በጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ በክልል ፖሊስ እና በፌደራል ፖሊስ መካከል ግጭት ተፈጥሮ የሰው ሕይወት አለፈ

በጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ በክልል ፖሊስ እና በፌደራል ፖሊስ መካከል በተፈጠረ ግጭት የአንድ ሰው ህይወት ሲያልፍ በአንድ ሰው ላይ የመቁሰል አደጋ መድረሱ ተገለፀ።

በጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በክልል ፖሊስ እና በፌደራል ፖሊስ መካከል በተፈጠረ ግጭት የአንድ ሰው ህይወት ሲያልፍ በአንድ ሰው ላይ የመቁሰል አደጋ መድረሱን የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ።

በአሁኑ ሰዓት የአካባቢውን ሠላም ወደነበረበት ከመመለስ ባሻገር ግጭት ፈጥረዋል የተባሉ ግለሰቦች በህግ ቁጥጥር ሥር በማዋል ተገቢው ማጣራት እየተካሄደ መሆኑንም ፖሊስ አመላክቷል።

የጋምቤላ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቡላ ኡቦንግ፤ በጋምቤላ ዩኒቨርሲቲ ትናንት ምሽት በተፈጠረ ግጭት የአንድ ሰው ህይወት ሲያልፍ አንድ ሰው ላይ የመቁሰል አደጋ የደረሰ መሆኑ ገልፀዋል፡፡

ፖሊስ የግጭቱን መንስኤ እያጣራ እንደሆነ የገለጹት ኮሚሽነሩ፤ የክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን እና መንግስት በህግ አግባብ በግለሰቦች ላይ ህጋዊ እርምጃ ለመውሰድ በምርመራ ላይ መሆኑን አስረድተዋል።

መላው ህብረተሰብ ወደ ግጭት፣ ኹከትና መረበሽ ሰዎችን እንዲያመሩ ከሚያደርጉ አንዳንድ ማህበራዊ የሚዲያ ገፆችና ያልተረጋገጠ መረጃን ከሚሰጡ ዘገባዎች እራሱን እንዲጠብቅ አሳስበዋል።

ህብረተሰቡ እንደ ከዚህ ቀደሙ ሁሉ የአካባቢውን ሰላም ከፀጥታ ሀይሉ ጋር በመሆን የማረጋገጥ ተግባር አጠናክሮ እንዲቀጥል ኮሚሽነሩ ጥሪ ማቅረባቸውን ከጋምቤላ ክልል ፕሬስ ሴክሬታሪያት ጽህፈት ቤት የተገኘው መረጃ ያመላክታል።