የምናልፍ መሪዎች የማያልፍ ጠባሳ ጥለን እንዳናልፍ ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡ – ም/ጠ/ሚ አቶ ደመቀ መኮንን

‹‹ድርጅት እና መሪዎች ያልፋሉ ህዝብና ታሪክ ግን ይቀጥላል፤ የምናልፍ መሪዎች የማያልፍ ጠባሳ ጥለን እንዳናልፍ ልንጠነቀቅ ይገባል፡፡››

‹‹ማንነትን ማክበር እና ማስከበር ስንል አጥር ማጠር እና የልዩነት ግንብ መገንባት ማለት አይደለም ፡፡ህዝብን ማድመጥ እና ታሪካዊ ወሰኑን ማስከበር እንጅ ተመልሶ ያደረ ጥያቄ ነው እያሉ ማለፍ ታሪኩ ያለፈበት ሂደት ነው፡፡››
‹‹ልታከብረን እና ልናከብራት የምንችላት ሃገር ለመገንባት በመጀመሪያ በህግ የበላይነት ልንገዛ ይገባል፡፡›› ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን

(አብመድ)

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን ግጭት ለታላቅ ሃገር እና ተስፋ ለሰነቀ ህዝብ የሚመጥን አይደለም፤ እንዲህ አይነት ህዝብን ከህዝብ የማጋጨት ስራ ዛሬ ሳይሆን በሁለተኛው የጣሊያን ወረራ ወቅት አማራን የትኩረት ማዕከል አድርጎ ሲሰራበት ነበር ዳሩ የህዝቡን አንድንነት ማፍረስ አልተቻላቸውም እንጅ ብለዋል፡፡

አማራን ከአገው፣ ቤተ እስራኤላዊያንን ከአማራ እንዲሁም ቅማንትን ከአማራ ለማጋጨት ጥረት ተደርጎ ነበር፤ ነገር ግን አባቶቻችን በብልጠት ሴራውን አክሽፈው እልፍ ዘመን የዘለቀ አብሮነትን አውርሰውናል ነው ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ፡፡

ማንነትን ማክበር እና ማስከበር ስንል አጥር ማጠር እና የልዩነት ግንብ መገንባት ማለት አይደለም ያሉት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ህዝብን ማድመጥ እና ታሪካዊ ወሰኑን ማስከበር እንጅ ተመልሶ ያደረ ጥያቄ ነው እያሉ ማለፍ ታሪኩ ያለፈበት ሂደት ነው ብለዋል፡፡

ልታከብረን እና ልናከብራት የምንችላት ሃገር ለመገንባት በመጀመሪያ በህግ የበላይነት ልንገዛ ይገባል፡፡ ሃገራችን ያከበረችንን ያክል አላከበርናትም ያሉት አቶ ደመቀ ሃገር ግንባታ ጊዜ ይወስዳልና በትዕግስት ሃገር ልንገነባ ይገባል ብለዋል፡፡
እኛ እና እናንተ አሉ አቶ ደመቀ ‹‹እኛ እና እናንተ ከግለሰብ እልፍ ያለ ኃላፊነት ስላለብን ስሜት ሳይገዛን እና ከንፈራችን እየመጠጥን እንዳናዳማ ትክክለኛ መሪ እና መፍትሄ ፈላጊዎች ልንሆን ይገባል ብለዋል፡፡››

ይህ ህዝብ አብሮ ኖሯል ፣ ተዋልዷል ፣ ደም አስተሳስሮታል እና! ይህ ቀን አልፎ ነገ አብሮ መኖሩ ስለማይቀር ‹‹መሪና ድርጅት ያልፋሉ ህዝብና ታሪክ ግን በዘመናት መካከል ይቀጥላሉና በሚያልፍ የመሪነት ዘመናችን የማያልፍ የታሪክ ጠባሳ እንዳንተው ልንጠነቀቅ ይገባል›› ብለዋል፡፡

በጎንደር ከተማ እየተካሄደ ያለው የሰላም መድረክ እንደቀጠለ ነው፡፡