በየአመቱ ከነሀሴ 14 ጀምሮ ለሶስት ቀናት በአማራ ክልል በሰቆጣና በላሊበላ ሻደይ፣አሸንድየ በትግራይ ክልል አሸንዳ፣ በዓል በድምቀት በመከበር ላይ ነው።በዓሉ ልጃገረዶች/ ሴቶች በተለያዩ ባህላዊ አልባሳትና ጌጣ ጌጦች ተውበው ሹሩባ ተሰርተው በነጻነት የሚጨፍሩበት፣ የመሰላቸውን ሀሳብ በዜማቸው የሚገልጹበት ታላቅ ዕለት ነው።
የበዓሉ ባለቤቶች ሴቶች በተለይም ወጣት ሴቶች ናቸው።
የኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚንስትር ዶ/ር አብይ አሕመድ በዓሉን አስመልክተው ባስተላለፉት መልእክት በአሉ የሴት ልጆች በተለይም ወጣት ሴቶች አንገታቸውን አቀርቅረው በሚሄዱበትና በአደባባይ ወጥተው ፍላጎታቸውን በማይገልጹበት ወቅት ሁሉ በሙሉ ነጻነት ይልቁንም በጋራና በአደባባይ የወደዱትን የሚያሞጉሱበት፣ የጠሉትን ሃሳብና ተግባር በነጻነት የሚያወግዙበት ድንቅ በአል ነው ብለዋል።
አሸንዳ/ ሻደይ የሴቶች ውበት፣ ክብር እና ነጻነት ማሳያ ብቻ ሳይሆን ነጻነት ራሷ ነጻ የምትወጣበትና በአደባበይም ስጋ ለብሳ የምትታይበት ታላቅ ቀን ነው ብለዋል ጠቅላይ ሚንስትሩ።
ጠቅላይ ሚንስትሩ በመልእክታቸው የሰሜኑ ክፍል የሀገራችን ህዝቦች ከሚያለያዩዋቸው ይልቅ አንድ የሚያደረጉዋቸው እንደሚበዙ ብዙ ከማስረዳት ይልቅ የአሸንዳን አንድ ሰበዝ በፍቅር ማሳየት ሁሉን ነገር ይገልጸዋል ብለዋል።
ይህን አስደሳችና አስዳናቂ ባህል፣ የሰሜን የሀገራችን ህዝቦች ብቻ ሳይሆን የመላ ኢትዮጵያ ህዝቦች፤
የኢትየዮጵያውያንም ብቻ ሳይሆን የአለም ሀብትና ቅርስ መሆን እንዲችል በአለም በማይዳሰስ ሀብትነት እንዲመዘገብ አጥብቀን መስራት ይኖርብናልም ብለዋል።
ልጃገረዶች/ሴቶች ከዋዜማው እስከ ማግሥት ልጃገረዶች የአሸንዳ ቅጠልን አሸርጠው አደባባይ በመውጣትና በየቤቱ በመዞር እየጨፈሩና እያዜሙ የሚያከብሩት በዓል ስያሜው በክረምት ወቅት ከሚበቅለው የአሸንዳ ተክል እንደተወሰደም ይነገራል።
በዓሉን ለመዘገብ በርካታ የአገር ውስጥና የውጭ መገናኛ ብዙሀን ወደ የአከባቢዎቹ ተሰማርተዋል።