የመከላከያ ሰራዊታችን በራሱ ዕቅድ ሙሉ ማጥቃት ከጀመረ ግን ሕወሓት “ተጠቃሁ” ብሎ ለመናገር እንኳ ጊዜ ሳያገኝ የሚፈፀም እንደሚሆን መታወቅ አለበት። – ከሀገር መከላከያ ሚኒስቴር

ከሀገር መከላከያ ሚኒስቴር የተሰጠ መግለጫ።

የጁንታው የድረሱልኝ ጥሪ …

አሸባሪው ህወሃት በሰጠው አሁናዊ መግለጫው… “…የኢትዮጵያ ሠራዊት በአነስተኛ ወይም ትናንሽ ማጥቃት ሲፈፅም የቆየውን አሁን ላይ በከባድ መሳሪያ፣ በአየር ኃይል ታግዞና ሁሉንም የፀጥታ ኃይሎች አቀናጅቶ መጠነ ሰፊ ጥቃት እየፈፀመ ነው።…” ይላል።

የጦርነቱን ዓላማ ሲገልፅም “…በትግራይ ህዝብ ላይ ዳግም ወረራ ለመፈፀም፤ ሰቆቃውን ለማብዛትና ለማጥፋት እንዲሁም ውጊያውን ትግራይ መሬት በማድረግ ሊጨርሰን ነው ” ይላል።

ይህንን ባለበት አንደበቱ “…የትግራይ ሰራዊት የኢትዮጵያን ሠራዊት ባለበት ተኮማትሮ እንዲቀመጥ አድርገነዋል…” ይላል።

“ተጠቃሁ” ከሆነ ወደፊትና ወደ ጎን እንቅስቃሴ አለ ማለት ሲሆን፣ “አኮማትሬያለሁ” ግን ተዘርግቶም ሆነ ወደፊት መንቀሳቀስ የማይችል አድርጌዋለሁ ማለት ነው።

ሽብርተኛው ሁልጊዜ ውሸት ቀለቡ ነው፡፡ አንድ ነገር ሲፈልግ መጀመሪያ የሚያቅደው እንዴት ልዋሽ ብሎ ነው ፡፡ ቅጥፈቱ ደግሞ እልም ያለ ከመሆኑ የተነሳ “ይታወቅብኝ ይሆን? ” የሚል ጭንቀት የለበትም ፡፡

የዛሬው ፈሊጥ ደግሞ አይናችሁን ያዙ ላሞኛችሁ ዓይነት ሆኗል ፡፡ ለጋላቢዎቹ “መጠነ ሰፊ ጥቃት” ተሰነዘረብኝ እባካችሁ አድኑኝ እያለ ሲማጸን ፤ ለሚጋልባቸው ደግሞ “አኮማትሬያለሁ” እያለ መዘላበድ ሆኗል ፡፡

ይህ መንታ ምላስ እራሱ ወሮና አጥቅቶ ህዝብ ያጎሳቆለው ሳያንስ እና ኢትዮጵያን የማፍረስ ህልሙን በጀግናው መከላከያ ሰራዊታችን እና በመላው የፀጥታ ኃይላችን አልሳካ ሲለው፤ በተለመደ ውሸቱ ዓለምን ለማደናገር የድረሱልኝ ጥሪውን ያቀርባል።

“እንጦጦ እንደርሳለን” ያለ ኃይል ፣ ተገልብጦ “ድረሱልን…!” ፡፡ ወሮ “ተወረርን…!” አጥቅቶ “ተጠቃን…!” እያለ ውሸት የማያልቅበት ኃይል ነው።

የመከላከያ ሰራዊታችን በራሱ ዕቅድ ሙሉ ማጥቃት ከጀመረ ግን “ተጠቃሁ” ብሎ ለመናገር እንኳ ጊዜ ሳያገኝ የሚፈፀም እንደሚሆን መታወቅ አለበት።

የዚህ አሸባሪ የጁንታ ቡድን ውሸትና ማደናገሪያ እድሜው የመሸበት የቁራ ጩኸት ነው። በመሆኑም ህዝባችን በወሬ ሳይደናገር የቁርጥ ቀን ልጆቹ በመንግስታቸው ትዕዛዝ አይቀሬውን ድል እስኪያበስሩ የተለመደው ድጋፍ እንዳይለየን እንላለን።

ጥቅምት 01/2014 ዓ.ም