የኢትዮጵያ አየር መንገድ አለም አቀፍ የሴቶችን ቀን ምክንያት በማድረግ ሙሉ በሙሉ በሴቶች የሚመራ በረራ ወደ ኖርዌይ ኦስሎ ማድረግ ጀምሯል።
የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ ስራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ገብረማርያምን ጨምሮ የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በረራውን የማስጀመር ስነ ስርዓት ተካሂዷል።
የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ በዚሁ ወቅት፥ ሙሉ በሙሉ በሴቶች የሚመራ በረራ የማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ በመታደማቸው ደስታ እንደተሰማቸው ገልፀዋል።
በነገው እለት የሚከበረውን አለም አቀፍ የሴቶች ቀንን ምክንያት በማድረግ ከአዲስ አበባ- ስቶኮልም ወደ ኦስሎ የሚደረገው በረራ በሴት የአብራሪዎች ቡድን የሚመራ ነው።
በረራው ታሪካዊ እንደሆነ የተነገረ ሲሆን የአውሮፕላኑ አብራሪ፣ የበረራ አስተናጋጅ እና መላው ሰራተኞች በኢትዮጵያውያን ሴቶች ሙሉ በሙሉ የሚመራ ነው ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ከዚህ ባለፈም ከአየር ትራፊክ ቁጥጥር፣ የጭነት ቁጥጥር፣ የበረራ መለኪያ፣ የበረራ ደህነነት ቁጥጥር እና አጠቃላይ የአውሮፕላኑ ጉዞ ከትኬት ቢሮ ጀምሮ እስከ አውሮፕላኑ መነሻ ድረስ ሙሉ በሙሉ በሴቶች የሚመራ መሆኑን አየር መንገዱ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡
የአየር መንገዱ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ተወልደ ገብረማርያም በሁሉም የበረራ ዘርፍ ብቁ የሆኑ ሴቶች ተቋሙ ስላለው ደስተኛ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
ዋና ስራ አስፈፃሚው ሴቶች ለአየር መንገዱ ስኬት ከፍተኛ ሚና እንደነበራቸውም ነው የተናገሩት፡፡
በአፍሪካ ሴቶች ዋነኛ የሀብት መሰረት ቢሆኑም የፆታ እኩልነት አሁንም ድረስ እንደሌለ የገለፁት ዋና ስራ አስፈፃሚው ሴቶች የሚገባቸውን ቦታ እንዲያገኙ መስራት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
አየር መንገዱ ይህንን ፕሮግራም የጀመረውም ሴቶች የትኛውንም ስራ እራሳቸውን ችለው የመስራት አቅም ያላቸው መሆኑን አፅንኦት ለመስጠት ነው ብለዋል።
በኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅትም ሴቶች በከፍተኛ የመንግስት የስራ ሃላፊነቶች ላይ እየተሳተፉ መሆኑንም አንስተዋል።