ህልሜ አማርኛ ይፋዊ የአፍሪካ የስራ ቋንቋ እስኪሆን ድረስ መስራት ነው-ኒጀራዊቷ የፊልም ሰው ራማቱ ኪየታ

ህልሜ አማርኛ ይፋዊ የአፍሪካ የስራ ቋንቋ እስኪሆን ድረስ መስራት ነው-ኒጀራዊቷ የፊልም ሰው ራማቱ ኪየታ

ባህር ዳር፡ ጥቅምት 17/2010 ዓ/ም (አብመድ)በፊልሙ ዓለም የአፍሪካን ወዳጅነት ለማጠናከር እየሠራች ያለችው የአፍሪካ ፊልም ስራ ባለሙያዎች ማህበር አባል ራማቱ ኪየታ አማርኛ የአፍሪቃ ህብረት የስራ ቋንቋ እስከሚሆን ድረስ ጥረቷን እንደማታቋርጥ እንደገለጸች ዶቼ ዌሌ ዘገበ፡፡

‹‹አማርኛ ብቸኛው የአፍሪካ የስነ ጽሁፍ ቋንቋ ነው፡፡ኢትዮጵያ የአፍሪካ የነፃነት ተምሳሌት ናት፡፡ኢትዮጵያ በአማርኛ ትናገራለች፡፡

አፍሪካ ደግሞ አፍሪካን መምሰል አለባት፡፡የአፍሪካን ባህል በማዳበር ወዳጅነት መመስረት አለብን ››ትላለች ራማቱ ኪየታ ፡፡

እስካሁን በአማርኛ ላይ ምን ሰራሽ ለሚሉኝ ራሴን የአማርኛ ቋንቋ አምባሳደር አድርጌ በመሾም ዓለም አቀፍ ፊልሞች ላይ አማርኛን እስከ ሆሄያቱ እየጨመርኩ ነው የምትለው ነገ ደግሞ ፊልሞቼን በሙሉ ወደ አማርኛ እመልሳለሁ ለዚህ ስኬትም ከፕሮፊሰር ሀይሌ ገሪማ ጋር እየሰራሁ ነው ብላለች ፡፡

1ነጥብ 2 ቢሊየን ህዝብ ባላት አፍሪካ ጥንታዊውን ባለፊደል ቋንቋ የሚናገሩት 100 ሚሊየን አይደርሱም፡፡የአፍሪካ ህብረት መሪዎችን አነጋግሪያለሁ፡፡

አሁንም አማርኛ ይፋዊ የአፍሪካ የስራ ቋንቋ እስኪሆን ድረስ ጥረቴን እቀጥላለሁ ያለችው ራማቱ
ፊልሞቼም በአማርኛ ቋንቋ ይሰራሉ ብላለች፡፡

ፊልሞቿን በጀርመኖቹ ኮሎኝ እና ሀምቡርግ ስታሳይ ዶቼዌሌ አግኝቶ ያነጋገራት የአፍሪካ ፊልም ባለሙያዎች ማህበር አባል ራማቱ ኪየታ ለዶቼዌሊ አማርኛው ክፍለጊዜ እንደገለጸችው ፊልሟን በኒጀር፣በቡርኪናፋሶ፣በፈረንሳይ፣በጀርመን እና በሆላንድ ማሳየቷን ትናገራለች፡፡

አማርኛ እ.ኤ.አ. በ1955 ለአፍሪካ የስራ ቋንቋነት ታጭቶ እንደነበር መዛግብት ያሳያሉ፤ለምን እንደቀረ ግን ምክንያቱ እስካሁን በውል ባይታወቅም፡፡

ከዚህም በቀር አማርኛ በአንዳንድ የአሜሪካ ግዛቶች የስራ ቋንቋ ሲሆን፣እስራኤልም የስራ ቋንቋ ለማድረግ ህግ እያዘጋጀች እንደሆነ መረጃዎች ያሳያሉ፡፡

የአማርኛ ስርዓተ ፅህፈትን በ1980 ዓ.ም. ከኮምፒውተር ጋር ያስተዋወቁት ዶክተር አበራ ሞላ፣ አጻጻፉ እንዲሻሻል በአንድ ቁልፍ ብቻ የሚሰራ ሶፍትዌር እንዳበለፀጉ ለዝግጅት ክፍላችን ተናግረዋል፡፡

አማርኛን ከቴክኖሎጂ ጋር የበለጠ ለማስተዋወቅ እንደ አፕል አይነት የቴክኖሎጂ ኩባንያዎች ጋር እየሰራሁ ነውም ብለዋል፡፡

አማርኛ ሆሄያትን ጎግል እና ፌስቡክ ወደ አገልግሎት ማስገባታቸው ይታወሳል፡፡