ሲጠበቅ የቆየው የብሔራዊ መግባባት ውይይት ሁሉንም አካታችና አሳታፊ እንዲሆን ፓርቲዎች ከወዲሁ እየጠየቁ ነው

በመንግስትም በሲቪክ ማሕበራትም የውይይት መድረክ ባልደራስ እንዳይገለል ካሁኑ ተፈርቷል 

‹‹የትጥቅ ትግል ከመረጡ ኃይሎች ውጪ ሁሉም ወገን በውይይቱ ይካፈላል››

የሰላም  ሚኒስቴር

‹‹ውይይቱ  ሁሉንም ወገን ካላካተተ የታሰበውን ብሔራዊ መግባባት አይፈጥርም››

የፖለቲካ  ፓርቲዎች

በዮናስ አማረ

ሲጠበቅ የቆየውና የፖለቲካ ፓርቲዎችን ያሳትፋል የተባለው የብሔራዊ መግባባት ውይይት በመጪው ኅዳር ወር እንደሚካሄድ ተነገረ፡፡

አንዳንድ የፖለቲካ ፓርቲዎች ውይይቱን ‹‹በኅዳር የመጀመርያ ሳምንታት ለማድረግ ግብዣ እንደ ቀረበላቸው ለሪፖርተር አረጋግጠዋል፡፡ የነፃነትና እኩልነት ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኑሩ ወለላ በኅዳር የመጀመርያ ወይም ሁለተኛ ሳምንት የሚካሄድ 500 ሰዎች የሚካፈሉበት ውይይት እንደሚኖር ጥሪ ቀርቦልናል›› ብለዋል፡፡

ይሁን እንጂ የውይይቱ ዋና አመቻች ነው የተባለውና የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤትን ያቀፈው ማይንድ ኢትዮጵያ የተባለው ተቋም፣ የተቆረጠ ቀን አለመኖሩን ተናግሯል፡፡

የማይንድ ኢትዮጵያ የሥራ ኃላፊ ናርሶስ ብርሃን (ዶ/ር)፣ ‹‹ለማንም ፓርቲ የውውይ ጥሪ አላቀረብንም፤›› በማለት ለሪፖርተር ቢናገሩም፣

‹‹የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤትን በመወከል ማይንድ በተባለው የውይይት አመቻች ጥምረት ውስጥ የሚካፈሉት የፓርቲያችን ሊቀመንበር ናቸው፤›› ሲሉ የተናገሩት የነፃነትና እኩልነት ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኑሩ፣ የብሔራዊ መግባባቱ ውይይት በኅዳር መግቢያ ሊካሄድ መታሰቡን መረጃው እንዳላቸው አስረድተዋል፡፡

የብሔራዊ መግባባት ውይይትን በተመለከተ ጥያቄ የቀረበላቸው የባልደራስ ፓርቲ የፖለቲካ ዘርፍ ኃላፊ አቶ ጌታነህ ባልቻ በበኩላቸው፣ የደረሳቸው ጥሪም ሆነ ግብዣ አለመኖሩን በመጠቆም፣ ውይይቱ መቼና እንዴት ሊካሄድ እንደታሰበ እንደማያውቁ ገልጸዋል፡፡

ይህንኑ ፓርቲዎች ያቀረቡትን መረጃ በመመርኮዝ የብሔራዊ መግባባት ውይይቱ አንዳንዶችን አግልሎ ጥቂቶችን አካቶ ሊካሄድ ታስቦ እንደሆነ ለሰላም ሚኒስቴር የሥራ ኃላፊ ሪፖርተር ጥያቄ አቅርቦ ነበር፡፡ ለጥያቄው ምላሽ የሰጡት በሰላም ሚኒስትር የፖለቲካ ፓርቲዎች ጉዳይ ኃላፊ አቶ ምግባሩ አያሌው፣ ‹‹የትጥቅ ትግል ከመረጡ ኃይሎች ውጪ ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች ይሳተፋሉ›› ብለዋል፡፡ አቶ ምግባሩ አክለውም፣ ‹‹በምርጫ ሒደቱ የተካፈሉ ሁሉም ፓርቲዎች ይጋበዛሉ፤›› ብለው፣ ግብዣ ያልቀረበላቸው ፓርቲዎች ወይም የተገለሉ ካሉ ድርጊቱ አግባብነት የሌለው መሆኑን በመጠቆም የሰላም ሚኒስቴር እንደማይቀበለው አስታውቀዋል፡፡

የውይይት ግብዣ እንደደረሳቸው ያረጋገጡት የነፃነትና እኩልነት ፓርቲ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ኑሩ፣ የብሔራዊ መግባባት ውይይቱ ጉዳይ የአካሄድ ግልጽነት ያለበት መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ‹‹ኦነግን፣ ኦብነግን፣ ኦፌኮን፣ ባልደራስንና ሌላውን ትተህ ብሔራዊ መግባባት አመጣለሁ ብሎ ማሰብ ተገቢነት የለውም፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡

የብሔራዊ መግባባት አጀንዳን ከምሥረታው ጀምሮ አጠንክሮ ፓርቲያቸው ሲጠይቅ  መቆየቱን የተናገሩት አቶ ኑሩ፣ ‹‹የብሔራዊ መግባባት ጉዳይ ሆደ ሰፊነትና ሁሉንም አካታችነት ይፈልጋል፤›› ብለዋል፡፡ አሁን ግን በመንግሥት በኩል የራሱን ፍላጎት የሚያስፈጽሙ ኃይሎችን የማሠለፍና አንዱን ጥሎ ሌላውን አንጠልጥሎ የመጓዝ አዝማሚያ መኖሩን አስረድተዋል፡፡

የብሔራዊ መግባባት ውይይት ገና መሆኑን የተናገሩት የማይንድ ኢትዮጵያ ሥራ ኃላፊ ናርዶስ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ በቅርብ ሊኖር የሚችለው ቅድመ ውይይት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ‹‹እኛ የውይይት አመቻች ነን፣ ማን እንደሚሳተፍ፣ በምን አጀንዳዎች ላይ፣ እንዴት እንደሚካሄድ አንወስንም፡፡ ውይይቱ ገና ነው፡፡ ጊዜው ሲደርስ ለሕዝብ ይፋ ስለምናደርግ እንነግራችኋለን፤›› በማለት አስረድተዋል፡፡

ይሁን እንጂ የውይይቱ ጋባዥ ማን ሊሆን ይችላል ለሚለው ጥያቄ ማይንድ ኢትዮጵያ እንደሆነ አረጋግጠዋል፡፡ ፓርቲዎች ለውይይት ተጋብዘናል ብለው ማረጋገጫ ቢሰጡም፣ የውይይቱ ጋባዥ ማይንድ ኢትዮጵያ ግብዣ አላቀረብኩም ሲል መልሷል፡፡ በኢትዮጵያ ሁሉንም ባካተተ ሁኔታ ከምርጫ በኋላ ይካሄዳል ተብሎ ሲጠበቅ የቆየው የብሔራዊ መግባባት ውይይት፣ ሁሉንም አካታችና አሳታፊ እንዲሆን ፓርቲዎች ከወዲሁ እየጠየቁ ነው፡፡

አንዳንድ ፓርቲዎች በቅርቡ ለሚጀመረው የብሔራዊ መግባባት ውይይት ግብዣ ቀረበልን ቢሉም፣ አንዳንዶች ግን የሰማነው ነገር የለም ብለዋል፡፡