ዳባት ከተማ በሚገኝ እስር ቤት ታራሚዎች የእስር ቤቱን ግድግዳ በመቆፈር አመለጡ

ትናንት የካቲት 20 ቀን 2011 ዓ. ም ዳባት ከተማ በሚገኝ እስር ቤት በተለያዩ ወንጀሎች ተጠርጥረው በእስር ላይ የነበሩ ታራሚዎች የእስር ቤቱን ግድግዳ በመቆፈር ማምለጣቸውን የሰሜን ጎንደር ፖሊስ መምሪያ ሃላፊ ምክትል ኮማንደር ደሴ ሙሉዬ ለቢቢሲ ተናገረዋል።( BBC )

እንደ ኮማንደሩ ገለጻ እስር ቤቱ ስላረጀ በቀላሉ የሚሰበርና የሚቆፈር በመሆኑ ታራሚዎቹ ሰብረው መውጣት ችለዋል።

ካመለጡት እስረኞች መካከል ሁለቱ በግድያ የተጠረጠሩና ጉዳያቸው በምርመራ ሂደት ላይ ያነበረ መሆኑን ምክትል ኮማንደሩ ገልጸዋል። ሌሎቹ አስራ አምስት እስረኞች ግን በሌሎች ወንጀሎች የተጠረጠሩ ናቸው።

እስር ቤቱ ውስጥ በአጠቃላይ 25 እስረኞች የነበሩ ቢሆንም ሌሎቹ ስምንት ሰዎች እንዳላመለጡ ያብራሩት ምክትል ኮማንደር ደሴ፤ “ስምንቱ ሰዎች የማምለጥ እድል ቢኖራቸውም ሕግን በማክበር በእስር ቤቱ ቆይተዋል” ብለዋል።

ምክትል ኮማንደር ደሴ “እስረኞቹ ከተለያዩ ቀበሌዎች የመጡ በመሆናቸው በአንድ ላይ የመሆን እድል የለም። የተባበሩት ከእስር ማምለጥን ግብ አድርገው ነው” ሲሉ አስረድተዋል።

በግድያ ከተጠረጠሩት ውጪ ሌሎቹ አርሶ አደሮች እንደሆኑ ጨምረው ተናግረዋል። ታራሚዎቹ በቁጥጥር ስር በዋሉበት ወቅት ባስመዘገቡት አድራሻ መሰረት ወደ መኖሪያ አካባቢያቸው በመሄድ እንደሚያዙ ተናግረዋል። በወቅቱ ተረኛ የነበሩ የፖሊስ አባላትም ሃላፊነትን ባለመወጣት እንደሚጠየቁም አክለዋል።

እስረኞቹ እንዲያመልጡ ከውጭ እርዳታ ስለመደረጉ የተጠየቁት ምክትል ኮማንደር ደሴ፤ “እስር ቤቱ የተቆፈረው ከውስጥ ነው። ምንም አይነት የውጪ እርዳታ አልተጨመረበትም” ብለዋል።

ያላመለጡት ስምንት ታራሚዎች ነገሩን ባሉት መሰረት፤ ያመለጡትን እስረኞች ያስተባበረው በዳባት ከተማ በወንጀል ተጠርጥሮ የታሰረ ወጣት ነው።

በእስረኛው ሃሳብ አመንጪነት ያረጀውን ግድግዳ በመስበርና ትንንሽ የዲንጋይ ካቦችን በመናድ ሊያመልጡ መቻላቸውን ምክትል ኮማንደር ደሴ ገልጸዋል።