለታው ፊታውራሪ ሙሣ ደጃዝማች ሲባል በጣልያን፣ ደጃዝማች ሃብተ ማርያም በዚያች ወረቀት ልጅ በላይ ከራስ እምሩ ጋር በጌራ ሲማረክ በኪሱ ስለተገኘች በመርፌ ገደላቸው።” ገጽ 125

“በአሮፕላን መጥተው የተገደሉትም የጣሊያን ዑፍሴሮች ቦረሎ ሲያመልጥ ፲፩ ተገደሉ፤ ፩ዱም በቆሰለው ተሸክመው ለቀምት ወስደው ከአከሙት በኋላ “ለባንዲራህ ርገጣት፣ ካዳት ፣ አለዚያ እንገድልሃለን” ብለው ወታደሮች ሲጠይቁት “ባንዴራዬን ከመርገጥና ከመካድ ሞትን እመርጣለሁ” ብሎ መለሰ። በቆስለውም የጥይት ቁስል ስቃይ ተሰቃይቶ ሞተና ከገነዙት በኋላ ስለ ወንድነቱ በሚያፈቅራት ባንዴራው አልብሰው በክብር ቀበሩት፥ አዘኑለትም።” ገጽ 125

ዕቁባ ሚካኤል ገብረና ልጅ በላይ፣ ብላታ ወልደ ሚካኣኤል ተፈሪ፣ አቶ እንድርያስ ዘርኤና አቶ ሙሴ ብርሃነ፣ ባሻይ ገብረ እግዚአብሔር ወልደ ሚካኤል፣ ወንድሞቼ ስለሆኑ ወደ ስዩ (ደምቢዶሎ) ተቻግረው ጠረፍ ይዘው እንዲከላከሉ መጻፌ ለራስ ባማክራቸው፣ “ገንዘብ ከራስ እምሩ ይላክላችኋል ብለህ በኔ ስም ጻፍላቸው” ብለው ስለነገሩኝ ጻፍሁላቸው። ራስም እንደቃላቸው 5ሺህ ብር ላኩላቸውና ወደ ጐሬ ከነቀምት መጋዝ ጀመሩ። በዚሁም ጊዜ ዶክቶር ዓለመ ወርቅና ኰሎኔል ክፍለ ነሲቡ፣ ልጅ ቢኒያም ወርቅነህ ከነ ወንድሙ ጐሬ ከኛ ዘንድ ነበሩና ብፁዕ አቡነ ሚካኤልም በእውነተኛው ኢትዮጵያውነታቸው ለጠላት አትገዙ ሲሉ ነበር። በዚሁም ቂም አቡነ ሚካኤልና የራስ እምሩ አጐት ቀኛዝማች ይነሱ፣ ግራዝማች ተክለ ሃይማኖት በጐሬ ጣሊያን ገደላቸው።” ገጽ 125

ቢተወደድ ወልደ ጻድቅም ለጐሬ ሀገር ጥበቃ ስለመጡ ራስ እምሩ ጐሬ በመምጣታቸው ቅናት ቀንተው በስውር ሰዋቸውን ለጠብ አሠለፉ፤ ራስ እምሩም በብዙ ተደንቀው ሲጠባበቁ ሳለ፣ የንግድ ሥራ ተጠባባቂ ሆኖ ጐሬ ለመጣው ግራዝማች መስፍን ቀለመወርቅ አቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ ለጋምቤላ ጐምሩክ ተቆጣጣሪ ሆኖ እንዲሠራ ብለው ራስ እምሩ ቢያዙት ጣሊያንን ደስ ለማሰኘት ፲፭ ምክንያት እያመጣ እምቢ ብሎ አለ። ራስ እምሩንና ቢትወደድ ወልደ ጻድቅን ማጣላቱንና በወጋዴን ዲረክተርነቱ ለጣሊያን መርዳቱ ስለተመሰከረበት ወደ ጐሬ መላኩ ተረጋገጠ። ስለዚህ ሁሉ ክብር ራስ እምሩ ግራዝማች መስፍን ቀለመወቅርን በብዙ ተቆጡት። ግራማች መስፍን ቀለመወርቅ አለመታደል ከጐሬና ከጋምቤላ ጐምሩክ የሰበሰበውን ፴፭ ሺህ ብር በአጋሰስ በአሽከሮቹ አስጭኖ ላከ፤ እሱም ለሊት ገስግሶ ወደ ጋምቤላ ወርዶ በካርቱም በጂቡቲ ወደ ወዳጁ ወደ ጣሊያን ለመግባት ሲሰናዳ ተያዘ፤ ገንዘቡም ከሄደበት መንገድ ተመለሰ።” ገጽ 126

“ይህም ያልታደለ ግራዝማች በወዳጁ በጣሊያን እጅ መገደሉንና የተዋጉትን አርበኞች መማሩ ሰው ሁሉ የእግዚአብሄርን ወሰን የሌለው ፍርድ በብዙ አደነቀ። ያደንቃልም።” ገጽ 126

በቀጣዩ ክፍል “የጣሊያን መንግሥት ተስፋ ሚካኤል ትኩእ ካርቱም እንዳይወርድ ስለመከልከሉ፣ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ በራስ እምሩ እውነተኛው ድካም ካርቱም ለመውረድ በመቻሉ ማስደነቁ” በሚል ርእስ የተካተተውን የአርበኛውን ታሪክ እንኮመኩማለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው። :mrgreen:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 04 Sep 2019, 04:24
by Meleket
የአርበኛው የተስፋ ሚካኤል ትኩእ ትረካ ምዕራፍ 25 ደርሰናል፣ መልካም ንባብ። :mrgreen:

“ከ፲፱፻፲፰ ዓ.ም. ጀምሮ በደሴ ጉምሩክ ዳሬክቴርነቴ እስከ ነሐሴ ፲፱፻፳፫ ዓ.ም. ከፍ ባለው የሀገር ፍቅር ተቃዋሚነቴ (ተቆርቋሪነቴ) በደሴ ከነበሩ የጣሊያን ቆንስሎችና በመጨረሻም ከጄኔራል ካርሎ አናራቶን ፣ እንደዚሁም በ፲፱፻፳፯ ዓ.ም. በጐጃም ከነበረው የጣሊያን ቆንስል ከባሮነ ሙዝ ጋር እጅግ ረቂቅ በሆነው፣ ከፍ ባለው ፖለቲካዊ የዲፕሎማሲ ሥራ ሠርቸባቸው ስለነበረ፣ ከዚህም በላይ በሺሬ የጦር ሜዳ ብዙ የኔ የፖለቲካ ደብዳቤዎች ተገኝተው ወደ ጎንደር ስለተላኩ የነዚህ ደብዳቤዎች መርዝ ለኢጣሊያኖች ምንም እንቅልፍ የሚያስወስዳቸው አልነበረም።” ገጽ 127

“ስለዚህ በብዙ መንገድ ያለማቋረጥ፣ በየቀኑ የጣሊያን መንግስት “ተስፋ ሚካኤል ትኩእ ከነ ቤተ ሰዎቹ ከራስ እምሩ ጋር ይገኛልና ወደ ሱዳን ግዛትህ እንዳይወርድ በጥብቅ ከልክለህ እስክ መጣ ድረስ አቆይልኝ” እያለ ለእንግሊዝ መንግሥት በቴሌግራምና በደብዳቤም፣ ለየመኳንንቱ መላኩ ተመስክሮበታል። የጣሊያንም መንግስት ተስፋ ሚካኤል ትኩእ ካርቱም እንዳይወርድ መከልከሉን አልካደም።” ገጽ 127

“እኛ ኢትዮጵያኖች ነገሩን ሁሉ ከሥሩ ለመጀመር ፈርተነው ነው እንጂ የእንግሊዝ መንግሥት ባፉ ከኛ ጋር ቢሆን በልቡ ከጣሊያን ጋር መሆኑን አልዘነጋነውም ነበር።” ገጽ 127

“ቢሆንም በእግዚአብሔር ችሮታዊ ትእዛዝ በመጨረሻ የእንግሊዝ መንግሥት የዋለልን ውለታ ፈጽሞ የማይረሳ ነው። ስለምን? የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት አጼ ኃይለ ሥላሴን በሎንዶን፣ እኛንም በካርቱምና በግብፅ፣ በአደንና በኬኒያ ግዛቱም በስደተኞች ስም መቀበሉ እጅግ መልካም ሥራ ነው። በደስታም የተቀበለን የጣሊያን መንግሥት የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት በእጁ ቢያገባ ኖሮ ዕለቱን ጣሊያን ወደ ሂትለራዊ ጀርመን መንግሥት ዞሮ ቅኝ ሀገሮች መቀማቱ የማይቀር በመሆኑ ኃይልና ብርታት እንዳያበጅ ብሎ ስደተኞቹን አልሠጥም ብሎ ጣሊያንን የከለከለበት ምክንያት ይህ ነው። ጣሊያን ግን ባይሳሳትና ቂሙንም ለመወጣት ፈልጐ ካንተ ጋር በቃል ኪዳን ጓደኝነቴ የስምምነት ውል አልፈርምም ባይለው ኖሮ ስደተኞቹን ሁሉ ያለ ጥርጥር እንግሊዝ ለጣሊያን ባስረከበ ነበር።” ገጽ 127

“ የእንግሊዝ መንግሥት ግን ጣሊያንን ስላልተማመነው ከጣሊያን መንግሥት ፍቅር የዐዋቂው ክቡር ራስ እምሩን ፍቅር መርጦ በሳቸው ጥያቄ ፭ት ራሴን ካርቱም እንድሰደድ ፈቀደልኝ፤ ለራስም ወደ ኦጋንዳ ግዛት ፲፪ት ራሳቸው ሆነው እንዲሰደዱ በደስታ ፈቅዶላቸው ነበር። እንግሊዝም ጣሊያንን አስቀድሞ በብዙ መንገድ እንደጠረጠረው ያስረዳል፤ ክቡር ራስ እምሩም እኔን ጠርተው ከመነሳቴ በፊት ጥልቀት የተሞላበት (ጥልቀኛው) የፍልስፍና ምክራችውን ሰጡኝራስ እምሩም ሃሳባቸው እጅግ ሰፊ ስለነበረ ከኢትዮጵያ አርበኞች ወደ ኤውሮጳ የሚላከውንና ከኤውሮጳ ለነሱ ለሚላከውን ደብዳቤ እየተቀበልሁ እንድልክ አድርገው ወደ ካርቱም እኔን መላካቸውንም ለግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ጻፉላቸው።” ገጽ 128

“ገና በልጅነቴ ጸሐፊ ሁኜ ለጣሊያን መንግሥት ፲፪ ዓመት ሥራ ሥሠራ ሳለሁ፣ ኮማንዳቶረ ካቫሊ ኩራተኛው፣ ኮማንዳቶር ደሮሲ ዲያብሎስ፣ ኮንተ ማላሳኒ ዓለም ዘዋሪ፣ ኮመንደቶረ ብረየሊ እረፍት የሌለው፣ ሕውከተኛ እያሉ እኔን ከመጥላታቸው ብዛት የተነሳ በስድብ ስም ብቻ ይጠሩኝ ነበር። የጣሊያን መንግሥት የተመቼ ጊዜ ፈልጎ ኢትዮጵያን በመደምሰስ ለመያዝ ሃሳቡ መሆኑን በመረዳቴ ፲፭ ቀን ስንብት(እረፍት) ጠይቄ ሳለ አገልግሎቴ የሰጠኝን ሽጉጥና ጠበንጃ ይዜ ነሐሴ ፳፰ ቀን ፲፱፻፲፯ ዓ.ም. ከሀገሬ ከሠገነይቲ ተነስቼ በዙሪያ መንገድ ወደ ሸዋ በመምጣቴ በኔና በጣሊያን መንግሥት መካከል ከፍ ያለ ጠብ ተነሳ። መነሳቱንም የኢትዮጵያ መንግሥት አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኰንን አዲስ አበባ እንደገባሁ የወሎ ጉምሩክ ዳረክተር፣ በኋላም የጐጃም ጉምሩክ ዲረክተርነት ሾሙኝ፤ ከጣሊያን ቆንሱሎች ጋር ለመጣላትም የተገደድሁ ሆንሁ።” ገጽ 128

“ስለዚህ ደሴ ከነበረው የጣሊያን ቆንሱል ከጄነራል ካራሎ አናራቶኒ በኋላም ጐጃም በደብረ ማርቆስ ከነበረው ባሮነ ሙዝ ጋር በየቀኑ የከረረ ጥብና ስለ ሀገር ክርክር በመከራከራችን ብቻ ሳይሆን፣ በዕውቀት ሃሳባቸውን ስለማፈርስባቸው በኅዘን ሲቃጠሉ ስለነበሩ፣ ኢትዮጵያን ጣሊያን በያዘ ግዜ እንዳላመልጠው ፈለገኝ፤ ወደ ሱዳን እንዳልሰደድም አስቀድሞ ለእንግሊዝ ያስጠነቀቀው ሕይወቴን ፈልጎ ነበር። ሕይወቴም በእግዚአብሔር ወሰንና መሳይ የሌለው ሰፊ ቸርነቱ ዳነች።” ገጽ 128

በቀጣዩ ክፍል አቶ ገብረ እግዚአብሔር የተባለ ደፋር የወልቃይት ወጣት በሃገር ፍቅር ስሜት በቸረነይካ ምን አይነት ጀግንነትን እንደፈጸመ፣ ግብፆች የዋሉነት ውለታ፣ እንዴት አድርጎ ወደ ጎሬ ወደ ራስ እምሩ እንደደረሰ፣ ታሪኩ በእንግሊዝኛና ጣሊያንኛ በዐረብኛም የደመቀ ታሪክ ተጽፎለት እንደነበረ፣ ይህ ወደረኛ የሌለው ጀግና ኢትዮጵያ ነፃ ከወጣች ቀን የት እንደደረሰ፣ ወዘተ እንኮመኩማለን። አርበኛው በእግራቸው ከጎሬ የስሪታን ገደልማን ቦታ አልፈው፣ ባሮ ቃላን ድልድይ ተሻግረው ጋምቤላ እንደደረሱ ኣያሉም ካርቱም እንደገቡ ያጋጠማቸውን ሁኔታ የግዜውን የቦለቲካ ሁኔታ ያስቃኙናል።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው። :mrgreen:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 14 Sep 2019, 03:10
by Meleket
ለዛሬ አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ ስለ ጀግናዉ ወልቃይቴ አቶ ገብረ እግዚአብሔር ጀብድ ይገልጹልናልጠርጥር ነው ያ ጎንደር ላይ ጀብድ የፈጸመው ኮሎኔል ደመቀ ዘውዱ ከኒ ወልቃይቴ ጀግና ካቶ ገብረ እግዚአብሔር ያለ ጥርጥር ጀግንነትን ወርሷልእስቲ ወልቃይቴዎች ስለ አቶ ገብረእግዚአብሔር የምታዉቁትን ተጨማሪ መረጃ አካፍሉን! መልካም ንባብ!

“አቶ ገብረ እግዚአብሔር የተባለ ደፋር የወልቃይት ወጣት ወሰንና መሳይ በሌለው የሀገር ፍቅርና የዘር ጀግናነቱ ብዛት የተነሳ ጣሊያን ኢትዮጵያን ወረራት ማለትን ሲሰማ ጊዜ በብረታዊ የእሾህ ሺቦ የታጠረውን የቸረናካና የግብፅን ወሰን አቋርጦ ከወጣ በኋላ፣ አቶ ገብረ እግዚአብሔር ከጣሊያን በወሰደው ጠበንጃ ጥይት ያለማቋረጥ ተኩስ እየተኮሰ ከጣሊያን ጦር ብዙ ገድሎና አቁስሎም ስለቆሰለ ወደ የግብፅ ጠረፍ ዘበኞች ገባ፤ ግብፆችም ጣሊያንን ያለ ልክ ስለሚጠሉና ስለሚንቁትም ኢትዮጵያዊውን ጀግና ምክርና ርዳታም ሰጥተው በስውር ወደ ካይሮ ሰደዱት፤ በካይሮም ያለው የጣሊያን ቆንሱል በሰላዎቹ ብዛት በስውር ከተቀመጠበት ቦታ ገብቶ ቢያገኘውና ኃጢያቱን ዘርዝሮ ቢከሰውም፣ የኢትዮጵያ ወዳጆች የሆኑት ግብፆች የጣሊያንን ክስ ሳይሰሙ አቶ ገብረ እግዚአብሄርን ወደ ሱዳን እንዲገባ ለቀቁት። የአከዳዱና የጀግናነቱም ታሪክ፣ የፈጃቸውንና ያቆሰላቸውን ሰዎች ልክ ሳይቀር ራሱ ጣሊያን በሰፊው ሲጽፍለት፣ በዚሁም የአቶ ገብረ እግዚአብሔር የጣሊያንን ጦር ተኩስ ሰምተው የረዱ ግብፆችም በአቶ ገብረ እግዚአብሔር ባለ ታሪክ ጀግናነትና በሱዳን የሚኖሩትም የኢትዮጵያ ወንዶችና ሴቶችም የገንዘብ ርዳታ ሰጡትና ስለ ኢትዮጵያ ነፃነት ከሚከላከሉት ከክቡር ራስ እምሩ ዘንድ ጐሬ በሕይወት ደረሰ።” ገጽ 129

“ይህንኑ በድፍረት የተሞላውን ወንድነትና ጀግንነት ለወልቃይቴው ወጣት ላቶ ገብረ እግዚአብሔር ሰጥቶ ከየቸረነ ሊብያ ወደ የኢትዮጵያ ባንዴራ ወዳለቺበት ጐሬ ያደረሰ አምላክ በብዙ ሕዝብ ተመሰገነ። ወሰን የሌለው ቸርነቱም ተደነቀለት። ይደነቅለታልም።” ገጽ 129

“በሱዳንም እንደገባ ላቶ ገብረ እግዚአብሄር በሊብያ የሠራኸው ሙያ ይበቃሐልና ሱዳን ተቀመጥ ብለው ቢለምኑት “ኢትዮጵያ ገብቼ ደምዬን ለሀገሬ አፈስላትአለሁ እንጅ ምንም ቢሆን እንቅልፍ ሊወስደኝ አይችልም በማለት መለሰላቸው። ወደ ጐሬ እንደገባ ከክቡር ራስ እምሩ ጋር ተገናኘና ባልደረባነቱንም ለኔ ሰጡኝ፤ እኔም ታሪኩንና ያባቱን ስም የወጣበትን ቀንና ሰዓት የተቀበለውን ስቃይ ጽፌው በስደት ጠፋብን። አዋቂው ራስ እምሩም ያቶ ገብረ እግዚአብሔርን ህያው ታሪክ አስቀድመው ሰምተውት ስለነበረ እኔን ጠርተው ካማከሩኝ በኋላ ደመወዝ እንዲያገኝ ብለው በልጅ ግዛው አቡኔ በሚታዘዙ የክብር ዘበኖቻቸው ደንብ አገቡት፤ ርዳታም አደረጉለት።” ገጽ 130

ኢትዮጵያም ከጣልያን ወረራ ነፃ ወጥታ በተመለሰችበት ፲፱፻፴፫ ዓ.ም. ለዚሁ የወልቃይት ጀግና የኢትዮጵያ መንግሥት ቢፈልግና ቢያስፈልገውም ስላልተገኘ ሰው ሁሉ አዘነለት። ለዚሁም የወልቃይት ጀግና ከሊቢያ ምሽግ ሰብሮ፣ ጣሊያንን ወግቶና ብዙ ሰው ገድሎ፣ አቁስሎም ወደ ምድረ ግብፅ እንደገባ በእንግሊዝኛና ጣሊያንና፣ በዐረብኛም የደመቀ ታሪክ ተጽፎለት ነበር። ዳሩ ግን ይህ እንደዚህ ያለውን ወደረኛ የሌለው ጀግና ኢትዮጵያ ነፃ በወጣች ቀን ባለመገኘቱ በብዙ አዝናለሁ።” ገጽ 130

“ከኤርትራ መረብና ሽሬ መከላከል በመጨረሻ ድል ሆነን በጎንደርና በጐጃም በግንደበረትም እስከ ጐሬ ድረስ ከተከላከልን በኋላ ወደ ሱዳን ከነ ቤተ ሰዎቼ ለመሰደድ የተገደድሁ ሆንኩና ከጐሬ ተነስቼ ቡሬ የተባለው ሀገር ስደርስ፣ ክቡር ራስ እምሩ ከጐሬ በአረዮፕላን እስከ ካርቱም ሎንዶን እንዲሔድ የላኩትን ልጅ ፍቃድ ሥላሴ ኅሩይ ጋር ተገናኘንና እሱም እንዲህ አለኝ። ክብሩ ጌታዬ ራስ እምሩ ወደ ውጭ ሀገር ሳይሰደዱ በኢትዮጵያ ሆነው እንዲከላከሉ ጃንሆይና የኢትዮጵያ ኮሚሲዮኖች ውሳኔ የወሰኑበትን ትእዛዝ ይዤ መጥቻለሁና ወዴት ይሄዳሉ አለን። እኔም እጅግ ገረመኝና በሰፊው ኅሳብ አሰብሁ፤ በል ብዬም “ምን ግዜ ከኢትዮጵያ ወጥቼ የሰላም ሀገር በደረስሁ” ብሎ ሲል የነበረውን ሰው ሎንደን ደርሶ ሲመለስ ኃሳቤ ሁሉ ተለወጠ።” ገጽ 130

“ይህም የራስ እምሩ አማች ልጅ ፈቃደ ሥላሴ እንደ ከዚህ ቀደሙ ግርማዊ ጃንሆይ ራስ እምሩ ከኢትዮጵያ መሬት እንዳይወጡ የልፍኝ አስከልካያቸውን ቀኛዝማች በልሁን ከሎንደን ወደኛ ጐሬ ድረስ ልከው አስጠንቅቀዋቸው እንደነበረ ዓይነት ከግርማዊነታቸውና ካባቱም ዘንድ በጥብቅ ተልኮ መምጣቱን ስለተረዳሁት ተደነቅሁ። እንደገናም ልጅ ፍቃደ ሥላሴ “እኔና ባለቤቴ ወይዘሮ የምስራች እምሩ በየመርከባችን ሆነን በመለይካል ተያይተን ለመነጋገር ሳንችል ቀርተን እኔ ወደዚህ እሷ ወደ ካርቱም በመውረድዋ ብዙ ኅዘን አዘንሁ” እያለ አለን። ራስ እምሩም ሳይነሱ በጐሬ ይቆዩኝ ብሎ በሥልክ በኔው ፊት ተነጋገራቸው።” ገጽ 130

“የታሰበው ነገር ፈጽሞ ስህተት መሆኑን ስለተረዳሁት፣ እኔም ባለቤቴን ወይዘሮ ቀደስ ባህታንና ልጆቼን አበባ ተስፋ ሚካኤልና ፀሐይ ተስፋ ሚካኤልን፣ ሰሎሞን ንጉሤን ይዤ ከቡሬ በእግራችን የሰሪታን ገደልማና ገሃነብ እሳትዊ ቁልቁለት ስንወርድ ሳለን እንኳን ህፃናቱ ይቅርና እኛም በድካም ብዛት ፈጽሞ መንገድ መሄድ አቃተን። መሄድ አቅቶን በብዙ ከተጨናነቅን በኋላ እንግሊዝ ረቂቅ በሆነው ዐዋቂነቱ ለጥቅሙ ብሎ ጐሬን ከጋምቤላ ጋር ለማገናኘት በሠራው የብረት ድልድይ ባሮ ቃላን ተሻግረን፣ ተራራይቱን ዞረን አደርን። በዚሁም ልክ እንደ መቃብር ጥልቀኛው ጉድጓድ በሆነው ቦታ በወኃ ጥም ስንቃጠል አድረን በማግስቱ ጡዋት ተነስተን የእንግሊዝ ኩባኒያ ባሠራው መንገድ በካሚዮን ሆነን በአንበሳና በዘንዶ የተሞላውን በርሃ አቋርጠን በጊዜ ጋምቤላ ገባን። በዚሁም የነጮች መቃብር ተብሎ በተሰየመው ጋምቤላ የጉምሩክ ዲረክተር አቶ ተክለማርያም ኃይለ በክቡር ተቀብለው አስተናገዱን። በ፫ኛው ቀንም ከኢትዮጵያዊ ጋምቤላም በውል እንግሊዝ ወደ ወሰደው ተላልፈን ወደ ሱዳን ካርቱም በሚወስደን መርከብ ገብተን ጉዞ ጀመርን።” ገጽ 130

“በዚሁ የጋምቤላ ንዳድና ሙቀት፣ የሚናደፍ በያይነቱ ዝንብና አስጨናቂ ጥልቀኛው ጉድጓድ ለቀን ወደ ሱዳን ውዲቱ ኢትዮጵያ ሀገራችንን ለጠላታችን ለጣሊያን ለቀን ስደት በመሰደዳችን ምክንያት ከፍ ያለውን ኅዘን ለበስን። በኅዘን ተከበን በባህሩ ግራና ቀኝ ያለው ኑወር የተባለ ልብስ የሌለው፣ በጥቁረቱና በቁመቱ በርዝመቱ በሚያስደንቅ የኢትዮጵያ ’ላቅንሻ‘ ወንድ ከሴት ተሰብስበው በማድነቅ ሲመለከቱን ለኛም ለነሱም አንድ እንግዳ ነገር ሆነብን። መርዘኛው የጋምቤላን ዝንብ እየነደፈን በመመረር ከኮንጐ የሚመጣው ነጭ ዓባይና የጁባ ከባሮ ቃላ ባህር የሚገኛኙበትን ረግጠን ስናልፍ ሳላይ መርከቡ ተሰናከለና አንድ ሌሊት ሙሉ የመርከቡ አዛዥ ድምፁን ከፍ አድርጎ ለሠራተኖቹ ትእዛዝ ሰጠ። እኛም ቁጥር የሌለው ጐማሬና አዞ እንዳይበላን በብዙ ሰጋን፤ ፈጣሪን ለመንን፥፡ እሱም በቸርነቱ ሰማንና በሁለተኛው ቀን ጉዞ ቀጠልን። በመለይክልና በኮስቲ አድርገን የ፪ቱ ዓባዎች መገናኛ የሆነችዋን ካርቱም ከተማ ገባን።” ገጽ 131

“በዚሁም መርከብ ከኔና ከቤተ ሰዎቼም በላይ አቶ አብርሃም ዓብዱና አቶ ዳዊት ዓብዱ፣ አቶ ገብረ ሕይወት ደስታና በየነ ይዕብዮ አብረውን ነበሩና የስደቱን ጭንቅና መከራ አንድላይ ተቀበልን። አቶ ገብረ ሕይወት ደስታ ግን እንደ ከንቲባ ደስታ ከካርቱም በጅቡቲ አድርጎ ደናነ ሞቃድሾ ለመታሠር እምቢ ብሎ አዲስ አበባ ተመለሶ ገባ። በዚሁ ምሕረት የተለየው ጥቅምት ፲፱፻፳፱ ዓ.ም. በካርቱምም እንደገባን በሀገራችን መደምሰስ ወሰን የሌለው ኅዘንና በሙቀቱ ብዛት፣ በንዳዱም ብርታት የተነሳ ያለ ማቋረጥ ታመን ወደቅን፤ በያይነቱ የመረረ ስቃይ ሁላችን ተሰቃየን።” ገጽ 132

“ ‘መልካም ወጥ አምጪ አለኝ መልካም የት ተገኝቶ፣ ቀድሞ በጤና አዳም ሳይሰራ ቀርቶ።’ ማለትን እያሰብን በኢትዮጵያ ታሪክ ተሰምቶና ታይቶም የማያውቀውን ስደትና መከራ ለመቀበል ኃይልና ብርታቱን የሰጠንን አምላክ አሰብን፤ አመሰገንን።” ገጽ 132

በቀጣዩ ክፍል አርበኛዉ የሱዳን ስደታቸውን በተመለከተ አንዳንድ ጉዳዮችን ቀጥለውም ከአጤ ኃይለስላሴ ጋር የተጻጻፏቸውን ደብዳቤዎችም ያጋሩናል።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 26 Sep 2019, 04:05
by Meleket
የአርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእን የሱዳን የስደት ቆይታና ለአጤ ኃይለስላሴ ወደ ለንደን ከላኳቸው ድንቅ መልእክቶችና ብርቱ የትግል ጽናታቸውን የሚያሳይ የማጽናናት ምክራቸውን ለዛሬ እንጋራለን። መልካም ንባብ።

“ከክቡር ከዐዋቂው ራስ እምሩ ጋር ሳልታዘዝ በፈቃዴ ትግሬ ሺሬ ዘመቻ ዘምቼ ሳለሁ የመኳንንቶቻችን እውነት የሌለበት ልግመትና ጠላት እየጐለመሰ መሄዱንና ረዳቶች መንግሥታት ማግኘቱን ከጣሊያን እሥረኞች በብዙ ተገነዘብሁት። ምንም እንኳ የጣሊያን መንግሥት በኢትዮጵያ ገዥ ሆኖ ብዙ ጊዜ ለመቆየት አለመቻሉን ብረዳውም፣ ባለቤቴንና ልጆቼን ምሕረት ለሌለው ጠላቴ ለጣሊያን ጥዬ፣ ወይም ይዜ ከተወለድኩበት በሰው ሀገር የሰው ቤትና የሰውን ንብረት እየዘረፍሁ ለመመገብ ፈጽሞ ኅልናዬ ስለማይፈቅድልኝ፣ ከነቤተሰቤ ስደት መሰደዴን መረጥሁ። ያለ አንዳች ተስፋና ሥራ ሱዳን መሰደዴንም ለኢትዮጵያውያኖች ብቻ ሳይሆን ሁሉንም ኅዘን ሳያሳዝን አልቀረም።” ገጽ 133

“ለሞላው የዓለም ሕዝብ ትልቅ ተስፋና መሰደጃ የነበረው ንጉሠ ነገሥትና ሕዝብ ስደት መሰደድ ደረሰበት የተባለበት ምክንያት ማስረጃ፦ በዐረብ ሀገር ነብዩ መሐመድ እንኳ ሳይቀር ጠላቶቹ በተነሱበት ጊዜ ልጁ ሩሁያንና አጐቱን አድርጎ ከብዙ የዐረብ ስደተኞች ጋር ጉድለት በሌለበት እምነቱ ወደ ጥንታዊ ወደ ትልቁ የአክሱም ንጉሠ ነገሥት በቀጥታ ላካቸው። የነብዩ መሐመድ ባላጋራ የሆነው አቡ ተይብ ቁሮሽ የተባለውም የነብዩ መሐመድ ስደተኞች ከአኩሱማዊ ሕዝብ ጋር በብዙ መወዳጀታቸውን ስላወቀ በማስገደድ ስደተኞቹን መልሰህ ወደኔ ላክልኝ ብሎ በዚያን ጊዜ በአኹሱም ንጉሠ ነገሥት አልጋ ላይ ወጥቶ ለነበረው ኤላም ተሣሐም ጥያቄ ቢጠይቀው ጥያቄውን ምንም ሳይቀበለው ዝም ብሎ ቀረ።” ገጽ 133

“የአኩሱምም ን.ነ. ኤላም ተሣሐም የተባለው በማናቸውም የመካ መድና ስደተኞች ነገር ውስጥ ለመግባት ምንም አልፈቀደም። ስለምን ኢትዮጵያን ተማምነው በስደት የመጡበትን የዐረብ ስደተኞች በማናቸውም ጊዜ እምነታቸውን ስላላጓደለባቸው፣ እነሱም በኢትዮጵያ ን. ነገሥትን መኳንንቶቹ፣ በሀገሩም ሕዝብ ያደረጉትን ተስፋ በደስታ ስለተፈጸመላቸው እጅግ ተደሰቱ። በዚሁም ታማኝነትዋ ነብዩ መሐምድ ኢትዮጵያን እንዲህ ብሎ አመሰገናት መረቃትም። “ከጣዖታዊ አምልኮ የራቀች ኢትዮጵያ ንፅህት ሀገር ናት፤ ክርስቲያኖችም ለእስላሞች የሃይማኖት ጉዳይ ሳያነሱባቸው፣ የርኅራሔ መልካም ሥራ ስለሠሩላቸው እውነተኞችና ለጋሶች ነገሥታት ይንገሱብሽ” ብሎ አላት።” ገጽ 134

“ለአኩሱም ንጉሠ ነገሥት ለኤላ ተሣሐም የነፃነት ወዳጅ፣ ትዕግሥተኛ ነው ተብሎ በዐረቦች ዘንድ የምስጋና ሕያው ታሪክ ተጽፎለታል። ከእነዚሁም የነብዩ መሐመድ ስደተኞች ብዙዎቹ በ፮፻(መተኞቹ -ሰነዱ ፎቶ ኮፒ ሲነሳ ከአናቱ ስለተቆረጠ በትክክል ለማንነበብ አልተቻለም) በደስታ ወደ ሀገራችው ሲመለሱ ሌሎች በኢትዮጵያ እስላሞች ክርስቲያኖችም ሆነው በገነትዋ ኢትዮጵያ ቀሩ።” ገጽ 134

“ከ፲፰፹፰ ዓ.ም. በፊትና ከዚያም ወዲህ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ብዙ እንግዛህ የሚሉት ጠላቶቹ እንደተነሱበት እያወቀ በየጊዜው ለእነዚህ ጠላቶቹ መሬቱን እየቆረሰ ከመስጠቱና ሕዝቡንም በደምብ ካለማስተዳደሩም በላይ በቸገረው የመከራ ሰዓት ሊረዳው ምንም ከማይችል እጅግ ሩቅ ከሆነው ምሥራቃዊ የጃፓን ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ጋር ወዳጅነት ለመመሥረት ሞከረ። እንደገናም በ፲፱፻፳፪ ዓ.ም. የዘውድ ምረቃ ብሎ “የምድር ገነት” የሆነችዋን ኢትዮጵያን አበባና ፍሬም ለብሳ እጅግ አምራ በተጎናጠፈችበት የጥቅምት ወር ለዓለም መንግሥታት ራሱ ጠርቶ ፍሬያምነትዋን በማሳየቱም ከፍ ያለ ቅናት ቀኑበት። ፈጥነውም ዕለቱን በኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ላይ ተመካከሩበት።” ገጽ 135

“በዚሁ ጥልቀኛው፣ ጨካኝ ቅናታቸው ብዛት የተነሳ ኢትዮጵያን የግላቸው ለማድረግም ሲሉ የጠበቀ ምክር መከሩ፤ ፈጽመው ለመደምሰስም በጦርነት ተነስተው ተረዳዱባት። ዳሩ ግን ከሰማያዊ አምላክ ካልታዘዘ በቀር ምን ጊዜም በሰብአዊ ኅሳብ የሚፈጸም አንዳች ነገር እነሌለ ያልተገነዘቡት ኢጣሊያኖች ለኢትዮጵያ ሕዝብ ማጥፊያ በከንቱ ቁጥር የሌለው መሣሪያና መርዝ አሰናዱ። በእግዚአብሄር ሰፊ ቸርነት ዙሪያዋን ከከበቡዋት አረመኖች ነፃ ሆና የምትኖረዋን ጥንታዊት ኢትዮጵያን በጭራሽ ነፃነትዋን አስረክባ ለአረመኔው የፋሺስት መንግሥት ተገዥ እንድትሆነው በማሰቡ በአዋቂዎች ዘንድ ከዕብድነት ተቆጠረበት።” ገጽ 135

“የኢትዮጵያ ን.ነ. አጼ ኃይለ ሥላሴ ሎንዶን፣ አልጋ ወራሽና መኳንንት ኢየሩሳሌም፣ የተቀረውም ሕዝብ ግብፅና ጂቡቲ በሚያዝያ ወር ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ሲሰደዱ እኛም በ፲፱፻፳፱ ዓ.ም. ሱዳን ተሰደን በንዳድ ወድቀን ተጨነቅን።” ገጽ 135

“ ለግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ - ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ሎንዶን - ሕያው እግዚአብሔር እንኳን ከመዓቱ አወጣዎት፤ ለጤናዎስ እንደምን ከርመዋል? . . . ግርማዊ ሆይ። በህዳር ወር ፲፱፻፳፮ ዓ.ም አምቦን የጐበኙ ጊዜ ግርማዊነትዎ ፊት ቀርቤ ባለጋሮቻችን መነሳታቸውን የሴቶች ጭካኔ ይዘው በወጋዴንና በአሰብ፣ በአሥመራና በዓዲግራት መቀለ፣ በአሥመራ መረብ ዓድዋ መቀለ፣ ከአሥመራ በሠቲትና በጎንደር እስከ ጐጃም ደብረ ማርቆስ በ፬ቱ መአዘን በኩል ተዘጋጅተው መምጣታቸውንና እኛም እነሱን ለመቃወም በነዚህ ጠረፎች ላይ ብርቱ ጦርና ምሽግ፣ ሥልክና ራዲዮ ማቆም፣ ለሠራዊታችን ስንቅ የሚሆን እህል በየአውራጃው መሰብሰብና ወፍጮ አቁሞ ማስፈጨት፣ ወታደሩም ሁሉ በኤውሮጳ ሕግ መሠረት ልክ የደመወዝና መሣሪያ፣ ልብስና ምግብ እንዲሠጠው ያስፈልጋል።” ገጽ 136

“ደግሞ በ፲፱፻፳፰ ዓ.ም. ወር በጦርነቱ ውስጥ ሆነን በዳባት ሥልክ በኩል መቀለ ያለውን ፫፻ሺ ሠራዊታችን ጠላትን ሳይገጥመው በመቆየቱ ብርቱ ስንፍና የሚያመጣብን ሆኗል። ፫ኛ ጦርነቱ ይቆይ ብለዋል እያሉ ሰንፈው ሰውን የሚያሳንፉ ፈሪዎችና ፖለቲከኞች ሁሉ ስብከት መስበካቸውንና ለንጉሠ ነገሥት የጦርነት ድግስ ማቆየት አለማስፈለጉን፣ ፬ኛ ከሠቲት አንስቶ ሽሬ ድረስ ያለውን የኛው ግምባር እጅግ ሰፊና ረጅም ስለሆነ ለወልቃይትና ለሺሬ ተጠባባቂ ጦር በፍጥነት ማዘዝ ግዴታችን መሆኑን ለግርማዊነትዎ አሳስባለሁ እያልኩ የሳለፍሁለዎትን ደብድቤዎችና ቴሌግራሞች፣ ከዚህም ሁሉ አንዱ እንኳ ባለመፈጸሙ ምክንያት ጠላትም አንድ ጥይት ሳይተኮስበት በሰቲት ጎንደር መግባቱ እጅግ ያሳዝናል።” ገጽ 137

“ቢሆንም በእግዚአብሄር ኃይልና ቸርነት ጠላቶቻችን አልቀው ሀገራችንን ቶሎ ለቀው በመሔዳቸው(ስለሚሄዱ) ነፃነትዋን ያለ ጥርጥር ታገኛለች፤ ነገር ግን የዋሁ ሕዝባችን እርስ በእርሱ ስምምነትና አእምሮም አጥቶ እንደገና ተመልሶ በሌላ ሰው እጅ እንዳይገባ ባርነቱም ለዘለዓለም ሆኖ እንዳይቀር ዛሬ ጠንክሮ መጣጣር ያስፈልጋል። ያሳዝናል።” ገጽ 137

“ጃንሆይ! ዛሬ ግን የኢትዮጵያ ሕዝብ ወረቱ ስላለቀበትና ጨካኝ የሆነውን የጠላት ልዩ ልዩ ቀንበርና ሞት፤ ብርቱ እሥራትና ግርፋት ውርደትና ስድብ መንከራተትም ስላዘነበበት ነድዋል። “ይህም ሁሉ የመጣብን የፈጣሪያችንና የመንግሥታችንን ትእዛዝ ባለመፈጸማችንና ነፃነታችንን በመጣላችን ምክንያት ነው መዓት የመጣብን” እያለ በኅዘንና በጸጸት ፊቱን አዙሮዋል፤ ጨክኖም ከጣሊያን እየሸፈተ በየሀገሩ ተበታትኖ የሚተላለፈውን ጠላት ሌት ተቀን አደጋ እየጣለ መፍጀቱን በቅርብ ቀን የመጡ ሰዎች ያረጋግጣሉ።” ገጽ 137

ጎንደር በሠቲት መንገድ አርማ ጭሆ ላይ አንድ ኮሎኔል ከነጦሩ በድል ፈጽመው ስለበታተኑት ብዙ ብርና ባንክ ኖት በየሣጥኑ እንደተሞላ ቁጥር የሌለውም ብረትና ጥይት የሀወሣ አርበኞች ስላገኙበት በብዙ ተደስተዋል።” ገጽ 137

ዳግሞ ቋራ ላይ የነበረውን የጠላት ጦር ፈጸሙት፤ ሀገራችንን በእጃቸው አደረጉዋት። ደጃዝማች ኃይሉ ከበደ ሰቆጣን አላስረግጥም ብለው እየተዋጉት ኮረም ላይ ለነበረው ጠላት አደጋ በመጣል ወንድነታቸውን አሳዩት፤ ያሳዩታልም።” ገጽ 137

በትግሬ ወጣቱ ደጃዝማች ገብረ ህይወት ብዙ ቀን በስውር እየገጠሙት ስላጠቁት ጠላትን አሸብረውታል። ለ፭ት ዓመት የሚበቃቸውን ስንቅና መሣሪያ ጥይትም ማረኩት፤ ሀገሬውም አቅፎዋቸዋል። ደጃዝማች ወንድ ወሰንም በላስታ አንድ ቀን ጉድ አድርገው ወጉት፤ ሁለተኛ አልተመለሰባቸውምጐበዝ የተባለ ሁሉ የጠላትን ልብ ልክ ሰልሎ ስላወቀውና ስንፍናውንም ስለተረዳው በብረት ይቅርና በሰንጢና በቢላዋ አንገት አንገቱን ከመቁረጥ፣ ሆዱን ከመዘርገፍ ኣላቋረጠም ይባላል። ስለዚህ የጠላታችንም ሰዎች ብርቱ ረሐብና ጭንቅ ስለበዛባቸው ፫ና ፭ ወርም ቀለብ የማያገኙ ስለሆኑ እንኳንስ የሀገር ተወላጅ ይቅርና ነጮቹ ሳይቀሩ ብስጭት ከቦዋቸዋል፤ ሲያዙም መሞታቸውን ስላወቁት ወደ ሱዳንና ኬኒያ መክዳታቸው በይፋ ይወራል።” ገጽ 138

በተንቤንና በሺሬ፣ በመረብና በዓጋሜ ደም ዛሬም ይፈላል፤ ክረምት ጀምረው በብርቱ መዋጋታቸውንና የኢትዮጵያ ወጣቶች ተሰብስበው ስለ ነፃነታቸው መዋጋታችውን በግልጽ ራሱ ጠላታችን ያወራል። ስለዚህ በካርቱምና በጂቡቲ፣ በናይሮቢና በጁባ፣ በኮንጐም በኩል ለስደተኖች የሚያጥናና የግርማዊነትዎ የተስፋ ቃል በፍጥነት ቢልኩላቸው፣ በእነዚህም ሀገሮች ሰዎች ተልከው ቢጠይቁዋቸው ብርቱ የወንድነት ሥራ ይሠሩ ነበር። ግርማዊ ሆይ ነገሩም በብዙ መልካም ነውና አጥብቀው ያስቡበት። የካቲት ፩ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም ካርቱም። ፊርማ ታማኝዎ ተስፋ ሚካኣኤል ትኩእ።” ገጽ 138”

በቀጣዩ ክፍል አርበኛው ከሱዳን አጤዉም ከለንደን የተጻጻፏቸውን አንዳንድ መልእክቶች እንጋራለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 14 Oct 2019, 10:06
by Meleket
አርበኛው አቶ ተስፋሚካኤል ትኩእ ከሱዳን አጤዉም ከለንደን የተጻጻፏቸውን አንዳንድ ቀጣይ መልእክቶች ለግንዛቤና የዚያን ወቅት የፖለቲካ ትኩሳት ለማጤን እንገረምማቸዋለን። :mrgreen:

“ለግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ፣ ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ፣ ሎንደን። ጃንሆይ፡ ክቡር ራስ እምሩ ካርቱም ወርደህ ጠብቀኝ ብለው ከላኩኝ በኋላ በመንገድ ሳለሁ ልጅ ፈቃደ ሥላሴ ከጃንሆይ ዘንድ ባመጣው ደብዳቤ ምክንያት ቀሩ ማለትን ብሰማ ከተበተነና ምክሩም ከፈረሰ ብኋላ በመሆኑ ስገረም ተያዙ ማለትን ብሰማ ምንም ኣላመንሁም። ስለምን? የጠላታችን የጣሊያን ወሬ ሁሉ የውሸት ውሸት ስለሆነ ነው እማላምነው። - - - - - “ ገጽ 138

“ - - -በሙሴ ባርላሲና መርዝና ፖለቲካ የተነደፉና የተመረዙ ፊተውራሪ ወሰንና ፊታውራሪ ዮሐንስ ጆቴ ደጃች ሙስታፋም ሆነው ደጃዝማች ሸክ ሸጐለን መደብደባቸውንና የልጆቻቸውን ልጆች ከብዙ ሰው ጋር ገድለው ንፁህን ደም በማፍሰሳቸው ያላለቀሰ ሰው የለም። ብላታ ደረሣ ኣመንቴና ባላምባራስ አሸብር ገብረ ሕይወት ከብዙሰው ጋር በርሰሪሰ ዘልቀዋል። - - -ኢትዮጵያ ተመልሳ በሕይወት በደስታ ለመገኛኘትና ጫዋዎን ለመሣም ያብቃኝ፣ ኣሜን። ካርቱም የካቲት ፩ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም.” ገጽ 139

“ለግርማዊ ጃንሆይ፡ ሎንዶን። ከየቦታው ዛሬ የደረሰኝ ወሬ ይህ ነው። በማጅ እስከ ዛሬ ድረስ የኢትዮጵያ ባንዴራ እንደተተከለች ናት። ትግሬ ደጃዝማች ካሣ ስብሐትና የሐማሴን አርበኞች አብረው ዓጋሜ ስር ተጠግተው ወደ ደጋው ትግሬ እየተመላለሱ ብርቱ ሥራ ይሠራሉ። በዚሁ ሰሙን ዓድዋ ላይም ብርቱ አደጋ ጥለው ፈጻጽሙት፤ በኣውቶሞቢልም መተላለፍ ጠላት አልተቻለውም።” ገጽ 139

“መቀለ ትልቅ ምሽግ በአደጋ አፈረሱበት፤ ጎን ላይም 4ቱ ጄኔራሎች ብቻ አስተኝተዋቸዋል። በአዲስ አበባ ጄነራል ግራሲያኒም እጅግ ጠግቦዋል። ቀኛዝማች ሰለባና ቀኛዝማች አስፍሐ ባህታ፣ ፊታውራሪ ፀጋይ ንጉሠ አዲስ አበባን በስውር እያስሰለሉ ሲሠሩ ከርመው አሁን በቅርቡ አሩሲ ተሻግረው ጠላትን በድፍረት ያስለቅሱታል። ይፈጁታልም።” ገጽ 140

“የልጅ ኢያሱ ልጅ ነኝ የሚል ቴዎድሮስ የሚባል የጐጃም ደንገል በርላይ ተዋግቶና ሠርቶም ከተያዘ በኋላ በአረዮጵላን ወስደው ሐማሴን ውስጥ ደብረ ሲና ከሚባለው ቦታ አስረውታል። የኢትዮጵያ ልጆች ግን በእውነት ከእንቅልፋቸው በትክክል ተነስተዋል፤ ጠላትም በብርቱ ተጨንቆዋል ብሎ ዛሬ ከኢትዮጵያ የመጣ ሰው ምስክርነቱን አረጋገጠልኝ። ጃንሆይ ኢትዮጵያ ሙሉ ነፃነትዋን እምታገኝበት ቀን ቀርቦዋልና ከእግዚኣብሔር እድሜ ብቻ ይለምኑ። ካርቱም የካቲት ፱ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ፌርማ፣ ታማኝዎ ተስፋሚካኤል ትኩእ።” ገጽ 140

“ጃንሆይ ሎንዶን፡ - - - አንድ ግሪክ ላንድ ጣሊያን ነገር ሲያዋጣው እንዲህ ብሎ ጥያቄ ጠየቀው “እናንተ ጣልያኖች ኢትዮጵያን ያዛችሁዋት፣ ንጉሠ ነገሥትዋም ከሀገራቸው ወጥተው ተጥለው ቀሩ” ብሎ ቢለው፣ እንዲህ ብሎ መልስ መለሰለት። - - - “አጼ ኃይለ ሥላሴ በኢትዮጵያ ሆነው ከሚዋጉን ጦርነት አብልጠው በኤውሮጳ ሆነው ይወጉናል፤ ያስወጉናልም። ስለምን በኢትዮጵያ ተራሮች ላይ የሚተከሉ ትልልቅ መድፎች ለመግዛት ከጀርመን መንግሥት ጋር ተስማምተን የነበረውን ስምምነት የጢማሙ ያጼ ኃይለሥላሴ ብርቱ ፖለቲካ አፈረሰብን። ጀርመንም ጣሊያንን ስለረዳሁ የዓለም መንግሥታት ጠልተውኛልና አልሰጥህም ብሎ ከለከለን፤ ይህም ሁሉ የአጼ ኃይለ ሥላሴ ውስጣዊ የተሰወረ ሥራ ነው፤ ሰውየው በፖለቲካ ዓይቻሉም፤ በገንዘብም ቢሆን ከሁሉ ይበልጣሉ። የኢትዮጵያ ሕዝብ ምንም ኣይገዛልንም፤ ጦርነት መጀመራችንም ስህተታችን ነው” ብሎ መለሰልኝ ሲል ምስክርነቱን ገለጸልኝ።” ገጽ 141

በጦርነቱ ሰዓት አጼ ኃይለ ሥላሴን ለመርዳት ከኤርትራና ከሶማሊያም ጀኔራል ግራሲያኒን እየከዱ የመጡት የኤርትራ ሰዎች ዛሬ ስላስቸገሩት የከዱትን ሰዎች ልጆች እየተፈለጉ ከኣሥመራ ሰብስበው ዓድዋ ላይ የጭከና መጥፎ ሥራ እንዲሠራባቸው ብሎ ብርቱ ትእዛዝ አሳልፎ ከአሥመራ በካሚዮን ፯፻ ልጆች ዓድዋ ወስዶ የአረመኔ ክፉ ሥራ የሠራ መግደሉ ከብዙ ሰዎች አፍ በይፋ ተረጋግጦ ስለተወራ በከንቱ መገፋታችንንና መሞታችንን ለዓለም መንግሥታት ሁሉ የሚያስጮህና በብዙ የሚያከራክር ስለሆነ በጉዳዩ ያስቡበት። በጂቡቲም ያለው የኢትዮጵያ ቆንሱልና ስደተኞችም ጭምር ብዙ መከራ መቀበላቸውንና በብዙ መታወካቸውን እንሰማለን። - - ካርቱም መጋቢት ፲፩ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ታማኝዎ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ” ገጽ 141

“ሞዓ አንበሳ ዘእምነገደ ይሁዳ፡ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ፣ ሥዩመ እግዚአብሔር ንጉሠ ነገሥት ዘኢትዮጵያ ይድረስ ከተስፋ ሚካኤል ትኩእ። እንደምን ሰንብተሃል? እኛ በእግዚአብሔር ቸርነት ደህና ነን። የጻፍከውን ወረቀትና የላከውንም ፎቶግራፍ አየነው። በአሁኑ ግዜ በኢትዮጵያና በዜጐቻችን ላይ ከደረሰው መከራ በቀር፤ ከዚህም የበለጠ የሚያሳዝነን ነገር የለም። አሁንም ለችግርህ ለጊዜው ፴ ሰላሳ የእንግሊዝ ጊኒ በሚድላንድ ባንክ በኩል ልከንልሀልና መድረሱን እንድትጽፍልን ይሁን። ጥር ፳፮ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. በኢትዮጵያ፤ ሎንደን። በባለዘውዱ ማኅተም የታተመ ደረኝ።” ገጽ 142

ብቀጣዩ ክፍል አርበኛው ኣቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ ከአቶ ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ ጋር የተጻጻፏቸውን ደብዳቤዎች እንመለከታለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 25 Oct 2019, 03:10
by Meleket
ያርበኝነቱ ዘመን ታሪክ ይቀጥላል፡ ለዛሬ በዚያ በቀውጢዉ ሰዓት ሆድአደር ባንዶች ከፋሽስት ጋር ወግነው ንጹሐን ዜጎችን ያጠቁ በነበረበት ወቅት፡ ኢመይል ባልነበረበት ወቅት :lol: አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ በሱዳን፡ አቶ ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ ደግሞ ከንጉሠነገሥቱ ልዩ ጽሕፈት ቤት ከሎንደን የተጻጻፏቸውን አንዳንድ ደብዳቤዎች የዚያን ግዜ የፖለቲካ ትኩሳት ለማጤን ይቻል ዘንድ እንጋራው እስቲ! መልካም ንባብ። :mrgreen:

“ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ። እንደምን ሰንብተሃል፤ እኔ ለጤናዬ ብቻ ከወደቀብኝ መከራ በቀር እግዚኣብሔር ይመስገን ደህና ነኝ። ላቶ መብራህቱ ሎረንሶ የጻፍከውን ደብዳቤ አሳይቶኝ ስለችግርህ እጅግ ኣዘንሁ፤ ጃንሆይም የጻፉልህ ደብዳቤና የላኩልህ ፴ ፓውንድ እስካሁን ሳይደርስህ አይቀርም። አሁንም በካርቱም ላላችሁት ስደተኞች ጃንሆይ ማሰባቸው አልቀረም። ዳግም ዛሬ የተቻለውን ያህል ለሌሎቹ ገንዘብ ተልኮላቸዋል። ዝርዝሩም ስማቸውና አድራሻቸው ባቶ ገብረ መስቀል በኩል ተልኮዋልና እርሱ ወረቀት ሲፅፍ የእያንዳንዱን ሰው ደረሰኝ እየተቀበለ እንዲልክልኝ ሳላስታውቀው ስለቀረሁ አሁን አንተ እንድታስታውቀውና ደረሰኙን እንዲልክልኝ አደራ እንድትልልኝ። አንተም የራስህን ከዚህ ቀደም ለተላከልህ ገንዘብ ደረሰኙን ላክልኝ። አቶ መብራህቱ ታእዛዝም ደብዳቤ እጽፍልሀለሁ ብሎዋል፤ በሕይወት ይግጠመን። የካቲት ፳፩ ቀን ፲፱፻፳፱ ዓ.ም. ሎንዶን። ፊርማ ወልደ ጊዮርጊስ።” ገጽ 142

“ይድረስ ከክቡር አቶ ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ ሎንዶን። እንኳን እግዚአብሄር ከመዓቱ አወጣዎት። ለጤናዎስ እንደምን ከርመዋል? እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን እኔ ደህና ነን፤ በናንተ ኅዘንና ርዳታም ጭንቁና መከራው አልፎ የምንደሰትበት ቀን ሣይመጣልን ዓይቀርም። የካቲት ፲፩ ቀን ያጻፉልኝ ደብዳቤ፤ እግዚአብሔር ይስጥልን። ባቶ ገብረመስቀል በኩል ገንዘብ ስለተላከላቸው ሰዎች የእያንዳንዱ ሰው ደረሰኝ ተቀብሎ እንዲልክልዎት ነግሬው አለሁ። እሱም ከካርቱም ውጭ የወጡ ሰዎች እስኪመለሱና እስኪፈርሙለት ነው እንጅ እልካለሁ ብሎኛል፤ ደግሜም አስታውሰዋለሁ። ያቶ መብራህቱ ታእዛዝ ደህንነት ስለጻፉልኝ በብዙ አመሰግንዎታለሁ፤ ከዚሁ ጋር እምልከውን ማስተዋሻና ሰላምታዬም ጭምር ለግርማዊ ጃንሆይ እንዲያቀርቡልኝ እለምንዎታለሁ። በሕይወት ለመገናኘት እግዚአብሔር ያብቃን፤ አሜን። መጋቢት ፲ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ካርቱም ተጻፈ። ፌርማ፣ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ።” ገጽ 143

“ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል ካርቱም። እንደምን ሰንብተዋል እኔ በእግዚአብሔር ቸርነት ደህና ነኝ፤ በሐምሌ ፲፫ ቀን የጻፉልኝ ደብዳቤና ከዚህ ደብዳቤ ጋር የላኩት የሐጂ መሐመድ ዓማን ደብዳቤ ስለ ደረሰኝ ወደ ጃንሆይ አቅርቤው ነበርና ለሐጅ መሐመድ የተጻፈውን ምላሽ ከዚህ ጋራ ስለላኩለዎ እንዲሰጡዋቸው እለምነዎታለሁ።” ገጽ 143

“- - - በየቀኑ እየበረሩ ካርቱም የገቡት ነጮች ብዙ ናቸው ስላሉት፣ እነዚህ ነጮች በኢትዮጵያ የነበሩ የውጭ ሀገር ሰዎች ናቸውን ወይስ ጠላቶቻችን ራሳቸው ናቸው። ስለዚህ ለይተውና፤ ደግሞ የተቻለዎትን ያህል ስማቸውንና ቁጥራቸውን ጨምረው በቶሎ እንዲልኩልን እንለምንዎታለን። እጅግ የሚጠቅመን ይሆናል፤ ዝርዝራቸውን ማወቅ። - - - ፌርማ ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ” ገጽ 143

“ይድረስ ለክቡር ወዳጄ አቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ፡ ለጤናዎ እንደምን አሉ? እኔ በእግዚአብሔር ቸርነት ደህና ነኝ። ለጃንሆይ የጻፉት ለእኔም በ13/3/38(ለመጀመርያ ጊዜ በፈረንጅ አቆጣጠር መጻፋቸው ተጢኗል) የጻፉልኝ ደርሶዋል፤ ጃንሆይም ተመልክተውታል። ስለዚህ ቀጥሎ ያለውን እንድጽፍልዎት አዘውኛል። ገጽ 144

“፩ኛ ጠላታችን ለሕዝቡ የሚጥለውን ወረቀት ለመቃወም እንዲቻል ቃሉን ማግኘት ያስፈልጋልና ሲሆን ዋናው እንዳለዎ አለዚያ ግልባጩን እንደተቻለ በቶሎ ቢልኩልን።

፪ኛ የአዲስ አበባ ራዲዮ መዘጋቱን፣ አርበኛውም መዋጋቱን ስለሰማን እዚህ ለሥራ እንዲያገለግል ለማድረግ እንዲቻለን ማስረጃ ጭምር የሚያውቁትን ያህል በዝርዝር እንዲጽፉልን አደራ እልዎታለሁ።

፫ኛ የቆሰለው ጋስፓሪኒ መሆኑን የነገሩዎት ከሰዮ የመጡ ሰዎች አስፋፍተው ቢጽፉልን። የሞቱትንም ኦፊቻሌ ስማቸውን ለማወቅ የሚቻል ቢሆን እጅግ መልካም ነበር።

፬ኛ አቶ በለጠ ሣህለ ሚካኤል የተባለውን ከዚህም ቀደም አልሰማንም ነበር፤ ነገሩ ምን እንደሆነ ያመጣውም ወረቀት የማን እንደሆነ አጥርተው ቢጽፉልን የተላከውስ ከነማነው?

፭ኛ ከወሎ የመጣው ሰው ስሙ ማን ይባላል? ምናልባት የምናውቀው እንደሆነ ለመረዳት ነው።

፮ኛ የደጃዝማች ገብርሕይወትና የደጃች ኃይሉ ከበደ ወሬ እጅግ ደስ የሚያሰኝ ነው። ከነርሱ ዘንድ እንደዚሁ እንደ በለጠ ተልኮ የመጣ የማናውቀውና ያልሰማነው እንዳለ ወሬውንም ያገኙበትን ጨምረው ለጃንሆይ ቢጽፉላቸው ደስ ይላቸዋል። ወደነርሱስ ለመድረስ የሚችል ሰው ለማግኘት ይቻላልን?

፯ኛ አቶ መኮንን ደስታ ከጐጃም መንገድ በዚሁ ሰሞን ይገባል ያሉት ምናልባት በመልእክት እንደሆነ የሚመጣው፤ ደግሞ ጊዜ አለፈ እንዳያሰኝ በቶሎ የነገሩ አኳሆንና ምክንያት ለጃንሆይ ቢላክላቸው እጅግ መልካም ነው።” ገጽ 144

፰ኛ ወደ ሱዳን እየሸሱ ስለገቡት ኢጣሊያኖች አሁን ሊሰልሙ ነው ያሉት ከዚህም ቀደም በዚያ በኩል የገቡትን ስለጻፉልን የተቻለ ያህል ስማቸውንና ማዕረጋችውን ጨምረው እንዲጽፉልን ጽፈንልዎ ነበር። መቸም እንደሚያውቁት እዚህ በፈረንጆች ዘንድ የፖለቲካም፣ የፕሮፓጋንድም ሥራ ለመሥራት እውነት ነው ብለው እንዲያምኑ ጥቃቅኑን ሁሉ አጠራቅሞ ማስረዳት ያሳምናቸዋል፤ ነገር ግን ነገሩ እውነት ሆኖ ሳለ ዋናውን ጉዳይ ብቻ ብንናገር ዓይንና ጥርስ ካልተጨመረ እያሉ እያቀለሉ አስቸግረውናል። ስለዚህም ከዚህ ቀደም አሳስቤዎ ነበር። አሁንም አደራዎን። የኛን ችግር እዚህ ሆነው ባያዩት ነው እንጂ የሚገፉበት ነገር ሲገኝ ዛሬ ማን ችላ ይላል። እግዚኣብሔር በሕይወት ይግጠመን። ሎንዶን፤ መጋቢት ፲፪ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ፊርማ ወልደ ጊዮርጊስ ወደ ዮሐንስ” ገጽ 145

“ይድረስ ካቶ ተስፋ ሚካኤል እንደምን ሰንብተዋል ለጤናዎ። እኔ እግዚኣብሔር ይመስገን ደህና ነኝ። በመስከረም ፴ ቀን ወደ ጃንሆይምወደኔም የጻፉት ደብዳቤ ደርሶዋል። የስደተኞችንም ዝርዝር አሳምረው ጽፈው ስለላኩት አመሰግንዎታለሁ። “ ገጽ 146

“በኬንያ በኩል ላሉት ስደተኞች በርስዎ በኩል የተላከውን አኳሆን የሚገልጥ ማስረጃ ተጽፎ እንዲላክ ስላስታወሱት በነገሩ ሳይታሰብበት አልቀረም ነበርና አሁንም የኢትዮጵያ ጉዳይ የደረሰበትን አኳሆን ባጭሩ የሚያስረዳ ዝርዝር ማዘጋጀት ስለተጀመረ በሱዳን ላላችሁትም በቅርብ ጊዜ ሳይደርስ አይቀርምና እርስዎም ይደርስዎታል። እስከዚያው ድረስ ከዚህም ቀደም እንደጀመሩት ስደተኞቹን በምክር እንዲያጽናኑዋቸው በሱዳን ያሉትን ረዳቶቻችን የሆኑትን ወዳጆቻችንን እንዳያስቀይሙ እንዲመክሩዋቸው ያስቡበት። ላቶ መብራህቱም ሰላምታዎን አድርሻለሁ፤ ጥቅምት ፲፪ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም. ሎንደን ተጻፈ፡ ፊርማ ወደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ።” ገጽ 146

“ይድረስ ለክቡር ወዳጄ አቶ ተስፋ ሚካኤል ትኩእ። እጅጉን እንደምን አሉ፤ እኔ እግዚአብሔር ይመስገን ደህና ነኝበመጋቢት ወር የጻፉልኝ ደብዳቤዎ ደረሰኝ፤ የተቻለዎትን ያኽል በዝርዝር ስለጻፉልኝ አመሰግነዎታለሁ። የሚገኘው ነገር በዝርዝር ቀኑ፣ ቦታው፣ የሰው ስም እየተጨመረ፣ እየተጣራ ይጻፍ ብዬ ያስቸገርኩዎ እዚህ የምንነግራቸው ሰዎች ዝርዝር ሲያጡበት እኛ የምንፈጥረው እየመሰላቸው ስላስቸገሩን ነው። ይህንንም ባለፈው ደብዳቤዬ ስለጻፍኩልዎ ነገሩን ስለተረዱት ደስ አለኝ።” ገጽ 146

“መቸም ሰው አምላኩና ግዜው እንደሚፈቅድለት መጠን የተገባ መስሎ የታየውን መፈጸም፣ ይልቁንም ለእኛ ለሁላችን ያችን የመሰለች አገር ላጣን የምንገደድበት ዋና የተገባ ሥራችን ስለሆነ መጣራችን አልቀረም። አሁንም ምንም ግራና ቀኝ ክፉወሬ ቢወራ ልባችንን አለመግደል ነው። ፈቃድና መቁረጥ የማያሸንፈው የለም፤ እንደ ጉዳዩ መጠን ግን ግዜ ይጠይቃል፤ ጊዜም ዋና መሣሪያ ነው።” ገጽ 146

“የንጉሠ ነገሥታችንም አሳብ በዚሁ የጠና ነው፤ ያለብን ጉዳይ የ፳፬ ሰዓት ያልሆነ የብዙ ሺ ትውልድ ጉዳይ መሆኑን አንዘንጋ። ይህም ጊዜ ከድቶን የተናደውን ለመገንባት ጽናትና ፈቃድ ያስፈልጋል። ስለዚህ የማይለወጥ የለምና ዋናው ነገር ልብን ማጽናት፣ ተስፋ አለመቁረጥ ነው። ወደፊትም እንደዚሁ በተቻለዎ ወንድሞችዎን ያበርቱ፣ እርስዎም ይበርቱ። አቶ ሎረንሶ ታእዛዝ ደና ነው። ያለውም እዚሁ ሎንዶን ነው። በሕይወት ይግጠመን። ሚያዝያ ፮ ቀን ፲፱፻፴ ዓ.ም፨ ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ልዩ ጽሕፈት ቤት። ፊርማ፣ ወልደጊዮርጊስ።” ገጽ 146

በቀጣዩ ክፍል አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ “ከባለቤቴና ልጆቼ ጋር በእንግሊዝ መንግሥት ተገድጄ ከካርቱም ገዳሪፍ መሔዴ” በሚል ርእስ ያካተቱትን የምዕራፍ ሠላሳ ትረካቸውን እንኮመኩማለን።

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።
:mrgreen:

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 07 Nov 2019, 03:12
by Meleket
የኒህን ቆፍጣና አርበኛ ታሪክና እሳቸው ያሞገሷቸው፡ ለፋሽስት ጣልያን ባንዳ አንሆንም እምቢ አሻፈረኝ ብለው በዱር በገደሉ የተጋተሩትንና የተናነቁትን ቀደምት፡ የነ ኮሎኔል አድኃኖም ክፍለእዝጊ የነ አቶ ገብረመድኅን ወልደሥላሴና አቶ አብርሃ ክፍሉ እንዲሁም የነዘርሀንስ ወልደ ስላሴና፤ ዘራኤ ሠናይ ናይዝጊ ሄናንና የመሰሎቻቸውን ታሪክ ከሱዳኑ የስደት ቆይታቸው ጋር አያይዘው ያስኮመኩሙናል፣ አርበኛው ተስፋሚካኤል ትኩእ። መልካም ንባብ። :mrgreen:

“ምንም እንኳ እኔን ከነቤተ ሰዎቼ ጣሊያንን ደስ ለማሰኘት ብለው እንግሊዞች ከካርቱም በፖሊስ አስገድደው ገዳሪፍ ቢያመጡኝም፣ ከኔ ርዳታ የሚፈልጉ ብዙ ወንድሞቼ በጋዳሪፍ ስለቆዩኝ ስደተኞቹን ለማስጠናት ከፍ ያለ ኃላፊነት ገጠመኝ። ከአርማ ጭሆ የመጡትም አቶ መንግሥቱ ወልደ ኪዳንና አቶ መለስ ገብረዝጊ መሳፈሪያ ገንዘብ አጥተው ሲላቀሱ ደረስሁና “ጠባያችሁን አርሙ፤ የተገኘውን ሥራ እየሠራችሁ በብዙ ትዕግሥትና ጥንቃቄ አርፋችሁ ተቀመጡ። ጊዜው መጥፎ ነው። ፈላጊያችንም እጅግ ብዙዎች ናቸውና ተጠንቀቁ” ብዬ ባስረዳቸው “አንሰማም” አሉኝ። ሌት ተቀንም ያለ ማቋረጥ ምክርና ክርክራቸውንም ቀጠሉብኝ።” (ገጽ 147)

አከለጉዛይ ሀገራችን ሔደን በየቀኑ ከጣሊያን መንግሥት ማርከን እየሰበሰብን በዓጋሜ ዋሻ ያስቀመጥነው ብረታችንን አምጥተን አርማ ጭሆ ገብተን ለሀገራችን ደማችንን እናፈሳለን እንጂ በሱዳን ንዳድ ተቃጥለን በችግርና በረሐብ አንሞትምና የተቻለውን ምክር አምጣ” ብለው አሉኝ። እኔም “እንሔዳለን ካላችሁ መልካም ነው፤ ሰዎቻችን ሁሉ በከሰላ እንዲቆዩና አቶ አድኃኖም ክፍለዝጊና አቶ ገብረ መድኅን ወልደ ሥላሴ፣ አቶ አብርሃ ክፍሉ ብቻ በብዙ ጥንቃቄ እንድትሔዱ፤ ሀገራችን ከገባችሁ በኋላ ደም ብታፈሱ ሰላማዊ ሰዎችን ጭምር ታስፈጃላችሁና አደራችሁን ተጠንቀቁ” ብዬ መከርሁዋቸውና በመሔዳቸው ተስማማን። እኔም ለደጃዝማች ገብረ ሕይወት መሸሻና ለሌሎችም አርበኞች የግርማዊነታችውን ጤናነትና በፍጥነት ወደ ኢትዮጵያ መመለሳቸውን የሚያስረዱ ብዙ ደብዳቤዎች፣ ለትግሬ ሕዝብ የሚያጥናኑ ስብከቶች አሰናድቼ አቶ አድኃኖምና አቶ ገብረ መድኅን፣ አቶ አብርሃን ወደ ደጃዝማች ገብረ ሕይወት መላኬን ሎንዶን ለጃንሆይ አስታወቅሁ።” ገጽ 147

“የዛሬው ካፒተን አድኃኖምና ጓደኖቹም አቁርደት ላይ ባለፈረስ ባንዶች በቀን ከበው ካስጨነቁዋቸው በኋላ በሰይፍ ተከላክለው፣ በዱር በገደል ብለው አመለጡና በአንሰባ በአሥመራ ሽከቲ እናደቆ አድርገው ወደ ዓጋሜ ወጥተው አቶ ገብረ ማርያም ቤት ጐልዓ ሰነበቱ። ከሴት አርበኛ ከወይዘሮ አመተ ጋራም ተገናኙና ወንድ የሆኑ የኢሮብ ሴት ወይዘሮ አመተም ዘንድ በዋሻ ካስቀመጡት ብረት ፭ት ጠመንጃ ከነ ጥይቱ አወጡ። የወይዘሮ አመተ የወንድም ልጅ አቶ ገብሩንም የአርበኞች ሁናቴ ለመመርመር ቦራ ሠለዋ ላኩ። አቶ ገብሩም በቦራና በሠለዋ አርበኞች በርትተው መነሳታቸውንና ጥይትና ጠበንጃ በገበያ መሸጡን መሰከሩ። ደጃዝማች ገብረ ሕይወት ዘንድ የተላኩት ሰዎችም ዓሲምባ መግባታቸውንና ማንም ሰው ሊገናኛቸው አለመቻሉን አረጋገጡላቸውና በአከለጉዛይ በባህሪም ፮ወር ሐድን ሲያድኑ ከርመው ፭ት ብረትና ጥይት በከሰላ ተራራ ዋሻ ቀብረው ወደኛ ገዳሪፍ በደህና በመመለሳቸው ለእግዚአብሔር ምስጋና አቀረብን።” ገጽ 148

“በሐምሌ ፩ ፲፱፻፴፻ ዓ.ም. ከካርቱም ከባለቤቴና ከልጆቼ ጋር በእንግሊዝ መንግሥት ተገድጄ ገዳሪፍ እንደገባሁ ዛሬ ወይም ነገ ለወዳጃቸው ለጣሊያን ያስረክቡኛል በማለት እንቅልፍና እረፍት ሳይወስደኝ ከረምሁ፤ እነ አድኃኖምም በህዳር ወር ፲፱፻፴፩ ዓ.ም ሰገነይቲ እስከ ዓጋሜ ሔደው በሚያዝያ ወር ተመለሱ። በዚሁም ጊዜ ዶክተር ላምፒ የተባለ አመሪካናዊ የወንጌል ሰባኪ ነኝ የሚል ሰው የኢትዮጵያ ዜጋ ለመሆን ስለጠየቀ፣ ለጋስዋ ኢትዮጵያም እውነት መስሎዋት ዜግነትና ሰፊ መሬት በጐለለ ክብርና ፖለቲካዋም ሳይቀር ሰጠቸው። የላምፒም ጓደኞች እነ ዶክቶር ደ ሐርቲ የጣሊያን መንግሥት ወሰንና መሳይ የሌለው ደግነት ስላለው ለሱ ተገዙ እያሉ ስብከት ሲሰብኩለት የነበሩት፣ የላምፒ ሚሲዮኖች እሱም ራሱ ዶክቶር ላምፒ ሳይቀር ኢጣሊያኖች አባርረው ከኢትዮጵያ አስወገዱት፤ ካርቱም ስደት ተሰዶ ላምፒ በመምጣቱ እግዚአብሔርን አመሰገንን፤ ከሐሊነቱንም አደነቅን።” ገጽ 148

በአሜሪካን ስም ወንጌል እናስተምራለን የሚሉ የእንግሊዝ ሚሲዮኖች ገና አቡነ ዘበሰማያት ማለት ሲጀምሩ አሸጋግረው ባንዴራቸውን ያስተክላሉ ተብሎ የተነገረላቸው ታሪክ እያነሳን ከወዳጄ ካቶ ተመስገን ገብሬ ጋር በሰፊው ስለክፋታቸው ተነጋገርን። እነዚህንና እነዚህንም የመሰሉ የማናቸው መንግሥት ወንጌልን በኢትዮጵያ እንዲሰብኩ መቀበል ትልቅ የማይታረም ኃጥያት መስሎ ይታየኛልና የኢትዮጵያም ወጣቶች በነገሩ እንዲቆረቆሩበት ባለ ብዙ ተስፋ ነኝ። በዚሁ ጊዜ ሁሉ የእንግሊዝ መንግሥት ወደ ጣሊያን ተራርቀን (ታርቀን) እንድንገባ አባበለን፤ እምቢ ስላልነውም አዘነ፤ እኔንም ከነቤተሰዎቼ ለማበሳጨት ብሎ በኬኒያ ካሉት የኢትዮጵያ ስደተኞች ጋር ትጻጻፋለህ ብሎ ምክንያት አድርጎ በማስገደድ ገዳሪፍ ላከኝ።” ገጽ 149

“የጣሊያን መንግሥት የእንግሊዝን መንግሥት በሱዳንና በጁቡቲ፣ በኬኒያና በግብፅ በኢየሩሳሌምም ያሉትን የኢትዮጵያ ስደተኞች በማስገደድ እጃቸውን ይዘህ አስረክበኝ ብሎ ስላስጨነቀው ደስ ለማሰኘት ደከመ። በዓለም መንግሥታትም ፊት ቀርቦ በጀነብ ጉባኤ “በጣሊያን ጦር ሠራዊት ኃይል የተያዘቹዋን ኢትዮጵያን ብለን የዓለምን ሕዝብ ወደ ጦርነት አግብተን በእሳት አናቃጥለውምና ኢትዮጵያን ጣሊያን መያዙን እንወቅለት” ብሎ መሰከረለት። በዚህ ጊዜ የዓለም መንግሥታትም እንግሊዝ ጣሊያንን መፍራቱንና ጦርነት መጥላቱን ስለተረዱት እፍረት አፈሩ፤ ስንፍናቸውን አሳዩ፤ ሱሪያቸውን ሁሉ ለሂትለራዊው ጀርመን አስረክበው በመሸበርም ተንቀጠቀጡ፤ እፍረትና ውርደትም ለበሱ።” ገጽ 149

“የመስኮብ ባለ ጥንታዊ ታሪክ ሕዝብ ባይገጥመው ኑሮ ግን የኤውሮጳ ነገሥታት ሁሉ የጀርመን መንግሥት ተገዥዎች ለመሆን ውሳኔ ወስነው ነበር። የጀመርንንም ጥበብና ጀግንነት በኩራት ምክንያት ሰባብሮ ሽባ ያደረገው የእግዚአብሔር መለኮታዊ ኃል መሆኑን የማይዘነጋ ነው። የእንግሊዝም መንግሥት አጥብቆ የከነከነው ጦርነት ፈጥኖ ተነሳበት፤ ኢትዮጵያም የዓለም መንግሥታት የቃል ኪዳን ማኅበርተኛቸው ሆና ሳለች በግፍ በጣሊያን ወረራ ስትወረር በመርዳታቸው ፈነታ፣ መስዋዕት እንድትሰዋላቸው ለጣሊያን አሳልፈው የሰጡዋትን ኢትዮጵያ፣ በሰማያዊ ተአምራት፣ ወሰን የሌለው ረድኤት ነፃ ስትወጣ፣ የኢትዮጵያ ገዥ ለመሆን የተመኘቺው ጣሊያንና ጓደኞችዋ ወደ ገሃነመ እሳታዊ የጀርመን ባርነት ሲገቡ በመታየታቸው ለኢትዮጵያ ሕዝብ ብቻ የግል አምላኩዋ የሆነው አምላክ በብዙ ተመሰገነ። ይመሰገናልም።” ገጽ 149

“በዚህም ወደረኛ የሌው የሱዳን ባለታሪክ ስደታችን በየቀኑ የገጠመን ጭንቅና በኅዘን የተለወሰ መከራ ሊነገር ዓይቻልም። በሌሎቹም ሀገሮች ተሰደው የነበሩት ኢትዮጵያውያኖችም ቢሆኑ ከኛ የባሰ ስደት ቢገጥማቸውም፣ በትዕግስትና በብርታት ቀጥ ብሎ ስለነፃነቱ ጭንቅና መከራ ያልተቀበለ ኢትዮጵያዊ ምንም አልነበረም። የጦርነቱን መራርነትና የስደቱንም መከራ ያልቀመሰ ሰው በቃል ቢነግሩት፣ በጽሁፍም ቢያሳዩት ምንጊዜምው ቢሆን ሊገነዘበው ዓይችልም። ገጽ 149

የኢትዮጵያ ደፋር ሕዝብ ግን እምነቱን በፈጣሪው ላይ ብቻ አድርጎ የተረገመው አረመኔው ግራኝ አህመድ ይማም ተብሎ በያይነቱ የውጭ ሀገር ሰዎች ሰብስቦ ወደ ኢትዮጵያ ለወረራ ቢያስገባቸው፣ በኢትዮጵያ ሕዝብ ላይ ምሕረት የሌለው መገደል፣ በገዳማትና በአብያተ ክርስትያኖች ጨካኝ ወረራና ዘረፋ፣ በእሳት ማቃጠልንም ፳ ዓመት ሙሉ ቢያዘንብበትም ፈጣሪውን አልረሳም። ስለዚህ በሚመካበት አምላኩ ኃይል፤ ግራኝ አህመድ በደንቀዝ አጠገብ ባለች በር ሲወድቅ ተከታዎቹ በሰማያዊ ኃይል ድል ሆነው በሐረር ከተማ ቢሰበሰቡ ሕያው የኢትዮጵያ አምላክ ፫ት ዓመት ሙሉ በሚያንቀጠቅጥ የረኃብ ቅጣት ከቀጣቸው በኋላ የኢትዮጵያ ጠላቶች በዚሁ መሳይ የሌለው ረኃብ ተጨንቀው የገዛ ልጅጆቻቸውና ሚስቶቻቸውን ከበሉ በኋላ፤ በትልቅ ውርደት እንዲሞቱ ያደረገውን የኢትዮጵያ የግል አምላክ እያሰቡ ተጥናኑ።” ገጽ 150

“ሐዲስ በሆነው በያይነቱ መሣሪያውና በሀብቱ፣ በጓደኞቹ ምስጢራዊ የተሰወረ ረቂቅ ፖለቲካዊ ርዳታና እገዛ በመተማመኑ በቅፅበት ፈጣሪውን ረሳ፤ “የኃይለኞች ኃይለኛ የጣሊያን ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ሙሉ ምሕረት አድርጎላችኋልና በአርበኝነትና በስደትም ያለህ የኢትዮጵያ ሕዝብ ግባ” ብሎ አዋጅ አናገረ። እምነቱን በፍጡር ላይ ያላደረገው የኢትዮጵያ ጥንታዊ ባለ ታሪክ ሕዝብ ግን፤ በውዳሴ ከንቱ የተነፋ የጣሊያን መንግሥት መሪ የሙሶልኒን አታላይ ስብከት አዋጅ ምንም ሳይቀበለው ዝም ብሎ በአርበኝነቱና በስደቱ ረግቶ ቀረ፤ ወደ ጠላት ከመግባቱም መሞቱን መረጠ። የኢትዮጵያም ተራሮችና ሜዶች ሸለቆችና ሸንተረሮች ደማቸውን አጠጥተው በማርካታቸው አስደነቁ፤ ገነትዋ ሀገራቸውንም አስከበሩዋት፤ ያስከብርዋታልም።” ገጽ 150

“በእነዚህ ደስታ የሌላቸው የዘመቻና የጦርነት፣ የአርበኝነት፣ የስደት ዓመታቶች ከባለቤቴና ከልጆቼ ጋር በሱዳን የእንግሊዝ መንግሥት ባለሥልጣኖች ተገድጄ ከካርቱም ገዳሪፍ እንደወጣሁ፣ የዛሬው ደጃዝማች ውብነህ ተሰማ ባለቤታቸው ወይዘሮ ዘነበሽና ልጆቻቸውን ገዳሪፍ ጥለው በአርማጭሆና በወገራ እስከ በለሳ ሲወናጨፉ፣ ባለቤታቸው ከነልጆቻቸው በባዶ ቤት ተዘግተው አገኘሁዋቸውና በብዙ አዘንሁ። ለግርማዊ ጃንሆይም ሎንዶን የአድዋ አባገሪማ ተወላጅ ግራዝማች ውብነህ ተሰማ ቤተሰዎች ብዙ በመቸገራቸው ምክንያት እንዲታደጕኣቸው ብዬ ብጽፍም ዕድል ሳያገኙ ስለቀሩ በብዙ ተጨነቅን፣ የፋሽር ተወላጅ ናዚር አብዱላሂ የተባለ የጣሊያን ጠላት የሆነ ያንድ ክፍለ ሀገር ገዥ ርዳታ ይሠጣቸው ጀመር።” ገጽ 151

ጀግናው ግራዝማች ውብነህ ወንድማቸው አቶ ሐጐስ ተሰማ ግን በየቦታው ጣሊያንን አጥብቀው ወጉት፤ ለሊት ተቀን በመውጋታቸውም አስጨነቁት፤ እንኳን ወንድ ሴቶችም አርበኞች ሆኑ ሀገሬውም ራስ ውብነህ፣ ደጃዝማች ሐጐስ ተሰማ ብሎ ሾማቸው። እራስ ውብነህና ደጃዝማች ሐጎስ፣ ያጐታቸውም ልጅ ደፋሩ ደጃዝማች ዋኘው ሲቀሩም ፸፭ ዘመዶቻቸው በጦር ሜዳ አለቁ። ይህም ሁሉ ሲሆን ከባለቤታቸውና ከልጆቻቸው ይበልጥ ሀገራቸውን አፍቅረው በመጋደላቸው ታሪክ ጸሐፊ አቀብቆ ሊያስብበት በተገባው ነበር። ናለመኖሩም ለሐዲሱ ትውልድ የአሞራው ውብነህ ተሰማና ሐጐስ ተሰማ፣ የለስላሳው ሎጋ ዋኘው ሰውነት በጠላት ጥይት በመበሳሳቱ የመረረ ስቃይ መሰቃየቱንና ደጃዝማች ዋኘው ተብሎ በዚሁ የመረረ ስቃይ እየተሰቃየ በአዲስ አበባ ሆስፒታል መሞቱን ሳላስታውስ አላልፈውም። ደጃዝማች ሐጐስ ተሰማም ከብዙ ጥይቶች በጉሮሮአቸው ያለ ጥይት በበለጠ እህል አላስበላም፣ ውኃም አላስጠጣም ብሎዋቸው በሆስፒታል ዛሬም ወድቀው ይታያሉ።” ገጽ 151

“ይህም ሁሉ ሲሆን ባለ ጥንታዊ ታሪክ ደፋሩ የኢትዮጵያ ሕዝብ እምነቱን ሳያጓድል “ቸሩ እግዚአብሄር ያውቃል” ከማለት አቋርጦ አያውቅም ነበር። በዚሁም እምነት ብዛት የጦርነቱን መራራነት፣ የአርበኝነቱንና የስደቱን መከራ በትልቅ ትዕግስትና ችሎታም በማሳለፉ፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ በዓለም መንግሥታት ዘንድ በብዙ ተመስግኗል። ይመሰገናልም።” ገጽ 151

“ገብረ ዘወሃብከኒ ፈጸምኩ” “ሃቦ እግዚኦ ዕረፍተ ወብርሃነ ዘለዓለም - ነፍስኄር ሌ/ኮሎኔል አድኃኖም ክፍለ-እግዚእ - ግንቦት ፳፱ ቀን ፲፱፻፰፰ዓ.ም. በሠገነይቲ ከተማ ጽንዓደግለ አከለ ጉዛይ የአባታችን ነፍስኄር ኮሎኔል አድኃኖም ክፍለእግዚእ በምናደርገው ተዝካር፡ ጸበል ትካፈሉልን ዘንድ በአክብሮት እንለምናለን” ቤተሰባቸው በሙሉ” ገጽ 151

“በ፲፱፻፩፰ በታህሳስ ወር ከጣልያን ከድተው ወደ ኢትዮጵያ መንግስት የገቡት የአከለጉዛይ ልጆች ስም አቶ (በኋላ ሻለቃ) አድኃኖም ክፍለ እግዚእ ማይ ኢላ መሐሪ ሀጎስ አዲ ቆንፅ፤ ገብረ መድኅን ወልደ ሥላሴ፥ አዲቆንፅ፣ ዘርሀንስ ወልደ ስላሴ አዲ ቆንፅ፤ ዘራኤ ሠናይ ናይዝጊ ሄና በሰሩት ጀግንነት በጣም የሚያኮራ ታሪክ ትተው ያለፉ ጀግኖች ናቸው። በእውነት ናቸው የሚያውቃቸው ሁሉ ይመሰክርላቸዋል በእውነት ጀግኖች በወጣትነት በጣም ቆራጥ በሆነ ጀግንነት ህይወታቸውን ያበረከቱ ለሀገራቸው ለኢትዮጵያ ነው።” ገጽ 152

ይህን ታሪክ ብርቅ የሚያደርገው አሁን ያለው አዛውንት ትውልድ ንፍጡ ባፍንጫው ይዝረከረክበት በነበረ ወቅት ለነጻነቱ ሲል ብርቱ ገድልን ባከናወነ ኤርትራዊ አባት አርበኛ የዓይን እማኝነት የተጻፈ በሳል ፖለቲካዊ ትንታኔ መሆኑ ነው።

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 07 Nov 2019, 07:56
by YAY
ዝከበርካ መለከት ወይ ምልክት፡ እዞም ሰብኣይ ናይ አየነይቲ ሃገር አርበኛ ወይ ሓርበኛ እዮም ኔሮም፧

ኣቶ ተስፋሚካኤል ትኩእ ናይ አየነይቲ ሃገር አርበኛ ወይ ሓርበኛ እዮም ኔሮም፧ ናይ ዓደቦኦም ሃገሮም ኢትዮጵያ፧
ወይሲ ናይ ዓደቦኦም ሃገሮም ኤርትራ፧ ቍሩብ ተደናጊረ ኣለኹ።

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 07 Nov 2019, 08:36
by Meleket
YAY wrote:
07 Nov 2019, 07:56
ዝከበርካ መለከት ወይ ምልክት፡ እዞም ሰብኣይ ናይ አየነይቲ ሃገር አርበኛ ወይ ሓርበኛ እዮም ኔሮም፧

ኣቶ ተስፋሚካኤል ትኩእ ናይ አየነይቲ ሃገር አርበኛ ወይ ሓርበኛ እዮም ኔሮም፧ ናይ ዓደቦኦም ሃገሮም ኢትዮጵያ፧
ወይሲ ናይ ዓደቦኦም ሃገሮም ኤርትራ፧ ቍሩብ ተደናጊረ ኣለኹ።
ኽቡር YAY ሓወይ ጽቡቕ ሕቶ ሓቲትካ ኣሎኻ። መልሱ ኣነ ዛይዀንኩስ ባዕልኻ ነቱይ ዛንታ ሃሰስ ቢልካ ክትረኽቦ ምሓሸ ነቢሩ። ሓሳበይ ካብ ሓተትካኒ ግና ከም ርድኢተይ እዞም ሐርበይናዊ ኣቦ ተጻይ ገበትቲ፣ ተጻይ ዓመጽቲ፣ ተጻይ ፋሽስቲ ምእንቲ መትከሎምን እምነቶምን ዝተጋደሉ ኣቦ ኢዮም። ብዙሓት ደቂ ሀገርና ብግድነታዊ ዕስኽርና ብኣልማማ ዓሳኽር ጥልያን ኪኮኑ ተቐሲቦምሉ ኣብ ዝነበሩ ግዜ፡ ቦሎኽ ቢሎም ወጺኦም “እምቢ ንፋሽስቲ” ዝበሉን፣ ተፃዩ ምእንቲ ናጽነቶም ዝተጋደሉ ሓርበይና ኢዮም እንተበልኩ ትሰማማዕ’ዶ ትኸውን፧ መበቆሎም ኤርትራ ቃልሶም ድማ ምስ አኃዋትና ደቂ ኢትዮጵያ ጌሮም ክብሪ ደቂ ሀገር ምእንቲ ናብ ንቡር ኪምለስ ዝተጋደሉ አቦ ኢዮም። ስለምንታይ ምስ ኢትዮጵያዉያን ኣኃዋትና ሰሚሮም ተጋዲሎም፧ እንተተባህለ መልሱ ካልእ ዝበለጸ ኣማራጺ ስለዘይነበረ ኪከውን ይኽእል። ካብታሪኽ እንፈልጦ ካልእ ኣማራጺታት “አሜን” ቢልኻ ንፋሽስቲ ክትግዛእ ወይ ተዓስኪርካ አገልጋሊኡን መጋበሪኡን ምዃን ኢየን ነቢረን። ቀዳሞት ጀጋኑና ግና ከከም ዝጥዕሞም ይገብሩ ነቢሮም፣ ካብ ታሪክ ወልደሚካኤል ኮነ ባህታን ካልኦትን ከምኡ ኢና እንመሀር። አይመስለካን፧ ብርግጽ እዚኦም ሓርበይናዊ ኣቦ ፍሉይ ፍቕሪ ኢትዮጵያ ዝነበሮም ይመስሉ፣ ኤርትራዉነቶም ግና ንሓንቲ ደቂቅ እኳ ኣብ ዋጋ ዕዳጋ ኣየእተውዎን። ክንዲዝዀነ ሓርበይና ክልቲኡ ሕዝብታት ኤርትራን ኢትዮጵያን ኪኾኑ ተኽእሎ አሎ፧ ኣይመስለኻን፧ ቼጉቬራ ብ1928 ኢዩ ተወሊዱ ንሶም ድማ ከምቱይ አብ አርእስቲ እዙይ ጽሑፍ ዛሎ፣ ዳርጋ ብኣስታት 36 ዓመታት ቅድሚኡ ዝነበሩ ሓርበይና ናይ ሓንቲ ሃገር ጥራሕ ዘይኾነስ ሓርበይና ናይ ቀርኒ ኣፍሪቓ ኢዮም፣ ተቃላሳይን ተጋዳላይን ተጻይ ፋሽስታውያን ገዛእቲ! :mrgreen:

ዝበለጸ ነቱይ ዛንታ ስዓቦሞ እቱይ ቅኑዕ ርድኢት ባዕልካ ክትረኽቦ ኢኻ።

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 07 Nov 2019, 13:52
by kerenite
Aite meleket wedajachin,

Your hero was an ethiophile same as zeray deres or aman andom or bereket simon. They were more ethiopians than the ethiopians themselves.

Re: ተስፋሚካኤል ትኩእ (1892 – 1964)] - ወለዶና ክነቦ ዝግባእ መኽዘን ታሪኽ

Posted: 08 Nov 2019, 08:39
by Meleket
kerenite wrote:
07 Nov 2019, 13:52
Aite meleket wedajachin,

Your hero was an ethiophile same as zeray deres or aman andom or bereket simon. They were more ethiopians than the ethiopians themselves.
ክቡር ሓውና ኣይተ kerenite

ሓቅኻ ኢኻ ኣይተጋገኻይ፤ እዞም ተጻይ ፋሽስት ምስ ኢትዮጵያዉያን የኅዋትና ኮይኖም ልተጋደሉን ልጸዓቱን ኤርትራዊ ሓርበይና ክቱር ፍቕሪ ኢትዮጵያ ኔሩዎም ኢዩ። እቱይ ናይቱይ ግዜ ንቕሓት እቱይ ሕብረተሰቦም ከምኡ ስለልነበረ ኪከውን ይኽእል፤ ገሊኡ መፍቀሬ-ኢትዮጵያ ገሊኡ ድማ መፍቀሬ-ዓረባዊ ዓለም ዝነበረሉ ግዜ ኣብ ታሪኽና ኔሩ ኢዩ። ነቱይ ኩነቶም በዙይ ናይሕዪ ኣተሓሳስባ ለይኮነስ በቱይ ናይቱይ ግዜ ኣተሓሳስባ ክንርድኦ ልሓሸ ኢዩ። ናይ ቀደም ቀደም ቀደም ታሪኽና ምልስ እንተደኣ ቢልካ ርኢኻዮ ፈቲና ጸሊእና ኢትዮጵያውነት እዉን ኣካል ታሪኽና ኢዩ ልነበረ፤ ክንድዝኮነ ድማ እኒ ባሕረነጋሲ ይስሓቕን ኣዝማች ካሊት (ቀሊት :mrgreen: ) ክሳብ ውሽጢ ኢጦብያ ኣትዮም ንመኒካ ትብሎ ነቱይ ቤተስኪያን ዜዕኑ ዝነበረ ዘሪጋ እቱይ ግዜ፡ ምስ ደቂ ቦርቹጋል ሓቢሮም እስቲህናይ ኣቢሎም ኢዮም። ድሓር ብዝማዕበለን ዝተሃላለከን ቦለቲካዊ ኩነት ድማ ሕዪ ንሕና መሬትናን ባሕርናን 9 ብሄራትናን ሒዝና እንሄና ኢትዮጵያዉያን ኣሕዋትና ድማ ነታ ሕዪ ለላ ኢትዮጵያ ወኒኖም ይርከቡ ማለት’ኡ። ሓቂ ኢዩ ገሊኦም ክቱር መፍቀሬ-ዓረባዊ ዓለም ኣሕዋትና፡ ዓስራይ ብሄር ቢልኩም ጸብጽቡና ቢሎም ኔሮም ልብሉ ሰባት እኔሄው፡ እንተኰነ ግዳ ክሳብ ሕዚ ኣይሰለጦምዪ!

ሕዪ ናብቱይ ጕዳይና ምስ እንምለስ፡ እስከ ንመለሳ ምእንቲ ኪኾነና ንስኻ ክቡር ሓወና ኣይተ kerenite ናይቱይ እዞም ሓርበይና ኣቦ ዝነበሩሉ ዘመን ልነበሩ ካልኦት ሓርበይናታት ሃገርና ዛንታኦም ኣሊሽኻ ኣምጽኣልና’ሞ ክንመሃረሉን ክንፈልጦን ግበር። ወላ ብቋንቋ ዓረብ ልተጻሕፈውን አልሽ ኢኻ፡ ኣይዞኻ!

ብርግጽ ነዞም ኤርትራዊ ሓርበይና ኣቦ ምስ’ቲ ምስ ገበትቲን ዓመጽትን ወረርትን ሰሚሩ ተጻይ ሃገሩ ምስ ዝነበረ ኣይተ በረኸት ስምዖን ክተመሳስሎም ‘ናይ እማነይ ኢየ ልብለካ’ ገሪሙኒ’ኡ። እዞም ሓርበይና ተጻይ ሕዝቢ ኤርትራ ሰሪሖም ዲዮም’ከ፧ ወላስ ስለምንታይ ንፋሽስቲ “አሜን” ቢሎም ለይተገዝኡ’ ኢዩ፧ ወዳጄ ንሶም “እምቢ” ቢሎም ኢዮም ዘዋጽኦም ልገበሩ።

ብመዳይ ስነጽሑፍ እዉን እንተጠመትናዮ፣ ኣብቱይ ግዜ እቱይ ነቱይ ዝነበሩሉ ግዜን ኩነትን ዚገልጽ ታሪኽ ከምዙይ ጌሮም ብዙሓት ኪነብዎ ብዝኽእሉ መገዲ ቋንቋ ኣሕዋቶም ኣጽኒዖምን መሊኾምን ብውቁብ ኣምሓርይና ሰኒዶም ምጽንሖም፣ እሞ ድማ ድኅሪ ዳርጋ አስታት ሚእቲ ዓመት ኣነን ንስኻን ካልኦትን ከይተረፍና ብዛዕብኦም ክንዛረብን ክንነቦምን ዝገበሩ ኤርትራዊ ሓርበይና ኢዮም። እዙይ ክንዲዝዀነ ብርግጽ ብርግጽ እዞም ኣቦ ኤርትራዊ ሓርበይና ስነጽሑፍን ታሪኽን ተንታኒ ቦለቲካን እዉን ኢዮም እምበር! ከምትፈልጦ ሓዉና ክቡር ተጋዳላይ ባዱሪ ብቋንቋ ኣሕዋትና ዓረብ ገቢሩ ብዛዕባ ኣብ ሃገራት ዓረብን ሃገርናን ዘሕለፎ ገድሊ ሕዪ ቅድሚ ገለ 3 ዓመታት ሰኒዱልና ኢዮ። እዚኦም ኣቦ ድማ ቅድሚ ሚእቲ ዓመት ልነበረ ታሪኽ ብቋንቋ ኣምሓርይና ሰኒዶምልና ማለት’ኡ።

በል ክቡር ሓዉና kerenite ብመዳይካ ናይቲ ዘመንን ቅድሚኡን ዝነበረ ታሪኽ ሃገርናን ዞባና ዜዘንትው፡ ካልኦት ኣለዉ እትብሎም ኤርትራዉያን ሓርበይናታት ዘዘንተዉዎ ዛንታ፡ እንኰላይ ብቋንቋ ዓረብ ዛሎ ኣሊሽኻ ሃየ ኣይትሕመቕ ኣምጽኣዮ እሞ ክንፈልጦምን ክንመሃረሉን። እምበር እዞም ኤርትራዊ ሓርበይና ኣቦ ልዕሊ ኢትዮጵያዉያን ኢትዮጵያዊ እንተኰኑ ንሓዉካ ከም ነፍስኻ ፍቶ እናተባህሉ ተማሂሮም ኢዮም ልኾኑ እምበይ ወዳጃችን!